Sunday, January 29, 2012

«ገና በመንገድ ሳለህ ከባላጋራህ እንድትታረቅ ትጋ»ሉቃ 12፣58

ከዚህ ቀደም ስለእርቅ ጉዳይ በተነሳ ሃሳብ ዘመድኩንን ኃያልና የማይንበረከክ ክንድ ባለቤት እንደሆነ አጋኖ ደጀሰላም ብሎግ ዘግቦ ነበር። ዘመድኩንም ሲኦል ብወርድ እንኳን ከበጋሻው ጋር እርቅ አይሞከርም በማለቱም ተገርመን አስተያየት ጽፈን በደጀሰላም ላይ አስነብበናል። ሰጥተን የነበረውም አስተያየት ከላይ የሰጠነውን ርእስ መሰረት ያደረገ ነው። በወቅቱ የሰጠነውን አስተያየት እንዳለ አቅርበነዋል፣
«Anonymous said... ከሳሽንም ተከሳሽንም በደንብ አውቃቸዋለሁ። ወደ ዝርዝር ብንገባ ከአምላክ የሚያጣላ ይሆናልና ተከድኖ ይብሰል። የሆኖ ሆኖ ፍርድ ቤት ስለምስጢረ ሥላሴ ሳይሆን ስለስመ ማጥፋት ወንጀል የቀረበ ክስን እያየ እንደሆነ ከክሱ ጭብጥ ስንረዳ ከሳሽና ተከሳሽ ክርክሩን በእርቅ ቢጨርሱት 1/ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉ ። 2/ሃይማኖተኞች ሃይማኖት በሌላቸው(ዓለማውያን) ፍርድ ቤቶች የሚያደርጉት ክርክር ሃይማኖቱን ያስነቅፋልና ይህንን ለማስቀረት 3/የበደሉንን ይቅር ማለት ስለሚገባን ዘመድኩን ዕርቅ አልቀበልም ማለቱ እውነተኛ ኦርቶዶክሳዊ መሆኑን ሳይሆን የሚያመለክተው አለማወቁን፤ ግብዝነቱንና የታይታ ክርስቲያን መሆኑን እንጂ የክርስቶስ ልጅ መሆኑን አይደለም። ክርስቶስ ፍርድ ቤት ይለያችሁ ሳይሆን ያለው ከባላጋራህ ጋር አስቀድመህ ታረቅ ነው ያለው። እኔ ከአንድ እስላም ጋር ብጣላና ብታረቅ በሰውነቱ እንጂ የሱን ሃይማኖት ለመቀበል ስላልሆነ ዘመድኩን እሱ ከበጋሻው ጋር ታረቀ ማለት እሱ እንደሚለው ተሃድሶ ሆነ ማለት አይደለም። የሚያሳብቅ ውሸት መሆኑ ደግሞ ሲዖልም ቢሆን እወርዳለሁ በማለት አንድ ክርስቲያን በህይወት ዘመኑ ዕድል ፈንታውና የፍርድ ዕጣው በፍጹም ሊሆን ቀርቶ ሊመኝ የማይገባውን መናገሩ አሳዛኙ አባባል ነው። እውነተኛ ክርስቲያን ነኝ ለማለት ማረጋገጫና ሌላውን የማሰመኛ ቃል አድርገን ሲዖልም ቢሆን እወርዳለሁ ማለት ከየት የተገኘ ትምህርት ነው። እኛ እድል ፈንታችንና መንፈሳዊ ፍላጎታችን መቼም ቢሆን ከክርስቶስ ጋር መኖር ነው እንጂ ሲዖልም ቢሆን ወርደን የምናረጋግጠው እውነተኛነታችን ስለሌለ ይህንን ቃል ከመጠቀም(ሎቱ ስብሐት)እንላለን። ሳጠቃልል ዘመድኩን የምትረታ መሆንህን ብታውቅ እንኳን ከፍርድ ቤት ክርክርና ጭቅጭቅ በኋላ ከምታገኘው የረቺነት ኃላፊ ጠፊ ዝና ይልቅ ለክርስቶስ ብለህ ሁሉን ትተህ የምታደርቀው እርቅ ብዙ ኃጢአትህን ይሸፍናል፤ ሰማያዊ ክብርንም ያስገኝልሃልና ከልብህ መክረህ ታረቁ የሚሉ ሽማግሌዎች ካሉ ወደመጡበት አትመልስ ወንድማዊ ምክሬ ነው። September 10, 2011 12:37 PM የሚል አስተያየት ሰጥተን የሰማን የለም።
የያኔውን የደጀሰላም ብሎግ «ወደፊት በሉለት ይለይለት» ሙሉ ጽሁፍን ለማንበብ ከፈሉጉ (እዚህ ላይ ይጫኑ)
  አሁን ደግሞ «ደጀሰላአም» የተሰኘ ብሎግ በወቅቱ ብለነው የነበረውን አስተያየት የሚያጠናክርና የክሱ ሂደት የፈራነው ግምት የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ መድረሱን ከታች አስነብቦናል። መልካም ንባብ!

