Saturday, January 30, 2016

ፓትርያርክ ማትያስ ስለማኅበረ ቅዱሳን የጻፉት ደብዳቤ ከመዘግየቱ በስተቀር ሀቅነቱ ጥያቄ የሚያስነሳ አይደለም!

ማኅበረ ቅዱሳን ማለት ለተረት፤ ለእንቆቅልሽ፤ ለልማድና ለባህል እምነት ጥብቅና የሚቆም፤ የወንጌል ቃል ጆሮውን የሚያሳክከው፤ በኢየሱስ ክርስቶስ የእውነት መንገድ ላይ ቆሞ እንዳይገለጥ መጋረጃ የሚጋርድ የጠላት መልእክተኛ ማለት ነው። ማኅበረ ቅዱሳን በሀገሪቱ ላይ የብርሃን ወንጌል እንዳይበራ የጭለማ ሥራ የሚሰራ፤ ሰዎች በእጃቸው ያለውን እውነት እንዳያዩ ወደገደል የሚመራ እውር መሪ ማለት ነው።
ማኅበረ ቅዱሳን ማለት በአንድ ወቅት የእግዚአብሔር ሕዝብ የተባለው እስራኤል በእግዚአብሔር ላይ ያለውን እምነት ትቶ የራሱን የልብ መሻትና ምኞት በተከተለበት ወቅት እንደሆነው ዓይነት በተመሳሳይ መልኩ በሀገራችን በኢትዮጵያም ከፊት ሆኖ በሀሰት እየመራ በእውነት የሚፈርድ እንዲታጣ ያደረገ፤ በሀሰትም የሚያስተምር እንዲበዛ የፈለፈለ፤ ልቡን ያደነደነ ትውልድ እንዲበረከት ሚና የተጫወተ ማኅበር ነው።
ያንን የእስራኤል ዐመጽ ነቢዩ ኤርምያስ እንዲህ ሲል ተናግሮት ነበር።

«እናንተ ሰነፎች ልበ ቢሶች፥ ዓይን እያላችሁ የማታዩ፥ ጆሮም እያላችሁ የማትሰሙ ሕዝብ ሆይ፥ ይህን ስሙ። በውኑ እኔን አትፈሩምን? ከፊቴስ አትደነግጡምን? ይላል እግዚአብሔር፤ እንዳያልፍ አሸዋን በዘላለም ትእዛዝ ለባሕር ዳርቻ አድርጌአለሁ፤ ሞገዱም ቢናወጥ አያሸንፍም፥ ቢጮኽም አያልፍበትም። ለዚህ ሕዝብ ግን የሸፈተና ያመፀ ልብ አላቸው፤ ዐምፀዋል ሄደውማል። በልባቸውም፦ የፊተኛውንና የኋለኛውን ዝናብ በጊዜው የሚሰጠውን፥ ለመከርም የተመደቡትን ወራት የሚጠብቅልንን አምላካችንን እግዚአብሔርን እንፍራ አላሉም። በደላችሁ እነዚህን አስቀርታለች፥ ኃጢአታችሁም መልካምን ነገር ከለከለቻችሁ። በሕዝቤ መካከል ክፉዎች ሰዎች ተገኝተዋል፤ እንደ አጥማጆችም ያደባሉ፥ ወጥመድንም ይዘረጋሉ ሰዎችንም ያጠምዳሉ»           ኤር 521-26

ማኅበረ ቅዱሳን በዘመናት ብዛት ማን እንደጻፋቸውና ማን እንዳስገባቸው የማይታወቁ የተረትና የእንቆቅልሽ መጻሕፍት እንዳይነኩ ዘብ የቆመ የጠላት ወታደር ነው። ብዙዎች እውነት በመናገራቸውም ያወገዘና ያስወገዘ ማኅበር ነው። ለምሳሌ አንድ አስረጂ እናንሳ!

መስተብቍእ ዘመስቀል በተባለው የቤተክርስቲያን የጸሎት ክፍል ውስጥ እንዲህ የሚል ክህደት ተሰንቅሮ ይገኛል። 
«ለእሉ ክልዔቱ ፍጡራን/ለማርያም ወለመስቀል/ ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ፤ እስመ ተዐረዮሙ በክብሮሙ»
ለነዚህ ሁለቱ ፍጡራን  (ለማርያምና ለመስቀል) ለፈጣሪ የሚሰጠው  ምስጋና ይገባቸዋል። በክብር ፈጣሪያቸውን ተካክለዋልና!

