Sunday, August 22, 2021

በድንግል ማርያም የትንሣኤና የእርገት ታሪክ ላይ ችግር አለ!

ቅዱሳንን ስለማክበር ምንም ጥያቄ የለንም። ለቅዱሳንም መታሰቢያ ማድረግ የነገሮች ሁሉ ባለቤት የሆነው ኢየሱስን እስካልተካ ድረስ ችግር የለውም። ለክርስትና አስተምህሮና ለተጋድሎ ጽናት አርአያ ይሆኑናልና ታሪካቸውን እንናገራለን። ነገር ግን በሃይማኖታዊ አስተምህሮ ወቅት በወንጌል ላይ ብዙ ጥያቄዎችን የሚያስነሱትና የስህተት ችካሎች አልነቀል ያሉት በመታሰቢያና በአክብሮት ምክንያት ስር ተወሽቀው ኢየሱስን እየጋረዱ ስላስቸገሩ ነው። ከነዚህ የስህተት አስተምህሮዎች መካከል አንዱ የሆነው በማርያም እረፍት፤ ቀብር፤ ትንሣኤና እርገት ላይ ያሉ አስተምህሮዎች ሰዎች ዓይናቸውን ከኢየሱስ ላይ አንስተው ወደሌላ የመዳን መንገድ እንዲመለከቱ ያደረገው ተጠቃሽ ነው።

ስለማርያም እረፍት፤ትንሣዔና እርገት አብያተ ክርስቲያናት አንድ ዓይነት የእምነት አቋም የላቸውም። እንዲያውም ስለማርያም ሞትና የእርገት ዕለት በግልጽ የሚታወቅ ማስረጃ እንደሌለ በ5ኛው ክ/ዘመን የኖረው የሳላሚሱ ኤጴፋንዮስ ተናግሯል። ዕረፍቷና እርገቷ በኢየሩሳሌም እንደሆነ  የሚናገሩ ቢኖሩም  ይህንን አባባል የማይቀበሉ አብያተ ክርስቲያናትና የቴኦሎጂ ምሁራን ሞልተዋል። በኢየሩሳሌም አርፋለች የሚለውን አባባል የማይቀበሉበትን ማስረጃ ሲያቀርቡም ዮሐንስ በወንጌሉ ላይ እንደተናገረው «እናትህ እነኋት አለው። ከዚህም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ወደ ቤቱ ወሰዳት» ዮሐ19፤27 ባለው መሠረት ማርያም እስከ ሕይወቷ ፍጻሜ ድረስ ከዮሐንስ ጋር ስለኖረችና ወንጌላዊው ዮሐንስም ከጌታ ሞት በኋላ በኢየሩሳሌም  ጥቂት ዓመታትን ከቆየ በኋላ በ37 ዓ/ም ገደማ ወደ ቤዛንታይን ከተማ ኤፌሶን ሄዶ ወገኖቹን ወንጌል እያስተማረ መቆየቱንና  ማርያም በሞት እስከተለየችው ድረስ  ከ48-52 ዓ/ም እዚያው እንደነበር ብዙ ተጽፏል።
በኋላም በቅርብ ርቀት ባለችው ደሴተ ፍጥሞም  በግዞት መኖሩንና በመጽሐፍ ቅዱሳችን የተጻፈውን ራእይ የተመለከተውም እዚያ እንደሆነ ይታወቃል ። አንዳንዶች ከዶሚኒሽን አገዛዝ ቀደም ብሎ የራእይ መጽሐፉን  ከ55-65 ዓም ገደማ እንደጻፈም በታሪክ አስቀምጠዋል።