Friday, January 27, 2012

ሕሙም እንዳይረዳ የተቃውሞ ዘመቻ!


የአቶ እንዳለ ገብሬን ሕይወት ለመታደግ የገቢ ማሰባሰቢያ መንፈሳዊ ጉባዔ ሊካሄድ ነው
"ማኅበረ ቅዱሳን" ጉባዔው እንዲካሄድ በመፍቀዳቸው ብፁዕ አቡነ ፊሊጶስን ስም አጠራራቸው እስኪረሳ እንዲያልፉ እርግማን አወረደባቸው
ባደረበት የልብ ሕመም ምክንያት ውጭ ሀገር ሄዶ ካልታከመ በስተቀር የመዳን ተስፋው የመነመነው የአቶ እንዳለ ገብሬን ሕይወት ለመታደግ ከ450 ሺህ በላይ ወጪ የተጠየቀ ሲሆን፣ ቤተክርስቲያንን በማገልገል ላይ ያሉት መምህራንና ዘማርያን፣ በጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤት አዳራሽ ጥር 20 ቀን 2004 ዓ.ም ከቀኑ ሰባት ሰዓት የሚጀምርና ገቢው ለዚሁ ወንድም መታከሚያ የሚውል መንፈሳዊ ጉባዔ አዘጋጅተዋል፡፡
ይህንን የተቀደሰና ሁሉም ወገን ሊረባረብበት የሚገባ ዕርዳታ በወንጌሉ ቃል መታጀቡና መመራቱ በዘልማድ ማኅበረ ሰይጣን የሚባለውና ራሱን "ማኅበረ ቅዱሳን" እያለ የሚጠራው ፈሪሳዊ ማኅበርን በማስኮረፉ ጉባዔውን ለማደናቀፍ በመውተርተር ላይ ይገኛል፡፡ ካለ እኔ በስተቀር ቤተክርስቲያን ልጅ የላትም የሚለው ይኸው ማኅበር፣ ልዩ ልዩ አቃቂሮችን በማውጣት ራሱ ፈራጅ፣ ራሱ ፈጻሚ በመሆን በምዕመናንና በቤተክርስቲያን መካከል እንደ ግድግዳ ቆሞ ማወክ ከጀመረ ዓመታት ያስቆጠረ ሲሆን፣ ይህንኑ ጉባዔ ያዘጋጁት ለእርሱ ዓላማ አንገዛም ያሉ ሰባክያነ ወንጌልና መዘምራን በመሆናቸው፣ እንደተለመደው የተሃድሶ ታፔላውን ከፍ አድርጎ በማንሳት ያዙኝ ልቀቁኝ እያለ ነው፡፡(ዘመቻውን ለማንበብ እዚህ ይጫኑ)
ዘወትር ስድብና ዕርግማን ከአፉ የማይጠፋው "ማኅበረ ቅዱሳን" የወንድማችንን ሕይወት ለመታደግ ማንኛውም ሰብዓዊ ፍጡር ዕርዳታ እንዲያደርግለት በመማጸን ፈንታ በሲኖዶስ ያልታገዱትና ያልተከለከሉት ሰባክያንና ዘማርያን እንደታገዱና እንደተወገዙ አስመስሎ በማውራት ጠቅላይ ቤተክህነት አዳራሽ ለምን ተፈቀደላቸው ብሎ በመጮህ ላይ ነው፡፡ ይባስ ብሎም፣ "አንድ አድርገን" በተባለው ብሎጉ፣ ". . . ፈቃጆች ነገ ስም አጠራራቸው እስኪረሳ ድረስ ያልፋሉ. . ." በማለት ሆን ብሎ በስም ባይጠራቸውም ጉባዔው እንዲካሄድ የፈቀዱትን እነአቡነ ፊሊጶስን ወርፏል፡፡

Thursday, January 26, 2012

መግደልና ማቃጠል!!





በሀላባ ቁሊቶ አክራሪ ሙስሊሞች ለጥምቀት በዓል በወጡ ክርስቲያን ምዕመናን ላይ ጉዳት አደረሱ

የሀላባ እና አካባቢው ምዕመናን ከፍተኛ ክርስቲያናዊ ገድል በመጋደል ሃይማኖታቸውን መከላከላቸው ተሰማ

ጉባ በተባለች አነስተኛ መንደር ለገበያ በወጡ ክርስቲያኖች ላይ የማኅተም መበጠስና የገንዘብ ዝርፊያ ተካሂዷል

መንግሥት ተገቢውን እርምጃ ካልወሰደ መጪው ጊዜ እጅግ አስቸጋሪ እንደሚሆን ተገምቷል


በደቡብ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ከሻሸመኔ በስተምዕራብ በግምት 75 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በምትገኘው በሀላባ ቁሊቶ ከተማ ጥር 12 ቀን 2004 ዓ.ም ለጥምቀት በዓል በወጡ ክርስቲያኖች ላይ ጥቃት መድረሱን ከዚያው አካባቢ የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

