Tuesday, October 18, 2011

የሕይወት ውሃ የት ይገኛል?



በዚህች ሰማርያ በሚባል ከተማ የምትኖር አንዲት ሴት ነበረች። በጥቂቱ በተገለጠው ታሪኳ ፭ ባሎች ነበሯት፤ ስድስተኛውም አብሯት ይኖራል። የምትኖረው በሲካር ከተማ ነው። ሲካርና ሴኬም ጎረቤታሞች ናቸውና የአምልኰ ስግደት የሚፈጽሙበት ገሪዛን የሚባል ተራራ በቅርቧ ይገኛል። ይህ ተራራ የበረከት ተራራ እንደሆነ ተነግሮ ስለነበረ ይኸው በረከት ከእርሱ እንደሚወርድ ከማሰብ ሰማርያውኑ ይሰግዱበታል። በዘዳግም ፲፩፤ ፳፱ ላይ እንዲህ የሚል ተጽፎ ይገኛልና። «....በረከቱን በገሪዛን ተራራ፤ መርገሙንም በጌባል ተራራ ታኖራለህ የሚል ቃል ስላለ በረከት ሲሹ ገሪዛን፤ መርገም ለማውረድ ጌባል ላይ ሲጸልዩ ኖረዋል። ኢዮአታምም በገሪዛን ተራራ ላይ ወጥቶ «የሴኬም ሰዎች ሆይ እግዚአብሔር እንዲሰማችሁ ስሙኝ» ሲል የተናገረውንም ይዘው እግዚአብሔር እንዲሰማቸው እነርሱም እዚሁ ተራራ ላይ ወደእግዚአብሔር ሲጮሁ ዘመናትን አልፈዋል።።( መሳ ፱፤፯) ይህች ውሃ ልትቀዳ ወደያዕቆብ የጉድጓድ ውሃ የወረደችው ሰማርያዊት ሴትም «አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰገዱ» ስትል ምስክርነቷን ሰጥታለች። አሁን እዚያ ለስግደት አልወረደችም፤ ይልቁንም ከአባቶቻቸው የውሃ ጉድጓድ አንዱ በሆነው ከያዕቆብ ጉድጓድ ውሃ ልትቀዳ ባዶ እንስራዋን ይዛ ነው የተጓዘችው። እዚያ የውሃ ጉድጓድ አጠገብ ደግሞ ከቀኑ ስድስት ሰዓት አካባቢ አንድ የደከመው ሰው ለእረፍት ተቀምጧል።(ዮሐ፬፤፮) ውሃ ሊቀዳ አይደለም። ስራውንም ጨርሶ እረፍት ይሻ ዘንድ የተቀመጠ እንዳልነበር እረፍት የሌለው ሥራው ማረጋገጫችን ነው። ይልቁንም ለተጠሙ የሕይወት ውሃ ቃሉን እያጠጣ እርካታንና እረፍትን ማግኘት ላይችሉ በገሪዛን ተራራና በጌባል ላይ ሲንከራተቱ ለኖሩት እርካታን ሊሰጣቸው እንጂ! ዛሬም ውሃ እየተጠሙ የሚፈልጉ፤ ጠጥተው ያልረኩ፤ በየጓሮአቸው የሚቆፍሩ፤ ኩሬውን ለማጣራት የሚባክኑ፤ ብዙ ደረቅ ወንዝ የተሻገሩ ሰዎች አሉ። የሕይወት ውሃ የት እንዳለ ቢሰሙም እንዴት እንደሚገኝ፤ አግኝተውትም እንዴት እንደሚጠጡት የማያውቁም ቁጥራቸው የትየለሌ ነው። አስፈሪው ነገር መፈለጋቸው ሳይሆን በብዙ ፍለጋ ሲባክኑ፤ በአይናቸው ሥር ያለውን የሕይወት ውሃ ተሰውሮባቸው ሳያገኙትና ጠጥተው ሳይረኩበት ሞት ባህረ ኤርትራ እንዳያሰጥማቸው ነው። የእርካታው ውኃ ከሰማይ መጥቶ ሳይጠጡትና ሳይረኩበት ሞት ማዕበል የኑሮ መርከባቸውን ሰባብሮ እስወዲያኛው ይዟቸው እንዳይሄድ ነው የሚያስጨንቀው። እስኪ ከዚህ ዓይነቱ አስፈሪ ጥማትና የሕይወት ውሃን ከማጣት ችግር የተላቀቀችውን የአንዲት ሰማርያዊት ሴት ታሪክ እንመልከትና እንደእሷው የሕይወት ወሃ ፍለጋ አቅጣጫችንን እናስተካክል።
(ሙሉውን ጽሑፍ ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ)