Thursday, May 29, 2014

በአቡነ ጳውሎስ ላይ ሲፈጸም የቆየው የሊቃነ ጳጳሳቱ አድማና የማኅበረ ቅዱሳን ጣልቃ ገብነት በአቡነ ማትያስ ላይም ቀጥሏል!

ከሊቃነ ጳጳሳቱ ግማሾቹ የራሳቸውን የጉባዔ ላይ የድምጽ ጡንቻ በማፈርጠም ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ ከሚመስሏቸው ጋር የመቀናጀት ጠባያቸው ከምንኩስና ጀምሮ የተዋረሳቸው እንጂ ድንገት የተከሰተባቸው ዐመል አይደለም። ገሚሶቹ ሊቃነ ጳጳሳት ደግሞ ከዚህ ፈርጣማና  ጠንካራ የቡድን  አቅም መፍጠር ከቻሉት ጋር መለጠፍ የሚፈልጉት አንድም ብቻቸውን መዝለቅ እንደማይችሉ ስለሚያውቁ፤ በሌላ መልኩም ሊመጣ ይችላል ከሚሉት ጥቃት ራሳቸውን ለመከላከል ከመፈለግ ራስን የማዳን ዘዴ የተነሳ ነው። ጥቂቶች ቢሆኑም አንዳንዶቹ ደግሞ ያልሆነ ንትርክና ጭቅጭቅ እንዲነሳ የማይፈልጉ፤ ዝም ብለው በመመልከት ታዛቢ የሚመስሉ በእድሜ የገፉ ሲሆኑ በጣት የሚቆጠሩት ደግሞ ስለቤተክርስቲያን የሚገዳቸው ነገር ግን ድምጻቸው ብዙም የማይሰማላቸው ናቸው።
 የቡድን ኃይል መፍጠር የቻሉት አብዛኛዎቹ ሊቃነ ጳጳሳት የወጣትነት ዐመል ብዙም ያልራቃቸው፤ በቂ ኃብት ማከማቸት የቻሉ፤ ለተሸከሙት ማዕርግ ሳይሆን ለስምና ለዝና የሚጨነቁ በተለይም ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ንክኪ ያላቸው ናቸው። እነዚህኞቹ ለቤተ ክርስቲያን የሚታይ፤ የሚጨበጥ፤ ለትውልድ የሚተላለፍ ቋሚ ቅርስና ሀብት መፍጠር ያልቻሉ ነገር ግን በምላስ የሰለጠኑ፤ እምቢተኝነትና ቡድንተኝነት እውቀት የሚመስላቸው ናቸው። ቤተክርስቲያን መታመስ የጀመረችው እነዚህኞቹ ቅዱስ ወደተባለው ሲኖዶስ የመቀላቀል እድል ካጋጠማቸው በኋላ ነው። ማኅበረ ቅዱሳንም ከሀገር ቤት እስከ ውጪ ሀገር ድረስ በቤተ ክርስቲያኒቱ መልክና ቁመና ስሩን የሰደደው በእነዚህኞቹ ጀርባ ታዝሎና ተንጠላጥሎ ነው።
የቀድሞውን ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እግር ተወርች አስረው አላሰራ ሲሉ የነበሩት እነዚህ ቡድንተኞች ዛሬም አንድ ግንባር ፈጥረው እድሜ ካላስተማራቸው አረጋውኑ መካከል ጥቂቶቹን አሰልፈው ማኅበረ ቅዱሳንን ከጀርባቸው አቁመው ፓትርያርክ ማትያስንም በተመሳሳይ መልኩ አላሰራ፤ አላንቀሳቅስ፤ አላላውስ እያሏቸው ይገኛል። በዚህ መልኩ የት ድረስ መጓዝ እንደሚቻል ለመገመት አይከብድም። ነገር ግን «ህልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደርም» እንዲሉ አበው መላ መፈለግ ፓትርያርክ ማለት «ርእሰ አበው» ማለት እንደመሆኑ መጠን የተሰጠውን ሥልጣን ለቡድንተኞች አስረክቦ የተነገረውን የሚቀበል ተላላኪ ማለት ባለመሆኑ ሥልጣኑ ሙሉዕ መሆኑን ማመን የግድ ይሆናል። ስለዚህ በአድመኝነት፤ ለማኅበሩ ወግነው አላሰራ ለሚሉ ምን መደረግ አለበት?  ነገሮች እየጠሩ፤ የችግሩም ገፈት ከላይ ካልተወገደ በስተቀር ተለባብሶ የትም አይደረስም። ቤተ ክርስቲያንም አትድንም፤ ባለማዕርጎቹም በዘመናቸው ንስሐ አይገቡም። ስለዚህ የማያወላዳ እርምጃና ውሳኔ ያለምንም ማቅማማት መውሰድ የግድ ይላል። ጥቂት ነጥቦችን እናንሳ።
1/ ከአድመኞቹ ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብዙዎቹ ቃል የገቡበትን መሃላ አፍርሰው የቤተ ክርስቲያኒቱ ተጠሪ ነን ካሉ በኋላ ደመወዝተኛ፤ አበልተኛና የጥቅሟ ተከፋይ ሲያበቁ መንፈሳዊነቱን ክደው፤ ሀብት ንብረት አፍርተው ፤ እንደዓለማውያኑ የሚሊዮን ብር ቤቶችን የገነቡ፤ በባንክ ያከማቹ ስለመሆናቸው መረጃና ማስረጃ የሚቀርብባቸው ስለሆነ በሊቀ ጳጳስነት ማዕርግ የእግዚአብሔርን መንግሥት ብቻ ለማገልገል  ብቃት የሚጎድላቸውና «ለሁለት ጌቶች መገዛት አትችሉም» ያለውን የወንጌል ቃል ያፈረሱ ስለሆነ ከያዙት ማዕርግ ተሰናብተው ወደዓለማዊ ሀብታቸው እንዲሄዱ ሊሸኙ ይገባል።
2/ ገሚሶቹ ሊቃነ ጳጳሳት ቃለ መሃላ ከፈጸሙበት «ኩሎ ኀደግነ» ሁሉን ትተን ተከተልንህ ካሉ በኋላ በቀጥታ ያለሰማንያ ጋብቻ በትዳር ወልደው ከብደው የሚኖሩ፤ ገሚሱም በአዲሱ የቤተሰብ ህግ እንደተመለከተው « ትዳር በሚመስል ሁኔታ አብሮ መኖር ራሱ ጋብቻ እንደተፈጸመ ይገመታል» በሚል የህግ መንፈስ መሰረት አግብተው ዓለሙም፤ ሊቀጵጵስናውም ሁሉም ሳይቀርባቸው አጣምረው የያዙ ስለሆነ በእነዚህኞቹ «ጸሊማን አርጋብ»  ላይ በቂ ማስረጃ መቅረብ ስለሚችል በማያወላዳ ውሳኔ ለሌሎች ትምህርት ሊሆን በሚችል መልኩ ለትዳራቸው ታማኝ ሆነው እንዲኖሩ በክብር መሸኘት አለባቸው።