ሆን ተብሎ እና ታቅዶ በተሰነዘረው በዚህ ጥቃት በርካታ ክርስቲያን ወንዶችና ሴቶች፣ ሕፃናትና ዐዋቂዎች ከፍተኛ የመፈንከትና የመቁሰል አደጋ ደርሶባቸዋል፡፡ ጉዳቱ የደረሰው ምዕመናን የቅዱስ ሚካኤልና የመድኃኔዓለም ታቦታትን ወደ ቤተመቅደስ ለመመለስ አጅበው በሚጓዙበት ወቅት መሆኑን ምንጮቻችን አረጋግጠዋል፡፡ በዕለቱ በክርስቲያኖች በኩል ከወትሮው የተለየ ግጭትን የሚያነሳሳ ምንም ነገር አለመፈጸሙንና ታቦታቱ ተጉዘው በከተማዋ አደባባይ ለዕረፍት በቆሙበት ወቅት፣ አድፍጠውና ተዘጋጅተው ምቹ ሰዓትና ቦታ ይጠብቁ በነበሩ ሙስሊሞች በኩል የድንጋይ እሩምታ መጀመሩን እማኞቻችን አስረድተዋል፡፡

Thursday, January 19, 2012

በጥምቀትም ከእርሱ ጋር ተቀበራችሁ!



(ከእንግሊዝኛ ማጣቀሻ ጋር)

