Monday, July 22, 2013

የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ጉዞና ልምላሜ የተለየው ዛፍ አንድ ናቸው!

አዲስ አበባ የሀገሪቱ ርእሰ መዲና እንደመሆኗ መጠን የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት በገንዘብ፤ በባለሙያና በሠራተኛ አቅም ትልቁ ሀገረ ስብከት ነው። በዚህ ሦስት ተቋማዊ አቅም በአግባቡ መጠቀም ከተቻለ ለሌሎች ሀገረ ስብከቶች የሚተርፍ በቂ ኃይል ያለው ሀ/ስብከት ነው። የርእሰ መዲናይቱ ሀ/ስብከት እንደመሆኑ መጠን የተሻለ ሥራ፤ ክፍያና ኑሮ ለማግኘት ከገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን የሚፈልሰው አገልጋይ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል። የሚያሳዝነው ግን አዲስ አበባ ከተማ ከተኛችበት እየነቃች እዚህም እዚያም ጉች ጉች ብለው የሚታዩት ግንባታዎችና የተዘረጉ መንገዶች ለአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ለውጥ ምን እንደሚመስል ለማየት የሚያስችል ዐይን እንዲኖረው የፈየደለት ነገር አለመኖሩ ነው። የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት አስተዳደር ወደኋላ መሄድ ከጀመረ ዓመታት ተቆጥረዋል። ዛሬም የሚታይበት አንዳች እንቅስቃሴ የለም። ለውጥ የሂደት ክስተታዊ ግዴታ ቢሆንም ይህ አመክንዮ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ለምን እንዳልጎበኘው ግራ ያጋባናል። ምናልባት እንደ ቀንድ አውጣ የዐርባ ዓመት እንቅልፉን አልጨረሰ ይሆን? ጊዜ ደግሞ ታክሲ አይደለም። ጊዜ ሲሄድ ባለበት ከሚቆመው ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት በስተቀር።
የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ተቋማዊ የኋሊዮሽ መንገድ ስንገመግም ቤተክርስቲያኒቱ የት እንዳለች ፍንጭ ሊሰጠን ይችላል። እነማን ቤተ ክርስቲያኒቱን እየመሯት እንዳሉ ያመላክተናልም። በሌላ ቋንቋ ቤተ ክርስቲያኒቱን የ40 ዓመት የቀንድ ዐውጣ እንቅልፍ ውስጥ እንደገባች የተቀመጡባት ሰዎች አመራር ይጠቁመናል። ዋልታ የሌለው ጣሪያ በአናቱ ዝናብ ማስገባቱ አይቀርምና ለጣሪያው መበስበስ የአናቱ ክፍተት ምክንያት ከመሆኑ ውጪ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል? የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት መበስበስ የላይኛው ጣሪያ የመበስበሱ ምልክት ተደርጎ ቢወሰድ አያስኬደንም ትላላችሁ?
የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን የበሰበሰ ጣሪያ ለመጠጋገን ብዙ ተሞክሯል። መጽሐፉ እንደተናገረው በአሮጌው አቁማዳ ላይ አዲስ ለመጣፍ እየተሞከረ መበጣጠሱን የከፋ አደረገው እንጂ የተቀየረ አንዳች ነገር የለም። በእነ እገሌ ዘመን የነበረው አስተዳደር ጥሩ ነበር እንዳንል የሁሉም ዘመን ችግር በመጠን ከሚበላለጥ በስተቀር በይዘቱ አንድ ነው። በእርግጥ ይዘቱ መጠኑንና ዓይነቱን ጨምሮ ዛሬ ሀ/ስብከት ሳይሆን «ኃላፊነቱ የተወሰነ የነጣቂዎች ማኅበር» ወደመሆን በመሸጋገሩ ከድሮዎቹ አስተዳደር ዛሬ የከፋ ደረጃ ላይ መድረሱ እውነት ነው። አንዱን ሾሞ አምሮቱ ሲጠረቃ ሌላ ያልጠረቃ በመሾም ችግሩን በማባባስ በኩል ያ! ያልታደለው ሲኖዶስ ለሀ/ስብከቱ ውድቀት ትልቁን ድርሻ ይወስዳል። ምክንያቱም ሲኖዶሱ ያልጠረቃውን በጠረቃው አመራር በማለዋወጥ ካልዘሩበት የሚያጭዱ ነጣቂዎችን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በማኅበር አደራጅቶ ባልለቀቃቸውም ነበር። 

ለዚህ ጥሩ ማሳያ የሚሆነን ንቡረ እድ መምህር ገ/ማርያም ገ/ሥላሴ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ እያሉ አውድማውን ሳያሄዱ የተመረተውን ዝም ብለው የሚቅሙ አጋሰሶችን አፍ በመዝጋታቸው ብቻ በእህል በሎች ክስ ባላባረሯቸውም ነበር። የሆነው እውነታ ግን ጠርጎ በሎችን መረን ለቆ፤ «ሊሰራ የማይወድ አይብላ» ብለው የታገሉትን ጠንካራ ሰው ባላባረረም ነበር። ድሮስ ጠርጎ በልን ሊታደግ የሚችለው ከጠርጎ በል በቀር ማን ሊሆን ይችላል?
የንቡረ እድ ገ/ማርያም ገ/ሥላሴ ወንጀል የቤተ ክርስቲያኒቱን ሙዳየ ምጽዋት ዘረፋ ማስቆም መቻላቸው ነበር። ከ200 ሺህ ብር በላይ ተቆጥሮ የማያውቀው የመንበረ መንግሥት ቅ/ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ  ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ የተቆጠረው በንቡረ እድ ገ/ማርያም ክትትል መሆኑ ታሪክ መዝግቦታል። የሌሎቹም አድባራት ሙዳየ ምጽዋት ሣጥኖች እየተዘቀዘቁ ከመገልበጥ የተረፉት በኚሁ ሰው አስተዳደር ዘመን ስለመሆኑ ገልባጮቹ ሳይሆን አገልጋይ ካህናቱ የሚናገሩት እውነታ ነው። ምን ያደርጋል ታዲያ? እውነተኛና ሀቀኛ እርሟ የሆነችው ቤተ ክርስቲያን ንብረ እድ ገ/ማርያምን ከአዲስ አበባ ወደሽሬ  በመወርወር ሲኖዶሱ ቁጭቱን ተወጣባቸው። ገልባጮችንም አስደስቷል። አባ ገ/ማርያም ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት መነሳታቸውን የሰሙ ምሽት ሙዳየ ምጽዋት ገልባጮች ሻምፓኝ ሲራጩ ማደራቸው ተሰምቷል። እንግዲህ ይህ ክፍል ነው በመበደሉ ምክንያት ሲኖዶሱ በነፍሱ የደረሰለት። አሳዛኝ ዘመን?
ዛሬ ደግሞ በፓትርያርክ ማትያስ ምርጫ ላይ የአንበሳውን ድርሻ የወሰዱት አባ እስጢፋኖስ ለፈጸሙት የታማኝነት አገልግሎት ከፓትርያርኩ በገጸበረከትነት የቀረበላቸው ስጦታ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሲሆን በፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስነት ሽፋን ተዝቆ የማያልቀውን ካዝና የድርሻቸውን እንዲናኙ  ተመድበው እነሆ ከመነሻው በስመ ሥልጠና ሽፋን ተረክበው እያመሱት ይገኛሉ። የሚያሳዝነው ደግሞ ገና ምኑንም ሳይጀምሩ አባ እስጢፋኖስ አድባራቱን ገንዘብ አዋጡና ወደ ሀገረ ስብከቱ ገቢ አድርጉ እያሉ ሥልጠና በተባለው አሰልቺ መድረክ ላይ ነጋ ጠባ መጮሃቸው ነው። አዋጡ ማለት ምን ማለት ነው? ፐርሰት ክፈሉ ነው? ወይስ የሀ/ስብከቱ ጽ/ቤት የሚጦራቸው ድኩማን አሉት? ጥያቄውን ለአቡኑ እንተውና ከአዋጡ ጭቅጨቃቸው የምንረዳው እውነታ ቢኖር ሀ/ስብከቱ ዛሬም ፈውስ የራቀው መሆኑን ነው። ሥልጠና በተባለው የጩኸት መድረክ ላይ ሥልጠናውን የሚካፈሉት እነዚያው የቤተ ክርስቲያንን ሙዳየ ምጽዋት የሚገለብጡ ሰዎች መሆናቸውን ስናይ አቡኑ አዲስ ነገር መጀመራቸውን በማሳየት በቀደመው ጎዳና ለመሄድ ያቀዱት ስላለመሆኑ የሚያሳምን አንዳች  ሥር ነቀል ተቋማዊ ለውጥ አለመኖሩ ቁልጭ ብሎ ይታየናል።  ስልጠና በተለወጠ ሰውና ለለውጥ በተዘጋጀ አእምሮ ላይ የሚዘራ ዘር እንጂ የለውጥ መንገድ እንቅፋት ሆኖ በቆየና በጨቀየ አእምሮ ላይ ሲሆን ስናይ ረዳት ሊቀጳጳሱ ወይ ስራውን አያውቁትም፤ ወይም ስራው አያውቃቸውም።
 አቡነ ቀውስጦስ የሀ/ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ሳሉ በተጠናወታቸው ዘረኝነት የጎጣቸውን ሰዎች እያመጡ ሲሰገስጉና ሲያሳድጉ ንቡረ እድ ገ/ማርያም በሩን ዘግተ አላሳልፍ ስላሏቸው ብቻ በሲኖዶስ ጉባዔ ላይ ከሳሽ ሆነው መገኘታቸውን አንዘነጋውም። ዛሬም አቡነ እስጢፋኖስ የንቡረ እድ ገ/ማርያምን ወደ አዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅነት ዳግም የመመለስ የካህናት ጥያቄ አልቀበልም ያሉት ንቡረ እዱ እጅ ከወርች አስረው ረጅም እጆችን ሁሉ ስለሚያስቆሙ ከወዲሁ የተወሰደ መላ መሆኑ ይገባናል። አቡኑ ሙስናን የሚዋጉ ከሆነ ምነዋ! የሙስናውን በር ድርግም አድርገው የዘጉትን ንቡረ እድ በሥራ አስኪያጅነት ማስቀመጥ ፈሩ? በእርግጥ አቡኑ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሳሉ ጥንቱኑ በሩን የከፈቱት እሳቸው አይደሉ እንዴ? ስለሆነም ሙስናን የመዋጋት ብቃትም፤ ሞራልም የላቸውም። ስልጠና መልካም ቢሆንም ሙስና በስልጠና አይጠፋም። ሙስናን በሚጠየፍና ለመዋጋት በተዘጋጀ አመራር እንጂ በገንዘብ አዋጡ ስልጠና ሊሆን አይችልም። የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ጽ/ቤትም ይሁን አድባራቶቹ በእነማንና በተደራጀ አዲስ አመራር ተዋቅሯል?
 ሙስናው ከዐለማውያኑ በዐይነቱ የከፋ ሆኗል። አፍኒንና ፊንሐሶች ተፈልፍለዋል። ሁሉም በዐመጻው ተካክሏል። ጠቅላላው ታማሚ በመሆኑ መድኃኒት የሚሆን ነገር ርቋል። ለዓለም ትተርፍ ዘንድ አደራ የተጣለባት ቤተ ክርስቲያን በባላንጣ ተወራለች።  አሳዛኝ ዘመን!
የሚገርመው ደግሞ ሰሞኑን ከጳጳሱ እግር ከሥር ሥራቸው ቱስ ቱስ የሚሉ የማኅበረ ቅዱሳን አሸርጋጆችን ስንመለከት  በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ውስጥ እንደፈለጉ ለመፋነን እድል ማግኘታቸው ጠቋሚ ሲሆን የሚፈሩትን ማኅበር ለማገልገል ግንባራቸውን እንደማያጥፉ  የሊቀ ጳጳሱ የቆየ ልምድ ደግሞ ያረጋግጥልናል። ከወዲያ ፓትርያርክ ማትያስ በቀጥታ መስመር በውዳሴና በተጠናው ደካማ ጎን በኩል በለስላሳ ጥበብ ተይዘዋል። ከወዲህ አቡነ እስጢፋኖስ በረዳት ሊቀ ጳጳስነት ተጠፍንገዋል። በመሀከል የሲኖዶስ ጸሐፊው የማቅ ታማኝ አባል አባ ሉቃስ ተቀምጠዋል። ጥሩ የመድረክ አዳማቂ የነበሩት አቡነ ጢሞቴዎስ ለማኅበሩ ያበረከቱት አስተዋጽኦ ለምርቃት ሳይበቃ በጎዶሎ ቀን ከኮሌጅ ተማሪዎች ጋር ተጋጭተው ከሥፍራ ተወግደዋል።  ያገለገሉትን መለስ ብሎ የማያየው ይህ ማኅበር ከአባ ጢሞቴዎስ ጋር ራሱ ተጣልቶ ከመለያየት የገላገለው የተማሪዎቹ ግርግር ሳያስበው መከሰቱ ነበር። ከጀርባም ሆኖ የተማሪዎቹን ችግር በማራገብ ነዳጅ ያርከፈክፍ የነበረው ይህ እድል ሳያልፈው ለመጠቀም ካለው ፍላጎት የመነጨ ነበር። ያሰበው በተማሪዎቹ ችግር ጀርባ ፍጻሜ አገኘ።  ከዚህ የተነሳ ማኅበሩ በትኩስ በትኩስ ምድብተኞች ለመገልገል እድል ያረግድለታል ወይም  አካሄዱን ያውቅበታል። ይኸው እንደ ሳሙና እየተሙለጨለጨ ዛሬ ላይ ደርሷል። ከዚህ በፊት ውጥረት ሲበዛበት የዐባይን ቦንድ እገዛለሁ እስከማለት መድረሱ እንደሳሙና በመሙለጭለጭ ላለመያዝ መሄድ የሚችልበት ስልት ረቂቅ መሆኑን ያሳያል።
ከላይ እያልነው እንደመጣነው በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ውስጥ  ዛሬም አዲስ ለውጥ የለም። በላተኞች ስልጠና እየወሰዱ ከመሆኑ በስተቀር አዲስ የሥራ ኃይል፤ አዲስ የመዋቅር ለውጥ የለም። አሁንም የታመነባቸው፤ የሚታወቁና የተመሰከረላቸው ሰዎች በለውጥ ሂደቱ ውስጥ የሉም። በአምናውና በካቻምናው በሬ አርሶ ምርት መጠበቅ ከቶ እንዴት ይቻላል? ካልዘሩበት ማጨድ ማለት ይህ ነው።
ሁለት ወገኖች ግን ተጠቃሚዎች ይሆናሉ። ሀ/ስብከቱ በፓትርያርክ ማትያስ የተሰጣቸው ሽልማት ሲሆን ከዚህ በሚገኘው ሲሳይ የሚናኙት አዲሱ ሊቀ ጳጳስና ከአባ ጳውሎስ ሞት በኋላ ታማኞቹ ብቻ ቦታ ቦታቸውን የያዙለት ማኅበረ ቅዱሳን ተጠቃሚዎች ናቸው።
ከዚህ በተረፈ ሀ/ስብከቱ ከሕመሙ ይድናል ብለን እንድንጠብቅ የሚያደርገን የሚታይ አዲስ መንፈስ፤ አዲስ መዋቅር፤ አዲስ የአሰሪና ሰራተኛ ግንኙነት፤ አዲስ የውጤት ምዘና ስልት፤ አዲስ የልማት እቅድ የለም። ካህናቱ ከላይ የሚፈሰውን መመሪያ እንደቧንቧ ከሚጠጣ በስተቀር በሂደቱ ላይ ወሳኝ አካል ተደርጎ አልተወሰደም። ጉዞው ከየት ወደየት? ነው ብንል ከድጡ ወደማጡ ነው መልሳችን። ገንዘብ አዋጡ፤ ገንዘብ አዋጡ! ድሮም ዛሬም ከሀ/ስብከቱ ውስጥ ያልጠፋ የበላዮች ድምጽ አልቀረም። ዛሬ ላይ ይህንን እንደዘገብን አምላክ ቢፈቅድ የዛሬ ዐመትም እንዲሁ የለውጥ ያለህ ብለን እንዘግብበት ይሆናል። የዚያ ሰው ይበለን!

Friday, July 19, 2013

«መጽሐፈ አበው» ስለመነኮሳት ምን አለ?

ምንኩስና ምንድነው? ለመጽደቅስ ጠቃሚ ነው?  የመንግሥተ ሰማያት መውረሻ ስልት ነው? የክብር ወይስ የመከራ፤ የተጋድሎ ወይስ የፍልሰት ጎዳና ነው? ብዙ ሊባልለት የሚችልና ሊባልበት የሚገባ ይህ ሰዋዊ ሥርዓት ቆሜለታለሁ ከሚለው ዓላማ ጋር እየተጣረሰ ዘልቆ በዚህ ዘመን ያለበትን ደረጃ እንድንመለከት «መጽሐፈ አበው» የተባለው ትልቁ መጽሐፍ  በምንኩስና ላይ ካሰፈራቸው ሕግጋት ውስጥ በጥቂቱ ለማቅረብ ወደድን። የግእዙን ትርጉም አንብበው ይህ ሰዋዊ ሥርዓት ዛሬ በሕይወት አለ ወይ? ብለው ራስዎ ይጠይቃሉ።  የሕይወት መንገድ የመሆን፤ አለመሆኑ ጉዳይ ተከድኖ ይቆየንና ምንኩስና ራሱ ተነስቼበታለሁ ከሚለው አቋሙ ጋር ዛሬ ላይ የለም። መነኩሴስ ማነው? «መጽሐፈ አበው» እንዲህ ይናገራል።
መነኮስ ከሀገሩ ወደሌላ ሀገር ይሂድ። በዚያም በዋሻ፤ በኮረብታው፤ በተራራው ይንቀሳቀስ። በረሃብ፤ በብርድ፤ በጥም፤ በመራቆት፤ በድካም፤ በትጋት ይኑር። ልብሱ የከብት ቁርበት፤ የፍየል ቆዳና ለምድ ይሁን። ሥጋ በሕይወት ዘመኑ አይብላ። የዘወትር ምግቡ የበረሃ ጎመን፤ ቅጠልና የዛፎች ፍሬ ብቻ ይሁን። ካገር አገር አይዙር። ወደሠርግ፤ ወደ ድግስ አይግባ። በሕዝብ መካከል የሚኖር መነኮስ ቢኖር እርሱ ውሸታም ነው። የአጋንንት ረድእ፤ አገልጋይ ነው። ወንድ መነኩሴና ሴት መነኩሲት በአንድ ላይ አይኑር፤ ይራቁ። በአንድ ላይ እየኖሩ፤ በአንድ አጸድ እያደሩ ንጽህ እንጠብቃለን ቢሉ ውሸት ነው። ነብርና ፍየል አንድነት ይኖሩ ዘንድ እንዴት ይቻላል? መነኩሴ ማንንም አይማ። ሃሜተኛ ጸሎተኛ አይደለም። አብዝቶ የሚበላ መነኩሴ የትም እንደሚፈነጭ ፈረስ ነው። መነኩሴ በፀሀይ ግባት አንድ ጊዜ ብቻ ይብላ። ወፎች መብል አይተው በወጥመድ ይያዛሉ። ትልቁ አንበሳ በመብል ምክንያት ወጥመድ ውስጥ ይወድቃል። አዳም በመብል ወደቀ። ይሁዳ ከወጡ አጥልቆ በበላ ጊዜ ሰይጣን ገባበት። ሠይጣን መነኮሳትን በመብል ፤በመጠጥ፤ በሃሜት፤ በሳቅና በስካር ያድናቸዋል። ልቅ፤ ልቅ እየጎረሱ፤ የላመ የጣመ እያግበሰበሱ መነኮስ መባል አይገባቸውም። በእንቅልፍ ተውጠው፤ ከጸሎት ተለይተው እንደአዞ ተገልብጠው እንዲተኙ ያደርጋቸዋል። ዘማውያንም ይሆናሉ። ያኔም አጋንንቱ በመነኮሳቱ ላይ ይዘፍናሉ። በእጃቸውም ይጨበጭባሉ። እንደፈረሶች ሰኮና ሆነው ይረግጡአቸዋል። የዓለምን ጣዕም የቀመሱ፤ የወደዱ መነኮሳት የነፍሳቸውን ደዌ ያያሉ። የነፍሳቸውንም መድኃኒት ይተዋሉ። በሕዝባውያን መካከል የሚመላስ መነኮስ  ከቅዱሳን ክብር መድረሻ የለውም። መነኮስ ወደዓለማዊ ችሎት፤ ሸንጎና ፍር አይሂድ።  ምሥክር አይሁን። መነኩሴ ማለት ምዉት ማለት ነውና አይቻለሁ፤ ሰምቻለሁ፤ ዳኝነት አውጡልኝ አይበል። ለሕዝባውያን አበ ነፍስ አይሁን። መነኮስ የሞተ ነውና የሚሰማ ጆሮ፤ የሚናገር አፍ የለውም። ዓለም ውስጥ እየኖረ ዓለምን አሸንፋለሁ ቢል ውሸታም ነው። አትመነው። አፉን፤ ጆሮውንና ዓይኑን የማይጠብቅ መነኩሴ ነፍሱን አያድናትም። መነኮስ እነዚህን ሦስት ሰይፎች ካልታጠቀ መነኮስ አይባልም። የዋህነት፤ ትህትናና ድህነት ናቸው። የዋህነት ከቂም፤ ከበቀል ከጥላቻና ከስጋዊ ነገር ሁሉ መራቅ ነው። ትህትና ራስን ዝቅ ማድረግ ሲሆን ድህነት የኔ የሚለው ሀብትና ገንዘብን ሁሉ መናቅ ናቸው። መነኮስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል። በሕይወት ዘመኑ በእንደዚህ ያልተጠበቀ መነኮስ፤ መነኮስ አይደለም።