ዋናው ነገር  ማርያም በኤፌሶን ከዮሐንስ ጋር ኖራለች ወይስ አልኖረችም? ነው ጥያቄው። በኢየሩሳሌም አርፋለች የሚሉ ሰዎች አንድም ጊዜ ከዮሐንስ ጋር በኤፌሶን ኖራለች ሲሉ አይደመጥም። ለምን?  ዮሐንስ ማርያምን እንደእናት ሊይዛት አደራ ተሰጥቶታል የሚባል ከሆነ ከዮሐንስ ጋር ኤፌሶን ስለመቀመጧ የማይነገረው ለምንድነው?  ዮሐንስ እስከ 96 ዓመቱ ድረስ ከኤፌሶንና ከደሴተ ፍጥሞ ውጪ ስለመኖሩ የተነገረ ታሪክ የለም። ማርያም ከዮሐንስ ጋር በኤፌሶን አልኖረችም ብሎ በመከራከርና በኢየሩሳሌም ኖራ፤ እዚያው ማረፏን በግልጽ በመናገር መካከል ትልቅ ልዩነት አለ። «እነኋት እናትህ» ባለው መሰረት አብረው ኤፌሶን ኖረው እዚያው ማረፏን በሚያምኑና ኢየሩሳሌም ኖራ እዚያው አርፋለች በሚሉት ሰዎች መካከል ያለው ልዩነት የማይታረቅ ነው።
ሮበርት ክሬው የተባለ የነገረ መለኮትና የታሪክ ጸሐፊ ዮሐንስ ወንጌላዊ ዘመኑን ሁሉ በኖረበት ከኤፌሶን ከተማ 8 ኪሎ ሜትር ወጣ ብላ ባለች ኰረብታ ላይ በተሰራ ቤት ውስጥ እንደኖረና ማርያምም እዚያ ማረፏን ጽፏል።  ይህንን በኤፌሶን ያለውን የማርያምን መቃብር የዓለም ክርስቲያኖች እንዲሆም ሙስሊሞች ሳይቀሩ ይጎበኙታል፤ ይሳለሙታል።  በቱርክ ግዛት ያለው ይህ ስፍራ በቱርካውያን ሙስሊሞች ዘንድ «ሜሪዬማና» ተብሎ ይጠራል።
ቅድስት ማርያም ከዚህ ዓለም የተለየችው መቼ ነው? ለሚለው ጥያቄ ጥንታዊያን አብያተ ክርስቲያናት የሚባሉት የምሥራቁና የምዕራቡ ጎራዎች የተለያየ አመለካከት አላቸው።
በተወለደች በ58 ዓመቷ ዐርፋለች የሚሉ አሉ። በ72 እና 63 እድሜዋም አርፋለች የሚሉ መረጃዎች አሉ። እንደ ግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አስተምህሮ ግን የሚታመነው በ64 ዓመት እድሜዋ ማረፏ ነው።  ኖረችበት ተብሎ ከሚገመተውና አርፋለች ከሚባለው ቦታ ያለው ልዩነት እንዳለሆኖ በጥር ወር ከዚህ ዓለም ተለይታ በ40ኛው ቀን ማረጓን የሚናገሩ አሉ። ይህም ሞትና ትንሣኤዋን ከልጇ ጋር ለማመሳሰል የተደረገ ጥረት ነው። በነሐሴ ወር አርፋ ከተቀበረች በኋላ ትንሣዔዋን ሳያዩ መቃብሯ ባዶ ሆኖ ስላገኙት ሐዋርያት ሱባዔ ይዘው በሦስተኛው ቀን ተገለጸችላቸው የሚሉም አሉ። እንደኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አስተምህሮ ደግሞ በጥር ሞታ፤ በነሐሴ ተቀበረች የሚል ትምህርት አለ። በጥር ወር አርፋ፤ በነሐሴ ተቀብራለች የሚሉ ሰዎች ሥጋዋ በገነት ዛፍ ስር ለስምንት ወራት መቀመጡንና በሱባዔ ጸሎት በተደረገው ልመና የተነሳ ሥጋዋ ከሰማይ ወርዶ ለመቀበር መቻሏን አስፋፍተው ጽፈዋል።
በጥር ወር እንዳረፈች ያኔውኑ ለምን አልተቀበረችም?፤ ተብለው ሲጠየቁ ወደ ቀብር ሥጋዋን ተሸክመው ይሄዱ የነበሩት ሐዋርያት ላይ ታውፋንያ የሚባል ወንበዴ ጎራዴ ሲመዝባቸው ዮሐንስ ብቻ ሲቀር ሐዋርያቱ ጥለዋት በመሸሻቸውና ዮሐንስ ብቻውን ቀርቶ ወደ  መቃብር ሳትገባ ወደ ገነት ዛፍ ስር በመወሰዷ እንደሆነ ይነገራል።  ዮሐንስም ወደቤት በተመለሰ ጊዜ ሸሽተው የነበሩት ሐዋርያት ሥጋዋስ የታለ? ብለው ቢጠይቁት በገነት ዛፍ ስር መቀመጧን ስለነገራቸው ዮሐንስን ገነት ዛፍ ስር ሬሳዋ መቀመጡን አይቶ ለምን እኛስ ይቀርብናል በማለት ነሐሴ 1/ ቀን የጾም የጸሎት ሱባዔ ጀምረው በ15ኛው ቀን ትኩስ ሬሳ ከገነት ዛፍ ስር እንደመጣላቸውና እንደቀበሯት ይናገራሉ።
እዚህ ላይ ይሄንን ታሪክ የሚያፈርሰውና ተረት እንደሆነ የሚያሳየንን ነገር እናንሳ!
ገነት ውስጥ የሰው ሬሳ የሚቀመጥበት ዛፍ ስለመኖሩ ማስረጃችን ምንድነው? ሬሳውን ተሸክመው ገነት የገቡት ኃይሎች ታውፋንያ የተባለውን ሽፍታ ማስወገድ ለምን አልቻሉም? እጁን ቆረጡት የተባለው ተረት ለምን አንገቱን አልሆነም? ከሐዋርያቱ ተለይቶ ብቻውን የቀረው ዮሐንስ ከሽፍታው ሰይፍ እንዴት ተረፈ?  ይሄ ሁሉ ውጣ ውረድ ሲከናወን ሐዋርያቱ: መላእክቱ: ኢየሱስም አብረዋት ከነበሩ ከማርያም ሥጋ መንከራተት ጋር ምን ትርፍ አላቸው? 
ታሪኩን በሚያማልልና ልብን በሚቦረቡር ተረት መቀባባት ያስፈለገው ሰዎች ከወንጌል እውነት እንዲወጡና ልብን በተረታ ተረት በመሙላት በከንቱ ሃሳብ ውስጥ አስጥሞ ለማስቀረት ነው።
ሌላው ጥያቄ የሚያስነሳው ነገር  በጥር ወር አርፋ  ከቀብር በፊት ወደገነት ዛፍ ስር ስለመወሰዷና  ዮሐንስ ወደ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ከነገራቸው በኋላ እሱ ያየውን እኛም ማየት አለብን ያሉትና የጾም: የጸሎት ሱባኤ የገቡት ነሐሴ 1 ቀን ነው ይባላል። በጥር ወር  ገነት ገባ ለተባለ ሬሳ ምላሽ ለማግኘት ሐዋርያቱ ለምን እስከነሐሴ መቆየት አስፈለጋቸው? ሥጋዋስ 8 ወር ሙሉ ለምን ሳይቀበር ቆየ?  ሐዋርያቱ ሱባዔ ባያደርጉና እንዲቀብሯት ሬሳዋ ባይሰጣቸው ኖሮ የማርያም ሥጋ ከገነት ዛፍ ስር አይንቀሳቀስም ነበር ማለት ነው?
ለማርያም ሥጋ መቀበር ምክንያት የሆነው የሐዋርያቱ ሱባኤ መያዝ እንጂ ከቀብር ተለያይቶ የሚቀር ሆኖ ነበር ማለት ነው።
እንደሰዎቹ አባባል በጥር ወር አርፋ ሳይቀበር የቀረውን የማርያምን ሥጋ በስምንተኛው ወር ከገነት ወጥቶ ከተሰጣቸውና ከቀበሯትም በኋላ ቢሆን ወደሰማይ ስታርግ ሐዋርያቱ ለማየት አልቻሉም። የተረቱ ባለቤቶች እርገቷን ያየው ቶማስ ብቻ ነው ካሉን በኋላ ለተረቱ የታሪክ ፍሰት ውበት ሲሰጡት እንዲህ ነበር ይሉናል። ሐዋርያቱ ማርያምን ቀብረዋት ወደቤታቸው ከተመለሱ በኋላ ቶማስ በደመና ተጭኖ ከሀገረ ስብከቱ ከሕንድ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመለስ በሦስተኛው ቀን ወደ ሰማይ ስታርግ የዳመናው ጎዳና ላይ ማርያም ስታርግ አገኛት። ቀድሞ የልጅሽን እርገት ሳላይ ቀረሁ አሁን ደግሞ ያንቺን ሳላይ ልቀር ነው? ብሎ ቢያዝን ትንሣኤዬን ያላንተ ማንም አላየም ካለችው በኋላ የተገነዘችበትን ጨርቅ እና ሰበን ለምልክት ሰጥታው እንዳረገች በሰፊው ይተረታል።
ሰዎቹ ነገሩን ሁሉ ለማጣፈጥ የሚጠቀሙበት ተረት አስገራሚ ነው። የሰው ልጅ ከትንሣኤው በኋላ የዚህን ዓለም ጨርቅና ልብስ እንደተሸከመ ወደ ሰማይ ይገባል የሚል ክርስቲያናዊ አስተምህሮ አለ ወይ?
ወንጌል ከትንሣኤ በኋላ ክርስቶስን እንመስል ዘንድ እንለወጣለን ይላል እንጂ የመቃብሩን ልብስና ሰበን እየተሸከመ ሰው ወደሰማይ ያርጋል የሚል አስተምሮ የለውም።
« 2ኛ ቆሮ 3፤18
እኛም ሁላችን በመጋረጃ በማይከደን ፊት የጌታን ክብር እንደ መስተዋት እያብለጨለጭን መንፈስ ከሚሆን ጌታ እንደሚደረግ ያን መልክ እንመስል ዘንድ ከክብር ወደ ክብር እንለወጣለን»
ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን በመቃብሩ የተገነዘበትን ጨርቅ ትቶ መነሳቱን እንጂ  ያንኑ ለብሶ መነሳቱን አላነበብንም።
ዮሐ20፤6—8 
«ስምዖን ጴጥሮስም ተከትሎት መጣ ወደ መቃብሩም ገባ፤ የተልባ እግሩን ልብስ ተቀምጦ አየ፥ ደግሞም በራሱ የነበረውን ጨርቅ ለብቻው በአንድ ስፍራ ተጠምጥሞ እንደ ነበረ እንጂ ከተልባ እግሩ ልብስ ጋር ተቀምጦ እንዳልነበረ አየ»
የሁላችን አማኞች ትንሣዔ የክርስቶስን ትንሣዔ መምሰል ካለበት በቀብር ወቅት ከዚህ ዓለም ጉድጓድ የገባ ጨርቅ ወደ ሰማይ አብሮን የሚያርግበት ምንም መንገድ የለውም።
ተጠራጣሪ እንደሆነ ሁል ጊዜ የሚነገርበት ቶማስ በማርያም እርገት እሱ ብቻ የተለየ ተጠቃሚ እንደሆነ አድርጎ ለማቅረብ ሲባል የማስረጃ ጋጋታ ሲፈለግ የማርያም የግንዘት ጨርቅ ተገኘና ወደሰማይ ከማረጉ በፊት ቶማስ ተቀበለ የሚል ተረት  አቀረቡልን። ሌላው አስገራሚው ነገር በደመና ተጭኖ የመሄድ ተረት ነው።  በመንፈስ ተነጠቀ የሚል መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነት በደመና ተጫነ ከሚለው ጋር የትርጉም አንድነት የለውም። (የሐዋ 8:39)
ቶማስ በደመና ተጭኖ ሲጓዝ የሚለውን አባባል እንደፊልጶስ መነጠቅ አድርገን ብንቆጥረው እንኳን የቶማስ ሰብአዊ ማንነትና የማርያም ሰማያዊ የእርገት ማንነት የተለያየና ፈጽሞ የማይገናኝን ነገር ነው።  የቶማስን የዳመና ላይ ውይይትን ከረቂቅ  ክርስቶሳዊ አዲስ ፍጥረት ጋር ለማገናኘት መሞከር የጥንቶቹን የሮማውያን የቬነስ ወጎች/fable story/ እንድናስታውስ ያደርገናል።