ቆላስ ፪፥፲፪ (Colossians2:12) « በጥምቀትም ከእርሱ ጋር ተቀብራችሁ፥ በጥምቀት ደግሞ፥ ከሙታን ባስነሣው በእግዚአብሔር አሠራር በማመናችሁ፥ ከእርሱ ጋር ተነሣችሁ»
ኦሪቱ የአዲስ ኪዳኑን ጥምቀት በማንጻትሥርዓት ታከናውነዋለች። ከኃጢአት ማንጻት! ማንም ቅድስናንና ንጽሕናን ሲሻ ይህንን የማንጻት ልማድ መፈጸም ግዴታው ነው። እንደሕጉ የታዘዘውን መስዋዕት አቅርቦ የሥርዓቱ ማጠቃለያ በምንጭ ውሃ ሰውነቱ መታጠብ አለበት። የማንጻት ልማዱ የሚከናወነው ከሰፈር ውጭ ነው።
«ንጹሕም ሰው የጊደሪቱን አመድ ያከማቻል ከሰፈሩም ውጭ በንጹሕ ስፍራ ያኖረዋል ርኵሰትም ለሚያነጻ ውኃ ለእስራኤል ልጆች ማኅበር ይጠበቃል ከኃጢአት ለማንጻት የሚሆን ነው» ዘኁ ፲፱፣፱ (Numbers19:9)
ፈሳሽ ያለበት ይሁን ለምጽ የወጣበት ወይም ቆረቆር የታየበት ይሁን የመርገም ወራቷ የመጣባት ሴት ሁላቸውም እንደሕጉ የታዘዘውን የኃጢአት መስዋዕት አቅርበው ሲያበቁና ሥርዓቱ ከተከናወነ በኋላ ለመንጻት በምንጭ ውሃ መታጠብ የግድ ነው። ያኔ ነጽተው ወደሕዝቡ ይቀላቀላሉ። አለበለዚያ ከሕዝቡ ጋር ሕብረት አይኖቸውም።ፈሳሽ ነገር ያለበት ሰው ከፈሳሹ ነገር ሲነጻ ስለ መንጻቱ ሰባት ቀን ይቈጥራል ልብሱንም ያጥባል፥ ገላውንም በምንጭ ውኃ ይታጠባል፥ ንጹሕም ይሆናል» ዘሌ ፲፭፣፲፫ (Leviticus15:13)
«የሞተውን ወይም አውሬ የሰበረውን የሚበላ ሰው ሁሉ፥ የአገር ልጅ ወይም እንግዳ ቢሆን፥ ልብሱን ያጥባል፥ በውኃም ይታጠባል፥ እስከ ማታም ርኩስ ይሆናል ከዚያም በኋላ ንጹሕ ይሆናል። ልብሱንና ገላውን ባያጥብ ግን ኃጢአቱን ይሸከማል» ዘሌ ፲፯፣፲፭-፲፮ (Leviticus17:15-16) ያ ማለት ኦሪት የምታነጻውና መስዋዕቱን ፍጹም የምታደርገው በውሃ በመታጠብ ነው።
የዚህ የማንጻት ልማድ የድንጋይ ጋኖች አብነት ሆነው በዘመነ ሐዲስ ከአንድ ሰርግ ቤት ተቀምጠው እናገኛቸዋለን። ቦታው ቃና ዘገሊላ ነው። እነዚህ የድንጋይ ጋኖች በኦሪቱ ለማንጻት ሥርዓት የምንጭ ውሃ የሚጠራቀምባቸው ነበሩ። ወንጌሉ አገልግሎታቸውን ለይቶ አስቀምጦልናል።
«አይሁድም እንደሚያደርጉት የማንጻት ልማድ ስድስት የድንጋይ ጋኖች በዚያ ተቀምጠው ነበር፥ እያንዳንዳቸውም ሁለት ወይም ሦስት እንስራ ይይዙ ነበር» ዮሐ ፪፣፮ (John2:6)
እነዚህ የማንጻት ሥርዓት የድንጋይ ጋኖች የመጀመሪያውን የአዲስ ኪዳን ተአምርም አስተናግደዋል። የእውነተኛው የወይን ግንድ ደም ለዓለሙ ሁሉ እንደሚፈስ ምሳሌ ሆነዋል። ቅድስት ማርያም ወይን እንዳለቀባቸው ባሳሰበች ጊዜ ጌታም እውነተኛው ወይን ለዓለሙ ሁሉ የሚፈስበት ጊዜ ገና መሆኑን ሲያስረዳ «ኢየሱስም፦ አንቺ ሴት፥ ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም አላት» ዮሐ ፪፣፬ (John2:4)እውነተኛ ወይን እስኪሰጥ የኦሪቱ የማንጻት ሥርዓት የድንጋይ ጋኖች ጊዜው እስኪደርስ ድረስ ተአምር አስተናግደዋል። እነሱ ሲፈጽሙ የቆዩበትን የማንጻት ሥርዓት አዲስ ኪዳን በማይደጋገምና አንዴ በሚፈጸም የኃጢአት ሥርየት ለውጣዋለች። እሱም «ጥምቀት» ነው። ኦሪት ከሰፈሩ ውጭ ሁልጊዜ በሚፈጸምና በሚፈሰው የደም መስዋዕት ማሳረጊያ የሚሆን የመንጻትን ሥርዓትን ታዛለች።
አዲስ ኪዳን ደግሞ ከሰፈሩ ውጭ በተሰቀለውና አንዴ በሞተው የበጉ መስዋዕት ምሳሌ የውሃ ጥምቀትን በመቀበሩ ጠልቀው፣ ከውሃው በመውጣት ትንሳዔውን መስክረው፣ አንዴ በፈጸሙት ሥርዓት የኃጢአት ስርየት ታስገኛለች።
ለዚህም ነው ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ ያለው።
ቆላስ ፪፣፲፪ (Colossians2:12) «በጥምቀትም ከእርሱ ጋር ተቀብራችሁ፥ በጥምቀት ደግሞ፥ ከሙታን ባስነሣው በእግዚአብሔር አሠራር በማመናችሁ፥ ከእርሱ ጋር ተነሣችሁ»
