Friday, July 12, 2013

በቅድስት ሥላሴ ኮሌጅ ያለው ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል!

ቀደም ሲል ስንል እንደቆየነው ሁሉ አሁንም ደግመን እንለዋለን። የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ አስተዳደራዊና አካዳሚያዊ ችግሮች ይህንን ያህል እንኪያ ሰላንትያ ውስጥ የሚያስገባ አልነበረም። ቤተክርስቲያኒቱ ባላት አቅም፤ የሰጠችውን መክፈልተ ሲሳይ ለተማሪዎቹ በተገቢው መንገድ ማድረስ ለመቻል ባለሙያና ትጉህ አስተዳደር ለማስቀመጥ መሞከር ቀዳሚው ነጥብ ሲሆን፤ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ እንደመሆኑ መጠን ቀሚስ ለባሽ ሳይሆን ራሱን ለውጦ ሌላውን መለወጥ የሚችል የተማረ ኃይል ለማፍራት ደረጃውን የጠበቀ የምሁራን ስታፍ በመመደብ የነገይቱን ቤተ ክርስቲያን ይረከቡ ዘንድ ማስቻል ሁለት የተሰናሰሉ አስፈላጊ ኩነቶች ሆነው ሳሉ የአስተዳደርና ብቃትና አርቆ የማሰብ ርእይ በዞረበት ያልዞረው ቤተ ክህነት ጉዳዩን አጡዞ መውጫ ወደሌለው አዘቅት ውስጥ ኮሌጁን እየወረወረው ይገኛል።
መነሻ ምክንያቶቹም ሁለት ናቸው።
1/ የአባ ጢሞቴዎስ ደካማ አስተዳደርን ለማስወገድና ከእርሳቸው ጋር የተማማሉ መሰሪ የኮሌጁ ሹማምንት የሚፈትሉት ውል የለሽ የነገር ልቃቂት ጋር የፓትርያርክ ማትያስ « ከእርስዎ ጋር ሞቴን ያድርገው » ቃል ኪዳን ላይበጠስ መተሳሰሩ ቀዳሚው ነው።
2/ ከነዚሁ ወሳኝ ከሆኑና ነገር ግን ጉዳዩን እንደናዳ ድንጋይ እያንከባለሉ ተማሪዎቹ ላይ የሚመርጉት ትላልቅ ኃይሎች እንዳሉ ሆነው በተገኘው አጋጣሚና ክፍተት ተጠቅሞ ከኮሌጁ ድኩምና መዝባሪ አስተዳደሮች ጋር በፕሮቴስታንታዊ ተሓድሶ ዜማ እየታገዘ የሚጠላቸውን ሰዎች በመጥረግ ራሱ ባዘጋጃቸው ተላላኪዎች በመተካት የኮሌጁን የመተንፈሻ ሳንባ ለመቆጣጠር የሚፈልገው ያ መሰሪ ማኅበር ባሰማራቸው ጉዳዩ ፈጻሚዎቹ በኩል ከወዲህ ጠርዝ ከተማሪዎቹ ችግር ጋር እንደአዞ እያነባ ከጀርባ ሲጮህ መገኘቱ ነው።
ከእነዚህ ሁለት ስውርና ግልጽ ኃይሎች ማለትም አንዱ የተማሪዎቹን ጩኸት እየጮኸ ከጀርባ ሆኖ ግፋ በለው ቢልም  ሌላኛውን ኃይል የተማሪዎቹን ጩኸት ላለመስማት ምክንያቶችን እየደረደረ እነሆ ወራቶችን አስቆጥሯል። ከዚህ ቀደም እንዳልነው አዲሱ ፓትርያርክም የመጣ ደብዳቤ ከመፈረም ውጪ እርባና የሌለው ሥራ ሳይሰሩ፤ ይባስ ብለው በሰላም ሀገር ኮሌጁ ይዘጋ ወደሚል ምክንያት የለሽ ውሳኔ ደርሰዋል። በጣም አሳዛኝ ነገር ነው።
ማኅበረ ቅዱሳን በአባ ጢሞቴዎስ እጅ እንዳልበላና እንዳልጠጣ ( ስንት ደብዳቤ እንዳላስፈረማቸው) ዛሬ በማኅበሩ የተሐድሶ ጥቁር ፋይል ላይ የተመዘገቡና አልታዘዝ ያሉትን ሰዎች አባ ጢሞቴዎስ ከጎናቸው ስላቆሙና አባረው ወደማኅበሩ ጊሎቲናዊ ጥርስ ውስጥ ስላላስገቡ ብቻ «ሐራ ተዋሕዶ» በተባለ የመጮኺያ ማሽን በኩል በአባ ጢሞቴዎስ ላይ አንዲት ቅጠል የማይበጥስ እርግማኑን ይወረውራል።