 እግዚአብሔር ቢከብር ክብር የባህርይው እንጂ አክባሪ የሚጨምርለትና የሚቀንስለት ነገር የለም። ማንም የቱንም ያህል ቢከበር ከእግአብሔር ፈቃድ አንጻር እንጂ በራሱ ብቃት በሚያመጣው ችሎታ አይደለም። ደግሞም በክብር እግዚአብሔርን የሚስል፤ የሚያክልና አቻ የሚሆን ፍጥረት ፈጽሞ የለም። «በልዑል እመሰላለሁ» ካለው ከሰይጣን በስተቀር ከፍጥረታት ውስጥ በክብር እግዚአብሔርን የሚተካከል የለም።
«ከዳመናዎች ከፍታ በላይ ዐርጋለሁ፥ በልዑልም እመሰላለሁ አልህ» ኢሳ 1414

ነገር ግን እግዚአብሔርን የሚመስለው ማንም የለም? በማንም ልንመስለውና ከማንም ጋር ልናስተካክለው አይገባም። ራሱ እግዚአብሔር በነቢዩ አንደበት እንደዚህ ሲል ተናግሮናልና።

«እንግዲህ እተካከለው ዘንድ በማን መሰላችሁኝ? ይላል ቅዱሱ። ኢሳ 4025»
  
ማኅበረ ቅዱሳን ማለት እንደነዚህ ዓይነት ተረቶችና ክህደቶች እንዳይነኩ ለእውነት ሁሉ ጠላት ለሆነው ለሰይጣን ጥብቅና ቆሞ የሚከራከር ማኅበር ነው። መንፈሳዊ ኮሌጆችና ዩኒቨርሲቲዎች የእውቀትና የማስተዋል ተቋማት እንደመሆናቸው መጠን ጥያቄ የሚጠይቁና ከእግዚአብሔር ቃል የተገናዘበ አሳማኝ ምላሽ እንዲሰጣቸው የሚተጉትን በክህደትና በምንፍቅና እየወነጀለ መቆሚያና መቀመጫ የሚያሳጣ፤ ወይ ከእውቀቱ ወይ ከእውነቱ አንዱንም ያልያዘ ድርጅት በመሆኑ ነው።
ስለዚህ ፓትርያርክ ማትያስ ለመንፈሳዊ ኮሌጆች ጥያቄ ምላሽ የሚሰጥ ደብዳቤ ለመጻፍ የተገደዱት ከኮሌጆቹ ተማሪዎች ጥያቄ አንጻር ብቻ ሳይሆን ፓትርያርኩ ለሚያደርጉት ትግል የሊቃነ ጳጳሳቱ ድጋፍ አናሳ ሆኖ በመገኘቱ ቢያንስ የትግላቸው አጋር የተማረውን ክፍል ለመያዝ ከመፈለግ የተነሳ ይመስላል።
በዚህ አጋጣሚ የመንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎችና የቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳይ ግድ የሚለው ሁሉ ከፓትርያርኩ ጋር በመቆም የያዙትን ትግል ከግብ ለማድረስ በጸሎትና በሃሳብ እንዲያግዝ ለማሳሰብ እንወዳለን።
ደብዳቤዎቹን ለማንበብ ሊንኩን ከከፈቱ በኋላ ለማስፋትና በደንብ ለማንበብ ጽሁፉን ይጫኑት!
እዚህ ይጫኑ 1

እዚህ ይጫኑ 2

እዚህ ይጫኑ 3

እዚህ ይጫኑ 4

Monday, January 25, 2016

ተሐድሶ ወደቀደመ የወንጌል ቃል መመለስ ማለት ነው!

(ተሐድሶ ተስፋዬ)

ለኦርቶዶክስ የተከለከለ ፅሑፍ !!
ድንገት እንኳ ብታነቡም እንዳትጨርሱት !!

በሰላም አለቃ በክርስቶስ ኢየሱስ ስም ሰላም ብያለሁ፣ሰላሙ ይብዛላችሁ !! እስኪ ደግሞ ትንሽ ለክርስቶስ ብዬ ልሰደብ !!

የኦርቶዶክስ ህዳሴ በኛ በልጆቿ ከግብ ይደርሳል !! አሜን የምትሉ ለምልሙልን !! እንደምንም አንብቧት ።
ከተሀድሶ እንቅስቃሴዎች ዉስጥ በትንሹ ላካፍላችሁ...