3/ ለዚህ ጥሩ አብነትና ምሳሌ ሊሆን የሚችለው በግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከዚህዓለም በሞት የተለዩት የአቡነ ሺኖዳ አስተዳደር ተጠቃሽ ነው። ሊቃነ ጳጳሳት የራሳቸውን ሀብት ማፍራት አይችሉም። መነኮሳት ከመነኮሱበት ገዳም ውጪ ሌላ ገዳም በፍጹም አይቀበላቸውም። ከገዳሙ ከወጣ ምንኩስናውን እንደተወ ይቆጠራል። በሴት የተጠረጠረ መነኩሴ በቀጥታ ተጠርቶ ይጠየቃል እንጂ እንደኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ተሸፋፍኖ ያሻውን እንዲፈጽም እድል አይሰጠውም። መረጃና ማስረጃ ከቀረበበት ቀሚሱን ከታች አንስቶ፤ እስከ አንገቱ ድረስ መሃል ለመሃል በመቀስ ቀደው መቋቋሚያ ገንዘብ ሰጥተው ሕዝባዊ እንዲሆን ያሰናብቱታል። ይህ ለሌላው ትምህርት፤ ለቤተ ክርስቲያንም ክብር ይሆናል። ነገር ግን በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያለው ነገር በዚህ ዘመን አሳፋሪ ሆኗል። ከሊቃነ ጳጳሳቱ ትዳር የመሰረቱ ሞልተዋል። የመነኮሳት ነጋዴ መሆናቸው ሳይታወቅ ሚሊየነር ሆነዋል። ዝሙትና ስርቆት ቤተ ክርስቲያኒቱን እንደነቀዝ እየበላት ነው። በዚህ መልኩ ከቀጠለች የቤተ ክርስቲያኒቱ ኅልውና አስጊ ነው። እዚህ ላይ ከነጋ ድራስ ገብረሕይወት ባይከዳኝ መጽሐፍ ጥቂት ቃል እንዋስ። «እግዚአብሔር መንግሥታችንን፤ ቤተክርስቲያናችንን ለባዕድ አሳልፎ አይሰጣትም እያለ ሕዝባችን በስንፍና ያለሥራ ይኖራል» እውነትም ብዙ ጊዜ እግዚአብሔር ከጥፋት ተከላከለን፤ ነገር ግን እኛ ለቸርነቱ የተገባውን ሥራ ሠርተን በተግባር አላሳየንም» ብለዋል ነጋድራስ በጽሁፋቸው ከዛሬ ሰማንያ ዓመት በፊት።  ይሁን እንጂ ዛሬም ከስንፍናችን ፈቀቅ አላልንም። እግዚአብሔር ራሱ ይጠብቅ ብለን እኛው ያጠፋናትን ቤተ ክርስቲያን እንደባለእዳ ትተንለታል።
4/ ማኅበረ ቅዱሳን ማነው? የማነው? ምንድነው? ብዙ የሚያጠያይቅ ጉዳይ ነው። የጠራና የማያሻማ መልስ ያስፈልገዋል። ተለባብሶ በበግ ለምድ ተሸሽጎ አይዘለቅም። ስለማኅበረ ቅዱሳን ጥብቅና የሚቆም ማንም ቢኖር የማኅበሩ አባል የመሆን መብቱ የተከበረ ነው። ነገር ግን ሊቀጳጳስ ከሆነ በኋላ ቤተ ክርስቲያን የሰጠችውን የሲኖዶስ አባልነት ሥልጣን ይዞ የማኅበረ ቅዱሳን አባል መሆን አይችልም። መሆን ከፈለገ ጵጵስናውን ማስረከብ አለበት።  አንድ ሚኒስትር የኢህአዴግ ምክርቤት አባልና የሰማያዊ ፓርቲ አባል በአንድ ጊዜ መሆን አይችልም። አንዱን ይተዋል፤ ወደአንዱ ይጠጋል እንጂ። ይህንን ለማስተካከል የፓትርያርኩ ሥልጣን ምሉዕ ነው። እነዚህ በሁለት ልብ ሲኖዶሱን የሚያውኩ ጳጳሳት በህግ አግባብ ካልተወገዱ የሲኖዶስ ሕውከት ማብቂያ አይኖረውም። ስለማኅበረ ቅዱሳን የሚከራከር ሊቀጳጳስ ከሲኖዶስ አባልነቱ ወደታች ወርዶ የተራ ማኅበር ደጋፊ ከሆነ ማዕርጉን ተገፎ  በማኅበር አባልነቱ እንዲቀጥል ከሲኖዶስ ሊባረር ይገባዋል።
5/ ፓትርያርክ ማትያስ ቆምጨጭ ያለና እርምት የሚሰጥ እርምጃ ከመውሰድ ውጪ በእንደዚህ ዓይነት የአድማና የቡድን ጭቅጭቅ እየተሰላቹ የትም አይደርሱም። ሊቀጳጳስ የሚባለው ማዕርግ ሊከበር የሚችለው ራሱ ማዕርጉን የተሸከው ሰው አክብሮ፤ የሚያስከብር ሥራ ሲሰራበት ብቻ ነው። ሹመትማ ይሁዳም ከሐዋርያት አንዱ ነበር። ነገር ግን ጥፋት እንጂ ልማት አልሰራበትምና ሐዋርያ መባሉ ቀርቶ «ሰያጤ እግዚኡ» ከመባል አልዳነም። ስለዚህም ቤተ ክርስቲያንን ከመሸጥ የማይመለሱ እነዚህ አድመኞች ሊቃነ ጳጳሳት ሻጮች ቢባሉ ምንም አያስነውርም። ስም መጥቀስ አያስፈልግም እንጂ እነማን ማናቸው? ምን አደረጉ? ምንሰሩ? በደንብ ይታወቃል።
6/ ቤተ ክርስቲያንን ከውድቀት ለማዳን፤ ማዕርጋት ዋጋና ክብር እንዲኖራቸው ለማድረግ ሲባል ያልተፈለገ ነገር ግን አስገዳጅ እርምጃ እስከመውሰድ የሚዘልቅ ክስተት መፈጠሩ አይቀርም።  ፓትርያርክ ከሆኑ በኋላ ከሚቆጠቁጠው የመንፈሳዊ ኅሊና ቁጭትና ከታሪክ ወቀሳ ለመዳን መስራት የሚገባውን ሁሉ ካልሰሩበት ማዕርጉን ተሸክሞ መቀመጥ በቤተክርስቲያን ውድቀት ላይ መተባበር በመሆኑ ሹመቱን አስረክቦ የራስን ነጻነት ማወጅ የተሻለ ነው።
በአቡነ ጳውሎስ ላይ ሲፈጸም የቆየው የሊቃነጳጳሳቱ አድማና የማኅበሩ ሴራ በአቡነ ማትያስም ላይ የሚቀጥለው  እስከመቼ ነው?
 አቡነ ማትያስ አርፈው የማኅበሩ አባል ሊቀ ጳጳስ ሌላ ፓትርያርክ እስኪሆን ድረስ ይህ ውጊያ አያቆምም።

