Monday, October 31, 2011

እውነቱን ብንናገር ምን ይለናል?


በዚህች ምድር ላይ ከተስፋፋውና በሰዎች ልቡና ላይ ከተማውን ከመሠረተው አስፈሪ ኃጢአት መካከል እውነትን ለመናገር የሚችል ሰው እየጠፋ መምጣቱ ቀዳሚውን ይዟል። ዓይኑ ያየውን፤ ጆሮው የሰማውን ሽምጥጥ አድርጎ በመካድ ልቡ ያመነጨውን እውነት አድርጎ ማውራትና ማስወራት፤ ይህንንም እንደእውነተኛ ምስክርነት መቁጠር ባህል እየሆነ መጥቷል። ሰዎች ከሥልጣን ኮርቻ ለመፈናጠጥም ሆነ ከሥልጣን ኮርቻ አስፈንጥሮ ለመጣል እውነቱን በሃሰት ቀይሮ እንደዘመናዊ የውጊያ ስልት መሳሪያ አድርጎ ሲጠቀምበትም መታየቱ የአደባባይ ምስጢር ነው። የሀሰት ምስክር ቀርቦበት ሞት የተፈረደበትን፤ ከርቸሌ የወረደውን፤ የተደበደበውን፤ የተንገላታውን፤ መልካም ስሙ የጎደፈውን፤ከማኅበራዊ ኑሮ የተገለለውን፤ ከማእረግ፤ ከሽልማት የታገደውን፤ ረዳት አጥቶ አልቅሶ የቀረውን ሰው ቤቱ ይቁጠረው! በማለት ብቻ ምንም እንዳልተፈጠረ የራሳችንም ሆነ የአካባቢያችንን ሁኔታ ላለመልከት የኅሊናችንን በር መዝጋት እንዴት ይቻለናል? ይልቅስ ለመናገር እንድፈር።
በዚህች ምድር ላይ የሀሰት መንገስ ጉዳይ በሥጋውያን ሰዎች ዘንድ አሳዛኝ መሆኑ ባይካድም አስተሳሰባቸው በሥጋዊ ደማዊ ኅሊና ላይ የሚመሠረት በመሆኑ ሀሰትን እንደመሳሪያ መጠቀማቸው ላይደንቅ ይችላል። አሳፋሪውና አሸማቃቂው ነገር እግዚአብሔርን እናውቃለን፤ የጽድቅ ልጆች ነን በማለት ዘወትር ስለቃሉ በመናገር ላይ ያለነው የእምነት ሰዎች ዘንድ እውነትን በሀሰት ተክተን እንደዘወትር ጸሎት በልባችን ላይ ጽፈን መያዛችንና ጠቃሚ መስሎ በታየን ጊዜና ቦታ ለዓላማችን ማስፈጸሚያ አገልግሎት ላይ ማዋላችን ነው። የሚዋሹ የሃይማኖት ሰዎች ብዙ ጊዜ እውነትን እውነት በምትመስልና ወደእውነት በተጠጋጋች ውበት የሚፈጽሟት ስለሆነ የዋሹ መስሎ አይሰማቸውም ወይም ውሸት መስሎ በተሰማቸው ጊዜ የኅሊናቸውን ቆሻሻ ለማጠብ ትንሽ ናት በምትል ምላሽ ውስጣቸውን አረጋግተው ከመንፈሳዊ ሰውነታቸው ምንም እንዳልጎደለ ራሳቸውን በራሳቸው አሳምነው ያንኑ መደበኛ ውሸታቸውን በተለመደው ጥበብ ይቀጥላሉ።
አንዳንዶቹም መዋሸታቸውን ቢያውቁም ምንም አዲስ ነገር እንዳልተፈጠረና ነባራዊ ክስተት አድርገው በመቁጠር ባገኙት ቦታ ሁሉ የአዞ እንባ እያነቡ፤ ለሃይማኖታቸው የሚውል እስከሆነ ድረስ ይህንኑ በዘመናዊ ውሸት አንዳንዴም ባስ ሲል ዘመነኞቹ «ቀደዳ »የሚሉትን ዓይነት ውሸት የዕለት ሕይወታቸው አድርገው ይዘውት ይታያሉ። ለምሳሌ«ኬንያ ውስጥ አንድ ግለሰብ ባንድ ጊዜ አንድ በርሜል ውሃ ጭልጥ አደረገ የሚልና ጃፓን ከምድር እስከሰማይ የሚደርስ እስክሪብቶ ገበያ ላይ አዋለች» የሚል የውሸትና የቀደዳ ንጽጽሮች ናቸው። እንደዚሁ ሁሉ የሃይማኖት ሰዎች የሚባሉት ይህንኑ የንጽጽር ተግባር ዘወትር ሲፈጽሙት ይታያሉ። ግን ሰዎች እውነትን እንዳይናገሩና ውሸትን ሥራቸው እንዲያደርጉ ያስገደደ ማነው?
ሙሉውን ጽሁፍ ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ

Saturday, October 29, 2011

«ደመና ተበትኖ እንደሚጠፋ እንዲሁ ሲኦል የሚወርድ ዳግመኛ አይወጣም»ኢዮ7፤9



የትኛውም ሃይማኖት በንድፈ ሃሳብ ደረጃ (theoretically) ከሚያመልከው አምላክ ሕግና ትእዛዝ ከወጣ ቁጣና ቅጣት እንደሚጠብቀው የወል የእምነት ስምምነት አለ። ይህንኑ ቅጣት አስቀድሞ ለመከላከል በሕይወታቸው ሳሉ ያደርጉ ዘንድ የሰጣቸውን መመሪያ በሚችሉት አቅም ሁሉ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ ተግባራዊ ለማድረግ ደፋ ቀና ማለታቸውም አይቀሬ ይሆናል። እንደዚያም ሆኖ ከሞተ በኋላ መልካሙ ሥራው መልካም ዋጋው ሆኖ ስለመከፈሉ ወይም ቁጣን ስለመቀበሉ ማረጋገጥ አይችሉምና ከአጠገባቸው ለተለየው ሟች በመሪር ልቅሶና በልዩ ልዩ ዓይነት የሥርዓት አቀባበር ሰውዬውን በመንከባከብ እንዲሁም በማሰማመር የልባቸውን ስሜት በጥሩ መንፈስ ለመሙላት ይጥራሉ። ምግብና መጠጥ፤ ማብሰያ ቁሳቁስና አልባሳትን ጭምር እዚያ በጉድጓዱ ከተማ እንዳይቸገር አብረው በመቅበር የችግሩ ልባዊ ተካፋዮች ለመሆን ሁሉን ያደርጉለታል። ጉድጓዱን ጥልቅ በማድረግ፤ ወደ ጎን ልዩ የኪስ ጉድጓድ በማዘጋጀት፤ የሬሳውን የማረፊያ አቅጣጫ ወደምሥራቅ፣ ወደምዕራብ ወይም በቁመት በመቅበርም ዘላለማዊ እረፍት ያገኝ ዘንድም ይደክሙለታል። አንዳንዶችም ሬሳውን ዛፍ ላይ በመስቀል ወይም በእሳት በማቃጠል ከአምላኩ እንዲታረቅ ይጥሩለታል። ይህንና ይህንን የመሳሰለውን ሁሉ ማድረጋቸው ሰውየው ዘላለማዊ እረፍትን እንዲያገኝ ከሚያመለከው አምላክ እንዲታረቅና ማድረግ ያለባቸውን ባለማድረጋቸው የሟች ነፍስ እንዳትከሳቸው ከመፍራት የተነሳ ነውጽሁፉን ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ

Thursday, October 27, 2011

ማኅበረ ቅዱሳን ....




ይህ ማኅበረ ቅዱሳን የሚባለው ድርጅት ከብዙዎች ጋር እየተላተመ ነው። ይህንን መላተም ሚዲያዎች ሁሉ እያራገቡት ይገኛሉ። ነገሩ ምን ይሆን? እንዲያው ባጋጣሚ እየሆነ ያለ አይመስልም። «ከመምህሩ ደቀመዝሙሩ» እንዲሉ የማይገባበትና ቤተክርስቲያኗን ከጥቃት ለመከላከል በዚህ ዘመን ከሰማይ የወረድኩ እኔ ነኝ እያለ ነው ብለው ያሙታል። ጳጳሳቱ ተኝተዋል፤ ሰባክያኑም ጰንጥጠዋል፤ ተሃዳስያኑም በርክተዋል እያለም ይናገራል ሲሉ ብዙዎቹ ያወሩበታል። ጳጳሳቱ ከተኙ መንፈስ ቅዱስ እየመራቸው አይደለም ማለት ይሆን? ሰባክያኑ ከጰንጤቆስጤ ጎራ ከተቀላቀሉ እሱ ከየትኛው መንፈስ ጋር መሆኑ ነው? መታደስን የሕይወታቸው መመሪያ የሚደርጉ ከበዙ ታዲያ እሱ(ማኅበረ ቅዱሳን) ከምኑ ላይ ነው የቆመው? ለማንኛውም እንዲወገዙና እንዲረገሙ የጠየቀበትን አቤቱታ ለማወቅ እስኪ ይህንን ጽሑፍ ያንብቡለት።
(ጽሁፉን ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ)

