Friday, July 19, 2013

«መጽሐፈ አበው» ስለመነኮሳት ምን አለ?

ምንኩስና ምንድነው? ለመጽደቅስ ጠቃሚ ነው?  የመንግሥተ ሰማያት መውረሻ ስልት ነው? የክብር ወይስ የመከራ፤ የተጋድሎ ወይስ የፍልሰት ጎዳና ነው? ብዙ ሊባልለት የሚችልና ሊባልበት የሚገባ ይህ ሰዋዊ ሥርዓት ቆሜለታለሁ ከሚለው ዓላማ ጋር እየተጣረሰ ዘልቆ በዚህ ዘመን ያለበትን ደረጃ እንድንመለከት «መጽሐፈ አበው» የተባለው ትልቁ መጽሐፍ  በምንኩስና ላይ ካሰፈራቸው ሕግጋት ውስጥ በጥቂቱ ለማቅረብ ወደድን። የግእዙን ትርጉም አንብበው ይህ ሰዋዊ ሥርዓት ዛሬ በሕይወት አለ ወይ? ብለው ራስዎ ይጠይቃሉ።  የሕይወት መንገድ የመሆን፤ አለመሆኑ ጉዳይ ተከድኖ ይቆየንና ምንኩስና ራሱ ተነስቼበታለሁ ከሚለው አቋሙ ጋር ዛሬ ላይ የለም። መነኩሴስ ማነው? «መጽሐፈ አበው» እንዲህ ይናገራል።
መነኮስ ከሀገሩ ወደሌላ ሀገር ይሂድ። በዚያም በዋሻ፤ በኮረብታው፤ በተራራው ይንቀሳቀስ። በረሃብ፤ በብርድ፤ በጥም፤ በመራቆት፤ በድካም፤ በትጋት ይኑር። ልብሱ የከብት ቁርበት፤ የፍየል ቆዳና ለምድ ይሁን። ሥጋ በሕይወት ዘመኑ አይብላ። የዘወትር ምግቡ የበረሃ ጎመን፤ ቅጠልና የዛፎች ፍሬ ብቻ ይሁን። ካገር አገር አይዙር። ወደሠርግ፤ ወደ ድግስ አይግባ። በሕዝብ መካከል የሚኖር መነኮስ ቢኖር እርሱ ውሸታም ነው። የአጋንንት ረድእ፤ አገልጋይ ነው። ወንድ መነኩሴና ሴት መነኩሲት በአንድ ላይ አይኑር፤ ይራቁ። በአንድ ላይ እየኖሩ፤ በአንድ አጸድ እያደሩ ንጽህ እንጠብቃለን ቢሉ ውሸት ነው። ነብርና ፍየል አንድነት ይኖሩ ዘንድ እንዴት ይቻላል? መነኩሴ ማንንም አይማ። ሃሜተኛ ጸሎተኛ አይደለም። አብዝቶ የሚበላ መነኩሴ የትም እንደሚፈነጭ ፈረስ ነው። መነኩሴ በፀሀይ ግባት አንድ ጊዜ ብቻ ይብላ። ወፎች መብል አይተው በወጥመድ ይያዛሉ። ትልቁ አንበሳ በመብል ምክንያት ወጥመድ ውስጥ ይወድቃል። አዳም በመብል ወደቀ። ይሁዳ ከወጡ አጥልቆ በበላ ጊዜ ሰይጣን ገባበት። ሠይጣን መነኮሳትን በመብል ፤በመጠጥ፤ በሃሜት፤ በሳቅና በስካር ያድናቸዋል። ልቅ፤ ልቅ እየጎረሱ፤ የላመ የጣመ እያግበሰበሱ መነኮስ መባል አይገባቸውም። በእንቅልፍ ተውጠው፤ ከጸሎት ተለይተው እንደአዞ ተገልብጠው እንዲተኙ ያደርጋቸዋል። ዘማውያንም ይሆናሉ። ያኔም አጋንንቱ በመነኮሳቱ ላይ ይዘፍናሉ። በእጃቸውም ይጨበጭባሉ። እንደፈረሶች ሰኮና ሆነው ይረግጡአቸዋል። የዓለምን ጣዕም የቀመሱ፤ የወደዱ መነኮሳት የነፍሳቸውን ደዌ ያያሉ። የነፍሳቸውንም መድኃኒት ይተዋሉ። በሕዝባውያን መካከል የሚመላስ መነኮስ  ከቅዱሳን ክብር መድረሻ የለውም። መነኮስ ወደዓለማዊ ችሎት፤ ሸንጎና ፍር አይሂድ።  ምሥክር አይሁን። መነኩሴ ማለት ምዉት ማለት ነውና አይቻለሁ፤ ሰምቻለሁ፤ ዳኝነት አውጡልኝ አይበል። ለሕዝባውያን አበ ነፍስ አይሁን። መነኮስ የሞተ ነውና የሚሰማ ጆሮ፤ የሚናገር አፍ የለውም። ዓለም ውስጥ እየኖረ ዓለምን አሸንፋለሁ ቢል ውሸታም ነው። አትመነው። አፉን፤ ጆሮውንና ዓይኑን የማይጠብቅ መነኩሴ ነፍሱን አያድናትም። መነኮስ እነዚህን ሦስት ሰይፎች ካልታጠቀ መነኮስ አይባልም። የዋህነት፤ ትህትናና ድህነት ናቸው። የዋህነት ከቂም፤ ከበቀል ከጥላቻና ከስጋዊ ነገር ሁሉ መራቅ ነው። ትህትና ራስን ዝቅ ማድረግ ሲሆን ድህነት የኔ የሚለው ሀብትና ገንዘብን ሁሉ መናቅ ናቸው። መነኮስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል። በሕይወት ዘመኑ በእንደዚህ ያልተጠበቀ መነኮስ፤ መነኮስ አይደለም።