Thursday, July 18, 2013

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለምን ተሐድሶ ያስፈልጋታል? ክፍል ሁለት፡-

      
              (www.tehadeso.com)
ላደግንባት፣ ቃሉን ላወቅንባት እና አሁንም እያገለገልንባት ላለችው ለዚህች ቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ሁሉ ዐዲስ የሆነውን የእግዚአብሔርን ቃል በመደገፍ እንደ ቃሉ የሆነ እና የሰላም አለቃ የሚሰለጥንበት ተሐድሶ እንደሚያስፈልጋት፣ በሙሉ ልባችን እናምናለን፡፡ ቤተ ክርስቲያን ተዘፍቃበት ካለው ሁሉን አቀፍ ችግር ለመውጣት የሚያግዛት በመንፈስ ቅዱስ መሪነት የሚከናወን ተሐድሶ አስፈላጊ ነው፡፡
“…እንደ ምሕረቱ መጠን ለዐዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብና በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ አዳነን..”  የሚለው ዐረፍተ ነገር፣ ተሐድሶ በእግዚአብሔር መንግሥት አስፈላጊው እና ፍሬያማው እውነት እንደሆነ ያሳያል፡፡ የእግዚአብሔር ምሕረት ከፍተኛነት በመንግሥቱ ውስጥ ለሚኖረን ቦታ የሚያበቃን፣ በመንፈስ ቅዱስ በኩል የሆነው መታደስ ነው፡፡ ይህ እውነት ለግለሰብም ለቤተ ክርስቲያንም በእኩልነት ይሠራል፡፡ አንድ ሰው ከጠፋው ማንነቱ ተመልሶ ለእግዚአብሔር መንግሥት ዜጋ እንዲሆን ከመንፈስ ቅዱስ የሆነው ተሐድሶ እንደሚያስፈልገው ሁሉ ቤተክርስቲያንም የቀበረችውን እውነት ቆፍራ እንድታወጣ እና ለእግዚአብሔር ሐሳብ እሺ በጄ ብላ እንድትታዘዝ ከመንፈስ ቅዱስ የሆነው ተሐድሶ ያስፈልጋታል፡፡

ባለፈው በክፍል አንድ ጽሑፋችን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለምን ተሐድሶ አንደሚያስፈልጋት ሦስት መሠረታዊ ምክንያቶችን አንሥተን ማቅረባችን ይታወሳል፡፡  ዛሬ ደግሞ ቀጣይ ሐሳቦችን እናቀርባለን፡፡

•    የሥጋዊ  አሠራር ሥር መስደድ፡-


በቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ ሰውና መንፈሳዊ አሠራር ከጠፋ ሰነባብቷል፡፡ ቤተ ክርስቲያን፣ ነገሮች ሁሉ በጸሎት የእግዚአብሔርን ምሪት በመፈለግ ሳይሆን የሚሠራባት፣ የሰውን ፊት በማየት የሚከናወኑባት የዓለማውያን ሸንጎ ሆናለች፡፡ ከሞላ ጎደል በማንኛውም ጉዳይ ለማለት ይቻላል ቤተ ክርስቲያኗ የእግዚአብሔርን ምሪት ጠይቃ አገልጋዮችዋንና ምእመናኗን አስተባብራ በአንድነት በጸሎት በፊቱ ወድቃ የምትከውናቸው ነገሮች የሏትም፡፡ ይልቁንም በአሠራርዋ ከእሷ የተሻለ እንቅስቃሴ ካለው ከመንግሥት ፖሊሲዎች እና ወቅታዊ አጀንዳዎች በመነሣት እነዚያን አጀንዳዎች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለማስፈጸም ከመሯሯጥ ያለፈ ሥራ ተሠርቶ አይታወቅም፡፡ መንግሥት “አቅም ግንባታ” ሲል ቤተ ክህነትም አቅም ግንባታ፣ መንግሥት “ደን ልማት” ሲል ቤተ ክርስቲያንም ደን ልማት፣ መንግሥት የፀረ ሙስና ርምጃ ሲወስድ ቤተ ክርስቲያንም ያውም ላትተገብረው ስለ ሙስና ማውራትን እንደ ትልቅ ቁም ነገር ወስዳ መጽሐፍ ቅዱሳዊ የሆነ የአሠራርም ሆነ የአመለካከት ለውጥ ለማምጣት ምንም  ዝግጅትና ርምጃ ሳታደርግ የሰሞኑ ነጠላ ዜማዋ አድርገዋለች፡፡
እውነተኛው ባለ ራእይና የምሪት አለቃ እግዚአብሔር ተረስቶ፣ ትልቁ ሕገ መንግሥት መጽሐፍ ቅዱስ ተዘንግቶ “ምን ተባለ” እያሉ ሥራ ለመሥራት መሞከር በእስካሁን እንቀስቃሴዋ እንደታየው የተሻለ ለውጥ አላመጣላትም፡፡ መንግሥት የሚያወጣቸው ሕጎችና አፈጻጸሞች የተሳሳቱ ናቸው ባንልም፣ ቤተ ክርስቲያን ግን በእግዚአብሔር መንግሥት አሠራር ውስጥ የዓለማዊውን መንግሥት አሠራር ሙሉ በሙሉ ያውም ምን እንደሆነ እንኳ ሐሳቡ ሳይገባት ለመፈጸም ከሞከረች የሥጋዊነት መገለጫዋ ነው፡፡
በሌሎችም በቤተ ክርስቲያን በሚሠሩ ሥራዎች፣ የእግዚአብሔርን ቤት እንደ መንደር እድር በዘፈቀደ የመምራት እንቅስቃሴዎች ስለምታደርግ፣ ይበልጥ ከእግዘአብሔር ሐሳብ ሲያርቃት እንጂ ወደ ዘላለማዊ አምላኳ ሲያስጠጋት አላየንም፡፡ የሚደረጉት ማንኛቸውም ነገሮች ሥጋ ሥጋ ከመሽተት ያለፈ አንዳች መንፈሳዊነት አይታዩባቸውም፡፡ ከነጭራሹም መጽሐፍ ቅዱስ ተነብቦ የማይታወቅ እስኪመስል ድረስ ከመንፈስ ቅዱስ የሆነ አሠራር ጠፍቷል፡፡ መንፈስ ቅዱስ በሲኖዶስ ጉባኤ እንደሚገኝ ለማሳየት  በጉባኤው አንድ ባዶ ወንበር ቢቀመጥም፣ መንፈስ ቅዱስ ከሲኖዶስና ከቤተ ክርስቲያን ሥፍራ ካጣ ዘመናት ተቆጥረዋል፡፡ የማናውቃቸውን ብዙ “ቅዱሳትና ቅዱሳን” እንድንቀበል አድርጋ በስማቸው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ስታስገነባላቸው ለመንፈስ ቅዱስ ግን ሥፍራ አልተገኘለትም፤ በርግጥ በሚያምኑበት ልብ ውስጥ ያድራል እንጂ የሰው እጅ በሚሠራው ሕንፃ አይኖርም፡፡
ይህ የቤተ ክርስቲያናችን ሥጋዊነትም፣ ሕዝቡን ከእግዚአብሔር ቤት ገፍቶ ሲያስወጣው እንጂ ወደ ንጉሥ ክርስቶስ ቤት ሲመልሰው አልታየም፡፡ ያደጉባትን ቤተክርስቲያንንም፣ በዚህ ሥጋዊነትዋ ምክንያት “አይንሽን ለአፈር” እያሉ ጥለዋት የሚሄዱ ምእመናን ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡ ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን ሥጋዊነትዋን ጥላ በመንፈስ ቅዱስ እየተመራች ለብዙዎች ፈውስ ትሆን ዘንድ ተሐድሶ ያስፈልጋታልና “መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ” እንላለን ፡፡


