Friday, May 25, 2012

ፋሲካ

             ምንጭ፦http://bethelhemm.blogspot.com
በሚያስፈራው ሌሊት ጩኸት ሲበረታ
ግብጽ ተሸበረች ጌታ በኩሯን መታ
ሞት መግባት አልቻለም ወደ እስራኤል ቤት
ታትሞ ስላየ የደም ምልክት
ደጃቸውን ዘግተው ፋሲካ አደረጉ
በደም ተከልለው ሌሊቱን አነጉ
ባሕሩን ተሻግረው ከነዓን ሲገቡም
የልጅ ልጆቻቸው ፋሲካን አልረሱም
ይህ ሥርዓት አልፎ የእግዚአብሔር በግ መጣ
ሰውን የገዛውን የሞት ኃይል ሊቀጣ
የሰው ፍቅር ስቦት ከሰማያት ወርዶ
ጠላትን ረታው ፋሲካችን ታርዶ 

በመስቀል ተሰቅሎ ስለሆነ ቤዛ
ወገኖቹን ዋጅቶ በራሱ ደም ገዛ
ንጉሡ እንዲገባ ደጆች አይዘጉም
ሌሊቱ አልፏልና የሚያሰጋን የለም
የሕይወታችን ጉበን በደም ታጥሯልና
ሞት እያየ አለፈን ኃይሉን አጥቷልና
ለምሕረት በሚጮኸው የደሙ ምልክት
ባሕሩን ከፍለን አልፈን እንገባለን ገነት
የዘላለም አምላክ የምስጋና ጌታ
ምርኮን የማረከ ማኅተሙን የፈታ
ሞትን ድል የነሳው የናዝሬቱ ኢየሱስ
በዙፋኑ ያለው የአርያም ንጉሥ
ከፍ ከፍ ይበል ይድረሰው ምስጋና
መከራን ታግሶ ለእኛ ታርዷልና
ፋሲካን ስናደርግ ኖረን በእድሜ ጸጋ
ክርስቶስ ፋሲካ መሆኑን አንዘንጋ፡፡