Tuesday, May 22, 2012

"ማኅበረ ቅዱሳን" የሚታዘዘው ለማን ነው?

                             http://awdeselam.blogspot.com
ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ወቅታዊ ሁኔታና የወደፊት ዕጣ የሚነጋገር ሁሉ የሚስማማበት አንድ ነገር አለ። ይኸውም "ማኅበረ ቅዱሳን" የቤተ ክርስቲያን አባቶችን በአንድም በሌላም መንገድ በመከፋፈል እራሱን ብቸኛ የቤተ ክርስቲያንዋ ነጻ አውጪ አድርጎ የመመልከቱ ነገር ነው። አንዳንድ ጊዜማ ከማኅበሩ መመሥረት በፊት በቤተ ክርስቲያን ሥራ እንዳልተሠራ፣ እንዳልተደከመባት አድርጎ በድፍረት በመናገር የወጣቱን ክፍል ለማሞኘት ይሞከራል። 
ይህ ማኅበር ፊት የማያሳዩትን በስደት ውጪ ሀገር የሚኖሩትን አባቶች በማቃለልና ሃይማኖት ለዋጮች እንደሆኑ አስመስሎ በማቅረብ፣ ለብዙ ክብር የበቁትን፣ እያንዳንዳቸው ለቤተ ክርስቲያን ከሃምሳ ዓመታት በላይ የደከሙትን አባቶች በመናቅና በማዋረድ፣ ወጣቶች ለአባቶቻቸው አክብሮት እንዳይኖራቸው ሰድቦ በማሰደብ በስደት ባሉባቸው ቦታዎች ሲያሳድዳቸው ተስተውሏል አሁንም እየተስተዋለ ነው። በቅዱሳን ስም ራሱን ለሚጠራ ማኅበር የከበሩትን ማዋረዱ የተመረጡትን መናቁ ስሙ እንደማይገባው የሚያሳይ ነው።
ይህ ብቻ አይደለም። ይኸው ማኅበር በስደት ያለችውን ቤተ ክርስቲያን ሲያሳድድ “ከአዲስ አበባ ሲኖዶስ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የሰንበት ትምህርት ቤት ማደራጃ መምሪያ ሥር የምተዳደር ነኝ” … “ሲኖዶስ አንዲት ናት” … “ከእናት ቤተ ክርስቲያን ጋር መደባለቅ ያስፈልጋል” በማለት በውጪ ያለውን ሕዝብ በመደለል ነው። ሙከራው እንዳሰበው ባይሳካለትም በቂ ጥፋት ለማጥፋት ያገኘውን አጋጣሚ ሁሉ ተጠቅሟል።

ማኅበሩ እራሱን በአዲስ አበባ ሲኖዶስ ሥር እንደሆነ አድርጎ ቢያቀርብም በምግባሩ ግን እዚያም ያሉትን አባቶች መከፋፈሉና አልታዘዝ ባይነቱ ዓይን እያወጣ ከመጣ ቆይቷል። እስከ አሁን አንዳንዶች በጠቅላይ ቤተ ክህነት የሚገኙ መምሪያ ኃላፊዎችንና አንዳንድ አባቶችን በገንዘብ፣ ሌሎችንም ደካማ ጎናቸውን አሰመልክቶ ምስጢር እንደሚያወጣ በማስፈራራት አፋቸውን ለጉሞ ቆይቷል። የወደፊቱን እግዚአብሔር ያውቃል። እንደሚታወቀው ይህ ማኅበር “አጥፍተሃል” … “ተሳስተሃል” ... “አሁንስ በቃ! ... አልበዛም እንዴ?” የሚለውን ሁሉ “ተሐድሶ ናቸው” በማለት ወይም “ኑፋቄ አስተምረዋል” ብሎ ስም በማጥፋትና አመጽን በማስተባበር ቅን የቤተ ክርስቲያንዋን አገልጋዮች ስም እያጎደፈ ነው። ብዙዎች ጭንቅ ሆኖባቸው የማኅበሩን ድክመት እያወቁ ተሸክመው ባልተማሩ ልጆች እየታዘዙ “ስቀሉ ሲባሉ እየሰቀሉ” “አውርዱ ሲባሉ እያወረዱ” ማኅበሩ ሊያገኝ ከሚገባው በላይ ሥልጣን እንዲኖረው ምክንያት ሆነዋል።
ያም ሆነ ይህ “ይህቺ ባቄላ ያደረች እንደሆነ አትቆረጠምም” እንደተባለው ወይም “ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ቆመን ማውረድ እንዳያቅተን” ተብሎ እንደተተነበየው ዓይነት ነገር እንዳይመጣ ሁሉም ሊያስተውል ይገባዋል።
የወቅቱ የቤተ ክርስቲያን ችግር ማለትም የአባቶች መለያየትን ማኅበሩ የጥፋት ተልእኮውን ለመፈጸም ተጠቅሞበታል እየተጠቀመበትም ነው::  እንዲያውም ሁለቱንም ሲኖዶሶች በማቃለልና ባለመታዘዝ የማኅበሩን አጀንዳ የሚያካሂዱ ጥቂት አባቶችን እያታለለ ራሱን እንደ ሦሰተኛ አማራጭ እያቀረበ ነው:: ለዚህም ነው በሁለቱ ሲኖዶሶች መካከል ሰላም እንዲወርድ የማይፈልገው የተጀመረውን የሰላም የእርቅ እንቅስቃሴ ለማምከን የሚንቀሳቀሰው። በአባቶች መካከል ሰላምና እርቅ መምጣቱ ለቤተ ክርስቲያን የሚበጅ ሆኖ ሳለ በቤተ ክርስቲያን ሥር ነኝ ለሚለው ለ"ማኅበረ ቅዱሳን" አልዋጥ ማለቱ ማኅበሩ ድብቅና መሠሪ ተልእኮ እንዳለው በግልጽ የሚያሳይ ነው::      

ስለዚህ ማኅበር ጉዳይ ብዙ ማለት ይቻላል። የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ግን ከዚህ በታች ያለውን ደብዳቤ ለአንባቢ ለማቅረብ ሲባል እንደ መግቢያ እንዲሆን ብቻ ስለሆነ እዚህ ላይ እናበቃለን። እንደ ማጠቃለያ የምንለው ቢኖር ሁሉም አቅሙንና ደረጃውን ቢያውቅ፣ ሁሉም ድርሻውን እየታዘዘ ቢሠራ፣ ልጆችም ለመረገም በመቸኮል ፈንታ እንደ ልጅነታቸው በአባቶቻቸው እግር ሥር ቁጭ ብለው ተምረው ቢመረቁ እድሜያቸውም የሚረዝም ለቤተ ክርስቲያንም የሚበጅ መሆኑን ነው።
መልካም ንባብ …
በ2003 ዓ/ም ለማኅበሩ የተጻፈውና ያልተቀበላቸውን ደብዳቤዎች ለማንበብ፤
1/ለገጽ አንድ እዚህ ይጫኑ
2/ ለገጽ ሁለት እዚህ ይጫኑ
3/ ለገጽ ሦስት እዚህ ይጫኑ
ምንጭ፦ http://awdeselam.blogspot.com