•    አስተዳደራዊ ብልሽቷ አገልጋዮቿንና ሕዝቧን ስላስጨነቀ


ስለ ኦርቶዶክሳዊቷ ቤተ ክርስቲያናችን ሲነሣ፣ አብሮ ሳይነሣ የማይታለፍ ነገር አስተዳደራዊ ብልሽቷ ነው፡፡ ይህ ርእስ፣ ቤተ ክርስቲያናችን በመንፈስ ቅዱስና በእግዚአብሔር ቃል የተመሠረተ ሁለንተናዊ ተሐድሶ አግኝታ ወደ ጥንተ ቅድስናዋና ክብሯ መመለስ ይገባታል የምንለውን እኛን እና ቤተ ክርስቲያን ከቶውንም ለውጥ አያስፈልጋትም “ስንዱ እመቤት ናት” የሚሉትን ወገኖች ያስማማናል፡፡ አስተዳደራዊ ብልሽቱን ሰዎች የሚያነሡበት መንገድ ይለያይ እንጂ  “የቤተ ክርስቲያኗ ህልውና ያሳስበኛል” የሚል ወገን ሁሉ ያለ ልዩነት የሚያነሣው ርእስ ነው፡፡
ቤተ ክርስቲያንዋ ከተቋማዊ እንቅስቃሴ ይልቅ የግለሰቦች ጠንካራ እና ደካማ ጎን ተገዢ መሆኗ በርግጥ ያሳስባል፡፡ ባለፈው ዓመት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ካረፉ በኋላ በጠቅላይ ቤተ ክህነት አካባቢ የነበረው የአሠራር ዝርክርክነት ከእሳቸው ጋር ጠቅላይ ቤተክህነቱም የሞተ አስመስሎት እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡ በሰው ላይ የተደገፈ አስተዳደራዊ ሥርዓት ፍጻሜው ይሄ ነው ለማለት፣ የብፁዕነታቸውን እንደ ምሣሌ አነሣን እንጂ፣ ከእሳቸው በፊት የነበሩትም አሁንም ያሉት ፓትርያርኮች አሠራር ተመሳሳይ ነው፡፡ በዙርያቸው የሚሰበሰቡ ሰዎችም እነርሱ የሚፈልጉት እስከተሳካ ድረስ ለሌላ ነገር ግድ የሚላቸው አይደሉም፡፡
የደብር አስተደደር ሹመት እንኳ በጥንት ዘመን ከነበረው አውቀት ተኮር ሹመት፣ አሁን ወደ ዝምድና እና ጉቦ ተኮር ወደ መሆን ተሸጋግሯል፡፡ እንዲህ ያለው ሹመት፣ አንድን የደብር አስተዳዳሪ፣ በደብሩ ውስጥ ከሚገኙት በእውቀት ሻል ካሉ አገልጋዮች ይቅርና ከአንድ ዲያቆን ጋር እንኳ የሚስተካከል  ክብር ስለማያሰጠው መናናቁና ጥላቸው፣ ቡድናዊነቱና ወገንተኝነቱ ሥር የሰደደ ነው፡፡ በእውነትና በእውቀት ማስተዳደር ስላልተቻለ፣ ሊቃውንቱ ተገፍተው ጨዋና ወሬ አመላላሹ ተከብሮ እና ተፈርቶ ይገኛል፡፡  የሥራ ድርሻውን የሚያውቅና ሥራውን በአግባቡ የሚሠራ ሰውም ስለጠፋ ምእመኑ የክርስትና ካርድ እንኳ ለማውጣት ጉቦ እየተጠየቀ ይገኛል፡፡ የአገልጋዮች ቅጥር፣ ዝውውር እና የደመወዝ ጭማሪን በተመለከተ ወጥ የሆነ ሕግ ስለሌለ በአስተዳዳሪው እና በሀገረ ስብከት ሹመኞች ይሁንታና ተጠቃሚነት፣ ነገሮች እንደፈለጉ የሚደረጉበት ደብር እጅግ ብዙ ነው፡፡ በብዙ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት፣ መሪጌቶች ከዲያቆን ያነሰ ደመወዝ ስለሚከፈላቸው፣ ተስፋ የሚቆርጡበት ሁኔታ የተለመደ ነው፡፡ ከተማ አቀፍ የደመወዝ አከፋፈል እስኬል ስለሌለ የተሻለ ደመወዝ የሚከፍል ደብር ለመቀጠር እና ለመዘዋወር ያለው ሹክቻና የሚጠየቀው መደለያ ገንዘብ ቀላል አይደለም፡፡ ይህ የአስተዳደር ችግር ውጤት ነው፡፡
በአስተዳደር ችግር ውስጥ እንደገና ሊታይ የሚገባው ቤተ ክርስቲያንዋ የፋይናንስ አያያዝ ነው፡፡ ከገንዘብ አሰባሰቡ ጀምሮ በዐፄ ምኒልክ ጊዜ ከነበረው የገንዘብ አስተዳደር የተሻለ ነገር ምንም  የላትም፡፡ በገንዘብ አቆጣጠር ላይ ያለውን አካሄድ ስንመለከተው፣ ለአታላይ በጣም የተመቸ ነው፡፡ ምንም ዐይነት ዘመናዊ የሂሳብ አያያዝ መንገድ የማይታይበት፣ ዘመናዊውን የሂሳብ አያያዝ ዘዴ የተማረ ሰው የማይቀጠርበት፣ የደመ ነፍስ መድረክ ሆናለች፡፡ ሌላው የሂሳብ አያያዙ ከፍተኛው ድክመቷ፣ የቤተ ክርስቲያን አንድነት ተረስቶ  “ወነአምን በአሀቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን” የሚለው የአባቶች ትምህርት ተዘንገቶ፣ ደብሮች  እንደ ፌደራል መንግሥት፣ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት የሚፈለግባቸውን ብር ከሰጡ በኋላ፣  ገንዘቡን በገዛ ፈቃዳቸው የፈለጉትን ማድረግ የሚችሉበት መሆኑ ነው፡፡ ገጠር ያሉ አብያተ ክርስቲያናት በደመወዝና በንዋየ ቅዱሳት እጦት እየተዘጉ በአዲስ አበባ ግን ሰባ እና ሰማንያ ሚሊየን ብር በዝግ አካውንት የሚያስቀምጡ ደብሮች መኖራቸው የተለመደ ነገር ሆኗል፡፡
ቤተ ክርስቲያን አንድ እንደሆነች ከንግግር ባለፈ በቃሉ የሚታመን ከሆነ፣ የኑሮ ድካም ትከሻቸውን አጉቡጧቸው ወደ ከተማ የሚሰደዱትን የገጠር አብያተ ክርስቲያናት አገልጋዮችን ለመታደግና ባሉበት ቦታ በቂ ገንዘብ ከፍሎ ለማኖር ይቻል ነበር፡፡ ምእመኑ ከቤተ ክርስቲያን የሚፈልገውን አገልግሎት ለማግኘት ሲመጣ ቀድሞ የሚታየው ኪሱ እንጂ ልቡ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን የድሆች መጠጊያ መሆንዋ ከቀረ ሰንብቷል፡፡ እንደ መንግሥት ቢሮ  ገንዘብ ያለው ከፍሎ የሚስተናገድባት የሌለው ተገፍቶ የሚወጣባት ቤት መሆንዋ ለብዙዎች የልብ ስብራት ምንጭ አድርጓታል፡፡
እንደዚህም በእጅጉ የሚያሳዝነው የአስተዳደር ብልሹነት መገለጫ በገጠር ያሉ እና ሊዘጉ የተቃረቡ አብያተ ክርስቲያናትን ለሀገረ ስብከት የተመደበባችሁን ብር አልላካችሁም በመባል የሚደርስባቸው ማስፈራራት እና “ቤተክርስቲያኑን እንዘጋዋለን” ቁጣ ነው፡፡ ለእነዚህ የገጠር ካህናት፣ በነጻ የሚያገለግሏት ቤተ ክርስቲያን የበላይ ኃላፊዎች የአባትነት ፍቅርና ምስጋና ማቅረብ ቢያቅታቸው እንኳ የኑሯቸውን ሁኔታ እያወቁ ማስጨነቅ ባልተገባቸው ነበር፡፡ ዲታዎቹን የአዲስ አበባ አብያተ ክርስቲያናትን፣ የእስፖንሰር ገንዘብ እየጠየቁ ለቅንጦት ነገሮች ከማዋል፣ በጭንቅ በሬ ሸጠው ዓመታዊ መዋጯቸውን እንዲከፍሉ የሚገደዱትን የገጠር አብያተ ክርስቲያናት አባቶች መታደግ ይገባ ነበር፡፡
ይህንን የአስተዳደር ብልሹነት በቤተክህነት ሥር የሰደደውን ሙስና ባለፈው ሰኔ 29/2005 ዓ. ም.  ቅዱስ ፓትርያርኩ በተገኙበት፣ የቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎች ምረቃ ላይ መምህር ልዑል የተባሉ ሰው በዘይእሴ ቅኔ እንዲህ ሲሉ ገልጠውታል፡፡
ቤታችን ሆኗል ቤተ ወንበዴ፣ እጅግ ያሣዝናል በእውነት የሚፈጸመው ግፍ ተግባሩ፡፡
ሊቃነ ጳጳሳት ፍቀዱና፣  ቢ. ፒ. አር. ወፀረ- ሙስና ገብተው ይመርምሩ፡፡
ብዙዎች ስላሉ በግል መዝብረው የከበሩ፡፡
ዘረፉኝ እያለች በቀን ምንም ሳይፈሩ፡፡
ሙዳየ ምፅዋት ምስኪን ትጮኻለችና በበሩ
ዘረፉኝ እያለች በቀን ምንም ሳይፈሩ፡፡

እንዲህ ያለውን የውስጥ ብሶት በአደባባይ ሲቀርብ ሰምቶ ከማጨብጨብ እና ይበል ብለናል ከማለት ያለፈ የተደረገ ነገር የለም፡፡
ባለፉት ብዙ ወራት ሊፈታ ያልቻለውና ይልቁንም እየተባባሰ ያለው፣ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎች ጉዳይ ሌላው በቤተክርስቲያን የተንሰራፋውን አስተዳደራዊ ችግር አጉልቶ የሚያሳይ ነው፡፡ ተማሪዎች ችግር አለብን ሲሉ ሰምቶ የሚያስተናግድ እና ችግሩን የሚፈታ አባት አልተገኘም፡፡ በየአቅጣጫው ከእውነታ ይልቅ ለሁኔታ እና ለቀረቤታ የሚያደሉ አሠራሮች ቤተክርስቲያኗን ይጎዳል እንጂ አይጠቅምም፡፡ ደቀመዛሙርቱን በግፍ ለማባረርና አስተዳደራዊ ጥያቄያቸውን ላለመመለስ፣ ፖለቲካዊ መልክ እንዳለው በማስመሰል ከመንግሥት ጋር ለማጋጨት በመሪዎች እየተወሰደ ያለው ርምጃ አስተዳደራዊ ብልሽቱን ከማጋለጡም በላይ ጉዳዩን በንቀት እየተመለከቱት መሆኑን ማሳያ ነው፡፡  
ሌላው የአስተዳደር ብልሹነቱ ገጽታ የሆነው በሐዋሳ፣ በክብረ መንግሥት፣ በዲላ፣ በሐረርና በሌሎችም የሀገሪቱ ክፍሎች የተፈጠሩት ችግሮች እና የምእመናን መንገላታት ነው፡፡  ለችግሮቹ “ይህ ነው” የሚባል መፍትሔ ሳይሰጠው አሁንም እንደ ቀጠለ መሆኑን ስናስብ በተለይ አሁንም ተስፋ ሳይቆርጥ፣ ሲኖዶሱን እየተማጠነ ላለው ሕዝብ በእጅጉ እናዝናለን፡፡ የዚህ ችግር ፈጣሪዎች ከሆኑት መካከል አንዳንዶቹም መንፈስ ቅዱስ ይመራዋል የሚባለው ሲኖዶስ አባላት የሆኑ ጳጳሳት መሆናቸውን ማሰብ ልብን ያደማል፡፡ የመፍትሔ አመንጪ መሆን የሚገባቸው አባቶች የችግሩ ፈጣሪዎችና አባባሾች መሆናቸው የሚያስገርም እውነት ነው፡፡
በቤተ ክርስቲያን ያለው የአስተዳደር በደል እና የሥራ ዝርክርክርነት ከመነገር በላይ ነው፡፡ አገልጋዩም ሆነ ሕዝቡ በቤተ ክርስቲያን ባለው አስተዳደራዊ በደል ተስፋ ቆርጦ እና አዝኖ ይገኛል፡፡ እንዲህ ያለው ችግር በቶሎ መስተካከል ካልቻለ እንደደነበረ በግ እየበረረ የሌሎችን በረት በመሙላት ላይ ያለውን የምእመናን ፍልሰት በእጅጉ ያባብሰዋል፡፡ ከዚህ እና ከሌች አስተዳደራዊ ችግሮች ለወውጣት ተሐድሶ አማራጭ የሌለው መንገድ ነውና ደግመን መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ ልንል እንወዳለን፡፡
ይቀጥላል! …