ጥምቀት ከንስሐ በኋላ የምትፈጸም ስለመሆኗ መገንዘብ ያስፈልጋል። ንስሐ ደግሞ ስላለፈው ተጸጽቶ፣ በጥምቀት ስለሚገኘው ጸጋ አምኖ መቀበልን ይጠይቃል። መጥምቁ ዮሐንስ በዮርዳኖስ ዙሪያና በሄኖን ማጥመቂያው ሁሉ ሲናገር የነበረው የቅድሚያ አዋጅ «ንስሐ ግቡ» እያለ ይሰብክ እንደነበር እንያለን።
«ዮሐንስ በምድረ በዳ እያጠመቀ የንስሐንም ጥምቀት ለኃጢአት ስርየት እየሰበከ መጣ» ማር ፩፣፬ (Mark1:4)
«ከመምጣቱ በፊት ዮሐንስ አስቀድሞ ለእስራኤል ሕዝብ ሁሉ የንስሐን ጥምቀት ሰብኮ ነበር» የሐዋ ፲፫፣፳፬ (Acts13:24)
«እኔስ ለንስሐ በውኃ አጠምቃችኋለሁ፤ ጫማውን እሸከም ዘንድ የማይገባኝ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ግን ከእኔ ይልቅ ይበረታል፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስ በእሳትም ያጠምቃችኋል»ማቴ ፫፣፲፩ (Matthew 3:11)
ሐዋርያው ጴጥሮስም በበዓለ ሃምሳ ተሰብስበው ለነበሩት ነፍሳት ሁሉ አዲሱን የምስራች ከሰበከ በኋላ «ምን እናድርግ?» ብለው በጠየቁት ጊዜ የሰጣቸው መልስ ቅድሚያው ንስሐ ግቡ ነው። ቀጥሎም ኃጢአታችሁ ይሰረይ ዘንድ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ ነው። ከዚያም የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ትቀበላላችሁ ነበር ያላቸው ንግግሩን በማያያዝ።
«ጴጥሮስም፦ ንስሐ ግቡ፥ ኃጢአታችሁም ይሰረይ ዘንድ እያንዳንዳችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ፤ የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ» የሐዋ ፪፣፴፰ Acts2:38
«እምነት ከመስማት ነው፣ መስማትም ከእግዚአብሔር ቃል ነው» ሮሜ፲፣፯ Rome10:7 የሚለው ትምህርት በመጀመሪያ ገቢር ላይ ሲውል የተነገራቸውን ቃል አመኑ፣ ያመኑበትን ተቀበሉ፣ በተቀበሉት ተጠመቁ፣ ከዚያም ወደ መዳን ሕይወት ተጨመሩ ይለናል መጽሐፉ።
« በብዙ ሌላ ቃልም መሰከረና። ከዚህ ጠማማ ትውልድ ዳኑ ብሎ መከራቸው። ቃሉንም የተቀበሉ ተጠመቁ፥ በዚያም ቀን ሦስት ሺህ የሚያህል ነፍስ ተጨመሩ» የሐዋ ፪፣፵-፵፩ Acts40:41
ታዲያ እኛስ ምን ማድረግ ይጠበቅብናል?
፩/ « እነሆም፥ ድምፅ ከሰማያት መጥቶ። በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው አለ» እርሱን ስሙት ያለውን ብቻ ተቀብለን በማመን አንዲት ጥምቀት በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጠመቅ! ማቴ ፫፣፲፯,Matthew3:17 ኤፌ ፬፣፬, ማቴ ፳፰፣ ፲፱
፪/ ከተጠመቅን ደግሞ «ከእንግዲህስ ወዲያ ለኃጢአት እንዳንገዛ የኃጢአት ሥጋ ይሻር ዘንድ አሮጌው ሰዋችን ከእርሱ ጋር እንደ ተሰቀለ እናውቃለን፤ የሞተስ ከኃጢአቱ ጸድቋልና» ሮሜ ፮፣፮ እንዳለው ዳግም ወደኃጢአት አለመመለስ!
፫/ ያመነና የዳነ የክርስቶስ ፍሬ ይታይበት ዘንድ ግድ ነው። «በመልካም መሬት የተዘራውም ይህ ቃሉን ሰምቶ የሚያስተውል ነው፤ እርሱም ፍሬ ያፈራል አንዱም መቶ አንዱም ስድሳ አንዱም ሠላሳ ያደርጋል» ማቴ ፲፫፣፳፫ Matthew13:23
ከዚህ ከሦስቱ የወጣ ሁሉ ይህን ሆኗል ማለት ነው።
«አውቀዋት ከተሰጣቸው ከቅድስት ትእዛዝ ከሚመለሱ የጽድቅን መንገድ ባላወቋት በተሻላቸው ነበርና። ውሻ ወደ ትፋቱ ይመለሳል፥ ደግሞ። የታጠበች እርያ በጭቃ ለመንከባለል ትመለሳለች እንደሚባል እውነተኞች ምሳሌዎች ሆኖባቸዋል» ፪ኛ ጴጥ ፪፣፳፩-፳፪ 2 Peter2:21-22
ስለሆነም ጥምቀትን ከእውቀት ጋር ስለመዳናችን እንጂ ስለበዓል ጭፈራና የጭፈራ ስርዓት አከባበር እንዳይውል እንጠንቀቅ!
መልካም በዓለ ጥምቀት!!!!!!!!!