Tuesday, October 18, 2011

የሕይወት ውሃ የት ይገኛል?



በዚህች ሰማርያ በሚባል ከተማ የምትኖር አንዲት ሴት ነበረች። በጥቂቱ በተገለጠው ታሪኳ ፭ ባሎች ነበሯት፤ ስድስተኛውም አብሯት ይኖራል። የምትኖረው በሲካር ከተማ ነው። ሲካርና ሴኬም ጎረቤታሞች ናቸውና የአምልኰ ስግደት የሚፈጽሙበት ገሪዛን የሚባል ተራራ በቅርቧ ይገኛል። ይህ ተራራ የበረከት ተራራ እንደሆነ ተነግሮ ስለነበረ ይኸው በረከት ከእርሱ እንደሚወርድ ከማሰብ ሰማርያውኑ ይሰግዱበታል። በዘዳግም ፲፩፤ ፳፱ ላይ እንዲህ የሚል ተጽፎ ይገኛልና። «....በረከቱን በገሪዛን ተራራ፤ መርገሙንም በጌባል ተራራ ታኖራለህ የሚል ቃል ስላለ በረከት ሲሹ ገሪዛን፤ መርገም ለማውረድ ጌባል ላይ ሲጸልዩ ኖረዋል። ኢዮአታምም በገሪዛን ተራራ ላይ ወጥቶ «የሴኬም ሰዎች ሆይ እግዚአብሔር እንዲሰማችሁ ስሙኝ» ሲል የተናገረውንም ይዘው እግዚአብሔር እንዲሰማቸው እነርሱም እዚሁ ተራራ ላይ ወደእግዚአብሔር ሲጮሁ ዘመናትን አልፈዋል።።( መሳ ፱፤፯) ይህች ውሃ ልትቀዳ ወደያዕቆብ የጉድጓድ ውሃ የወረደችው ሰማርያዊት ሴትም «አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰገዱ» ስትል ምስክርነቷን ሰጥታለች። አሁን እዚያ ለስግደት አልወረደችም፤ ይልቁንም ከአባቶቻቸው የውሃ ጉድጓድ አንዱ በሆነው ከያዕቆብ ጉድጓድ ውሃ ልትቀዳ ባዶ እንስራዋን ይዛ ነው የተጓዘችው። እዚያ የውሃ ጉድጓድ አጠገብ ደግሞ ከቀኑ ስድስት ሰዓት አካባቢ አንድ የደከመው ሰው ለእረፍት ተቀምጧል።(ዮሐ፬፤፮) ውሃ ሊቀዳ አይደለም። ስራውንም ጨርሶ እረፍት ይሻ ዘንድ የተቀመጠ እንዳልነበር እረፍት የሌለው ሥራው ማረጋገጫችን ነው። ይልቁንም ለተጠሙ የሕይወት ውሃ ቃሉን እያጠጣ እርካታንና እረፍትን ማግኘት ላይችሉ በገሪዛን ተራራና በጌባል ላይ ሲንከራተቱ ለኖሩት እርካታን ሊሰጣቸው እንጂ! ዛሬም ውሃ እየተጠሙ የሚፈልጉ፤ ጠጥተው ያልረኩ፤ በየጓሮአቸው የሚቆፍሩ፤ ኩሬውን ለማጣራት የሚባክኑ፤ ብዙ ደረቅ ወንዝ የተሻገሩ ሰዎች አሉ። የሕይወት ውሃ የት እንዳለ ቢሰሙም እንዴት እንደሚገኝ፤ አግኝተውትም እንዴት እንደሚጠጡት የማያውቁም ቁጥራቸው የትየለሌ ነው። አስፈሪው ነገር መፈለጋቸው ሳይሆን በብዙ ፍለጋ ሲባክኑ፤ በአይናቸው ሥር ያለውን የሕይወት ውሃ ተሰውሮባቸው ሳያገኙትና ጠጥተው ሳይረኩበት ሞት ባህረ ኤርትራ እንዳያሰጥማቸው ነው። የእርካታው ውኃ ከሰማይ መጥቶ ሳይጠጡትና ሳይረኩበት ሞት ማዕበል የኑሮ መርከባቸውን ሰባብሮ እስወዲያኛው ይዟቸው እንዳይሄድ ነው የሚያስጨንቀው። እስኪ ከዚህ ዓይነቱ አስፈሪ ጥማትና የሕይወት ውሃን ከማጣት ችግር የተላቀቀችውን የአንዲት ሰማርያዊት ሴት ታሪክ እንመልከትና እንደእሷው የሕይወት ወሃ ፍለጋ አቅጣጫችንን እናስተካክል።
(ሙሉውን ጽሑፍ ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ)