Thursday, May 22, 2014

ግዝት(ውግዘት)…ኑፋቄ….መናፍቅነት…ግዝት-ዘበከንቱ… እና ወፈ-ገዝት መሆን!


 ( በአማን ነጸረ )
1. ግዝት(ውግዘት)፡ ማለት አንድ ምዕመን(አማኝ) በአፉ ክርስቲያን ነኝ ቢልም በተግባር ከሃይማኖት ወጥቶ ከበጎ ምግባር አድጦ(ተዛንፎ) ሲገኝ ከማኅበረ ምዕመናን እንዲለይ በስልጣነ-ክህነት የሚፈጸም መንፈሳዊ ቅጣት ነው፡፡
2. የውግዘት ዓላማ፡(ሀ)ቤ/ክ እንዳትረክስ፣(ለ)ኑፋቄው ወደ ሌሎች እንዳይዛመት፣(ሐ)ተወጋዡ በንስሐ እንዲመለስ እድል ለመስጠት ነው፡፡
3. የውግዘት ቅድመ-ሁኔታዎች፡(ሀ)ተጠርጣሪው ከሃይማኖት እና/ወይም ከበጎ ምግባር መውጣቱን ማረጋገጥ፣(ለ)ከጥፋቱ/ከክህደቱ እንዲመለስ ደጋግሞ መገሰጽና መምከር፣(ሐ)ተመክሮ ካልተመለሰ በስልጣነ-ክህነት አውግዞ መለየት፣(4)ውግዘቱ እንደጥሰቱ ዓይነት ከማዕረግ ዝቅ ማድረግ ወይም ስመ-ክርስትናን ነጥቆ መለየት ሊሆን ይችላል፡፡ከዚህ በኋላ ድርጊቱ-ኑፋቄ ተወጋዡም-መናፍቅ ይባላሉ፡፡በነገራችን ላይ ምንፍቅና የሚል ቃል በየመጻህፍቱ አላየንም፡፡በግእዙ ኑፋቄ ነው የሚባለው፡፡በአማርኛ መናፍቅነት፡፡
4. ግዝት-ዘበከንቱ እና ወፈ-ገዝት መሆን፡ ከላይ ያሉትን ቅድመ ሁኔታዎች ያላሟላ ግዝት ግዝት-ዘበከንቱ ሲባል ገዛቹም ወፈ-ገዝት ይባላል፡፡ነገር ግን ተጠርጣሪው በግልጽ የተወገዘ ሃይማኖትንና ምግባርን ሲያራምድ ያገኘነው እንደሆነ መናፍቅ ብንለው ፍርድ የለብንም፡፡
5. ከንቱ እና ከንቱ አንድ ወገን ብለን ስለመርገም ዘበከንቱም እንናገር፡ ሀቅ ላይ ያልተመሰረተና የሚረገመውን ሰው ህሊና የመውቀስ አቅም የሌለው ከንቱ እርግማን በመጽሐፈ ምሳሌ 26 ቁ 2 እንደተገለጸው….እንደሚተላለፍ ድንቢጥ፣ወዲያና ወዲህም እንደሚበር ጨረባ እንዲሁም ከንቱ እርግማን በማንም ላይ አይደርስም፡፡ፍትሐ ነገስቱም በአንቀጽ 11 እንዲህ አይነቱን ረጋሚ “ወኩሎ ዘይረግም ይረግም ነፍሶ” ይለዋል::
ምንጭ፡ (1) መርሐጽድቅ ባህለ ሃይማኖት በ1988 ዓ.ም በትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት የታተመ ገጽ 157 እስከ 161 ፣ (2)የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገጽ-237፣ (3) ጥቅሶች፡ ማቴ 18 ቁ 15-18፣2ተሰ 3ቁ14፣ቲቶ 3 ቁ 11፣1ጢሞ 1ቁ 19፣2ጢሞ 2 ቁ 17፣1ቆሮ 5 ቁ 5፣2ቆሮ 2 ቁ 6
መነሻ፡ በ40 ቀን ያገኘነውን ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ባልተሰጠ ስልጣነ-ክህነት ሊነጥቁ የሚሞክሩ ወፈ-ገዝት ወንድሞቻችን!!

Sunday, May 18, 2014

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊ ጳጳሳቱ በኩል የጉባዔ ተግዳሮት እንደሚገጥማቸው ይጠበቃል!





የዘንድሮው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ከመቼውም ጊዜ የተሻለ ምስጢራዊነቱን የጠበቀ እንዲሆን ተሞክሯል። ይህ ማለት ግን ከማኅበረ ቅዱሳን የተሰወረ የአጀንዳ፤ የውይይት ሂደትና የውሳኔ እልባት ነበረ ማለት አይደለም። ምስጢራዊነቱ  የቤት ልጅ ከሆነው ከማኅበረ ቅዱሳን ውጪ ለአብዛኛዎቻችን እንዲጠበቅ ያስፈለገበት ዋና ምክንያት በቅዱስ ፓትርያርኩ በተሰጠ የቅድመ ጉባዔ መመሪያ ቢሆንም በአንጻሩ ማኅበሩና ደጋፊ ጳጳሳቱም ምስጢራዊነቱ ቢጠበቅ የኅልውና ጉዳይ የባቄላ ወፍጮ እንዳይሆን ከመፈለግ የተነሳ እንደሆነ ውስጥ አዋቂ ምንጮች ግምታቸውን ያስቀምጣሉ። ምክንያቱም የዘንድሮው የጉባዔ ሂደት የማኅበሩን የሁለት ዐሥርተ ዓመታት ጉዞ ወሳኝ በሆነ መልኩ የሚመለከት ጉዳይ ከመኖሩ የተነሳ ምስጢራዊነቱ እንዲጠበቅ አስፈልጓልም በማለት ያክላሉ።
ቅዱስ ፓትርያርኩን ከገጠሟቸው ተግዳሮቶች አንዱ «ማኅበረ ቅዱሳን በምን ሕግና መንገድ ሊተዳደር ይገባዋል» በሚለው አንገብጋቢ ጉዳይ ላይና አዳዲስ ሊሾሙ በሚችሉ የእጩ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ላይ የተያዘው የሁለት ወገን ሰልፍ ምክንያት እንደሆነ ይነገራል።
አንዱ ሰልፍ  በቅዱስ ፓትርያርኩና በደጋፊዎቻቸው በኩል የሚነሳው ሃሳብ የማኅበሩ እንቅስቃሴ ከሰላምና ከፍቅር ይልቅ ቤተ ክርስቲያኒቱ በማኅበሩ የምትታወክበትና ያልተፈለገ እሰጥ አገባ ውስጥ የምትዘፈቅበት ምክንያት ስለበዛ እንደማኅበር መቆየት አለበት የሚያሰኝ አመክንዮ ባይኖርም እንኳን እንዲኖር ካስፈለገ አቅሙንና ደረጃውን አውቆ፤ እንቅስቃሴው ከአቅሙ ጋር ተገናዝቦ በተወሰነ ማዕቀፍ ውስጥ ብቻ ኅልው እንዲሆን የሚያስገድድ ህግ እንዲወጣለት ጥብቅ ፍላጎት ያላቸው መሆኑ ነው።
ሁለተኛው ሰልፍ ደግሞ የማኅበሩ አባላት በሆኑ ሊቃነ ጳጳሳትና ማኅበሩ ራሱ በስለላ መዋቅሩ በኩል በሚያካሂደው የሩጫ ዘመቻ የተነሳ ያለው ሰልፍ ሲሆን ይህም ሲከናወን የቆየውን ስልት ማስቀጠል የሚያችል ልዩ መብት በራሱ ሰዎች በኩል አርቅቆ ለማስጸደቅ መቻል ነው። ይኼውም ማኅበሩ እስካሁን ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ስር በተመሳሳይ የዘመቻ ስልት አፈንግጦ የወጣበትና በሥራ አስኪያጁ ስር እንዲቆይና የራሱን ኅልውና ለማቆየት አዲስ መተዳደሪያ ደንብ እንዲወጣ የተሰጠውን የቆይታ ጊዜ ባለመጠቀሙ በዚህ ጉባዔ ላይ በሚፈልገው የጊዜ መግዢያ መንገድ የመቋጨት ዓላማ እንዳለው ከውስጥ አዋቂ ምንጮቻችን ለማወቅ ተችሏል።
ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚነሳው ጉዳይ የአዳዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ሲሆን ማኅበሩና ታዛዥ ጳጳሳቱ የያዙት ስልት በሁለት መንገድ እየተሰናሰለ ለማስኬድ እየተሞከረ እንደሚገኝ መረጃዎች ያሳያሉ። ይኼውም በእነሱ ምርጫና አጽዳቂነት ተመልምለው ለሲኖዶስ መቅረብ የሚገባቸውን የመለየት ስራ ያከናወኑ ሲሆን በፓትርያርኩና በደጋፊዎቻቸው በኩል ሊቀርቡ የሚችሉ ነገር ግን ለማኅበሩ ኅልውና ስጋት ሊሆኑ እንደሚችሉ ቅድመ ግንዛቤ የተያዘባቸውን አስቀድሞ ውድቅ የማድረግ ስልት መያዙም ሌላኛው እቅድ ስለመሆኑም ይነገራል። በተለይም እንደአባ ሠረቀ ብርሃን ወልደሳሙኤልና መሰል ተቃናቃኞች በምንም ዓይነት መንገድ ቢሆን ከእጩዎች ዝርዝር ውስጥ መግባት እንደሌለባቸው በማኅበሩና ደጋፊ ጳጳሳቱ በኩል በጥቁር መዝገብ ውስጥ የሰፈሩ ናቸው። በሌላ መልኩም ንቡረ እድ አባ ገ/ማርያም ገ/ሥላሴ በሥራ ችሎታና ሙስናን በመዋጋት ጠንካራ ስለመሆናቸው ጥያቄ ባያስነሳም በማኅበረ ቅዱሳን ደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳት ዘንድ የማያጎበድዱ፤ ለሹመት ደጅ የማይጠኑና እጅ መንሻ  የማያቀርቡ በመሆናቸው ለእጩነት ችላ ከተባሉት መካከል ናቸው።  
በፓትርያርኩ በኩል ሊቀርቡ የሚችሉና ማኅበረ ቅዱሳን ዓይናቸውን ማየት የማይፈልጋቸው እጩዎችን ላለመቀበል በደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳቱ በኩል በሁለተኛነት የተያዘው ዘዴ  ደግሞ «እኛ ምን ሠርተን ነው፤ የአዳዲስ እጩዎች ምርጫ ለማጽደቅ እንዲህ የሚያጣድፈን ምክንያት የለም!»  የሚል ሲሆን ጊዜውን በማዘግየትና የምርጫውን በር በመዝጋት ያልፈለጓቸውን ሰዎችን ለማስቀረት እንደስልት መያዙ ነው።
በሌላ መልኩም ከፓትርያርኩ ስር የማይጠፉ ለዓመታት የጵጵስና ስካር እያንገዳገደ ያቆያቸው አንዳንድ መነኮሳት ሰርገው ለመግባት የሚያደርጉት ሩጫ ሳይጠቀስ መታለፍ የሌለበት ሆኖ ተገኝቷል። ለዚህ ማዕርግ ብቁ ስለመሆናቸው የምዕመናንና ምዕመናት ምስክርነት የሌላቸው እንዲሁም ያለደረጃቸው ካቴድራል የተሰጣቸው ጠልፎ በላዎችና ተሸክመው የመጡትን ዶላር መመንዘር የማይሰለቻቸው ደግሞ ጺማቸውን እየላጉ ጳጳስ ለመሆን ማስፈሰፋቸው ትኩረት የሚያሻው ነገር ነው።  ማኅበሩና ደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳቱ በአንድ በኩል ሠርተው ማሰራት የሚችሉትን ወደእጩነት እንዳይቀርቡ በር በመዝጋት ላይ ሲተጉ በሌላ በኩል ደግሞ በጓሮ በር መግባት የሚፈልጉ እንደቅድስት ሥላሴው ጎረምሳ አስተዳዳሪና መሰል የሹመት ስካር የሚያንገዳግዳቸው የችሎታ ባዶዎች አሰፍስፈው መገኘታቸው ጉዳዩን አስቸጋሪም፤ አሳዛኝም፤ አሳፋሪም ያደርገዋል።

ስለዚህ ፓትርያርኩ ተግዳሮት ገጥሟቸዋል ስንል በእነዚህ ውስብስብ እንቅስቃሴዎች የተነሳ ሲሆን መወሰድ የሚገባው ርምጃም ትኩረት የሚያሻው፤ ካለፈ በኋላ የማይቆጭ መሆን ስለሚገባው አበክረን ማሳሰብ እንወዳለን።

አጭር ነገር ግን የትኩረት አቅጣጫን የሚለውጡ ግንዛቤዎች፤

1/ ማኅበሩ እንደፈለገና እንዳሻው በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የሚናኝ ሆኖ መቀጠል የለበትም። ማኅበሩ ማኅበር እንጂ የቅዱስ ሲኖዶስ ቅርንጫፍ መሥሪያ ቤት ወይም የቤተ ክህነቱ የመምሪያ አካል አይደለም። ሲኖዶስ ስለአንድ ማኅበር ከዓመት ዓመት በአጀንዳ የሚነጋገርበት ምክንያት የለም። ስለዚህ፤
  ሀ/ ቢቻል ራሱን ችሎ ሥልጣን ባለው አካል ሕጋዊ ሰውነት አግኝቶ እንደማኅበር በሀገሪቱ ሕግ እንዲንቀሳቀስ  በነጻ መተው አለበት እንጂ ሲኖዶስ ሕግ አውጥቶለት በራሱ እጅ እየተለበለበ መቀጠል የለበትም።  «ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ቆሞ ማውረድ» ያቃተው ለምንድነው? ስለዚህ በዚህ ጉባዔ ፓትርያርኩ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እልባት እንዲያገኝ ማድረግ አለባቸው። በቀጠሮ የነፍስ መግዢያ ጊዜ የሚጠይቁ አፍራሾችን መዋጋት አለባቸው።
 ለ/ ማኅበሩ በኛው ስር ሆኖ ቢሰራ ውጤታማ መሆን ይችላል የሚል ግምት ካለ ( ከታየው ተሞክሮ የተነሳ የተሳሳተ ግምት እንደሆነ ቢታወቅም) የማኅበሩን ያለፈ ታሪክ ገምግሞ ወደፊት ምን ሊሰራ ይችላል በሚል ግንዛቤ ስር ሰፊ ጥናት ተወስዶ በተገደበና በተወሰነ የመተዳደሪያ ደንብ  ተቀርጾ አቅሙን ለክቶ በመስጠት የማያዳግም መቋቻ ሊደረግበት ይገባል።
2/ የእጩ ኤጲስ ቆጶሳትን ምርጫ በተመለከተ፤ ማኅበሩና ደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳቱ የያዙት ስልት የራሳቸውን የሲኖዶስ አባላት ቁጥር ከፍ የማድረግና የትኛውንም ውሳኔ በአብላጫ ድምጽ ሙሉ በሙሉ የመቆጣጠር ፖለቲካዊ ስልት ለማስፈጸም የፈለጓቸውን በጥቆማ የማቅረብ ሲሆን በዚሁ ተቃራኒ ደጋፊ ያልሆኑና ለኅልውናቸው ስጋት እንደሆኑ የሚታሰቡትን እጩዎች ደግሞ በልዩ ልዩ መንገድ የመከላከል ሁኔታ አለ። ስለዚህ ይህንን ማጤን አስፈላጊ ነው እንላለን።
3/  በሌላ መልኩም የማኅበሩንና የደጋፊዎቹን እንቅስቃሴ መቆጣጠር ብቻ ሳይሆን በእጩ ምርጫው ዝርዝር ውስጥ ያልተፈለጉ ሰዎች እንዳይገቡ ማድረግ በፓትርያርኩ በኩል እጅግ ትኩረት የሚያሻው ጉዳይ ነው። ስነ ምግባራቸው፤ እውቀታቸው፤ ችሎታቸው፤ የአስተዳደር ብቃታቸው፤ ተሞክሮአቸውና መንፈሳዊ ብስለታቸው ሳይታይ በብልጣብልጥ ዘዴና በገንዘብ አቀባባዮች የተጋነነ መረጃ የተነሳ ኤጲስ ቆጶስነትን ለማሸከም መሞከር ነገ ለሿሚው ኀፍረት፤ ለቤተ ክርስቲያኒቱም ሸክምና ውርደትን ሊያስከትል ስለሚችል የሹመት ስካር ያጠቃቸውን የጥቅምትና የግንቦት ተስፈኞች መከላከል ትኩረት ያሻዋል።

በመጨረሻም ቅዱስ ፓትርያርኩ በማኅበሩ ዙሪያ እየያዙ የመጡት ግንዛቤና ስጋት የመሆኑን ደረጃ የመገንዘብ አቋም የሚደገፍና የሚበረታታ ነው። ቤተ ክርስቲያኒቱ ከማኅበሩ ያለኪሳራ አንዳች አላተረፈችም፤ አታተርፍምም። ማኅበሩ ግን ያለቤተክርስቲያኒቱ ከባህር የወጣ ዓሳ ነው። ስለዚህ የፓትርያርኩ ስልጣን አንድን ማኅበር ጥግ ለማስያዝ የሚያንስ አይደለም። በቤተክርስቲያኒቱ ከፍተኛው የስልጣን እርከን ላይ የተቀመጠ ፓትርያርክ ከሀገሪቱ ሕግ ጋር ተቀናጅቶ የሚያስቸግረውንና ለአስተዳደር እንቅፋት የሆነውን ክፍል በህግ አደብ ለማስያዝ የማንም ጳጳስ የጩኸት እርዳታ አስፈላጊው አይደለም።  
ያለበለዚያ በማኅበሩ ተግዳሮት እየቆሰሉ እስከሞት መቀጠል አለያም አሜን ብሎ እጅ በመስጠት ታማኝ ሆኖ የማገልገል ምርጫ ብቻ ነው ከፊት ለፊት ያለው። አቡነ ጳውሎስን እያታለለ እስከኅልፈታቸው የተዋጋቸው ማኅበር ዛሬም ውጊያውን አላቋረጠም። ግን እስከመቼ?

Tuesday, May 13, 2014

በውስጡ ቀና መንፈሳዊ አባላት መኖራቸው ብቻ የሃይማኖት ማህበር አያሰኘውም!


(ከወልደገብርኤል ስሁል)
 
የየትኛውም እምነት ተከታዮች መንፈሳዊ ህይወትና የሃይማኖት ቀኖና በሚመለከቱ ጉዳዮች ያሻቸው ማመንና መከተል ይችላሉ፤ የቄሳርን ለቄሳር የእግዚአብሄርን ለእግዚአብሄር የሚለውን መርህ አክብረው ሁለቱን ሳያደበላልቁ እስከተጓዙ ድረስ። መጋቢት 1983 “በአቡነ ደርግ” ብላቴ ላይ የተቋቋመው ማ.ቅ. ዋና ዓላማው ጠመንጃ የታጠቀ የቅዱሳን ብርጌድ ሁኖ በማርክሲዝም የተከዳውን አምባገነን መንግስት የማዳን ተልእኮ ይዞ ሲሆን፤ ይህ ካልተቻለም “የብሄራዊ እርቅ መንግስት ይመስረት” በማለት ባቋራጭ የመንግስት ስልጣን ሊጨብጡ ይቋምጡ ለነበሩ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህራን (ማርክሲዝም ባዶ ሜዳ ላይ ጥሏቸው በመሄዱ የቆጫቸውና የደርግ ለሞት መቃረብ “ንስሃ” ለመግባት የተገደዱ የደርግ ቀኝ እጆች) በድህረደርግ ኢትዮጵያ የፖለቲካ መጫወቻ ካርድ ይሆናቸው ዘንድ ተጠፍጥፎ የተሰራ ማህበር ነው። መስራቾቹም የደርግ ደህንነት ያሰባሰባቸው አንዳንድ “ምሁራን”ና “መንፈሳዊ አባቶች” ሲሆኑ በህቡእ እንዲመሩት የተሰየሙትም ከነሱ የተውጣጡ “ታላላቅ ወንድሞች” ናቸው(ለማንም ግልጽ በሆነ ምክኒያት ስማቸውን እዚህ ላይ መጥቀስ ሳያስፈልግ)። ስለዚህ መስራቾቹና ህቡእ መሪዎቹ ፖለቲከኞች ናቸው፤ የተመሰረተበት ዓላማ ደግሞ መንፈሳዊም ሃይማኖታዊም አልነበረም፤ አሁንም አይደለም። በውስጡ ቀና መንፈሳዊ አባላት መኖራቸው ብቻ የሃይማኖት ማህበር አያሰኘውም።

Monday, May 5, 2014

«ኢየሱስ ለእኔ እንዲህ ነው፤ ለእናንተስ?»



የኦሪቱ የኃጢአት ማስተስርያ
ኢየሱስ በኔ ኃጢአት ምትክ ሞቶ ሕይወትን ይሰጠኝ ዘንድ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከ ህያው በግ ነው።
ዮሐንስ ወንጌላዊ እንዲህ ሲል እንደተናገረ;
 «በነገው ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፦ እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ» ዮሐ 1፤29

እስራኤል ዘሥጋ የተባሉት የብሉይ ኪዳን ሕዝቦች እግዚአብሔር ከሰጣቸው ተስፋ መካከል አንዱ ኃጢአት ቢሰሩ ወይም ቢበድሉ ከዚህ መንጻት የሚችሉበትን መንገድ  አሳይቷቸው ነበር።  ይኼውም
 «ማናቸውም ሰው ቢበድል፥ ሳያውቅም ለእግዚአብሔር በተቀደሰው በማናቸውም ነገር ኃጢአትን ቢሠራ፥ ለበደል መሥዋዕት ለእግዚአብሔር ከመንጋ ነውር የሌለበትን አውራ በግ ያቀርባል እንደ ግምጋሜህ መጠን በብር ሰቅል እንደ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን ለበደል መሥዋዕት ያቀርበዋል» ዘሌ 5፤15
ኃጢአተኛው ይህንን የኃጢአት ወይም የበደል መስዋዕት በታዘዘው ደንብ መሠረት ለሊቀ ካህናቱ ካቀረበ በኋላ እጁን በመስዋእቱ ላይ ጭኖ ከጸለየለት በኋላ ኃጢአተኛው ለሰራው ኃጢአት ምትክ ማስተሰርያ ሆኖ አንገቱን ይቆለምመዋል። ከደሙም የመሰዊያ ግድግዳው ላይ ይረጨዋል። ያን ጊዜም የኃጢአት መስዋዕት ሆኖ ኃጢአተኛው ከሰራው ኃጢአት ነጻ ሆኖ ይመለስ ነበር።
 ይህ ከኃጢአት ለመንጻት የሚደረግ የመስዋዕት ስርዓት ኃጢአት በሰሩ ቁጥር መቅረብ የሚገባውና ኃጢአተኞች ሁሉም ለየራሳቸው ያለማቋረጥ ለማቅረብ የሚገደዱበት የመንጻት ደንብ ነበር።  ይህን መስዋዕት ሁልጊዜ ለመፈጸም ያስገደደው ምክንያት ሊቀካህኑም ሆነ የሚሰዋው በግ  ዘላለማዊ ስላልነበሩና ብቃት ስለሚጎላቸው ነበር።   ሊቀካህኑ ለራሱ መስዋዕት እንዲያቀርብ ይገደዳል። በጉም  ነውር እንዳይኖርበት ጥንቃቄ ይደረግበታል።  እንደዚያም ሆኖ ፍጹም ማዳን አይችሉም።
  
«ሊቀ ካህናት ሁሉ ስለ ኃጢአት መባንና መስዋዕትን ሊያቀርብ ከሰው ተመርጦ ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ ስለ ሰው ይሾማልና፤እርሱ ራሱም ደግሞ ድካምን ስለሚለብስ፥ ላልተማሩትና ለሚስቱት ሊራራላቸው ይችላል፤በዚህም ምክንያት ስለ ሕዝብ እንደሚያቀርብ እንዲሁ ስለ ራሱ ደግሞ መስዋዕትን ስለ ኃጢአት ሊያቀርብ ይገባዋል» ዕብ 5፤1-3

ስለዚህ ይህንን ኪዳን በማስቀረት እግዚአብሔር አዲስ ቃል ኪዳን ለመግባት ወዷል። በዚሁ መሠረት እነዚህን አምስት ነጥቦች የሚያሟላ ነው ፤
1/ ኃጢአትን የሚያስተሰርየው ሊቀ ካህን በሞት የሚሸነፍ መሆን የለበትም።

2/ ሊቀ ካህኑ በመሐላ የተሾመ መሆን አለበት።

3/ ለራሱ መስዋዕት ማቅረብ የማይገባው ንጹህ መሆን አለበት።

4/ ሊቀ ካህኑ እንደኦሪቱ በግ የሚያቀርብ ሳይሆን ራሱ ለኃጢአተኛው በግ ሆኖ መሰዋት አለበት።

5/ ኃጢአተኛው ወደሞተለት ሊቀካህን በመቅረብ መናዘዝ እንጂ ስለኃጢአቱ በግ ማቅረብ አይጠበቅበትም።
ስለዚህ ይህንን የሚያሟላ መስዋዕት እግዚአብሔር አብ ልጁን ወደምድር ልኳል። እሱም ሰው የሆነው ኢየሱስ ነው። 
«ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ ማንም የለም፥ እርሱም በሰማይ የሚኖረው የሰው ልጅ ነው» ዮሐ 3፤13 
ኢየሱስ በመሃላ የተሾመ ዘላለማዊ ሊቀካህን ስለሆነ ዛሬ ሌላ ሊቀካህን የለንም። የኦሪቱ የኃጢአት መስዋዕት በግ ከኃጢአት ያነጻ ነበር። የአዲስ ኪዳኑ የእግዚአብሔር በግ ደግሞ ላመኑበት ለዘለዓለም ያድናል። ከዚህ ውጪ የመዳን መንገድ ለሰው ልጅ አልተሰራም። ኢየሱስም «መንገዱ እኔ ነኝ» ያለውም ለዚህ ነው። ሌላ የመዳኛና የመጽናኛ መንገድ በጭራሽ በዚህ ምድር በሌላ በማንም የለም።

«እነርሱም ያለ መሐላ ካህናት ሆነዋልና፤ እርሱ ግን፦ ጌታ። አንተ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘላለም ካህን ነህ ብሎ ማለ አይጸጸትም ብሎ በተናገረለት ከመሐላ ጋር ካህን ሆኖአልና ያለ መሐላ ካህን እንዳልሆነ መጠን፥እንዲሁ ኢየሱስ ለሚሻል ኪዳን ዋስ ሆኖአል።እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል።ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና።» ዕብ 7፤20-27
ስለዚህ ኢየሱስ በሞቱ ሞቴን ያሸነፈ፤ የሕይወቴ ቤዛና በሥጋ የተገለጠ የእግዚአብሔር ልጅ ነው። በእርሱም አዳኝነት አምናለሁ። «በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው»  ዮሐ 3፤36 እንዳለው የዘላለምን ሕይወት በሞቱ በኩል አግኝቻለሁ። ከሌላ ከማንም የድኅነትን ተስፋ አልጠብቅም። በኃጢአት ብወድቅ የምነጻው፤ የምነሳው በእሱ ብቻ ነው። የምለምነው፤ የምጠይቀው፤ የምማጸነው እሱን ብቻ ነው። በሩ እሱ ስለሆነም «አንኳኩ ይከፈትላችኋል» በማለት የሰጠኝ የመዳን ተስፋ የማይለወጥ ነውና። ኢየሱስ ለእኔ እንዲህ ነው። እናንተስ የመዳናችሁን ተስፋ የምትጠባበቁት ከእነማን ነው?

Sunday, May 4, 2014

አንዳንድ ቅዱሳን በጣም ያስቁኛል...፪ (ካለፈው የቀጠለ)


(by Tedy Sih)

ስለማህበረ ቅዱሳን ስውር አመራር የሙሉጌታ ማደናገርያና የዳንኤል እውነታ

ማህበሩን ከጥንስሱና ከአመሰራረቱ ጀምረን በተጨባጭ ለምናውቀው እንጂ ህቡእ ገጹ ለብዙሃኑ አባላት እስከቅርብ ጊዚያት ግልጽ አልነበረም። አሁን ግን ስለማህበሩ ቆም ተብሎ ማሰቢያና ለርኩሰቱ መላ መፈለጊያ ጊዜ መጥቶ በር እያንኳኳ ነው። በቤተክርስቲያኗ ላይ እስካሁን ያደረሳቸውና በሃገርም ደረጃ ሊያደርሳቸው የሚሰናዳባቸው ነገሮች ፈጥጠው ወጥተዋል። የማሀበሩ እኩይ ስነፍጥረት፣ እኩይ ዓላማና እኩይ አካሄድ እርቃኑ እየወጣ ነው። ይህም ሃቅ ዘግይተውም የተቀላቀሉትን ጨምሮ ለአብዝሃኞቹ ቀና አባላቱ ግልጽ እየሆነ መጥቷል። የቤተክርስቲያኗ ምእመናን፣ የልዩ ልዩ እምነት ተከታይ የሆኑት የሃገሪቱ ህዝቦች፣ እንዲሁም መንግስት ከእንቅልፋቸው በቅርቡ እየነቁ መጥተዋል። የማህበሩ ማንነት አጠያያቂ መሆን በጀመረበት በዚህ ወቅትም ከራሷ ከቤተክርስቲያና እና ከማህበሩ ከፍተኛ አመራሮችም እያፈተለኩ የሚወጡት መግለጫዎች ይበልጥ እርቃኑን እያስቀሩት አደገኛ ባህርያቱ ወደ አደባባይ እየተገለጠ መታየት ጀምሯል። ባለፉት ሳምንታት በማህበሩ አመራሮች የተሰጡ መግለጫዎች ላፍታ ብንመልከት እንቆቅልሹን በደንብ ይፈቱልናል። የመምህር ሙሉጌታ ሃይለማርያም ሃሰትና የዲያቆን ዳንኤል ክብረት እውነት ተደምረው ባለፉት ክፍሎች ስለማህበሩ የገለጽኳቸውን ነገሮች እውነትነት ይበልጥ ያረጋግጣሉ።
ማህበሩ ግልጽ ጥያቄዎች በመጡበት ወቅት የማህበሩ ዋና ጸሃፊ መምህር ሙሉጌታ ሃይለማርያም ከድንጋጤ የሚመስል ማብራርያ ሰጥቷል። መምህር ሙሉጌታ እንቁ መጽሄት ጋር ባደረገው አስገራሚ ቃለ ምልልስ ማህበሩ ከተቃውሞ ፖለቲካ ጋር ምንም ንክኪ እንደለለው በማበከር ስጋትና ምጸት በቀላቀለ ችኮላ አብዛሃኞቹ የማሀበሩ አባላት የኢህአዴግ አባላትና ደጋፊዎች ናቸው ብሏል። ይህንን ለማስረዳት የተጠቀመበት አመክንዮ ደግሞ አባላቶቻችን ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የወጡ ስለሆኑና በነዚህ ስፍራዎች ደግሞ ኢህአዴግ ሁሉንም አባላቱ አድርጎ ስለሚመለምል የኛም አባላት ብዙዎቹ እነሱ ናቸው የሚል ነው።
ቃለምልልሱም ብዙዎቹን የማህበሩ አባላት ከማስቆጣቱም በላይ ከእውነት የራቀ ነበር። ቁጣ የቀሰቀሰውም ይበልጥ ጥያቄዎቸ አስነስቶ ከማህበሩ አባላት ጋር ብቻ የሚነገር ግን ለማህበረሰቡ በግላጭ ለገበያ የማይቀርብ መረጃ እንዲወጣ በር ይከፍታል በሚል ነው። በዚህ መልኩም ህቡእ ገጽታው እንዳይጋለጥ በሚሹት ሁሉ የናሩ ነቀፌታዎች ተሰንዝረዋል። የነቃፊዎቹም ስጋት የማህበሩ አባላት የኢህአዴግ አባላትና ደጋፊዎች ናቸው በመባሉ አይደለም። አባባሉ ትክክል ስላለመሆኑ ዋና ጸሃፊውና ነቃፊዎቹም ሆኑ ከነሱ ውጭ ያለ ማንኛውም ወገን እንደማያጣው ያውቃሉና። የስጋቱና የቁጣው ምንጭ የማህበሩ አባላት ካላቸው የብሄር ወይም የፖለቲካ ወገንተኝት ተነስቶ ሲዘረዘር ዋና ጸሃፊው በሃሰት የለጠፈው ኢህአዴግነት ሳይሆን ማህበሩ በተልእኮና በገቢር የጨበጠው እውነተኛ ማንነት(ተቃዋሚነት) ስለመሆኑ ከራሱ ከአመራሩ ግልጽ ጥቆማና እማኝነት ተመስርቶ እንዳይታወቅ በመፍራት ነበር። የፈሩት ግን አልቀረም። መምህር ሙሉጌታ በቃለምልልሱ የዲያቆን ዳንኤል ክብረትን ስም ጠቅሶ ስላንቋሸሸ ዳንኤል በሰጠው ምላሽ ስውር አመራር እንዳለ ምናልባትም ለመጀመርያ ጊዜ ከውስጥ ሰው ይፋ ተደረጓል። ዳንኤልም የምናውቀውን ያክል የማህበሩን ህቡእ ገጽታ ደፍሮ ባያፍረጠርጥም ስለ ስውር አመራሩና ስለ እኩይ ድርጊቶቹ ከውስጥ አዋቂ በሚሰጥ እማኝነት ሰጥቷል።
ዳንኤል አደባባይ ካዋላቸው የማህበረ ቅዱሳን አካሄዶችም የሚከተሉት ዋና ዋናዎቹ ሲሆኑ እነሱንም አጠር አድርጌ በማስቀመጥ ከማህበሩ ፖለቲካዊ ተልእኮ አንጻር ትርጉማቸውን እገልጻለሁ።
ማህበሩ ስለ ቤተክርስቲያኒቱ ግልጽ መረጃ ሳይጨብጥና የት እንደሚያደርሳት ግልጽ ግብ ሳይኖረው ስለ መጓዙ ተናግሯል።
(መጀመሪያውንም በመንፈሳዊ ቤተክርስቲያኗን የሚደግፍ ሃይማኖታዊ ተልእኮ ያልነበረው ስለመሆኑ ይነግረናል። አመራሩም ቤተክርስቲያን ተኮር ስትራቴጂ የሌለውና የፖለቲካ አባቶቹ ጭፍን ፈረስ ስለመሆኑ በማያሻማ ቋንቋ ይመሰክራል።)
አመራሩ ማህበሩ ለቤተክርስቲያኗ አገልግሎት የተመሰረተ ሳይሆን ቤተክርስቲያኗ ለማህበሩ አገልግሎት ወደሚል አመለካከት መዞሩ፣
(አመራሩ ቤተክርስቲያኗን ለህቡእ ተልእኮው መሳካት ሊቆጣጠራት ይፈልጋል እንጂ እሷ የምትፈልገውን አገልግሎት ሊሰጥ አይሻም ። ሲጀምር የሚያገለግላት መስሎ ቢገባም ቀስ በቀስ ለተልእኮው ሊገለገልባት ወደሚያደርግ አቅጣጫ ማምራቱን ያሳየናል።)
ተሃድሶን ለማጋለጥ እንጂ ተሃድሶን እንዲፈጠር ያደረገውን መሰረታዊ ችግር ለመፍታት ስትራቴጂ የሌለው መሆኑ፣
(ማህበሩ የቤተክርስቲያኗን መሰረታዊ ቀኖናዎች እና አስተምህሮዎች ለመጠበቅም ሆነ ለማስፋፋት የቆመ ስላለመሆኑ ያስረዳናል። ይልቁንም የተሃድሶን አደጋ በተጋነነ ምስል እያቀረበ ብጥብጥ ህውከትና መመሰቃቀል ቤተክርስቲያኗን እንዳይለያት በትጋት እየተንቀሳቀሰ ስለመሆኑ ያስረዳል።)
የማህበሩ አመራር የእለት ተለት ነገሮችን ለማየት የሚሰበሰብ፣ ማህበሩ ስራውን ትቶ አባላቱን እንደሚሰልል፣ አባላቱ የሚወገዙትና የሚታገዱትም ማህበሩን ከነኩ ወይም የተለየ አቋም ከያዙ እንጂ ለቤተክርስቲያኗ እምነትና አስተምህሮ ወይም ለመንፈሳዊው ምግባር አደጋ ናቸው ተብሎ አለመሆኑ ገልጿል፣
(ማህበሩ በየእለቱ በሚከናወኑ ዓለማዊና ፖለቲካዊ ሂደቶች ትኩረት ሰጥቶ እንደሚንቀሳቀስ፣ አባላቱንም ማንነታቸውንና አመለካከታቸው የተለየ እንዳይሆን ሲል በየጊዜው እንደሚከታተል ብሎም ህቡእ ተልእኮውና እንቅስቃሴዎቹ እንዳይታወቁበት በከፍተኛ ጥንቃቄ ሚስጢራዊ ጉዞ እያካሄደ ስለመሆኑ አስረጅ ነው።)
ማህበሩ ስውር አመራር ያለው መሆኑ፣ ስውሩም አመራር ጥላቻውን የሚገልጽበት ሶስት መንገዶች ያሉት ስትራቴጂ እንዳለው፣ እነሱም ስለሚጠላው ሰው ክፉ በመናገር ስለሚጠላው ሰው የሚያውቀውን ጥሩ ነገር ባለመናገር እና ስለሚጠላው ሰው ተራ ነገር በመናገር የሚገለጹ ስለመሆናቸው፣ ከነዚህ በተጨማሪም ስውር አመራሩ የማስከፋትና የጭር ሲል አልወድም ስትራቴጂ ስለመያዙ አስረድቷል።
