Thursday, May 22, 2014

ግዝት(ውግዘት)…ኑፋቄ….መናፍቅነት…ግዝት-ዘበከንቱ… እና ወፈ-ገዝት መሆን!


 ( በአማን ነጸረ )
1. ግዝት(ውግዘት)፡ ማለት አንድ ምዕመን(አማኝ) በአፉ ክርስቲያን ነኝ ቢልም በተግባር ከሃይማኖት ወጥቶ ከበጎ ምግባር አድጦ(ተዛንፎ) ሲገኝ ከማኅበረ ምዕመናን እንዲለይ በስልጣነ-ክህነት የሚፈጸም መንፈሳዊ ቅጣት ነው፡፡
2. የውግዘት ዓላማ፡(ሀ)ቤ/ክ እንዳትረክስ፣(ለ)ኑፋቄው ወደ ሌሎች እንዳይዛመት፣(ሐ)ተወጋዡ በንስሐ እንዲመለስ እድል ለመስጠት ነው፡፡
3. የውግዘት ቅድመ-ሁኔታዎች፡(ሀ)ተጠርጣሪው ከሃይማኖት እና/ወይም ከበጎ ምግባር መውጣቱን ማረጋገጥ፣(ለ)ከጥፋቱ/ከክህደቱ እንዲመለስ ደጋግሞ መገሰጽና መምከር፣(ሐ)ተመክሮ ካልተመለሰ በስልጣነ-ክህነት አውግዞ መለየት፣(4)ውግዘቱ እንደጥሰቱ ዓይነት ከማዕረግ ዝቅ ማድረግ ወይም ስመ-ክርስትናን ነጥቆ መለየት ሊሆን ይችላል፡፡ከዚህ በኋላ ድርጊቱ-ኑፋቄ ተወጋዡም-መናፍቅ ይባላሉ፡፡በነገራችን ላይ ምንፍቅና የሚል ቃል በየመጻህፍቱ አላየንም፡፡በግእዙ ኑፋቄ ነው የሚባለው፡፡በአማርኛ መናፍቅነት፡፡
4. ግዝት-ዘበከንቱ እና ወፈ-ገዝት መሆን፡ ከላይ ያሉትን ቅድመ ሁኔታዎች ያላሟላ ግዝት ግዝት-ዘበከንቱ ሲባል ገዛቹም ወፈ-ገዝት ይባላል፡፡ነገር ግን ተጠርጣሪው በግልጽ የተወገዘ ሃይማኖትንና ምግባርን ሲያራምድ ያገኘነው እንደሆነ መናፍቅ ብንለው ፍርድ የለብንም፡፡
5. ከንቱ እና ከንቱ አንድ ወገን ብለን ስለመርገም ዘበከንቱም እንናገር፡ ሀቅ ላይ ያልተመሰረተና የሚረገመውን ሰው ህሊና የመውቀስ አቅም የሌለው ከንቱ እርግማን በመጽሐፈ ምሳሌ 26 ቁ 2 እንደተገለጸው….እንደሚተላለፍ ድንቢጥ፣ወዲያና ወዲህም እንደሚበር ጨረባ እንዲሁም ከንቱ እርግማን በማንም ላይ አይደርስም፡፡ፍትሐ ነገስቱም በአንቀጽ 11 እንዲህ አይነቱን ረጋሚ “ወኩሎ ዘይረግም ይረግም ነፍሶ” ይለዋል::
ምንጭ፡ (1) መርሐጽድቅ ባህለ ሃይማኖት በ1988 ዓ.ም በትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት የታተመ ገጽ 157 እስከ 161 ፣ (2)የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገጽ-237፣ (3) ጥቅሶች፡ ማቴ 18 ቁ 15-18፣2ተሰ 3ቁ14፣ቲቶ 3 ቁ 11፣1ጢሞ 1ቁ 19፣2ጢሞ 2 ቁ 17፣1ቆሮ 5 ቁ 5፣2ቆሮ 2 ቁ 6
መነሻ፡ በ40 ቀን ያገኘነውን ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ባልተሰጠ ስልጣነ-ክህነት ሊነጥቁ የሚሞክሩ ወፈ-ገዝት ወንድሞቻችን!!