Thursday, October 13, 2011

ምን እናድርግ?








የብዙዎቻችን ምርጫ አንድ ዓይነት አይደለም። እንደየመልካችን ይለያያል። በሥጋዊ አስተሳሰብ ልዩነት ውበት ነው ሊባል ይችላል። ይሁን እንጂ ሥጋ ያለነፍስ ምውት እንደሆነ ሁሉ ለነፍሳችን የምንሰጠው የልዩነት ውበት ነው አባባል ዋጋ የለሽ ይሆናል። በነፍስ ዘላለማዊነት ውስጥ ልዩነት ውበት ነው የሚባል ታሪክ የለም። በዚህ ምርጫ ላይ ዘላለማዊ ውበትን ለማግኘት የግድ ምርጫችን አንድ ዓይነት ብቻ መሆን አለበት። የምንጊዜም ምርጫችን በሥጋ ዓለም እስካለን በክርስቶስ ላይ ካልተመሠረተ በነፍስ ዘላለማዊነት ላይ ልዩነት ውበት ነው የሚባል ሥጋዊ አባባል ዋጋ የለውም። ፍላጎታችንን የሚከተል ምርጫ የህይወታችን መሠረት ላይሆን ይችላል። እምነታችንን የሚከተለው ምርጫ ግን ለዘላለማዊ ኑሮ ወሳኝ ነው። ስለሆነም ምን እናድርግ?
ማንም ሰው የእግዚአብሔርን የፍቅርና የምህረት እንዲሁም የደህንነትን ጥሪ ከተቀበለ፣ ለመዳንና ኃጢአቱ እንዲሰረይለት የሚከተሉትን እንዲያደርግ መጽሕፍ ቅዱስ ያስተምረናል::

1ኛ ንስሐ መግባት:- "ይህንም በሰሙ ጊዜ ልባቸው ተነካ፣ ጴጥሮስንና ሌሎችንም ሐዋርያት:- ወንድሞች ሆይ፣ ምን እናድርግ? አሉአቸው:: ጴጥሮስም:- ንስሐ ግቡ...አላቸው::" ሐዋ 2፣37-38

"እንግዲህ እግዚአብሔር ያለማወቅን ወራት አሳልፎ፣ አሁን በየቦታቸው ንስሐ ይገቡ ዘንድ ሰውን ሁሉ ያዛል..." ሐዋ 17፣30

"ኃጢአታቸሁ ይደመሰስ ዘንድ ንስሐ ግቡ ተመለሱም::" ሐዋ 3፣20


ንስሐ መግባት ማለት በመጀመሪያ ኃጢአተኝነታችንና ፍርድ እንደሚጠብቀን አውቀን፣ ከእግዚአብሔር ዘንድ ኃጢአታችን ሁሉ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም እንዲታጠብ መለመንና ከአሁን ጀምሮም በአዲስ ሕይወት እንጂ በድሮ በአጸያፊና ከእግዚአብሔር በተለየ ኑሮ ላለመኖር መቁረጥ ወይም መወሰን ነው:: ከእግዚአብሔር ጋር ታርቀን አዲስ ሕይወትን ለመጀመር የእኛ ውሳኔ አስፈላጊ ነው::