Friday, July 12, 2013

በቅድስት ሥላሴ ኮሌጅ ያለው ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል!

ቀደም ሲል ስንል እንደቆየነው ሁሉ አሁንም ደግመን እንለዋለን። የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ አስተዳደራዊና አካዳሚያዊ ችግሮች ይህንን ያህል እንኪያ ሰላንትያ ውስጥ የሚያስገባ አልነበረም። ቤተክርስቲያኒቱ ባላት አቅም፤ የሰጠችውን መክፈልተ ሲሳይ ለተማሪዎቹ በተገቢው መንገድ ማድረስ ለመቻል ባለሙያና ትጉህ አስተዳደር ለማስቀመጥ መሞከር ቀዳሚው ነጥብ ሲሆን፤ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ እንደመሆኑ መጠን ቀሚስ ለባሽ ሳይሆን ራሱን ለውጦ ሌላውን መለወጥ የሚችል የተማረ ኃይል ለማፍራት ደረጃውን የጠበቀ የምሁራን ስታፍ በመመደብ የነገይቱን ቤተ ክርስቲያን ይረከቡ ዘንድ ማስቻል ሁለት የተሰናሰሉ አስፈላጊ ኩነቶች ሆነው ሳሉ የአስተዳደርና ብቃትና አርቆ የማሰብ ርእይ በዞረበት ያልዞረው ቤተ ክህነት ጉዳዩን አጡዞ መውጫ ወደሌለው አዘቅት ውስጥ ኮሌጁን እየወረወረው ይገኛል።
መነሻ ምክንያቶቹም ሁለት ናቸው።
1/ የአባ ጢሞቴዎስ ደካማ አስተዳደርን ለማስወገድና ከእርሳቸው ጋር የተማማሉ መሰሪ የኮሌጁ ሹማምንት የሚፈትሉት ውል የለሽ የነገር ልቃቂት ጋር የፓትርያርክ ማትያስ « ከእርስዎ ጋር ሞቴን ያድርገው » ቃል ኪዳን ላይበጠስ መተሳሰሩ ቀዳሚው ነው።
2/ ከነዚሁ ወሳኝ ከሆኑና ነገር ግን ጉዳዩን እንደናዳ ድንጋይ እያንከባለሉ ተማሪዎቹ ላይ የሚመርጉት ትላልቅ ኃይሎች እንዳሉ ሆነው በተገኘው አጋጣሚና ክፍተት ተጠቅሞ ከኮሌጁ ድኩምና መዝባሪ አስተዳደሮች ጋር በፕሮቴስታንታዊ ተሓድሶ ዜማ እየታገዘ የሚጠላቸውን ሰዎች በመጥረግ ራሱ ባዘጋጃቸው ተላላኪዎች በመተካት የኮሌጁን የመተንፈሻ ሳንባ ለመቆጣጠር የሚፈልገው ያ መሰሪ ማኅበር ባሰማራቸው ጉዳዩ ፈጻሚዎቹ በኩል ከወዲህ ጠርዝ ከተማሪዎቹ ችግር ጋር እንደአዞ እያነባ ከጀርባ ሲጮህ መገኘቱ ነው።
ከእነዚህ ሁለት ስውርና ግልጽ ኃይሎች ማለትም አንዱ የተማሪዎቹን ጩኸት እየጮኸ ከጀርባ ሆኖ ግፋ በለው ቢልም  ሌላኛውን ኃይል የተማሪዎቹን ጩኸት ላለመስማት ምክንያቶችን እየደረደረ እነሆ ወራቶችን አስቆጥሯል። ከዚህ ቀደም እንዳልነው አዲሱ ፓትርያርክም የመጣ ደብዳቤ ከመፈረም ውጪ እርባና የሌለው ሥራ ሳይሰሩ፤ ይባስ ብለው በሰላም ሀገር ኮሌጁ ይዘጋ ወደሚል ምክንያት የለሽ ውሳኔ ደርሰዋል። በጣም አሳዛኝ ነገር ነው።
ማኅበረ ቅዱሳን በአባ ጢሞቴዎስ እጅ እንዳልበላና እንዳልጠጣ ( ስንት ደብዳቤ እንዳላስፈረማቸው) ዛሬ በማኅበሩ የተሐድሶ ጥቁር ፋይል ላይ የተመዘገቡና አልታዘዝ ያሉትን ሰዎች አባ ጢሞቴዎስ ከጎናቸው ስላቆሙና አባረው ወደማኅበሩ ጊሎቲናዊ ጥርስ ውስጥ ስላላስገቡ ብቻ «ሐራ ተዋሕዶ» በተባለ የመጮኺያ ማሽን በኩል በአባ ጢሞቴዎስ ላይ አንዲት ቅጠል የማይበጥስ እርግማኑን ይወረውራል።
እውነት የአባ ጢሞቴዎስ አስተዳደራዊ ድኩምነትና ግትርነት ለማኅበሩ የታየው ዛሬ ነው? ነፍሳቸውን ይማርና ከአቡነ ጳውሎስ ጋር አባ ጢሞቴዎስ በነገር ሲፋጠጡ፤ ማኅበሩ ለአባ ጢሞቴዎስ እሳቱ፤ ቅባቱ፤ መርዙ፤ ብረቱ እያለ ሲያሞካሽ አልነበረምን? ያንን ሁሉ ዛሬ ምን ውሃ በላው? ነገሩ ወዲህ ነው። ፈረንጆቹ /Use and throw/ ይሉታል። አንዴ ተጠቅመህ ሲያበቃ ወርውረህ መጣል ማለት ነው። አባ ጢሞቴዎስ እኔ ያልኩት እንደሚሉ፤ ግትርነት እንደሚያጠቃቸው፤ ተላላና ተደላይ መሆናቸው የዋለ ያደረ ባህርያቸው ነው። ይሁን እንጂ ማኅበሩ ያስፈልጉት በነበረበት ወቅት አገልግለውታል። ዛሬ ደግሞ አስፈላጊው አይደሉምና ከግዙፉ የተማሪዎቹ ችግር ጀርባ የቀድሞውኑ የምናውቃቸውን አባ ጢሞቴዎስን ይራገማል።
በሌላ መልኩ አዲሱ ፓትርያርክ የቀድሞውን ፓትርያርክ በየሚዲያው ሲያብጠለጥሉ እንዳልነበር ያቺ ታስነቅፍ የነበረችው ሥልጣን ተሽከርክራ እጃቸው ላይ ስትወድቅ ታሪክ ራሱን ይደግማል እንዲሉ ትንሹን የተማሪዎች ችግር መፍታት አቅቷቸው ታንክ የታጠቁ ያህል ቆጥረው ግቢያችን የሆነው ባድመን ልቀቁ የሚል አዋጅ ለማስነገር ሲበቁ ስናይ «ከበሮ በሰው እጅ ሲያዩት ያምር፤ ሲይዙት ይደናገር» የሚለውን ብሂለ አበው አስታወሰን። ለአባ ጢሞቴዎስ የሚከፈል ትንሹ ዋጋ መሆኑ ነው።
ተማሪዎቹም ራሳቸውን ማጥራት የሚገባቸው ማንም አፍና ምላስ ሆኖ የሚጮህላቸው ማኅበርና የማኅበሩ አቀንቃኝ ቀሚስ ለባሽ በመሃከል ተሰግስጎ መኖር እንደሌለበት ነው። ጥያቄያቸው አጭርና ግልጽ ነው። «አስተዳደራዊና የተማሪ ዕለታዊ ኑሮ ይስተካከል» የሚል ብቻ መሆኑን አበክሮ ማስረገጥ ይገባል። ከዚህ ውጪ ቤተ ክርስቲያኒቱ ራሷ መተኪያ የሌላትና ሁሉን የሰበሰበች ማኅበር ሆና ሳለ ሌላ የቀኝ ክንፍ ማኅበር አባል በመሆን ችግሩን የታከከና ለራስ መደላድል ሁኔታዎችን ማጽዳት የሚሉትን አንጥሮ አለመግፋት በራሱ ወንጀልም ኃጢአትም ነው።
ከዚህ የተነሳ ማለት የሚቻለው ነገር ቤተ ክህነቱም ራሱ ገርፎ ራሱ እየጮኸ ነው። ግቢውን ለቃችሁ ውጡልኝ ማለት ምን ማለት ነው? በሌላቸው ውክልናና እውቀት በአንድ በኩል የተሐድሶ አቀንቃኞች በኮሌጁ ተሰግስገዋል እያሉ፤ በሌላ መልኩ ደግሞ የአስተዳደር በደል ተፈጽሟል በሚል ዲስኩር ከተማሪዎች ጋር የሚጮሁ የሰው አራዊቶች ድምጻቸውን ያቁሙ። እነዚህኞቹም ራሳቸው ገርፈው ራሳቸው የሚጮሁ ቀላማጆች ናቸው።
እኛ የምንለው ተማሪዎቹም መባረር የለባቸውም፤ ማኅበር የሚባል የወፍ ጉንፋን በሽታ ከግቢው ይውጣ! አባ ጢሞቴዎስም ሌላው ቢቀር ዓይናቸው ደክሟልና ከሥራው አሳርፏቸው። በሽታው እንዳይዛመት የማኅበሩ የወፍ ጉንፋን ቫይረስ ያልለከፈው አባት ይሾም። ለዚያውም ካለ!!!  ጅራፎች ሆይ፤ በመከራ በገረፋችሁት ተማሪ ላይ ራሳችሁ ገርፋችሁ፤ራሳችሁ እንደተበደለ ሰው አትጩሁ!!!!!!!!!!