በሞት: ትንሣዔና በእርገት መካከል እንደዚህ ዓይነት ተረቶችን በሰውኛ ትረካ መጫወት እግዚአብሔር ስለሞትና ትንሣዔ በተናገረው ላይ መቀለድ ነው። ከሁሉ የሚገርመው ደግሞ ማርያምን በጥር ሞታለች ያሉ ሰዎች፤  በመጀመሪያው ሞት ዮሐንስ ብቻ እድለኛ ሆኖ በገነት ዛፍ ስር ለማየት በመቻሉ ይሄንን እድል እነርሱም ለማግኘት ሐዋርያቱ ሱባኤ ነሐሴ 1 ቀን ገቡ ያሉን ሰዎች ማብቂያ በሌለው ተረታቸው እንዲህ በማለት ሆዳችንን በተረት ይነፉናል።  ከቀበሯት በኋላ ቶማስ ብቻ ያየውን እርገቷን እኛም ማየት አለብን ብለው ሐዋርያቱ በድጋሚ በዓመቱ ነሐሴ 1 ቀን ሱባኤ ገቡ ይሉናል። ሐዋርያቱ ነሐሴ ወር ላይ ሙጭጭ ያሉበት የሱባኤ የፍቅር ጊዜ ለምን ይሆን? ደግሞስ እርገቷን ለሁለተኛ ጊዜ ለማረጋገጥ ለምን አንድ አመት መቆየት አስፈለጋቸው? 
ማርያም አንዴ ካረገች በኋላ በሱባኤ የሚደገም ሁለተኛ እርገት አለ ወይ?  እንደዚህ ዓይነት ተደጋጋሚ ሞትና እርገት እንዲደረግላቸው ሐዋርያቱ ይጠይቁ ነበር ብሎ ለመቀበል ይቸግራል። ከጌታ የተማሩት ትምሕርት በእንደዚህ ዓይነት ጥያቄ እንዲዋከቡ የሚያደርግ አልነበረም። ማርያምን በመቅበር: በማንሳትና በማሳረግ ጣጣ ውስጥ ሐዋርያቱ ለምን እንዲህ ተጨነቁ? የተረት አባቶቹ ለዚህ ጥያቄ መልስ ባይኖራቸው ሐዋርያቱ ወንጌልን ለዓለም ያዳርሱ ዘንድ የተሰጣቸውን ሰማያዊ ተልእኮ ትተው ዋሻ ተወሽቀው የሆነ ሥጋ ከሰማይ እስኪወርድላቸው ጊዜያቸው ፈጁ የሚለውን ተረት  ሰይጣን ለሚያዳምጡት ከሚረጨው  በስተቀር የክርስቶ አማኝ የሆነ ሰው እውነት ነው ብሎ በጭራሽ ሊቀበል አይችልም።
የሚያሳዝነው ነገር ሐዋርያቱ ሱባኤ ከገቡ በኋላ የማርያም ሥጋ ከሰማይ እንደገና ወረደ የሚሉን አሳፋሪ ታሪክ ነው። እንዲያውም ኢየሱስ ራሱ ማርያምን ሥጋ መንበር (የቁርባን መቀመጫ) አድርጎ ጴጥሮስን ንፍቅ ቄስ፤ እስጢፋኖስን ገባሬ ዲያቆን ሆነው ቀደሱና ቆረቡ ይሉናል።  የማርያም ሥጋ እንዴት መንበር መሆን ቻለ? ምን የሚባለውን ቅዳሴ ቀደሱ? ኢየሱስ ሰራዔ ካህን ሆኖ ከቀደሰ የማንን ሥጋ ቆረበ? የራሱን?  ለየትኛው ድነት ይሆነው ዘንድ ሊቆርብ ይችላል? 
አልቆረበም የሚባል ከሆነም ሰራዔ ካህናት በዚህ ምድር መቅደስ ውስጥ ከመቀደስ ባሻገር መቁረብ አይጠበቅባቸውም በማለት አብነታዊ የክህነት አስተምህሮን አያይዞ ማቅረብ  የተገባ ይሆናል።
ኢየሱስ የቀደሰው ቅዳሴ ከ14ቱ ቅዳሴያት መካከል የትኛውን ይሆን? ያኔ ቅዳሴያት ተደርሰው ነበር? ወይስ የመጀመሪያው ደራሲ ኢየሱስ ነው?
  እንደተለመደው አባባል ቅዳሴ እግዚእ ነው የተቀደሰው የሚሉ ቢኖሩም ክርስቶስ ራሱን በሁለተኛ መደብ አስቀምጦ « ነአኩተከ አምላክ ቅዱስ፤ ፈጻሜ ነፍስነ፤ ወሀቤ ሕይወትነ ዘኢይማስን»  (ትርጉም) "የማይጠፋ ሕይወት የሰጠኸን: የነፍሳችን ፈጻሚ: ቅዱስ አምላክ እናመሰግንሃለን" ብሎ እንደእሩቅ ብእሲ ( እንደምድራዊ ሰው ሲማፀን አይገኝም። የማይጠፋ ሕይወት ራሱ ሰጪ ሆኖ ሳለ የዘላለም ሕይወት ይሰጠው ዘንድ ኢየሱስ ወደሰማይ አይማፀንም።
“እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው።”ዮሐ 6፥47 ያለን ጌታ ሕይወት ከሱ ቁጥጥር ውጪ ያለ የሚያስመስለው ቅዳሴ እግዚእ የሰዎች ድርሰት እንጂ የኢየሱስ አይደለም።
እንደዚህ ዓይነቱ አደገኛ ክህደት፤ ሰዎች ለማርያም ባላቸው ፍቅር ውስጥ ተደብቆ ለዘመናት ሕይወትን ከመዳን መንገድ ሲያጠፋ ቆይቷል።
ደግሞም በምሴተ ሐሙስ በጉ የመስዋእቱን ሥርዓት ለሕይወታችን ድኅነት ከሰጠ በኋላ ወደምድር መጥቶ ሁለተኛ ማእድ የሚያዘጋጅበት ምንም መጽሐፍ ቅዳሳዊ አስረጂ የለም። እውነታውን ስናነብ እንዲህ የሚል ቃል ተቀምጦልናል።«ሰዓቱም በደረሰ ጊዜ ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ጋር በማዕድ ተቀመጠ። እርሱም፦ ከመከራዬ በፊት ከእናንተ ጋር ይህን ፋሲካ ልበላ እጅግ እመኝ ነበር፤ እላችኋለሁና፥ በእግዚአብሔር መንግሥት እስኪፈጸም ድረስ፥ ወደ ፊት ከዚህ አልበላም አላቸው። ጽዋንም ተቀበለ አመስግኖም። ይህን እንካችሁ በመካከላችሁም ተካፈሉት» ሉቃ 22፤14-17
"የእግዚብሔር መንግስት እስኪፈጸም ድረስ ከዚህ ማእድ ድጋሜ አልበላም" ያለውን ቃል ያጥፍ ዘንድ ኢየሱስን ዋሾ ማድረግ አደገኛ ክህደት ነው።
በጉ መስዋዕቱን ሕይወት ይሆናቸው ዘንድ ለሰዎች ከሰጠ በኋላ፤ በፍርድ ቀን  የደሙን ምልክት ለተቀበሉት ሁሉ ዋጋቸውን ይሰጣቸዋል እንጂ እሱ የመስዋእቱ ተካፋይ ስላልሆነ፤ ክርስቶስ በቀዳሽነት  ቆርቦ፤ ማቁረብ የሚባል ታሪክ ከወንጌል ቃል የተገኘ ሳይሆን ክፉ ጠላት በጭለማ የዘራው ዘር ነው።