2ኛ በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን:- ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነና ለሰው ልጆችም ብቸኛ የመዳን መንገድ እንደሆነ፣ ለኃጢአታችንም ሲል በመስቀል ላይ ደሙን እንዳፈሰሰና እንደ ሞተ እንዲሁም በሶስተኛው ቀን እግዚአብሔር ከሙታን እንዳስነሣውና በቀኙ እንዳስቀመጠው ከልብ ማመን:: በዚህ ምድር ላይ ቢሆን ወይም ከሞት በኋላ የነፍሳችን ጌታና ጠባቂ ኢየሱስ ብቻ እንደሆነ፣ እርሱም ከዘላለም ፍርድ ነፍሳችንን ሊያድን የሚችል ብቸኛ አዳኝ እንደሆነ ማመን::


Wednesday, October 12, 2011

ለስዕልና ለምስል ስግደትና በእነርሱ ፊት መጸለይ ይገባል?





ጥቅስ፤
   ኦሪት ዘሌዋውያን 26፥1 እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝና ለእናንተ ጣዖት አታድርጉ፥ የተቀረጸም ምስል ወይም ሐውልት አታቁሙ ትሰግዱለትም ዘንድ በምድራችሁ ላይ የተቀረጸ ድንጋይ አታኑሩ። ኦሪት ዘዳግም 4 15 እግዚአብሔር በኮሬብ በእሳት ውስጥ ሆኖ በተናገራችሁ ጊዜ መልክ ከቶ አላያችሁምና እጅግ ተጠንቀቁ 16 እንዳትረክሱ፥ የተቀረጸውን ምስል የማናቸውንም ነገር ምሳሌ፥ በወንድ ወይም በሴት መልክ የተሠራውን፥ 17 በምድር ላይ ያለውን የእንስሳን ሁሉ ምሳሌ፥ በሰማይም በታች የሚበርረውን የወፍን ሁሉ ምሳሌ፥ 18 በምድርም ላይ የሚሽከረከረውን ሁሉ ምሳሌ፥ ከምድርም በታች በውኃ ውስጥ የሚኖረውን የዓሣን ሁሉ ምሳሌ እንዳታደርጉ፥ 19 ዓይኖችህን ወደ ሰማይ አንሥተህ አምላክህ እግዚአብሔር ከሰማይ ሁሉ በታች ላሉት አሕዛብ ሁሉ የሰጣቸውን ፀሐይንና ጨረቃን ከዋክብትንና የሰማይን ሠራዊት ሁሉ ባየህ ጊዜ፥ ሰግደህላቸው አምልከሃቸውም እንዳትስት ተጠንቀቅ። 

 ጥቅስ፤
   ኦሪት ዘጸአት 20፥4 በላይ በሰማይ ካለው፥ በታችም በምድር ካለው፥ ከምድርም በታች በውኃ ካለው ነገር የማናቸውንም ምሳሌ፥ የተቀረጸውንም ምስል ለአንተ አታድርግ። እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ከግብጽ ካወጣ በኋላ አንዱ የሰጣቸው ትልቁ ትእዛዝ ቢኖር ምንም አይነት ምስል ወይም የተቀረጸ ነገር በፍጹም እንዳያደርጉ ነው። የሰውም ይሁን የእንስሳ ወይም የፀሐይና ጨረቃ ወዘተ ማናቸውንም ምስል ወይም ምሳሌ ማድረግ ክልክል ነው። ስለዚህም አይሁዶች እስከ ዛሬም ድረስ በምኩራባቸው የሰውም ይሁን የሌላ ነገር ስእልና ሃውልት ወዘተ አያደርጉም። ምክንያቱም በቃሉ እጅግ የተከለከለ እና ጣኦትን እንደማምለክ የሚቆጠር ስለሆነ ነው።