1.1. ""ማርታን ወደ ማርያም የመቀየር ተሐድሶ""

ሰዎች ወደ እግዚአብሔር ቃል ካልተመለሱ ወደ እግዚአብሔር አይመለሱም፤ ጌታ እንዳለው
“የሚያስፈልገው ግን ጥቂት ወይም አንድ ነገር ነው፤ ማርያምም መልካም ዕድልን መርጣለች፤ ከእርስዋም አይወሰድባትም አላት ።” (ሉቃ.10፥42)፡፡ እነማርታ ቤተ ክርስቲያኑን ሞልተውታል፤ ዳቦ ጋግሩ፤ ወጥ ሥሩ፤ልብስ እጠቡ፤ከበሮ ምቱ ሲባሉ አይሰለቻቸውም፤ የክርስቶስን ወንጌል ተማሩ ሲባሉ ግን እንኳንስ ሊማሩ የሚማሩ እኅቶችና ወንድሞችን እንኳን ማየት አይፈልጉም፡፡ በዓመት አንድ ቀን የጥምቀት በዓል ሲመጣ ለማይሰማ ታቦት መንገድ ይጠርጋሉ፤ ምንጣፍ ያነጥፋሉ፤ ጉልበታቸውን ሳይሰስቱ ያገለግላሉ፤ የሚሰሙት ወንጌል ግን የለም፤ የእነዚህ ሰዎች አገልግሎት የቅናት እንጅ የእምነት አይደለም፡፡
ለእግዚአብሔር ቃል ቅድሚያ ካልሰጡ ደግሞ ለማይሰማና ለማያይ ታቦት ምንጣፍ እንዳነጠፉ፣ ግብር እንደገበሩ ይኖራሉ እንጅ ዕረፍትን አይገኙም፡፡ እነዚህ ሰዎች ለጊዜው ደስተኞች ናቸው፡፡ ዐሥር ዐመት በዚህ መልኩ ካገለገሉ በኋላ “አሁን ለመዳናችሁ እርግጠኞች ናችሁን?” ብለን ብንጠቃቸው እንኳንስ እርግጠኞች ሊሆኑ እንዲያውም ፍርሐታቸው ጨምሮ እናገኛቸዋለን፤ ስንጠይቃቸው የሚሰጡን መልስ “ማንም ከመሞቱ በፊት ለመዳኑ እርገጠኛ መሆን አይችልም” የሚል ነው፡፡
እነዚህ ሰዎች ይንም አይነቱን ወንጌል ከየት እንዳገኙት እናውቃለን፡፡ አዲሱ ትምህርት ነው፤ ሐዋርያት ያወገዙት፣ “ማንም እኔ ካስተማርኋችሁ የተለየ ወንጌል ቢያስተምራችሁ የተወገዘ ይሁን” (ገላ.1፡8) ብለው ያስጠነቀቁን ትምህርት ይህ ነው፡፡
ስለ ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ክርስቶስ ለመሄድ መናፈቅ አልሰሙም ማለት አንችልም፤ የሰሙትን እንዳላመኑት ግን እናያለን፡፡ ክርስቶስ በቃሉ “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘለዓለም ሕይወት እንዲኖረው እንጅ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወድዶአልና፤ በእርሱ የሚያምን አይፈረድበትም ፤ በእርሱ የማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስላላመን አሁን ተፈርዶበታል ” (ዮሐ.3፡16-17) ያለው ቃል ዕረፈት ካልሰጠና እርግጠኛ ካላደረገን በምን እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን? ከዚህ ከጸና እውነት ያንሸራተተንና ከዓለቱ ነቅሎ በአሸዋ ላይ የሠራን ማነው? ይህን ከእግዚአብሔር እውነት የሚነቅል ትምህርት በእግዚአብሔር ቃል መዋጋት ተሐድሶ ነው፡፡
ብዙዎቻችን “የአገልግሎት ማኅበራት አባላት ነን” እያልን ከበሮ ለመምታት፣ ለመዘመር፣ ታቦት ለማክበር፣ ምንጣፍ ለማንጠፍ፣ የቤተ ክርስቲያን ቅጥረ-ግቢ ለማጽዳት፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ታቦት የሚሄድባቸውን መንገዶች ተከትሎ ለማጽዳትና ሰንደቅ ዓላማ ለመስቀል እንጅ የእግዚአብሔርን ቃል ለመስማት ጊዜ የለንም፡፡ ቃለ እግዚአብሔርን መስማት እግዚአብሔርን ማገልገል ነው ብለን የምናምን ስንቶቻችን ነን? ማርታ ማርያምን ለምን ተቃወመቻት? ቃለ እግዚአብሔርን መስማት እግዚአብሔርን ማገልገል እንደሆነ ስላልገባት ነበር፡፡ ክርስቶስ ግን ለሁሉ የሚበቃውን አንድ ታላቅ አገልግሎት አከበረ፤ እርሱም ቃሉን መስማት ነው፡፡ ተሐድሶ የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት የመታደስ አገልግሎት ነው፡፡
የጸጋ ስጦታዎቻችን የተለያዩ ናቸው፤ ለአንዱ የተሰጠው ለሌላው ላይኖረው ይችላል፤ የሚዘምር ላይሰብክ፣ የሚሰጥ ላያስተምር ይችላል፤ ለሁላችንም የተሰጠን ጸጋ ግን የእግዚአብሔርን ቃል የመስማት አገልግሎት ነው፤ በዚህ አገልግሎት ውጤታማ ያልሆነ ሰው ደግሞ በሌላ አገልግሎት ውጤታማ መሆን አይችልም፡፡ እግዚአብሔርን ስለማያውቀው የሚያገለግለው የሚያውቀውን ራሱን፣ አለቃውን፣ ታቦቱን፣ ገንዘብን፣ ክብርንና እውቅና መፈለግን፣ ተቃውሞን፣ ሥርዐትንና ታሪክን፣ እኔ ብቻ ትክክል ነኝ ማለትን እንጂ እግዚአብሔርን ሊያገለግል አይችልም፡፡ ተሐድሶ ከዚህ አይነት እስራት ነጻ ወጥቶ እግዚአብሔርን እንደቃሉ በእውነትና በመንፈስ ማምለክ (ማገልገል) ነው፡፡
.
1.2. የሚያስፈልገን ጸበል ወይስ ወንጌል?

ለነማርታ እነርሱ ካልደከሙ የእግዚአብሔር ጸጋ አይበቃም፡፡ የእነርሱ ማሰሮ የምትሞላው የእግዚአብሔር ጸጋ ሲፈስስባት ሳይሆን እነርሱ የፈጩት ዱቄት ሲጨመር ብቻ ነው፡፡ ቃሉን መማር መሥዋዕት አይደልም፤ ጸበል ካልጠጡ፣መክፈልት ካልበሉ እግዚአብሔርን አላገለገሉትም፡፡ ቃሉን ካልሰሙ ቤተ ክርቲያን መሳለም ምንድን ነው? ጸበል ውሃ አይደለምን? ህሊናችንን ከሞተ ሥራ ሊያነጻ የሚችል መለኮታዊ ጸበል የእግዚአብሔር ቃል ነው፤(ዕብ.9፡14) ዲያቆናት በኩስኩስት ጸበል ከሚቀዱ ይልቅ ከመለኮታዊው ጸበል ከቃሉ ለምእመናን የማጠጣት አገልግሎት ቢጀምሩ ምናለበት? እስከመቼ ምእመናን በውሃ እየተታለሉ ይኖራሉ? የሕይወት ውሃ መጽሐፍ ቅዱስ ተከድኖ ወይም አልባሌ ቦታ ተጥሎ ዘወትር የውሃ መቅጃ ኩስኩስት ስናጥን የምንኖረው እስከ መቼ ነው? ኧረ ተዉ ጎበዝ የእግዚአብሔር ፍርድ ሳይገለጥ ወደ ቃሉ እንመለስ! ተሐድሶ ከውሃና ከመክፈልት ወደ ሕይወት ውሃ ወደ እግዚአብሔር ቃል መመለስ ነው፡፡
እግዚአብሔር የሕይወት ምግብ አዘጋጅቶ እየጠበቀን እኛ እግዚአብሔር የሰበሰበውን ሕዝብ የሚያልፍ ምግብ ያውም ውሃ አጠጥተን የምንልከው እስከመቼ ነው? ወደ እግዚአብሔር ቃል ከመመለስ የበለጠ ምን ተሐድሶ አለ? ሰውን ወደ እግዚአብሔር ቃል ከመመለስ የበለጠ አገልግሎትስ የት ይገኛል? ተሐድሶ አዲስ ነገር አይደልም፤ እግዚአብሔር ተረስቷልና ይታሰብ፤ እግዚአብሔር ክብሩንና ቦታውን ተነጥቋልና ወደ ክብሩ ይመለስ የሚል ተጋድሎ ነው፡፡ ክብሩን ለማንም እንደማይሰጥ የተናገረው እግዚአብሔር ያስነሳው አገልግሎት እንጂ አንዳች የሰው ፍላጎት የለበትም፡፡ እናውቃልን ስንዴ፣ ሰልባጅ፣ ብር ፈልገው የሚሠሩ፣ የፕሮቴስታንት ተላላኪዎች እንደምንባል፡፡ እኛ ግን የቤተ ክርስቲያኒቱ መቆሳቆል፤ የነገሮች ቅጥ ማጣት፣ በእግዚአብሔር ቦታ የማይሰሙና የማያዩ ታቦታት መቀመጥና መክበር፣ ንስሓ መግባት አለመቻላችን ቤተ ክርስቲያናችንን እየጎዳ ያለ መሆኑ፣ ያሳሰበን የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንጂ በምንም ምክንያት በቤተ ክርስቲያን ላይ ክፉ አሳብ ያለን ሰዎች አይደለንም፡፡ እንዲውም በአመንነው እውነት ምክንያት ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር የሚጠቅም ልዩ ሸክም (ራእይ) ያለን ሰውች ነን፤ ራእያችን እንዳይዘገይ፣ መባረካችን እንዲፈጥን በመንገዳችን እንቅፋት አትሁኑብን እንላለን እንጂ በፍጹም እግዚአብሔር የማይፈልገው፣ ቤተ ክርስቲያንንም ሆነ ሀገርን የሚጎዳ አጀንዳ የለንም፡፡ አገልግሎታችን ሰማያዊና የከበረ መሆኑን እናውቃለን፤ ለዚህም ነው በነገር ሁሉ ስንፈተን “የማምነውን አውቀዋለሁ” ብለን ጸንተን እየተጓዝን፣ በየጊዜው ደግሞ እየበዛን ያለነው፡፡ የሚያበዛን የሕይወት ቃል የሆነው የእግዚአብሔ ቃል ነው፡፡ በተሐድሶ ያለ ሕዝብ በውሃ ዳር የተተከለ ዛፍ ነው፤ ቅጠሉ አይጠወልግም፤ ዘወትር ያፈራል እንጂ የመድረቅ ሥጋት የለበትም፡፡ ተሐድሶ ይህ ነው!
.
1.3. የምንሰብከው እግዚአብሔርን ወይስ የእኛን ሥነ ምግባር?