ወደዋናው ሃሳባችን ስንመለስ ለመሆኑ በማርያም ላይ ስንት ቀብር፤ ስንት ትንሣዔና ስንት እርገት ተደረገ? ብለን ብንጠይቅ እንደሚነገረው  ከሆነ ፤

1/ዮሐንስ ያየውና አፈር ያልነካው እርገት በገነት ዛፍ ስር

2/ አፈር የነካው የሐዋርያቱ ቀብር በነሐሴ 14 ቀን /ከስምንት ወር በኋላ/

3/ ቶማስ ያየው የትንሳዔ እርገት፤ ከቀብር በኋላ በሦስተኛው ቀን ነሐሴ 16

4/ ከአንድ ዓመት በኋላ ሐዋርያት ያዩት የነሐሴ 16 ትንሣዔና እርገት ናቸው።
እንግዲህ በማርያም ሞትና እርገት መካከል አራት ትእይንት መከሰቱን ዛሬም ድረስ ከሚሰጡት የቃል አስተምህሮዎችና የተዘጋጁ ጽሁፎች ውስጥ በግልጽ እናገኛለን። ማርያምን መውደድ አንድ ነገር ነው። ማርያምን ግን እየቀበሩና እያነሱ በቀብርና ትንሣኤ ማሰቃየት ደግሞ ሌላ አሳዛኝ ክስተት ይሆናል። እንዲያውም  ለዓለሙ ሁሉ መድኃኒት መሆን ከቻልኩ ሰባት ጊዜም ቢሆን እሞታለሁ ብላ ለልጇ ተናግራለች የሚሉት ተረትም በተዛማጅ ትምሕርትነት ይሰጣል። የእሷ መሞት የዓለሙ ሁሉ መድኃኒት መሆን ከቻለ የክርስቶስ ከእሷ መወለድ አስፈላጊ አይደለም የሚል ሃሳብን የሚያንጸባርቀው ይህ አባባል ከአሳሳች ትረካዎች ውስጥ የሚደመር ከመሆን አያልፍም።
እኛ  ማርያምን ብንወዳትና ብጽእት ብንላት «እናትህንና አባትህን አክብር»  ያለውን  የአምላክ ቃል መጠበቅ ብቻ ሳይሆን ለእርሷ  የተነገረ ቃል ስላለም ጭምር ነው። ከዓለመ አንስት መካከል በድንግልና መውለድ የሷ የተለየ ስጦታ ነው። በዚህም መመረጥ መቻሏን እናከብረዋለን። ነገር ግን የዘላለማዊ አምላክ የክርስቶስ ፤ እናቱ ስለሆነች በማዳላት ወይም አምላካዊ ባህርይውን በሰውኛ ጠባይ በመለወጥ ከፍርድ ሚዛኑ በማጉደል  የእሷን ሞትና ትንሣዔ የተለየ ያደርጋል ብሎ ማሰብ ስህተት ነው። የእሷ ሞትም የመድኃኒትነትን ውክልና ለሰው ልጆች የያዘ እንደሆነ ማሰብ ክህደት ነው። ብቸኛው መድኃኒት አንዱ ኢየሱስ ብቻ ነው። ማርያምም ይህንን አሳምራ ስለምታውቅ
«ነፍሴ በአምላኬና በመድኃኒቴ ሐሴት ታደርጋለች» ብላ ተነግራለች። ምክንያቱም ኢየሱስ ከእርሷ የተወለደ ቢሆንም ዓለሙን በማዳን ማንነቱ ውስጥ ለእርሷም አምላኳና መድኃኒቷም ስለሆነ ደስ እንደሚላት መስክራለች። የትንሣዔ በኩር የሆነው ሁላችንም በሞቱ እንድንመስለው እንጂ የተለየ አድሎአዊ ጥቅምን/ favour/ ለተለዩ ሰዎች በመስጠት አይደለም።ወንጌል የሚናገረው ይህንን ነውና። የክርስቶስ ሕይወት ተካፋዮች የምንሆነው በሞቱና በትንሣኤው እርሱን ስንመስል ብቻ ነው።

ሮሜ 6፥5 «ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን»