Sunday, October 9, 2011

የደም መስዋእት






እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ሊያደርግላቸው ከሚፈልገው ነገሮች ሁሉ ዋናውና ትልቁ ነገር ኃጢአትን ማስወገድ ነው:: ኃጢአት የሰዎች የችግራቸውና የመከራቸው ዋነኛ ሥርና ምክንያት ነውና:: የሕይወትና የበረከት ምንጭ ከሆነው ከአምላካቸው ከእግዚአብሔር ያለያያቸውና ያጣላቸው ዋናው ነገር ኃጢአት ነው:: ኃጢአት በሰዎች ታሪክ ሁሉ የሰው ልጆች የሞትና የመከራ፣ የሃዘንና የለቅሶ ምንጭ ነው:: የሰዎችን ከእግዚአብሔር መራቅ ስለዚህም ደግሞ የሕይወት እርካታ አለማግኘታቸውና የመቅበዝበዛቸው፣ እርስ በርስ ፍቅር የማጣታቸው፣ በመጨረሻም ለዘላለም ፍርድና ስቃይ ለሲኦልም የሚያበቃቸው ዋነኛ ክፉ የሰዎች ጠላት ኃጢአት ነው::            ( የቀረውን ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ)

Wednesday, October 5, 2011

መላእክት የሚወጡበትና የሚወርዱበት የሰማይ መሰላል
















"አሁንም የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል:-


ልባችሁን በመንገዳችሁ ላይ አድርጉ::" ሐጌ 1፣5


የእግዚአብሔር ቃል ልባችንን በመንገዳችን ላይ እንድናደርግ ይመክረናል:: በምን አይነት መንገድ ላይ እየተጓዝን እንዳለን ልንመረምር ይገባናል:: ከሁሉም በላይ መንገዱ ወዴት እንደሚወስድና እንደሚያመራ በትክክል ማወቅ አለብን:: በምድር ላይ ብዙ መንገዶች አሉ፣ ሁሉም ግን ያሰብነው ስፍራ አያደርሱንም:: ስለዚህ ትክክለኛውን መንገድ መምረጥና መጓዝ ከዚያም ልባችንን በመንገዳችን ላይ አድርገን መመርመር ይገባናል::

ዛሬ ብዙ ሰዎች በመኪናቸው ወዴት እንደሚሄዱ ያውቃሉ፣ የተሳፈሩትም አውቶቡስ የት እንደሚያደርሳቸው ጠንቅቀው ያውቃሉ፣ እንዲያውም አንዳንድ ሰዎች እጅግ የሚያስገርም የመንገድ እውቀት አላቸው:: ነገር ግን ብዙዎቹ የሕይወታቸው ጉዞ ወዴት እንደሚያደርሳቸው አያውቁም:: የመረጡት ሕይወት መጨረሻው ምን እንደሆነ እርግጠኞች አይደሉም:: የተሳሳተ መንገድ ላይ ይሁኑ አይሁኑ የሕይወታቸውን መንገድ የማይመረምሩ ጥቂቶች አይደሉም::

ወገኔ ሆይ፣ ወዴት እየሄድክ ነው? ይህ አኗኗርህ ወዴት ያደርስሃል? ትክክል ነው ብለህ የምትከተለው ሕይወትህና ሃይማኖትህ መጨረሻው ምንድነው? የተሳፈርክበት የሕይወትህ አውቶቡስ ወዴት እንደሚወስድህ በእርግጥ ታውቅ ይሆን? ወይስ ወዴት እየሄድክ እንደሆነ ቆም ብለህ አትመረምር ይሆን? ምናልባትም የትኛውንም መንገድ ብመርጥ ግድ የለም ትል ይሆናል:: የእግዚአብሔር ቃል ግን እንዲህ ሲል ይመክረናል:-
"ልባችሁን በመንገዳችሁ ላይ አድርጉ"!