የሚያስፈልገው ነገር አንድ ነው፤ የእግዚአብሔር ቃል፡፡ የእኛ ገድልና ድርሳን፣ የእኛ አመለካከትና ዕወቀት፣ የእኛ ቅኔና ትርጓሜ በቦታው ጠቃሚ ቢሆንም በእግዚአብሔር ክብር ላይ መጋረጃ ሲሆን ግን ጉዳት እንጂ ጥቅሙ አይታየንም፤ የሕይወት መንገድ የተገለጠበት መጽሐፍ “መጽሐፍ ቅዱስ” ነው፡፡ ይህን እውነት ማንም ማስተባበል እንደማይችል እናምናለን፡፡ ወደ እግዚአብሔር ቃል እንመለስ! (Back to the word of God!) ምንም ብንሰብክ፣ ምንም ብንቀኝ፣ ምንም ብናከማች የእግዚአብሔር ቃል ካልሆነ ይበተናል፡፡
ይህ ነገር ለምን ያሳስበናል? ሰዎች እንዲለወጡ፣ ንስሓ እንዲገቡ፣ እንደእግዚአብሔር ቃል እንዲመላለሱ እግዚአብሔር ይፈልጋል፤ ይህ ሊሆን የሚችለው ደግሞ እግዚአብሔርን በቃሉ መሠረት ስናውቀው ብቻ ነው፡፡ የግብፅ ፓትርያርክ የነበሩት አቡነ ሺኖዳ የተናገሩትን ምሳሌ አድረገን እንመልከት፤ “I confess before You, O Lord that I ought to have changed my trend of writing. I confess-in shame-that I often talked to people about virtue but little did I talk to them about you, though you are all in all” (The release of the spirit p.14) መልእክቱ ወደ አማርኛ ሲመለስ እንዲህ የሚል ነው፡፡ “ከአሁን በፊት ስጽፍበት የነበረውን ልማዴን መለወጥ እንደነበረብኝ አቤቱ በፊትህ እናዘዛለሁ፤ ለሕዝቡ ስለ ምግባራት (ስለመልካም ምግባር) ዘወትር ብዙ እንደ አስተማርሁ፣ ብንም እንኳን አንተ ሁሉ በሁሉ ብትሆንም ስለአንተ ግን ጥቂት እንደነገርኋቸው በሐፍረት እናዘዛለሁ፡፡” ስለ እግዚአብሔር ሳይሆን ስለ ሥነ ሥርዐት ስንሰብክ ከኖርን የምናልመውን ለውጥ ማምጣት አንችልም፤ የሚለውጠው እግዚአብሔር እንጅ የእኛ ቃል አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ በቃሉ እንጅ በእኛ የስብከት ጥበብ አይሠራም፡፡ እግዚአብሔር በቃሉ እንጂ በእኛ ተረት ለመጽናት ቃል ኪዳን የለውም፡፡
ዛፉን እየነቀልንና እያደረቅን ፍሬ የምንፈልገው ከየት ነው?
እስኪ ልብ በሉ! እግዚአብሔርን ከሰው ልብ የሚያፈናቅል (እንደዛፍ ተክል የሚነቅል) ትምህርት እያስተማርን በጎ ምግባር የምናገኘው ከምኑ ነው? አቡነ ሺኖዳ እንዳሉት ስለ እግዚአብሔር ሳይሆን ስለ በጎ ሥራ ስንሰብክ የምንኖረው እስከመቼ ነው? መቼም ቢሆን የሰይጣንን አሳብ አንስተውም፤ ዛሬስ ብሎ ብሎ ተሐድሶ መልካም ሥራን መቃወም ጀመረን? ተመልከቱ! ተሐድሶ ለየለት! የሚል ሰው አይጠፋም፡፡ እያልን ያለነው በዛፉ የማይኖር ፍሬ አያፈራም፤ ሰውን ከዛፉ የሚቆርጥና የሚያደርቅ ለመጥፋትና ለመቃጠል የሚያዘጋጅ የሐሰት ትምህርት ከቤተ ክርስቲያን ይራቅ፤ ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት ትታደስ ነው፡፡ይህ ነው ተሐድሶ!
በክርስቶስ የምንኖረው በቃሉ ስንኖር ብቻ ነው፤ ቃሉን እየተቃወምን ወይም ቃሉን ከአትሮንስ አውርደን የእኛን ተረት አትሮንስ ላይ የምንሰቅል ከሆነ፣ ዐውደ ምሕረቱን እንደ ስሙ የምሕረት ማወጃ አደባባይ ሳይሆን የሚያስር ትብትብ መስበኪያ ካደረግነው፣ እግዚአብሔር በቃሉ ነጻ ሊያወጣው የሚፈልገውን ሕዝብ የበለጠ የእስራት ቀንበር ከጫንንበት የት አለ የእኛ የክርስቶስ መልእክተኞች መሆን? የምንሟገተው ለማን ነው? ለራሳችን ወይስ ለክርሰቶስ? ለክርስቶስ ከሆነ ቃሉን ለምን አናጠናም/አንሰብክም? ዓለምን መቃወም የምንችለው በቃሉ ብቻ ነው፡፡ ለእኛ የተለየ ጥበብ የለንም፤ያለን ማረጋገጫ ቃሉ ብቻ ነው፡፡ ተሐድሶ ይህ ነው! ወደ እግዚአብሔር ቃል መመለስ! እግዚአብሔር ይመልሰን! የቤተ ክርስቲያናችንን የተሐድሶ ተስፋ በቃሉ እንደገና ወደ ክብሯና ቅድስናዋ የመመለስዋን ትንሣኤ ለማየት ነው!!!
ኢየሱስ ያድናል !!