Sunday, July 7, 2013

እነ አርቲስት ጀማነሽ “የቅዱስ ኤልያስ”ን መልዕክት ለፓትሪያሪኩ እንዳናደርስ ተከለከልን አሉ


(አዲስ አድማስ )“የማህበረ ስላሴ ዘደቂቀ ኤልያስ” አባላት፤ ከቅዱሳን አባቶች የተላክነውን የቅዱስ ኤልያስን መልዕክት ለአዲሱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ክርስቲያን ፓትሪያሪክ አቡነ ማቲያስ እንዳናደርስ ተከለከልን አሉ፡፡ አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን የተካተተችበት መልዕክት አድራሽ ቡድን፤ ባለፈው ማክሰኞ ረፋዱ ላይ መልዕክታቸውን ጋዜጠኞች ባሉበት ለፓትርያርኩ ለማቅረብ ፓትሪያሪኩ ጽ/ቤት በር ላይ ተገኝተው የነበረ ቢሆንም የጥበቃ አባላት “ለማነጋገር ፍቃድ የላችሁም” ብለው መልሰዋቸዋል፡፡ ከማህበሩ አባላት መካከል አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን እና መ/ር ወልደመስቀል ፍቅረማርያም ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ ለሁለት ጊዜያት ያህል 4 ኪሎ በሚገኘው መንበረ ፓትሪያሪክ ጽ/ቤት በመሄድ ከአባቶች የተላኩትን መልዕክት ለማድረስ ቢሞክሩም ከጽ/ቤቱ የጥበቃ ሃላፊዎች ማለፍ አልቻሉም።
“በመጀመሪያው ቀን ከማህበረ ስላሴ መልዕክት ይዘን መምጣታችንን ለጥበቃዎች በመንገር ወደ ውስጥ እንድንገባ ከተፈቀደልን በኋላ ሌሎች በግቢ ውስጥ የነበሩ ጥበቃዎች በድጋሚ አስቁመውን ከስላሴ ካቴድራል ማኅበር የመጣችሁ መስሎን ነው እንጂ እናንተ መግባት አትችሉም በማለት ፓትሪያሪኩን እንዳናገኝ ተደርገናል” የሚሉት መ/ር ወልደመስቀል፤ በተለይ አንዲት ሴት የጥበቃ አባል ከአግባብ ውጭ ጀማነሽን እየገፈታተረች እንድትወጣ ማድረጓን ገልፀዋል፡፡ በሚዲያ ሳይቀር ቅዱስ ፓትሪያሪኩ ማንም ሰው ያለከልካይ በአካል መጥቶ ሊያነጋግረኝ ይችላል ያሉትን መነሻ አድርገን በመጀመሪያ ቀን ያለቀጠሮ የሄድን ቢሆንም ለሁለተኛ ጊዜ ቀጠሮ ለማስያዝ ብንፈልግም የሚያስተናግደን አካል በማጣታችን ለመመለስ ተገደናል የሚሉት መ/ር ወልደመስቀል፤ ጥበቃዎቹ የሄድንበትን ጉዳይ ጠይቀውን ከተረዱ በኋላ ፈጽሞ መግባት አትችሉም፤ ቀጠሮ ማስያዝ ከፈለጋችሁ አንድ እማሆይ አሉ፤ እሣቸውን አነጋግሩ ተባልን፤ የተባሉት ግለሰብ ግን ፍቃድ ወጥተዋል የሚል ምላሽ አገኘን ብለዋል፡፡ “አሁንም ለሶስተኛ ጊዜ ስንሄድ ጥበቃዎቹ ፈጽሞ መግባት አትችሉም፡፡ አካባቢውን ለቃችሁ ሂዱ አሉን” ብለዋል - የማህበሩ አባላት፡፡
ባለፈው ማክሰኞ 10 የሚደርሱ ሴቶችና ወንዶች የማህበሩ መገለጫ የሆነውን ነጭ ባለቀስተ ደመና ጥለት ልብስ ለብሰው ፓትሪያርኩ ጽ/ቤት በሩ ላይ ቆመው ነበር፡፡ የነብዩ ኤልያስ መልዕክት ምንድነው ብለን የጠየቅናት አርቲስት ጀማነሽ ሠለሞን “መልዕክቱ ለፓትሪያሪኩ ስለሆነ እሳቸው ከሰሙ በኋላ ለህዝብ እንድታደርሱ ይነገራችኋል” ብላለች፡፡ የመንበረ ፓትሪያሪክ ልዩ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ታምሩ አበራ ከአዲስ አድማስ ስለ ጉዳዩ ማብራሪያ ተጠይቀው “እስካሁን ጥያቄ ያቀረበልን የለም፤ ቤተክርስቲያኒቷ የራሷ የቅሬታ አቀራረብ ሥርዓት አላት፡፡ ለቅሬታም ሆነ ለቡራኬ የሚመጡትን በቀጠሮ እናስተናግዳለን፡፡ እስከ ሀምሌ 21 ቅዱስ ፓትሪያሪኩን በስልክ ለማነጋገር የተያዙ ቀጠሮዎች አሉ” ብለዋል፡፡ ከነብዩ ኤልያስ መልዕክት አለን ያሉት ግለሰቦች “ኦርቶዶክስ” የሚለው ስያሜ “ለተንኮል” የገባ ስለሆነ የቤተክርስቲያኒቱ ስያሜ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን መባሉ ቀርቶ “የኢትዮጵያ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን” መባል አለበት በሚል አላማ እንደሚንቀሳቀሱ ይታወቃል፡፡

Saturday, July 6, 2013

የካህናቱ የ«እናውቃለን» እና «አናውቅም» እውቀት!