Tuesday, October 4, 2011

መጥተህ እይ


አንድ ጊዜ ኢየሱስን ሊሰሙትና ከእርሱ ሊማሩ፣ ከበሽታቸውና ካለባቸው ስቃይ ሁሉ ነፃ ሊወጡ ወደ እርሱ ብዙ ሕዝብ ይቀርቡ ነበር:: ከእነዚህም ውስጥ የታወቁ ኃጢአተኞች ይገኙበት ነበር:: ጌታም እነዚህን ሲቀበላቸው፣ ከእነርሱም ጋር ሲበላና ሲጠጣ የዚያን ዘመን የሃይማኖት ሰዎች አይተው እርስ በርሳቸው አንገራገሩ "ይህስ ኃጢአተኞችን ይቀበላል፣ ከእነርሱም ጋር ይበላል" አሉ:: ሉቃ 15፣1-2 እስከ ዛሬ ድረስም የተለያዩ የሃይማኖት ተከታዮችን ወይም ሃይማኖተኞችን ግራ የሚያጋባቸውና የሚገርማቸው አንዱ ነገር ይሄ ነው:: እንዴት ታላቅ ነብይ በኃጢአተኞች መካከል ይቀመጣል? እንዴት የእግዚአብሔር ልጅ በተናቁ መካከል ያስተምራል? እንዴት ጻድቅ የሆነው ኢየሱስ ከኃጢአተኞች ጋር ይበላል? እንዴትስ ከእነርሱ ጋር ይጠጣል? ይሄ ነው እንግዲህ በመጽሐፍ ቅዱስ የተገለጸውን አምላክ ከሌሎች አማልክቶች የሚለየው:: ለሰው አዕምሮ ከባድ የሆነውና ሊቀበለው የሚያስቸግረው፣ ዮሐንስም ደግሞ ሊገልጽልን የሚፈልገው ትልቅ ቁም ነገር ይህ ነው::
"ቃልም ሥጋ ሆነ ጸጋንና እውነትንም ተሞልቶ በእኛ አደረ፣ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነውን ክብሩን
 አየን::" ዮሐ 1፣14

እጅግ የሚገርመው ነገር ቃል ከሁሉ በፊት ከእግዚአብሔር ጋር መኖሩና ሁሉ ነገር በእርሱ መፈጠሩ ብቻ አይደለም:: በጣም የሚያስደንቀው፣ ለብዙ የሃይማኖት ሰዎችም ግራ የሚያጋባውና ለመረዳት የሚከብደው፣ ይህ ራሱ አምላክ የሆነው ቃል (ኢየሱስ ክርስቶስ) ሥጋ መሆኑ ነው:: አምላክ እንዴት ሰው ይሆናል? እንዴት ሥጋ ይሆናል? እንዴትስ በኃጢአተኞች መካከል ይመላለሳል? የእግዚአብሔርን ፍቅር የተለየና ከመታወቅም በላይ የሚያደርገው አንዱ ነገር እንግዲህ ይህ ነው::



«ሲያያት በሕይወት ይኖራል»








ወገኔ ሆይ፣ አንድ ጥያቄ ልጠይቅህ:- ታምመህ ታውቃለህ? በእርግጥ የበሽታን ምንነት በሕይወትህ ቀምሰህ ይሆን? መልስህ አዎን እንደሚሆን እገምታለሁ:: በሽታን የማታውቅ ከሆንክ ደግሞ እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን:: በሽታ መልካም አይደለምና:: የሰውን ሙሉ ጤንነት እያናጋ፣ ሰዎች እንደሚገባው እንዳይኖሩና እንዳይሠሩ የሚያደርግ ትልቅ እንቅፋት ነው:: ብርታትን ወደ ድካም፣ ውፍረትን ወደ ክሳት፣ ደስታንም ወደ ሃዘን የሚለውጥ በመጨረሻም ለሞት የሚያበቃ ክፉ የሰዎች ጠላት ነውና::

በአሁኑ ዘመን ግን ለብዙ በሽታዎች መድኃኒት ስላለ እግዚአብሔር ይመስገን:: ያለ መድኃኒት እንዴት እንሆን ነበር? ያለ መድኃኒትና ያለ እርዳታ እናቶች የልጆቻቸውን በሽታና ስቃይ እየተመለከቱ እንዴት ይሆኑ ነበር? የምንወዳቸው ወገኖቻችን በትንሹም በትልቁም በሽታ ሲሰቃዩና ሲረግፉ ማየት እንዴት ያሰቅቃል:: ዛሬም መድኃኒትና ሕክምና በሌለባቸው ቦታዎች፣ ሕጻናት ገና በለጋ እድሜያቸው በበሽታ ይቀጫሉ:: ሕክምናና መድኃኒት ባለማግኘት ሕይወታቸው የሚያልፈው የወጣቶችና የጎልማሶች ቁጥር ጥቂት አይደለም::


ሕክምና ባለበት አካባቢ ግን የሰዎች እድሜ የረዘመና ሽማግሌዎችና አዛውንት የበዙበት ይሆናል:: ሕጻናት በጤንነት ሲጫወቱና ሲቦርቁ ማየት እንዴት ደስ ይላል:: ሰዎች ያለ ስቃይ ሲወጡና ሲገቡ በደስታም ሲመላለሱ ማየት እንዴት መልካም ነገር ነው::