የጥምቀት በዓል መታሰቢያ ስዕሎች

Friday, January 13, 2012

የተስፋው ቃል!





«እኛ በመንፈስ ከእምነት የጽድቅን ተስፋ እንጠባበቃለንና» ገላ ፭፣፭
በተስፋ የሚጠብቅ ክርስቲያን ትክክለኛ እምነትን የያዘ ነው። ፍጹም የሆነ እምነት በሌለበት የጽድቅን ተስፋ መጠባበቅ የለም። ስለሚጠባበቁት ተስፋ ፍጻሜ እምነት ሊኖር የግድ ነው።
ወንድና ሴት ሊጋቡ ሲወስኑ በጋብቻ ውስጥ ሳሉ ስለሚሆነው ነገር ሁሉ አስቀድመው በተስፋ አምነው ይፈጽማሉ። በጋብቻቸው ልጆችን ይወልዱ ዘንድ ተስፋ አድርገው ያምናሉ እንጂ እየወለዱ አይጋቡም። ሴትም በጽንሷ መጨረሻ ወራት ልጇን ትወልድ ዘንድ በተስፋ ትጠብቃለች እንጂ የጽንስ ውጤት ምን እንደሆነ ሳታውቅ ጽንስን አትለማመድም። ስለሚሆነው ነገር ባለው ጽኑ እምነት የተነሳ ውጤቱን በተስፋ መጠበቅ የግድ ይሆናል ማለት ነው።
አንድ ሰው ቃል ከገባለት ሌላ ሰው የተገባለትን ቃል ፍጻሜ በተስፋ ይጠብቃል። የገባለት ቃል ፍጻሜው ምንም ይሁን ምንም የተስፋውን ቃል ያይ ዘንድ በልቡ አስቀምጦ ይጠብቃል።
እንደዚሁ ሁሉ የተበደለ እንደሆነ የሚያምን ማንም ቢኖር ወደፍርድ አደባባይ ቢሄድ የበደሉን ዋጋ መልካም ፍርድን በተስፋ ይጠብቃል። በተስፋ ስለሚጠብቀው ነገር የጸና እምነት ባይኖረው ወደፍርድ አደባባይ በደሉን ይዞ ሊሄድ አይችልም።
ኦርቶዶክስ ይሁን እስላም፣ ይሁዲ ይሁን ጄሆቫ ዊትነስ፣ ፕሮቴስታንት ይሁን ካልቪኒስት የሁሉም ሃይማኖት ተከታይ በሚያምነው ሃይማኖት ውስጥ የመጨረሻ ግቡን በተስፋ ይጠባበቃል። ውጤቱ ምንም ይሁን ምንም የሚጠባበቀውን ተስፋ በእምነት ሳይቀበል ሃይማኖታዊ ልምምዱን በኑሮው ሁሉ ሊተገብር አይችልም።
ተስፋውን የሚጠባበቀው ከማመን ነው። ማመን ደግሞ ከመስማት ነው። በተስፋው ነገር ላይ እምነት ሳይኖረው ተስፋ አያደርግም። የሚያምነው ደግሞ ስለሚጠባበቀው ተስፋ በደንብ በመስማት ነው። ሳይሰማ እንዴት ያምናል? መጽሐፉም «እምነት ከመስማት ነው» ያለውም ለዚህ አይደል!!

Friday, January 6, 2012

እኔ ማነኝ?



(by dejebirhan)

«እኔ ማነኝ? አንተስ ወንድሜ ማነህ?»

እኔ አበባ ነኝ ፣ የማለዳ ጤዛ ያረፈብኝ፣

ፍካት፣ ድምቀት የከበበኝ፣

ያይን ስስት፣መዐዛ ሽታ፣ የሞላብኝ፣

የንብ ቀሰም፣ ጣፋጭ ማር ነኝ፣

የከበርኩኝ፣ ውበትን የታጠርኩኝ፣

አበባ ነኝ፣ አበባ ነኝ፣

«እኔ ማነኝ፣ እንዴት አልኩኝ?

«አንተስ ማነህ፣ ለምን አልኩኝ?።

                                  ጠያቂ አዋቂ፣ ያ'በው ወግ፣

                                 ጸገየ እጽ ፣ የፍጥረት ሕግ፣

                              ለካስ ነበር-ወደማታው፣ መጠውለግ፣

                                      የመፍረስ ጫፍ ፣ ሌላ ጥግ፣

ታዲያስ እኔ ማነኝ?

ፍካት ድምቀት፣ የማይዘልቀኝ፣

ውበት ጤዛ፣ የሚያረግፈኝ፣

ከሰሎሞን የተሻልኩኝ፣ውበት የደረብኩኝ፣

ሆኜ ሳለሁ፣ ባዶ ገላ ያሸነፈኝ፣ እኔ ማነኝ?

                                   መልስ አገኘሁ፣ የራሱ ካደረገኝ፣

                                    ሳልፈልገው ከፈለገኝ።

                                   እኔ የኔ አይደለሁም፣

                               ውበቴን ሽንፈት አይጥለውም፣

                               መርገፍ ልብሴ፣ ወልቆ አይቀርም፣

አበባዬ ክርስቶስ ነው፣

እርቃኔን የሸፈነው፣

የኔን ከለሜዳ የለበሰው፣

ክብሩን ለኔ ያወረሰው፣

ሞት ሸማዬን የገሰሰው፣

እኔ ማነኝ? ብዬ ስለው፣

አበባህ ረግፎ የማትቀረው፣

አንተ የኔ ነህ፣ ሲለኝ ሰማሁ፣

እኔም ያንተ፣ ቃሌን ሰጠሁ፣

ዛሬም አለሁ፣ ነገም አለሁ፣

አበባዬ አይረግፍም፣ ዛሬም አብባለሁ፣

ነገም በሰማይ አብቤ፣ አብሬው እኖራለሁ።

                                አንተስ ወንድሜ ማነህ? ያለኸው የትነው?፣

                                  የወደቅኸው፣ ከወዴት ነው?፣

                                  ስታበዛ ሩጫ፣ ልብስ ስትሻ፣

                                 የትም የለ፣ ማካካሻ፣

                                     የዚህ ዓለም ማረሳሻ፣

                                ይልቅ ና አበባ ሰው፣

                                መርገፍ ገላ፣ ከሚፈርሰው፣

                               አዲስ አርጎ፣ የሚያድሰው፣

                                 ክርስቶስን ልበሰው!!!!
«ለእውነትም በሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ» ኤፌ 4፣24



Thursday, January 5, 2012

የአባታችሁን ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ!



ደጀሰላምና አንድ አድርገን የተባሉ ብሎጎችን እንጠይቃለን
 

                              ወንጌል ደግሞ«የአባታችሁን ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ» ይላችኋል።ዮሐ ፰፣፵፬

(by dejebirhan)ይህንን ቃል የተናገረው የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ለፈሪሳውያን ካህናት ነበር። ጌታ የመጣው የታሰሩትን እንዲፈቱ፣ በሞት ጥላ ስር ያሉ ወደሕይወት እንዲመጡ ነበርና የመንግሥቱን ወንጌል በቃል እያስተማረ፣ ኃይሉንም በግብር እየገለጠ የመጣ የይቅርታና የምህረት ባለ ቤት መሆኑን አሳይቷል። ከዚህም ውስጥ አንዱ የሆነው ጉዳይ ፈሪሳውያን በዝሙት የተያዘችውን ሴት በክስ ወንበር አቁመዋት እንደሕጋቸው በድንጋይ ተወግራ የምትገደል መሆኑን ቢያውቁም ጌታችንን ሊፈትኑትና የሚከሱበትን ምክንያት ሲሹ ፈታኝ በሆነው መንፈስ እየተነዱ ዘማዊቷን ከፊቱ አቅርበው የሙሴ ሕግ ተወግራ ትገደል ይላል፣ አንተስ በሕግህ ምን ትላለህ? ብለው ሲጠይቁት «መላልሰው በጠየቁት ጊዜ ግን ቀና ብሎ። ከእናንተ ኃጢአት የሌለበት አስቀድሞ በድንጋይ ይውገራት አላቸው» ዮሐ ፰፣፯
ኃጢአት ያልሰራ ማንም ፈሪሳዊ ካህን አልነበረምና ውልቅ ፣ውልቅ እያሉ እሱና ሴትየዋ በመቅረታቸው ፣ ከሳሾችሽ ወዴት አሉ? ሲላት «አንድም» ብላ መለሰች፣ እሱም «ሂጂ፣ ከአሁን ጀምሮ ኃጢአት ደግመሽ አትስሪ» ብሎ በፈውስና በሰላም እንዳሰናበታት እናነባለን።
ጌታ ብርሃን በመሆኑ በጨለማ ላሉ ሊያበራ እንጂ በአንድም ስንኳ ሊፈርድ እንዳልመጣ፣ የሚፈርድበት በልጁ ባላመኑ ሁሉ ላይ አብ መሆኑን፣ ኢየሱስ ቢፈርድም እንኳን ፍርዱ እውነት እንጂ በዘማዊቷ ላይ ህግ ጠቅሰው ለመፍረድ እንደሚሹ ፈሪሳውያን እንዳይደለ፣ ለራሱ የሚመሰክር አባቱ መሆኑንና ራሱም ቢመሰክር ምስክሩ እውነት መሆኑን የሚገልጸው የወንጌል ቃል በሰፊው ተጽፎልን እናገኛለን።
ስለራስህ ራስህ እንዴት ትመሰክራለህ? እውነት አርነት ያወጣኋችል እንዴት ትለናለህ? አንተ አባቴ ብትል እኛስ አብርሃምን የሚያክል አባት አለን ብለው ሲሞግቱ በየዘመናቱ እንደተነሱት ፈሪሳውያን በዘመናችንም በተነገረው ዘላለማዊ ቃል ትንቢት ሆኖ የሚመሳሰሉበትን አንድነት  እንረዳለን። ይኸውም፣
1/ ስለኢየሱስ የሚመሰክረው አብ ነው። ራሱ ቢመሰክርም ምስክሩ እውነት ነው። ፈሪሳውያኑ ራሳቸው ህግ ጠቃሽ፣ ራሳቸው ፈራጅ፣ ራሳቸው ፈታኝ ሆነው ከሚታዩ በስተቀር አንድም የእውነት ምስክር የሌላቸው የኃጢአት ባሪያዎች ናቸው። ዮሐ ፰፣፴፬