(ይህ ደግሞ በነ አቡነ ሺፈራው ተነድፎ ተግባራዊ እየሆነ ያለው የአሁኑን መንግስት ጥላሸት እየቀቡ ተቀባይነት የመንሳትና ድሮ የነበሩትን ሁሉ ቅዱስ አድርጎ የመሳል ስትራቴጂ በማህበሩ ስውር አመራር እንዴት እንደሚተገብረው ይጠቁመናል።ማህበሩ በግልጽ በሚታወቀው አመራሩ ሳይሆን በህቡእ አመራሩ ቁጥጥር ስር መሆኑ ይህም አመራር የጥላቻ ስትራቴጂ እንዳለው፣ ስለሚጠላቸውም ወገኖች( መንግስትንና የቤተክህነትን አመራር) ክፉውን ብቻ በመናገር በጎ ስራቸውን ባለመናገር እና ተራ አሉባልታ ፈጥሮ በማጥላላት የማስጠላት ስልት እንደሚተገብር ይመሰክራል። እውነትና ሃሰት አዛብቶ ጥላቻ ማራመጃ ከማድረጉ በተጨማሪም ጭር ሲል አልወድምን ሆን ብሎ በመከተል በማህበሩ በቤተክርስቲያኗ እና በሃገሪቱ ላይም አጠቃላይ ብጥብጥ በሚፈጥር የዓመፃ መንገድ ላይ መቆሙን ያሳያል።)
ማህበሩ በእውቀትና በተጨባጭ መረጃ ተመስርቶ ስራ ከመስራት ይልቅ በአሉባልታና በስሚ ስሚ እንደሚንቀሳቀስ እቅዶቹን 50 በመቶ ያህሉን እንኳን መስራት ያልቻለና እስካሁንም የባለጉዳይ መስመር እንጂ የሃሳብ መስመር የሌለው መሆኑ፣ የማህበሩ አመራር ተሰብስቦ ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች እንደገና ለብቻቸው ተሰብስበው ባሻቸው የሚቀይሩ ታላላቅ ወንድሞች እንዳሉ፣ ከነዚህ አመራሮቹም ውስጥ የማኅበሩ አባላት መንግሥትን እንዲፈሩ እና እንዲጠሉ የሚፈልጉ አካላት መኖራቸው፣ እነሱም ምንጊዜም አንዳች ከባድ ነገር ሲነሣ መንግሥት እንዲህ ብሎናል፣ በዚህ ስብሰባው እንዲህ ብሏል፣ ሊዘጋን ነው፣ ሊያስረን ነው፣ ሊጨርሰን ነው ከማለት ያለፈ አንድም ቀን በጎ ነገር ስለ መንግሥት እንደማያነሡ፣
(ማህበሩ በግልጽ እቅድና በአመክንዮ የተመሰረተ መርህ ከመመራት ይልቅ በአሉባልታና በበሬ ወለደ እንደሚነዳ፣ በግልጽ የሚታወቀው የማህበሩ አመራር የስውር አመራሩ አሻንጉሊት ስለመሆኑና ወሳኝ ወይም አድራጊ ፈጣ የሆነው ስውር አመራሩም በታላላቅ ወንድሞች እጅ እንደተያዘ ቁልጭ አድርጎ አሳይቶናል። ከታላላቅ ወንደሞችም መካከል በተለይም የነ ካህን ሽፈራው የድሮ ቀረ ማንዋል እንዴት ባለ ዘዴ ቤተክህነትን እያመሰ እንዳለ በቂ ምስክርነት ይሰጣል። ይህም ዘዴ ማህበሩና አባላቱ የአሁኑን መንግስት እንዲፈሩት፣ ያለተጨባጭ ምክኒያትም እንዲጠሉት እና በመከበብ ስሜት እንዲታጠሩ በማድረግ ለአመጽ እንዲነሳሱ ስለሚቀሰቀሱበት አጠቃላይ ሁኔታ በቂ ጥቆማ ይሰጣል።)
ዲያቆን ዳንኤል የገለጻቸው እነዚህንና ሌሎች በማህበሩ ውስጥ የታመቁ ሚስጥሮች በክፍል አንድና በክፍል ሁለት ባቀረብኳቸው ተከታታይ ጽሁፎቼ የተገለጹትን እውነታዎች ተጨማሪ ማስረጃ ይሰጣሉ። በተለይ የሱ ምስክርነት ክብደት የሚያሰጠውም ከጅምሩ አንስቶ ማህበሩን በይፋ እየመራ የነበረ በመሆኑ ከሱና ከመሰል ወንድሞቹ በላይ ሁነው ታላላቅ ወንድሞች በስውር ለቅዱሳኑ ማህበር ልዩ አመራር እንደሚሰጡ ከሱ በላይ እማኝ መጥራት ስለማይቻል ነው። እርግጥ ችግሮቹን ሙሉ በሙሉ ገላልጦ ባይጽፍም በመምህር ሙሉጌታ አስተያየት ተቆጥቶም ቢሆን ዳንኤል ይህንን ሲጽፍ አጽንኦት የሰጠው ስለስውሩ አመራርና ከቤተክርስቲያን አገልጋይነቱ የሚጻረሩ ፖለቲካዊ ገጾቹ ላይ ነው። ተወደደም ተጠላም ዳንኤል እሳት ለብሶ እሳት ጎርሶ “አውላላ ሜዳ ላይ የተኛውን በሬ፣ ነካክተው ነካክተው አደረጉት አውሬ።” እያለ ተማርሮ ስለማህበረ ቅዱሳን በልቡ ብቻ ይዟቸው የነበሩትን እውነቶች አጋልጧል። ማህበረ ቅዱሳንና የታላላቅ ውነድሞቹ ስውር አመራርም እርቃኑን ወጥቷል። የዳግመ ደርጊዝምና የዳግመ ሞናርኪዝም ፈረስ እንደሆነ ለምናውቀው ብዙ ባያስገርምም ቢያንስ እስካሁን ስለማህበሩ ሃቁን ለማያውቁት ግን የእውነት ብርሃን ፈንጥቆ ጨለማውን ያጋለጠ ምስክርነት ስለመሆኑ አንዳች ጥያቄ የለውም።
በዳንኤል ጽሁፍ የተደሰቱ አባላት ያሉትን ያህል ማህበሩን ለበለጠ አደጋ አሳልፈህ ሰጠህ ብለው የተከፉበትም ብዙ ናቸው። ጽሁፉን ተከትለው በየብሎጎች የወጡት አስተያየቶችም ይህንን ያሳያሉ። አንዳንዶቹ ድረ ገጾችም ጽሁፉን ላፍታ አትመው ካወጡ በኋላ ከገጾቻቸው አንስተውታል። ይህም በማህበሩ የተጠለለው ህቡእ ክንፍ እውነተኛ ማንነት ይፋ እንዳይወጣ የተደረገ ስልት ነው። በተለይ የማህበሩ ታላላቅ ወንድሞች በጣም ተደናግጠው ጉዳዩን ለማዳፈን የቻሉትን ያህል እየተሯሯጡ ነው። ከማዳፈኛ ስልታቸውም መካከል ዳንኤልን በማስፈራራት ወይም በማባበል ይቅርታ እንዲጠይቅ በማድረግ ሁሉም ነገር አማን የሚል ምስል ለምስጠትና ምንም ነገር እንዳልተፈጠረ ለማስመሰል ይጥራሉ። ለማባበል ከሚመስለው ጥረታቸውም አንዱ ጽሁፉ በዳንኤልና በሙሉጌታ አለመጣጣም የመጣ ችግር እንደሆነ ወይም ማህበሩ እንዴት ተሃድሶዎችን እንደሚዋጋ በሁለቱ አመራሮች የታየ የሃሳብ መለያየት ብቻ እንደሆነ ለመተንተን ሲጥሩ ይስተዋላሉ። ጎን ለጎን ደግሞ ዳንኤል ብዙ ጽሁፎች እንደጻፈ አንዳንዶቹም በብእር ስም እንዳሳተማቸው በመጠቆም ይቅርታ ካልጠየቀ ሚስጥሩን እንደሚዘከዝኩበት ፍንጭ እየሰጡም በአንዳንድ መጽሄቶች ባወጧቸው ጽሁፎች በግልጽ አስፈራርተውታል። በዛቻው ይሁን በማባበሉ ወይም በሁለቱ ተንበርክኮ ዳንኤል ይቅርታ ጠይቆ ከማህበሩ አመራር ጋር እንደታረቀ እየተነገረ ነው።
ይህ ሁሉ ሽር ጉድ ሰሚን ለማደናገር አልያም እርቃኑ የወጣውን የማህበሩ የውስጥ ጉድ ለማዳፈን ካልሆነ በስተቀር ስለማህበሩ እውነተኛ ማንንትም ሆነ በሱ ላይ ዳንኤል የሰጠውን እማኝነት በቅንጣትም የሚለውጥ ነገር አይደለም። እንዲያውም እውነቱን ለማዳፈን ተብሎ የሚደረገው ርብርብ ይበልጥ ጥያቄዎችን እንድናነሳና የማህበሩ የጥፋት ርኩሰት ከተቀደሰው ስፍራ እንዲወጣ አጥብቀን እንድንሻ ያስገድዳል። አዎ! የእግዚአብሄር ቤት የወንበዴዎች ዋሻ አይደለምና ማህበሩን ፈረሳቸው ያደረጉት እርኩሳን መናብርት ባስቸኳይ ይውጡ እንላለን። ይህ እንዲሆንም ከማህበሩ ታላላቅ ወንድሞች መካከል ፖለቲካዊ አመራር በመስጠት ቀንደኞች የሆኑትን በመጥቀስ እንዲሁም በህገወጥ መንገድ ተቋሞቻቸውን የመንቀሳቀሻ ማእከላት በማድረግ እየፈጸሟቸው ስላሉ ርኩሰቶች ጥቂት በመዘርዘር ወደ ጽሁፌ ማጠቃለያ ልሂድ።...”

( ከመልከፀዴቅ ጽሁፍ/ “የጥፋ ርኩሰት በተቀደሰው ስፍራ ሲቆም” ክፍል‐፫/ ተቀንጭቦ የተወሰደ)