 ስለዚህ ደጋግሞ መሞት፤ መነሳትና ደጋግሞ ማረግ አለ ከተባለ ያ ነገር ከክርስቶስ ትንሣዔ ጋር ያልተባበረ ስለሆነ አንቀበለውም። እንዲያውን ይህ ኑፋቄና ወንጌልን መካድ ነው።  ሐዋርያው ጳውሎስም የተናገረው ስለክርስቶስ ወንጌል በሞቱም ክርስቶስን እንዲመስል ነበር።

ፊልጵ 3፥10-11  «እርሱንና የትንሣኤውን ኃይል እንዳውቅ፥ በመከራውም እንድካፈል፥ ወደ ሙታንም ትንሣኤ ልደርስ ቢሆንልኝ፥ በሞቱ እንድመስለው እመኛለሁ»
የማርያም ሞትና ትንሣዔ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ካዘጋጀው የትንሣዔው በኩር አንድያ ልጁ የተለየ አያደርገውም። ከመግቢያችን ላይ ጀምሮ ለመግለጽ እንደሞከርነው የኤፌሶኑና የኢየሩሳሌሙ ታሪክ እንዳለ ሆኖ አብያተክርስቲያናት ሁሉ የተለያየ የሞትና የትንሣዔ አስተምህሮ ከመያዛቸው አንጻር  ኤጲፋንዮስ እንዳለው ትክክለኛው የታሪክ ቀን አይታወቅም። ቢታወቅም ስለድነታችን የሚጨምረውም: የሚቀንሰውም ነገር የለውም። አሁን የሚደረገውም ፍልሰታ ለማርያም በዓል ከልምድና ትውፊት ከተረትና ክህደት ጋር በማር የተለወሰ መርዝ ስለሆነ መጠንቀቅ አለብን።
ማርያምን እንወዳለን እያሉ በጥር ሞተች፤ ገነት ዛፍ ስር ስምንት ወር በሬሳ ቆየች፤ በስንት ሱባዔ ስጋዋ መጥቶ ነሐሴ ተቀበረች፤ እስከነ ምድራዊ ልብሷ አረገች፤ በዳመናው ጎዳና  ላይ ከቶማስ ጋር ጨርቅ ተለዋወጠች፤ እድል ላመለጣቸው ሐዋርያት ዳግመኛ በስንት ሱባዔ በሌላ ትንሣኤና እርገት ተረጋገጠች፤ መንበር ሆና ተነጠፈች ወዘተ በማለት እየገደሉና እያነሱ በማርያም ላይ መጫወት ተገቢ ነው ብለን አናምንም። የክርስቶስን ሞትና ትንሣኤንም ማፋለስና መካድ ይሆናል። የማርያም ትንሣኤና እርገት ለክርስትና ከታሪክ ባለፈ ለሕይወት የሚሰጠው የሕይወት ዋስትና የለውም። ሕይወት ኢየሱስ ብቻ ነው።  ሕይወት እንዲሆንላችሁ ከፈለጋችሁ ከተረት ዓለም ውጡ።
“ነገር ግን ሕይወት እንዲሆንላችሁ ወደ እኔ ልትመጡ አትወዱም።” ዮሐ 5፥40  የተባለው እንዳይፈፀምባችሁ በሕይወት መኖር አይሻላችሁምን?
ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር የሌላ የማንም ሞትና ትንሣኤ  ለሰው ልጆች መዳን የቀረበ መስዋእት የለም።
የማርያምም ሞትና ትንሣኤ ማንንም ሊያድን አይችልም።
የተነገረን በማርያም ትንሣኤ እንድናምን ሳይሆን “በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።”
  ዮሐ 3፥36 ተብሎ እንደተነገረው የቤዛነት ምትክ በሌለው በኢየሱስ ብቸኛ አዳኝነት ልናምን ይገባል!
መጽሐፍ እንዳለው "“መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና።”ሐዋ 4፥12
ከላይ የተጻፈው ጽሑፍ ዋና መልእክት ማርያንም ለመቃወም ወይም ንጽሕት: ቅድስት ማርያምን ከመጥላት የተነሳ አይደለም። ማርያም ራሷ የማትቀበለው ከእውነትና ከወንጌል ቃል ተቃራኒ አስተምህሮን በእግዚአብሔር ቃል ለማፈረስና ሰዎች ሁሉ ባልተሸቃቀጠው ወንጌል ብቻ እንዲኖሩ ለማስቻል ነው። በዚህም እውነት ለመገዛት እግዚአብሔር ይርዳን! አሜን!



















Friday, May 14, 2021

ኦርቶዶክስን የማፍረስ ዘመቻ!

 


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስን ተዋሕዶን የማፍረስ ዘመቻ ዛሬ የተጀመረ አይደለም። አብዛኛዎቹ ዘመቻዎች ውጫዊ ነበሩ። የዮዲት ጉዲት ዘመቻ: ከደቡብ ወደሰሜን የተካሄደው የገዳዎች ወረራ: የግራኝ: የማህዲስት: የካቶሊክ ሚሲዮናውያን: የፋሺስት ጣሊያን ዘመቻዎች ሁሉ መሰረታቸው ኢትዮጵያን የመቆጣጠርና ግዛት የማስፋፋት ቢሆንም ቤተ መንግስቱንና ቤተ ክህነቱን ትቆጣጠር የነበረችውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን የማፍረስ ግብ የሁሉም ወራሪዎች ተመሳሳይ አላማ ነበር። የሕዝቡን እምነትና ለመንግስት አሜን ብሎ የመገዛት ስነልቦናውን ለማፍረስ መጀመሪያ ኦርቶዶክስን ማጥፋት የሁሉም ግብ ነበር። የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከውጪ የመጣባትን ጥቃት ሙሉ በመሉ በመቋቋም ከመጥፋት ተርፋ ይሄን ሁሉ ዘመን መዝለቅ የቻለችው ውስጣዊ አንድነት ስለነበራት ብቻ ነው። ነገር ግን ከ1966 ዓ/ም በኋላ የኦርቶዶክስ ሲሶ መንግስትነት ተንኮታኩቶ ፈጣሪ የለሽ መንግስት በቦታው ሲተካ ከውጫዊ ጥቃት ይልቅ ውስጣዊ አንድነቷን የሚፈታተን አደጋ ተጋርጦባታል። ለሁለተኛው ፓትርያርክ በደርግ መገደል መነሻው ምክንያት የውስጠኛው አመራር  የሆነው የሲኖዶሱ መከፋፈል ነበር። ለአራተኛው ፓትርያርክ ሹመት የነመላኩ ተፈራ ደርጋዊ እጅ ቤተ ክህነቱ ውስጥ ዘልቆ መግባቱና ለአምስተኛው ፓትርያርክ ሹመትም ተረኛው የወያኔ እጅ እንደፈለገው ማቡካት መቻሉን ስለምናውቀው እውነቱን መካድ አይቻልም። 

ደርግ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሀብትና ንብረት ወርሶ ለ17 ዓመት: ህወሀት ለ27 ዓመት የቤተ ክርስቲያኒቱን የውስጥ አመራር ተቆጣጥረውት የቆዩት ለፖለቲካዊ አላማቸው የማታስቸግር ቤተ እምነት እንድትሆን ቀፍድዶ ለመያዝ እንደነበር ይታወቃል። 

ለኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የውስጥ አስተዳደር መበላሸትና ለጥቃት ተጋላጭ ያደረጋት ዋናው ምክንያት ቅዱስ የተባለው ሲኖዶስ በሚጠበቀው ደረጃ አስተዳደሩን በቅድስና መምራት አለመቻሉ እንደሆነ እርግጥ ነው። ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባለፉት 30 ዓመታት ውስጥ ከ25ሚሊዮን በላይ አማኞቿ ትተዋት የኮበለሉት በቁጥርም: በዝናም ሲኖዶስ የተባለው ማኅበር በጨመረ ቁጥር ነው። ለምን? ብሎ መጠየቅ የግድ ይላል። ይሄ ሲኖዶስ የሚባለው ማኅበር ትክክለኛው የበጎች እረኛ ሳይሆን የበጎቹን መንጋ ለቀበሮ አሳልፎ የሚሰጥ ለደመወዝ የሚኖር ቅጥረኛ ስለሆነ ብቻ ነው። በነቀዘ የአስተዳደር መዋቅር: በጉቦና በዘረፋ የተሰማራ አመራር: ዘመኑን የሚዋጅ ሃይማኖታዊ አስተምህሮ አለመኖር:  ፍትህ በአፍጢሙ በመደፋቱና በሌሎች ውስጣዊ ገፊ ምክንያቶች የተነሳ ብዙዎች ቤተ ክርስቲያኒቱን ለቀው ሄደዋል።  ያሉትም በሚያዩት ነገር ተስፋ ቆርጠው ቤታቸው ተቀምጠዋል። በአንድ ወቅት አንድ የሙስሊም ስኮላር ያለውን አስታውሳለሁ። እስልምና የምስራቅ አፍሪካ ሀገሮች በሙሉ ሲቆጣጠር የነቢያችንን ዘመዶች የተቀበለችው ኢትዮጵያን መቆጣጠር ያቃተን በኦርቶዶክስ የተነሳ ነበር። እኛ ያቃተንን ጳጳሳቶቿ ራሳቸው እያዳከሙልን ስለሆነ ምስጋና ይገባቸዋል ሲል ተደምጧል።  ነገሩን ቆም ብለን ስንመረምር ቤተክርስቲያኒቷ ጳጳሳት በበዙ ልክ ማደግ ሲገባት ጳጳሳቱ በበዙ መጠን እያሽቆለቆለች መገኘቷ የስጋውያን መሪነት የመንገሱ ማሳያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። 

በአጠቃላይ ከ1966 ዓ/ ም በፊት የነበሩ ውጫዊ አደጋዎቿን በውስጣዊ አንድነቷ መቋቋም የቻለችው ቤተ ክርስቲያን ውስጣዊ አንድነቷን የሚያናጋ ውስጣዊ ችግሮችን እያመረተች በመገኘቷ በምእመናኖቿ ቁጥር የቁልቁለት ጉዞዋን ተያይዛዋለች። በመንፈሳዊ ወሥጋዊ ዘመናዊ አስተዳደር አለመኖርና የፋይናንስ ስርአቱ ብልሹነት የተነሳ ዘረፋ: ጉቦ: ዘረኝነትና ዐመፃ በመንሰራፋቱ ራሷን ከውጪ ጥቃት እንዳትከላከልና ውስጣዊ ተጋላጭነቷ ከፍ እንዲል አድርጓታል።

ይህ ሁሉ ዐመፃና ስርአተ አልበኝነት ነግሶ እያለ አንዳንዶች እግዚአብሔር ስለሚጠብቃት ኦርቶዶክስ አትፈርስም ሲሉ ይደመጣሉ። ይሄ ግን በስመ እግዚአብሔር የሚፈፀም ራስን የማታተል ግብዝነት ነው። በራእየ ዮሐንስ ላይ የተመለከቱት ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ዐመጽና በደልን እንዲተዉና ወደእግዚአብሔር የቀደመ መንገዳቸው እንዲመለሱ ቢነገራቸው መስማትና ንስሐ መግባት ባለመፈለጋቸው የተነሳ አብያተ ክርስቲያናቱ በሙሉ ፈራርሰው ዛሬ በሙዚየምነት የሚጎበኙ የእስላማዊ ቱርክ የገቢ ምንጭ ፍርስራሽ ሆነው ቀርተዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንም መጨረሻ በዚህ መልኩ እንዳይደመደም የሚያስችል ሁኔታ እየታየ አይደለም። ሲኖዶስ የተባለው በስመ ቅድስና የተሰየመው የበላይ አካል በቅድስና እየመራት ከሆነ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ዐመጽ: ዘረፋ: ጎጠኝነት: የአመራር ክፍፍልና ልዩነት ለምን መለያዋ ሊሆን ቻለ? 