2/ኢየሱስ በኃጢአት ላሉ መፈታትንና በሞት ጥላ ስር ላሉ መዳንን ሊሰጥ መጥቷል። ዘማዊቷን «ሂጂ፣ ደግመሽ ኃጢአት አትስሪ »ሲላትና በነጻ ከእስራት ሲያወጣት የያኔው ፈሪሳውያንም ይሁኑ የዘመኑ፣ በጨለማ የኃጢአት ዓለም ሳሉ አንድ ዘማዊ፣ ወይም በስጋ ድካም የሚሰራውን ብዙ ብዙ ኃጢአት እየጻፉ የሚከሱ፣ በድንጋይ ወግረው ለመግደል አደባባይ የሚቆሙ ናቸው። ምክንያቱም እነሱ «እናንተ ከአባታችሁ ከዲያብሎስ ናችሁ የአባታችሁንም ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ። እርሱ ከመጀመሪያ ነፍሰ ገዳይ ነበረ፤ እውነትም በእርሱ ስለ ሌለ በእውነት አልቆመም። ሐሰትን ሲናገር ከራሱ ይናገራል፥ ሐሰተኛ የሐሰትም አባት ነውና» ዮሐ፰፣፵፬ በማለት ማንነታቸውን ገልጿል። ይባስ ብለውም ራሳቸው የሰይጣንን ስራ እየሰሩ ሳለ በተቃራኒው የራሳቸውን ግብር ለኢየሱስ ሰጥተው «አንተ ሳምራዊ እንደሆንክና ጋኔን እንዳለብህ እናያለን» ሲሉ ሰድበውታል። በእነሱ ዘንድ ሳምራዊ የሆነ ሰው ሁሉ ጋኔን አለበት፣ ከእነሱ ውጪ የተለየ ሃሳብም ያለው ጋኔን የያዘው ነው ማለት ነው። ዛሬም የዘር ውርስ ፈሪሳዊነትን የተረከቡት የሚጠሉትን አንተ ርኩስ ሳምራዊ ብለው ጎራ ይለዩበታል፣ ያለ የሌለ ኃይላቸውን ይዘው ይዘምቱበታል።
ከዚህ በላይ ያየነው የእግዚአብሔር ምርጦች ነን፣ የአብርሃም ልጆች ነን፣ የሙሴን ሕግ የምንጠብቅ ጥንቁቆች ነን እያሉ ነገር ግን እገሌ ተሃድሶ፣ እገሌ ሳምራዊ፣ እገሌ ሰዱቃዊ፣ እገሌ ደግሞ ኦርቶዶክሳዊ ነው በማለት እራሳቸው መርምረው፣ እራሳቸው መጽሐፍ ገልጠው፣ እራሳቸው በፍርድ ወንበር ተቀምጠው ከፈረዱ በኋላ አንደኛውን ወገን በድንጋይ ወግረው ለመግደል፣ የራሳችን የሚሉትን ወገን ደግሞ ከፍ ከፍ ሲያደርጉ ይታያሉ።
ያዕቆብ ፬፣፲፬«ሕግን የሚሰጥና የሚፈርድ አንድ ነው፤ እርሱም ሊያድን ሊያጠፋም የሚችል ነው፤ በሌላው ግን የምትፈርድ አንተ ማን ነህ? »የሚለው ቃል እነርሱ ዘንድ አይሰራም።
ዛሬም በዚህ ዘመን ክርስቶስ የሞተለትን አንድ ደካማ ወይም ኃጢአት ያሸነፈውን ወይም እነሱ ላቆሙት ህግ አልገዛም ያለውን ሰው ክስ መስርተውበት በሕጋቸው ወግረው ለመግደል፣ ራሳቸው ለኃጢአት ባሪያ ሆነው ሳሉ፣ ሌላውን ጋኔን አለብህ የሚሉ፣ የአብርሃምን ስራ ሳይሰሩ አብርሃም አባት አለን የሚሉ፣ የአባታቸውን የዲያብሎስን ስራ እየፈጸሙ በክስ አደባባይ የሚያቆሙ፣ ስም የሚያጠፉ፣ የሚደበድቡ፣ የሚወነጅሉ፣ የሀሰት አባት ልጆች መሆናቸውን የሚመሰክሩ ፈሪሳውያን በዚህ ዘመንም ሞልተዋል። ከእነዚህም ውስጥ ግንባር ቀደሞቹ ማኅበረ ቅዱሳን፣ እንደዚሁም ዓይንና ጆሮ ሆነውለት የሚሰሩ ደጀሰላምና አንድ አድርገን የተባሉ በስም ስለሰላምና አንድ መሆን የሚመስሉ፣ በግብር ግን ሰላምና አንድነት እንዳይመጣ ሌሊትና ቀን የሚደክሙት ተጠቃሾች ናቸው። ይህም በማስረጃ ይረጋገጣል።ውድ አንባቢያን አስተዋይ ልቦና ኖሮን እንደእግዚአብሔር ቃል እውነቱን በማወቅ ለወንጌሉ ምስክር ልንሆን እንደሚገባን በአጽንዖት አሳስባለሁ!!
ከታች ያለውን አስረጂዎች ይመልከቱ።