Sunday, January 24, 2016

"ቅድስና ለእግዚአብሔር"


(ተረፈ አበራ)
ሰው በክርስቶስ ሲያምን ጽድቅ ሆኖ ይቆጠርለታል ።ሮሜ 4:25 ይህ ማለት በታረሰ መሬት ላይ ተተክሎ እንደ ጸደቀ ወይን ይሆናል።ጻድቅ እንደ ዘንባባ ያፈራል እንደ ሊባኖስ ዝግባ ይለመልማል እንደሚል መጽሐፍ ፍሬ ያፈራል።መዝ 29:92 ፍሬው ቅድስና ይባላል።ጽድቅና ቅድስና እምነትና ሥራ ይባላሉ ።ያዕ 2:14 ቅድስና መለየት ማለት ሲሆን ሰው በክርስቶስ ጸጋ መጽደቁን የሚያረጋግጥበት የመንፈስ ፍሬ ነው ።ይህም ማለት ውስጣዊ ጤንነት እና ንጹህነት ወይም ከእንከን መራቅን ያመለክታል።እግዚአብሔር በባህሪው ቅዱስ ነው ።ሰዎችን በጸጋው ይቀድሳል።
  ቅድስና የሚያስፈልገን ነገር ግን ያልፈለግነው የሕይወት ውበት ነው።ደስታን፣ብልጽግናን፣ሰላምንና ስኬትን በምንፈልግበት መጠን ቅድስናን ፈልገን እናውቅ ይሆን? ቃሉ፦'ትቀደሱም ዘንድ ፈልጉ፥ያለ እርሱ ጌታን ሊያይ የሚችል የለምና።' ይላል።ዕብ.12፥14 ቅዱሱን ጌታ ለማየት የቅድስና ጥሪውን በመቀበል፣በደሙ በመታጠብ ከዓለም፣ ከኀጢአት፣ ከርኩሰትና ከሥጋ ሀሳብ በመለየት መኖር ያስፈልጋል።'እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ ተብሎ ስለ ተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደ ሆነ እናንተ ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ።'1ኛ ጴጥ. 1፥15-16።ክርስትና ለእግዚአብሔር የመለየት ኑሮ ነው።ልዩነቱ የበጎ ተጽዕኖ አቅም ነው።በተራራው ጌታ የሰበከንን የአማኝ ኑሮ ብናጠና ብልጫችንን እንረዳለን። ለሚበልጠው ታጭተን በሚያንስ አኗኗር እንዳንገኝ እናስተውል። በቅዱሱ ፊት በተጣለ ማንንነት መቆም አይቻልም።በሰው ፊት እንኳ ቆሽሾ መቅረብ ምን ያህል ይከብዳል? 'እኔ ኤልሻዳይ ነኝ፤ በፊቴ ተመላለስ፥ ፍጹምም ሁን፤' ዘፍጥረት 17፥1 ያለውን ጌታ ነው የምናመልከው። እግዚአብሔር የምንቀደስበትን መስዋእት አዘጋጅቷል። የተዘጋጀው መስዋእት ልጁ ነው።ህሊናችንን ቀድሶ መንፈሳችንን አንጽቶ በደላችንን አጥቦ ሊያቆመን ወደሚችለው እንቅረብ።አሮጌ(ያደፈ ልብስ)አልብሶ የሚከሰንን በደሙ ኀይል በስሙ ስልጣን ጥሎአል።ራእይ 12፥11 ቀዳሹ እኛን መቀደስ ፈቃዱ ነው እኛ መቀደስ እንፈልጋለን?ብሉይ ኪዳን 'ቅዱሳን ሁኑ'(ዘሌ 19፥2) ያለን ቅዱሱን ልጁን ላከ።ቀዳሹ ጌታም እኛን ተቀዳሾቹን በደሙ አነፃ።ከኀጢአታችን አጠበን(ራእይ 1፥6) ቀደሰን(1ቆሮ 6፥11) ክብሩን እንድናበራ ለየን።በመሆኑም እኛ ለርስቱ የተለየን ቅዱስ ሕዝብ ነን።(1ጴጥ 2፥9)።ለለየን ተለይተን መኖር ይጠበቅብናል።ቅድስና የሕይወት ዘመን ኑሮ ነው፡፡ስለዚህ ሁልጊዜ ሀሳባችንን ልናነፃ፣ንግግራችንን ልንገራ፣ ሰውነታችንን ከርኩሰት በጸጋው ኀይል ልንጠብቅ ይገባል። ቅዱሳን ለመሆን መጠራታችንን አንርሳ።(ሮሜ 1፥7)። የተጠራነው ለርኩሰት አይደለም።'ለርኵሰት ሳይሆን እግዚአብሔር በቅድስና ጠርቶናልና።"1ኛ ተሰሎንቄ 4፥7። ስለዚህ አባታችንን ለመምሰል በአንደበት ብቻ ሳይሆን በሕይወትም በቅድስና ማደግ አለብን።አባታችን መልኩን በኛ ሕይወት ውስጥ የማየት ናፍቆት አለው።የጠራን በባሕርይው ቅዱስ እንደሆነ እኛም በኑሯችን ሁሉ ከአለም እድፍ ራሳችንን በመጠበቅ በቅድስና መኖር አለብን። የቀደሰንን እንድንመስል ተወስኗል።'ልጁ በብዙ ወንድሞች መካከል በኵር ይሆን ዘንድ፥ አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአልና።'ሮሜ 8፥29።አስቀድሞ ወደታሰበልን ያድርሰን፤ካላደረሰን መድረስ የለምና። ይቀጥላል! እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን !!