ካህናቱ ከተራው ሕዝብ በቃለ እግዚአብሔር የተሻለ እውቀት እንዳላቸው ይታመናል። ይጠበቃልም። ነገር ግን አብዛኛውን ጊዜ መጻሕፍቱ ላይ «እያዩ የማያስተውሉ» ተብሎ የተነገረባቸው ደግሞ እነዚህ የእውቀት ማዕድ ያካፍሉ ዘንድ በክህነት አገልግሎት የተሰለፉትን ሆኖ ስናይ እጅግ ያስገርመናል። ካህናቱ እያዩ የማያስተውሉ ከሆነ የሚመሩት ሕዝብ ምን ሊሆን እንደሚችል መገመት አይከብድም።
አይሁዳውያኑ ካህናትና የመጻሕፍቱ መምህራን ስለብሉያት መጻሕፍት በቂ እውቀት እንዳላቸው ከመገመቱም በላይ ራሳቸውም በቂ እውቀት እንዳላቸው ስለራሳቸው ሲመሰክሩ እናነባለን። ይሁን እንጂ እውቀታቸው ሲመዘን ብዙውን ጊዜ አውቀን ተናገረናል የሚሉት አንደበት እርስ በእርሱ ከመጋጨቱ አልፎ ተርፎም ሰዎቹ ራሳቸውም ጭምር እርስ በእርሳቸው የሚጋጩበትም አጋጣሚ ታይቷል።
ለዚህም ጥሩ ማሳያ የሚሆነን ከላይ በርዕሱ ላይ ያስቀመጥነው ነጥብ ጥሩ መነሻ ይሆነናል። እነዚህ የእውቀት ማዕድ አደላዳዮች እንደሆኑ የሚታሰብላቸው ካህናት በአንድ ወቅት በአንድ ምላስ ሁለት ቃል በመናገር አንዴ «እናውቃለን» ያሉትን አንደበት ሽረው ወዲያው ደግሞ «አናውቅም» በማለት ሲናገሩ እናገኛቸዋለን።
ካህናቱ ይኸንን ቃል የተናገሩት ጌታ ኢየሱስ ከደብረ ዘይት ተራራ መልስ በቤተ መቅደስ ብዙ ካስተማረ በኋላ በድንጋይ ሊወግሩት በፈለጉና በመካከላቸው ተሰውሮ በወጣ ጊዜ ነበር።  ከዚያ አልፎ እንደወጣ ዘመኑን ሁሉ ዓይነ ስውር የነበረና በልመና የሚተዳደር አንድ ሰው ባገኘ ጊዜ «ደቀ መዛሙርቱም መምህር ሆይ፥ ይህ ሰው ዕውር ሆኖ እንዲወለድ ኃጢአት የሠራ ማን ነው? እርሱ ወይስ ወላጆቹ? ብለው ጠየቁት» ዮሐ 9፤2
ጌታም ሲመልስ፤ «በራሱም ይሁን በቤተሰዎቹ ኃጢአት ሳይሆን የእግዚአብሔር ሥራ ይገለጽ ዘንድ» እንደዚያ መሆኑ ከገለጸላቸው በኋላ የመጣበትን የማዳን ስራ በማሳየት በምራቁ ጭቃ ለውሶ ዓይኑን በመቀባትና በሰሊሆም መታጠቢያ በመታጠብ ዓይነ ብርሃኑ እንዲመለስ እንዳደረገለት እናነባለን።
የሚገርመው አስደናቂ ነገር የሚጀምረው እዚህ ላይ ነው። ዓይነ ብርሃኑ የጠፋው ይህ ሰው ዓይኑ ከበራለት በኋላ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ከመወለዱ አንስቶ እውር የሆነን ሰው ዓይን ያበራ ሰው ስለመኖሩ እንዳልተሰማ በመሰከረ ጊዜ ካህናቱ በተቃራኒው ሃሳቡን በመቃወም «ይህ ሰው ኃጢአተኛ እንደሆነ እናውቃለን» በማለት የመጀመሪያ ቃለ ጽርፈት ሲሰነዝሩ ታይተዋል። ዮሐ 9፤24
ዓይነ ስውር የነበረው ሰው የተደረገለትን ነገር አድንቆ ለካህናቱ ሲመልስ «ኃጢአተኛ መሆኑን አላውቅም፤ ዕውር እንደ ነበርሁ አሁንም እንዳይ ይህን አንድ ነገር አውቃለሁ አለ» ዮሐ 9፤25
ካህናቱ የማያውቁትን የብርሃን ጌታ እንደሚያውቁት አድርገው በላዩ ላይ የሀሰት አንደበት ሲከፍቱ፤ እውር ሆኖ መወለዱንና አሁን ግን ብርሃን እንደተሰጠው የተግባር ምስክር ሆኖ የራሱን ሕይወት ስለቀየረው ስለኢየሱስ ማንነት ከካህናቱ በተሻለ ማወቅ መቻሉ በእርግጥም አስገራሚ ነገር ነው። ምናልባትም ራሱ ባለቤቱ እንደተናገረው « የማያዩ እንዲያዩ የሚያዩም እንዲታወሩ እኔ ወደዚህ ዓለም ለፍርድ መጣሁ አለ» ያለው ቃል እንደተፈጸመባቸው የሚያስረዳን ነገር ይሆናል። ዓይነ ስውሩ የሥጋ ብርሃንም፤ የልቡና ዓይንም ሲገለጥለት የልቡናቸውን ብርሃን በእውቀት እንደሞሉ የሚያስቡና ዓይነ ሥጋቸውም ከልደታቸው ጀምሮ ምሉዕ እንደሆነ የሚተማመኑት ካህናት ግን በሁለቱም ወገን መጋረዳቸውን አንደበታቸው ያረጋግጣል። ይኸውም ከእናቱ ማኅጸን አንስቶ እውር ሆኖ የተወለደን ሰው ብርሃን መስጠት የቻለ ስለመኖሩ ከዚህ ቀደም እንዳልተሰማና ይህንን ለማድረግም ከእግዚአብሔር ካልሆነ በስተቀር ኃጢአተኛ ሰው ብርሃን መስጠት እንደማይችል ልቡናቸው እያወቀ የለም! ይህ ሰው «ኃጢአተኛ እንደሆነ እናውቃለን» ሲሉ በቃለ ሀሰት ምስክርነት እስከመስጠት ያደረሳቸው ነገር እያዩ የማያዩ ሰዎች ስለሆኑ ነበር።
 እነዚህ ልበ ዕውራን ካህናት የዕውርነታቸው መጠን የለሽነት የሚገለጸው ደግሞ የተነገራቸውን እውነት ለመቀበል አለመፈለጋቸው ብቻ ሳይሆን እየተነገራቸው የሰሙትን ለመሸከም የሚችል ልቡና የሌላቸው መሆናቸው ደግሞ ሌላው አስገራሚ ነገር ነው።
ካህናቱ ዓይኑ ስለበራለት ሰው በቅድሚያ ጥያቄ ያቀረቡት ለወላጆቹ ነበር። «እናንተ ዕውር ሆኖ ተወለደ የምትሉት ልጃችሁ ይህ ነውን? ታድያ አሁን እንዴት ያያል? ብለው ጠየቁአቸው» ዮሐ 9፤19
ወላጆቹም፤ ዓይነ ስውሩ ልጃቸው አሁን ዓይኑ እንደበራለት ከመሰከሩ በኋላ ማን እንዳበራለትና እንዴት እንደበራለት እንደማያውቁ በተናገሩ ጊዜ ካህናቱ ሁለተኛ ማረጋገጫ በመሻት ወደ ጉዳዩ ባለቤት በመሄድ ጥያቄያቸውን ዓይነ ስውር ለነበረው ሰው አቅርበዋል። እሱም ሲመልስ «ያበራለት ሰው ኃጢአተኛ መሆኑን እንደማያውቅ፤ ነገር ግን ዓይኑን እንዳበራለት እንደሚያውቅ ሊገባቸው በሚችል ቋንቋ በግልጽ ተናግሮ ሳለ መልሰው በጥያቄ ሲያደርቁት ይታያሉ። ዳኅጸ ልሳን በመፈለግ ለመክሰስና ሸንጎ አቁሞ ለማስወገዝ ወይም ለማስደብደብ ካልሆነ በስተቀር ወደእውነት ለመመለስ ለቀና ነገር ቀና ልብ መቼም የሌላቸው ናቸው።
«ደግመውም። ምን አደረገልህ? እንዴትስ ዓይኖችህን ከፈተ? አሉት» ዮሐ 9፤26 ዓይኑ የበራለትም ሰው ነገረ ስራቸው ሁሉ አስገርሞትና እንደዚህ አብዝተው ጥያቄ መጠየቃቸው በተደረገው ተአምር ተስበውና በኢየሱስ የማዳን ፍቅር ተሸንፈው ደቀ መዛሙርቱ ለመሆን የፈለጉ መስሎት በመሰላቸት ስሜት እንዲህ ሲል መለሰላቸው።
«እርሱም መልሶ፦ አስቀድሜ ነገርኋችሁ አልሰማችሁምም፤ ስለ ምን ዳግመኛ ልትሰሙ ትወዳላችሁ? እናንተ ደግሞ ደቀ መዛሙርቱ ልትሆኑ ትወዳላችሁን? አላቸው» ዮሐ 9፤26
ካህናቱ ነገረ መጻሕፍትን አዋቂዎች ናቸው፤ እድሜአቸውን ሁሉ በመቅደሱ ሲያገለግሉ ኖረዋል፤ በዚያ ላይ ዓይናቸው አልታወረም። በእርግጥም መጠየቃቸው ደቀመዛሙርት ለመሆን ከመፈለግ የተነሳ ሊሆን እንደሚችል ቢገመት ስህተት ላይሆን ይችላል። ስህተቱ ግን ካህናቱ ክርስቶስን ለማወቅ አለመቻላቸው ብቻ ሳይሆን ለማወቅም አለመፈለጋቸውን አለመረዳት ነው። ልበ ዕውራኑ ካህናትም ሲመልሱ እንዲህ አሉ።
«ተሳድበውም። አንተ የእርሱ ደቀ መዝሙር ነህ፥ እኛ ግን የሙሴ ደቀ መዛሙርት ነን፤ እግዚአብሔር ሙሴን እንደ ተናገረው እኛ እናውቃለን፥ ይህ ሰው ግን ከወዴት እንደ ሆነ አናውቅም አሉት» ዮሐ 28-29
ዕውር ሆኖ የተወለደውን ሰው ዓይኑ ብርሃን ስለማግኘቱ ለማወቅ አንድም ቦታ መፈለጋቸውን አናነብም።  ዓይነ ብርሃኑ የተመለሰለትን ሰው በጥያቄ ከማሰለችታቸው በላይ ተመጣጣኝ መልስ ቢሰጣቸው ካህናት ሆነው ሳለ የምላሻቸው ማሟሺያ ስድብ ጭምር ማከላቸው በእርግጥም እውቀት በተለይም መንፈሳዊ እውቀት ከላይ ከሰማይ ካልተሰጠ በስተቀር በትምህርትና በክህነት ማዕርግ ሊገኝ እንደማይችል ያረጋግጥልናል። ይህንንም እውነት ጌታችን ራሱ እንዲህ ሲል መናገሩ የታሪኩን እውነታ ያሳያል። «የላከኝ አብ ከሳበው በቀር ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል የለም» ዮሐ 6፤44  ለሰው ልጅ ትምህርትና እውቀት አስፈላጊ የለውጥ መሣሪያዎቹ እንደሆኑ ባይካድም  ከላይ ካልተሰጠ በስተቀር ይህ በራሱ ወደእውነተኛ መገለጥ ሊያደርስ አይችልም። ብዙ አዋቂዎች ባለማወቅ ደመና ተሸፍነው መገኘታቸው ዘወትር የምንመለከተው ሐቅ ነው።
ካህናቱ ዓይነ ስውሩን ከሰደቡት በኋላ «አንተ የእርሱ ደቀ መዝሙር ነህ፤ እኛ ግን የሙሴ ደቀ መዛሙርት ነን» አሉት።  የኢየሱስ ደቀ መዝሙር መሆን የተናቀ ደረጃ ሲሆን የሙሴ ደቀ መዝሙር መሆን መቻል በካህናቱ ዘንድ ትልቅ እድገትና እውቀት መሆኑ ነው። ዛሬም «የእርቃችን መንገድና እውነት፤ መድኃኒትና በር ኢየሱስ ብቻ» ብሎ መጥራት ያስነቅፋል። በዚህ ላይ ልዩ ልዩ የመዳኛ መንገዶችን፤ ብዙ ብዙ አማላጆችን ካልያዝክ በስተቀር  «ኢየሱስ» በሚለው ስም ላይ ብቻ መታመን ዋስትና እንደሌለው የሚያስተምሩ ካህናት አሉ። «ፊት የማያስመልሱ፤ አንገት የማያስቀልሱ» ብዙ የቃል ኪዳን ባለቤቶችን ከፊትህ ካላደረክ ገነትን በኢየሱስ ይቅር ባይነት ላይ ብቻ ታምነህ እንዲህ በቀላሉ አታገኝም! የሚሉ መምህራንና ካህናት አሉ። «ስድስቱን ቃላተ ወንጌልንና ዐሠርቱ ቃላተ ኦሪትን» ለመፈጸም ከመፈለግ ይልቅ «ተአምሯን ለመስማት ተሽቀዳደሙ» የሚለውን ማደንዘዣ ዘወትር የሚያነበንቡ ልበ እውራን ካህናት አሉ። «ኢየሱስ ጌታ ነው»  (1ኛ ቆሮ 12፤3) ብሎ መጥራት ይህ የመናፍቅ አባባል ነው የሚሉና ይህንንም በመፍራት በአፋቸው የማስገቡ ካህናት አሉ።
ካህናተ ቤተ መቅደስ፤ ዓይነ ብርሃኑ የተመለሰለትን ሰው ከሰደቡ በኋላ «አንተ የእርሱ ደቀ መዝሙር ነህ» ብለው ለእነሱ ጸያፍ የመሰላቸው፤ ነገር ግን የኢየሱስ ደቀ መዝሙር መሆን ከመቻል የተሻለ እድል እንደሌለ ስለማያውቁ ራሳቸውን የኢየሱስ ደቀ መዝሙር ከመሆን አግልለው «እኛ የሙሴ ደቀ መዛሙርት ነን» ማለታቸው ትልቁንና የተሻለው መጣላቸው መሆኑን አላወቁትም። እናውቃለን ይላሉ፤ አያውቁም፤ እናያለን ይላሉ እውራን ናቸው። አብ ስለወልድ ማንነት የገለጠላቸው ግን «ኢየሱስ ጌታ ነው» ሲሉ አያፍሩም። «በሩ እኔ ነኝ» ስላለ ዕለት ዕለት ያንን በር ብቻ ያንኳኳሉ። «አንኳኩ ይከፈትላችኋል» ያለው ቃል ስለማይታበል ተስፋቸው እሱ ነው።  የሌሎችን በር በመደብደብ፤ እባካችሁ ሂዱና ያንን «በሩ እኔ ነኝ» ያለውን ጌታ አስከፍቱልን ብለው በማስቸገር ባልተነገረ ድካም ውስጥ ራሳቸውን ሲያሽከረክሩ አይገኙም። እሱን በቀጥታ ለለመኑት አምላካችን የማያሳፍር በቃሉ የታመነ ተለማኝ ነውና።
«እኔም እላችኋለሁ። ለምኑ፥ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ይከፈትላችሁማል»   ሉቃ 11፤9
የሚገርመውና የሚደንቀው ነገር ካህናተ ሌዋውያኑ «ይህ ሰው ኃጢአተኛ መሆኑን እናውቃለን» ሲሉ ቆይተው የደቀ መዝሙርነት ጉዳይ ሲነሳ የተናገሩትን ቃል ሸምጥጠው በመካድ «ይህ ሰው ከወዴት እንደሆነ አናውቅም» ሲሉ መገኘታቸው ነው። «እግዚአብሔር ሙሴን እንደ ተናገረው እኛ እናውቃለን፥ ይህ ሰው ግን ከወዴት እንደ ሆነ አናውቅም አሉት» ዮሐ 9፤29  ከወዴት እንደሆነ ካላወቁት ከምን ተነስተው ነው « ይህ ሰው ኃጢአተኛ እንደሆነ እናውቃለን» ብለው ለመናገር ድፍረት ያገኙት?  ለዚህ ሁሉ ያላዋቂ ሳሚ ዓይነት ምላሻቸው ዋናው ምክንያት ካህናቱ ራሳቸውን የሚስሉት ከሌላው የተሻለ እውቀትና ማንም ያልደረሰበት ትምህርት እንዳላቸው ስለሚያስቡ ብቻ ነው። እውነትና ከአብ ዘንድ ስለወልድ ያለው መገለጥ ከሌላ ከማንም ዘንድ ሊኖር ይችላል ብለው በፍጹም አያስቡም። ቢኖር እንኳን ከእነሱ የተለየውን ሁሉ እንደኑፋቄና ክህደት ይቆጥሩታል።
በዘመናችን የወልድን መሲህነት፤ ብቸና አዳኝነትና ከምድር እስከሰማይ የተዘረጋውን ሕያው መሰላል በማንሳት ሌሎችን በምትክነት አበጅተው፤ ለምትክነቱም የሚጠቅም መከላከያ ምሽግ ቆፍረው የሚሟገቱ ካህናትና አዘጭዛጭ ማኅበራት አሉ።  «እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ አለው» ዮሐ 1፤52  የሚለውንና ከባለቤቱ ከራሱ የሰማነው ቃል አይበቃንም፤ የግብጻዊው መነኩሴ የህርያቆስም ይጨመርልን፤ አብሮም ይዳበል በማለት «አንቲ ውእቱ ሰዋስዊሁ ለያዕቆብ» መላእክት የሚወጡባትና የሚወርዱባት መሰላል አንቺ ነሽ (ቅዳሴ ማርያም) የሚሉ ካህናትና አዘጭዛጮች አሉ። ይህንን የቃል ልዩነት ለማስማማት ሲሉ አንዴ እናውቃለን፤ አንዴ ደግሞ አናውቅም የሚሉ ልበ እውራን አሉ። ራሳቸውን ከክርስቶስ ደቀ መዝሙርነት ሰልፍ አውጥተው እኔ የተክልዬ ልጅ፤ የሳማ ሰንበት፤ የዜና ማርቆስ፤ የአርሴማ፤ የሙሴ…………..የሚሉ አሉ። የአጵሎስና የኬፋ ዓይነት መሆኑ ነው።
«ጻፎችና ፈሪሳውያን በሙሴ ወንበር ተቀምጠዋል። ስለዚህ ያዘዙአችሁን ሁሉ አድርጉ ጠብቁትም፥ ነገር ግን እየተናገሩ አያደርጉትምና እንደ ሥራቸው አታድርጉ። ከባድና አስቸጋሪ ሸክም ተብትበው በሰው ትከሻ ይጭናሉ፥ እነርሱ ግን በጣታቸው ስንኳ ሊነኩት አይወዱም። ለሰውም እንዲታዩ ሥራቸውን ሁሉ ያደርጋሉ፤ ስለዚህ አሽንክታባቸውን ያሰፋሉ ዘርፉንም ያስረዝማሉ፥ በምሳም የከበሬታ ስፍራ፥ በምኵራብም የከበሬታ ወንበር፥በገበያም ሰላምታና። መምህር ሆይ መምህር ሆይ ተብለው እንዲጠሩ ይወዳሉ» ማቴ 23፤2-7 ዛሬም በተግባር አለ። ካህናቱ ያውቃሉ ግን እውነትን አያውቁም!!