አሁን በቅርቡ በታየው የቤተ ክርስቲያኒቱ መግለጫ በተባለው ጉዳይ ላይ (አባ) ወ/ ኢየሱስ ወይም ህፃን የተባለው ጎረምሳ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወክሎ ያደረገው ንግግር የሚያሳየው የቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓትና ሕግጋት እየፈረሰ መሆኑን ያመላክታል። ይህ ሰው በመኪና ስርቆት ወንጀል ተፈርዶበት 4 ዓመት ከርቸሌ የከረመ መሆኑ እየታወቀ በቤተ ክርስቲያኒቱ ዓመታዊ በዓላት በልደት: በጥምቀት: በዘመን መለወጫ: በከፍተኛ ስብሰባዎች እየተገኘ በውክልና መግለጫ የሚሰጠው በምን አግባብ ነው?



 አባ ሕጻን (በአማን ዘውእቱ ሕጻን) ከዘመናዊ ትምህርት ይሁን ከቤተ ክርስቲያኒቱ ትምህርት ሩቅ ነው። ግን መግለጫ በመስጠት ቀዳሚ ነው። እውነት ነው: ሲኖዶሱ በዝምታ ድባብ ሲዋጥ አላዋቂዎች ቢሰለጥኑባት አይገርምም። "ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ" እንዲሉ!

የዓሳ ግማቱ ከጭንቅላቱ ነው እንደተባለው በመላው ሀገሪቱ እየታየው ባለው የቤተ ክርስቲያን መቃጠልና የምእመናን እልቂት ፊት ለፊት መናገር ሲገባቸው እንደቀንድ አውጣ አንገታቸውን ቀብረው የቆዩ ሁሉ ቅዱስ ፓትርያርኩ በትግራይ እየተከሰተ ያለውን እልቂት ማውገዛቸውን ተከትሎ ፓትርያርኩ ላይ አፋቸውን ሲከፍቱ ስናይ ቅጥረኞች ቤተክርስቲያኒቱን እንደወረሯት ማሳያ ነው። በልብስ ሰፊነት ባደለቡት ገንዘብ ያገኙትን ሹመት በመንፈሳዊ ብቃት ያገኙት ያህል እንድንቆጥርላቸው ይፈልጋሉ። የብርሃኑ ጁላ ታናሽ ወንድም 



ሆነው ፓትርያርኩ የተናገሩትን የግላቸው አቋም ነው ብለው የማን ቅጥረኛ እንደሆኑ ሲያሳብቁ እነርሱ በማን ፈቃድ? የማንን አቋም? እንዳንፀባረቁ ድንቁርናቸው ራሱ ያጋልጣቸዋል። ጊዜ ወለድ የሆኑ ጳጳሳት ባሉባት ቤተክርስቲያን ውስጥ የሚገርመው ውድቀቷ ቶሎ አለመፈፀሙ ብቻ ነው። 

የኦሮሚያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መስራቹ አቶ በላይ መኮንን ባቋቋመው ቲቪ ላይ ከጀነራል ጳጳሳቱ ጋር ተሰይሞ እንደሕዝብ አማራን: እንደተቋም አሁን ያለው ሲኖዶስ ሲያዋርዱና ሲዘለፉ ተመልክተናል።  


ፓትርያርኩ የትግራይ ህዝብ እየተጨፈጨፈ ነው ብለው መናገራቸው ስህተት ተደርጎ የተቆጠረው የኦሮሚያ ኦርቶዶክስን ለማቋቋም እንደእጅ መንሻ ለመንግስት ለማቅረብ መሆኑ ያልገባው ካለ እሱ ጅል መሆን አለበት። ፓትርያርኩ የአስተዳደር ብቃት ችግር እንዳለባቸው ይታወቃል። ነገር ግን ለቤተክርስቲያን ባለመቆርቆር ወይም በዘረኝነት እሳቸውን ለመክሰስ ብቃት ያለው አንድም ጳጳስ እንደሌለ እርግጠኞች ነን።

የአቶ አሻግሬ መንግሥት ተለያይቶ የነበረውን ሲኖዶስ ያሰባሰበው በተለያየ ጎራ በፖለቲካ ውጊያ እንዳያስቸግሩትና ሰብሰብ ባለ ጠላት ላይ ኃይሉን በሙሉ ለማሳረፍ እንዲያስችለው እንጂ መንፈሳዊ መልእክት ከሰማይ ወርዶለት አይደለም። በአጠቃላይ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የማፈራረስ እቅድ በመንገድ ላይ ይገኛል። ውስጣዊ አንድነቷ የለም። ሲኖዶሱ እንደእከ " እኔን ነው?" ከማለት  የእንቅልፍ አዚም መውጣት አልቻለም።

ምእመኑ የተመሪነት ፍላጎቱ ቢኖረውም መሪ እንደሌለው የበግ መንጋ በሃዘንና በስቃይ እየተቅበዘበዘ ነው። የጊዜ ጉዳይ እንጂ ኦሮሙማ ቤተ መንግሥቱንና ቤተ ክህነቱን ከመዋጥ ከመሰልቀጥ አይመለስም። መጨረሻውስ ምን ይሆን?

እድሜ ይስጠን ገና ብዙ እናያለን: እንሰማለን!