እውነት የአባ ጢሞቴዎስ አስተዳደራዊ ድኩምነትና ግትርነት ለማኅበሩ የታየው ዛሬ ነው? ነፍሳቸውን ይማርና ከአቡነ ጳውሎስ ጋር አባ ጢሞቴዎስ በነገር ሲፋጠጡ፤ ማኅበሩ ለአባ ጢሞቴዎስ እሳቱ፤ ቅባቱ፤ መርዙ፤ ብረቱ እያለ ሲያሞካሽ አልነበረምን? ያንን ሁሉ ዛሬ ምን ውሃ በላው? ነገሩ ወዲህ ነው። ፈረንጆቹ /Use and throw/ ይሉታል። አንዴ ተጠቅመህ ሲያበቃ ወርውረህ መጣል ማለት ነው። አባ ጢሞቴዎስ እኔ ያልኩት እንደሚሉ፤ ግትርነት እንደሚያጠቃቸው፤ ተላላና ተደላይ መሆናቸው የዋለ ያደረ ባህርያቸው ነው። ይሁን እንጂ ማኅበሩ ያስፈልጉት በነበረበት ወቅት አገልግለውታል። ዛሬ ደግሞ አስፈላጊው አይደሉምና ከግዙፉ የተማሪዎቹ ችግር ጀርባ የቀድሞውኑ የምናውቃቸውን አባ ጢሞቴዎስን ይራገማል።
በሌላ መልኩ አዲሱ ፓትርያርክ የቀድሞውን ፓትርያርክ በየሚዲያው ሲያብጠለጥሉ እንዳልነበር ያቺ ታስነቅፍ የነበረችው ሥልጣን ተሽከርክራ እጃቸው ላይ ስትወድቅ ታሪክ ራሱን ይደግማል እንዲሉ ትንሹን የተማሪዎች ችግር መፍታት አቅቷቸው ታንክ የታጠቁ ያህል ቆጥረው ግቢያችን የሆነው ባድመን ልቀቁ የሚል አዋጅ ለማስነገር ሲበቁ ስናይ «ከበሮ በሰው እጅ ሲያዩት ያምር፤ ሲይዙት ይደናገር» የሚለውን ብሂለ አበው አስታወሰን። ለአባ ጢሞቴዎስ የሚከፈል ትንሹ ዋጋ መሆኑ ነው።
ተማሪዎቹም ራሳቸውን ማጥራት የሚገባቸው ማንም አፍና ምላስ ሆኖ የሚጮህላቸው ማኅበርና የማኅበሩ አቀንቃኝ ቀሚስ ለባሽ በመሃከል ተሰግስጎ መኖር እንደሌለበት ነው። ጥያቄያቸው አጭርና ግልጽ ነው። «አስተዳደራዊና የተማሪ ዕለታዊ ኑሮ ይስተካከል» የሚል ብቻ መሆኑን አበክሮ ማስረገጥ ይገባል። ከዚህ ውጪ ቤተ ክርስቲያኒቱ ራሷ መተኪያ የሌላትና ሁሉን የሰበሰበች ማኅበር ሆና ሳለ ሌላ የቀኝ ክንፍ ማኅበር አባል በመሆን ችግሩን የታከከና ለራስ መደላድል ሁኔታዎችን ማጽዳት የሚሉትን አንጥሮ አለመግፋት በራሱ ወንጀልም ኃጢአትም ነው።
ከዚህ የተነሳ ማለት የሚቻለው ነገር ቤተ ክህነቱም ራሱ ገርፎ ራሱ እየጮኸ ነው። ግቢውን ለቃችሁ ውጡልኝ ማለት ምን ማለት ነው? በሌላቸው ውክልናና እውቀት በአንድ በኩል የተሐድሶ አቀንቃኞች በኮሌጁ ተሰግስገዋል እያሉ፤ በሌላ መልኩ ደግሞ የአስተዳደር በደል ተፈጽሟል በሚል ዲስኩር ከተማሪዎች ጋር የሚጮሁ የሰው አራዊቶች ድምጻቸውን ያቁሙ። እነዚህኞቹም ራሳቸው ገርፈው ራሳቸው የሚጮሁ ቀላማጆች ናቸው።
እኛ የምንለው ተማሪዎቹም መባረር የለባቸውም፤ ማኅበር የሚባል የወፍ ጉንፋን በሽታ ከግቢው ይውጣ! አባ ጢሞቴዎስም ሌላው ቢቀር ዓይናቸው ደክሟልና ከሥራው አሳርፏቸው። በሽታው እንዳይዛመት የማኅበሩ የወፍ ጉንፋን ቫይረስ ያልለከፈው አባት ይሾም። ለዚያውም ካለ!!!  ጅራፎች ሆይ፤ በመከራ በገረፋችሁት ተማሪ ላይ ራሳችሁ ገርፋችሁ፤ራሳችሁ እንደተበደለ ሰው አትጩሁ!!!!!!!!!!