Monday, July 1, 2013

በጎልጉል ድረ ገጽ በቀረበው ''አንተ ማነህ?'' ጽሁፍ ላይ አቶ የኑስ (ዮናስ - በመጽሐፍ ቅዱስ) ላቀረቡት የግል ወቀሳ ጽሑፈ የተሰጠ ምላሽ


አቶ የኑስ (ዮናስ) የተባሉት - በመጽሐፍ ቅዱስ) ላቀረቡት የግል ወቀሳ፤
አቶ ዮናስ !!!
አሁንም

ስላም ይብዛልዎት እያልኩ ነገርን ነገር ያነሰዋልና ባላሰብኩት ነገር ላይ በሰነዘሩብኝ የሃሰት ክስ ላይ ተመስርቼ አንዳንድ የጋራ ጥያቂዎችን እንዳቀርብ ይፍቅዱልኝ???
1) የሙስሊሙ ጥያቄ በአገሪቱ ውስጥ በሙሉ መልካም አስተዳደር እንዲመጣ ነው ወይስ በእኛ ላይ ብቻ በደል ስለደረሰብን ትግላችን ለሙስሊሙ መብት ብቻ የሚል ነው?
2) በየቦታውና በየጊዜው በሚደረገው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ዘዎትር የሚሰማው መፈክር 'መሪዎቻችን ይፈቱ' እንጂ በታሰሩ ጋዜጠኞች፤ ፖለቲከኞች፤የመብት ተከራካሪዎችና በአጠቃላይ ፍትህ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ስትሉ ሰምቼ አላውቅምና ይህ ከምን የመጣ ነው?
3) ያስታውሱ እንደሆነ ''ሰማያዊ ፓርቲ'' ባዘጋጀው ሰልፍ ላይ አዘጋጆች ከተከሰሱበት ምክናያት አንዱ በሰልፉ ላይ አንዳንድ ሙስሊም ወገኖች ባቀረቡት ጠበብ ያለ ግለኛ መፈክር ምክንያት ነበር ታዲያ በቅንነት ለአንድ አገርና ሕዝብ በተሰለፈ ሁሉን አቀፍ ሰልፈኛ መካከል እንዲህ ዓይነቱ ሥራና ዝንባሌ የት የሚያደርሰን ይመስልዎታል?
4) ጥያቄዎቼ የሁላችንንም የወደፊት የጋራ ጉዳይ የሆነውንና አገርን ለመልካም አስተዳደር ለማብቃት ከሚደረገው አጠቃላይ እንቅስቃሴ አንጻር ሊኖረው የሚገባውን ፋይዳ ከወዲሁ ቆም ብለን ለማሰብ እንድንችል በማሰብ የተሰነዘሩ መሆናቸውን ከወዲሁ አስበው በቅንነት እንዲመልሱልኝ በኢትዮጵያዊ ጨዋነት በትህትና እየጠየኩ ባለፈው እንደነካኩት እንደ ሃይማኖት ልዩነትና ክርክር አድርገው የሚቆጥሩት ከሆነ ግን ለፍላጎትዎ ማርኪያ የሚሆንዎን ጥሩና መሰረት ያለው ክርክር ወይም በመረጃ የተደገፈ ማስረጃ በክርስትናና በእስልምና መካከል አገሪቱ ባፈራቻቸው ምሑራን በአማርኛ በስፋት የሚቀርበውን ''Аnswering Islam ''  ድህረ ገጽ ቢከታተሉ ለችግርዎ የተሻለ መልስና ግንዛቤ ሊያገኙ ይችላሉና ትኩረትዎን ወደ እዚህ ድህረ ገጽ ቢያደርጉ ይሻልዎታል ማለት እወዳለሁ። ለአገራችን ጠቅላላ ችግር ብዙ የሚሠራ ሥራ ስላለ እኔን ለጊዜው ቢተውኝ??? አሁንም ጨዋ ሙስሊም ወገኖቼን እወዳለሁ። ክፋትን ተላብሰው ባልሆነ ነገር በመካፋፈል ለትውልድ መርዝ የሚረጩትንና እየረጩ ካሉ የእኛው ጉዶች ጋር ግን ምንጊዜም ስምምነት እንደሌለኝ ላሳውቅዎት እወዳለሁ። ደግሞም አንዳንዶች በመድረክ ላይ እየወጡ ''አላህ ወ-አክብር'' እንደሚሉት ዓይነት ማስመሰል ጨርሶ አላውቅበትምና በዚህ አይገምቱኝ። ደግሞም የእኔን እምነት መከተል አለባችሁ በማለት ከፍቅር ሌላ ሰይፍ አላነሳም። ሰይፍ የሚያነሱ በሰይፍ ስለሚጠፉ!!!

አሁንም ለጋራ የአገራችን ችግር
በጋራ አብረን በቅንነት እንሰለፍ!!!

ምድራዊ አገራችንን ኢትዮጵያን እግዚአብሔር ያስባት!!!

አሁንም አክባሪዎ

በይስሃቅ በኩል የአብርሃም ዘር

ተናገር ነኝ