Wednesday, January 20, 2016

ተቀባይነት ያጣ እውነት!



ብዙ ብለናል፤ ብዙ ተብሏል።  ችግሩ ያለው የሚነገር እውነት አለመኖሩ ሳይሆን እውነቱን የሚቀበል መጥፋቱ ላይ ነው። ተቀባይነት ያጡ እውነቶችን መጽሐፍ ቅዱስን ዋቢ አድርገን እናቀርባለን።

1/ ታቦት

ታቦት ማለት ማደሪያ፤ማኅደር ማለት ነው።  ቃልኪዳናዊ አሠራሩም ከዚህ የሚከተለውን ይመስላል።
«እኔ እንደማሳይህ ሁሉ፥ እንደ ማደሪያው ምሳሌ እንደ ዕቃውም ሁሉ ምሳሌ፥ እንዲሁ ሥሩት። ከግራር እንጨትም ታቦትን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፥ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን። በውስጥና በውጭም በጥሩ ወርቅ ለብጠው፤ በእርሱም ላይ በዙሪያው የወርቅ አክሊል አድርግለት። አራት የወርቅ ቀለበቶችም አድርግለት፥ እነርሱንም በአራቱ እግሮቹ ላይ አኑር፤ በአንድ ወገን ሁለት ቀለበቶች፥ በሌላው ወገን ሁለት ቀለበቶች ይሁኑ። መሎጊያዎችንም ከግራር እንጨት ሥራ፥ በወርቅም ለብጣቸው። ለታቦቱ መሸከሚያ በታቦቱ ጐን ባሉት ቀለበቶች መሎጊያዎቹን አግባ። መሎጊያዎቹም በታቦቱ ቀለበቶች ውስጥ ይኑሩ፥ ከቶም አይውጡ። በታቦቱም ውስጥ እኔ የምሰጥህን ምስክር ታስቀምጣለህ። ከጥሩ ወርቅም ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ የስርየት መክደኛ ሥራ። ሁለት ኪሩቤል ከተቀጠቀጠ ወርቅ ሥራ፥ በስርየት መክደኛውም ላይ በሁለት ወገን ታደርጋቸዋለህ» ዘጸ 25፤10-18
ይህንን የእግዚአብሔር መመሪያ ያላሟላ ታቦት፤ ታቦት ሊባል አይችልም። ከዚህ የሚጨመርም፤ የሚቀነስም ከእግዚአብሔር  ቃል ያፈነገጠ ነው። ይህ አንዱ ታቦት ሁለቱን የምስክር ጽላቶች ይይዛል። ካህናቱ ሲሸከሙም በመሎጊያዎቹ ጽላቱ ውስጥ እንዳለ አራት ሰዎች በአንድ ጊዜ ይሸከሙታል እንጂ አናት ላይ ቁጢጥ የሚል ጽላት የለም። ይህ ያፈጠጠ ያገጠጠ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ነው። ይህ የእግዚአብሔር ቃል እንዲሻሻል የተነገረበት ጊዜ የለም። ዛሬ ታቦት የሚባለው ከየት የመጣ ነው? ዓላማው፤ አሰራሩ፤ እቅድና ግቡ ምንድነው? ብዙ ሰዎች ስለተከተሉት ወይም እድሜ ጠገብ ስለሆነ ውሸት መቼም ቢሆን እውነት ሊሆን አይችልም። ታቦትን የተመለከተ የእግዚአብሔር ዓላማ በዚህ ዘመን ለማንም አልተሰጠም።

2/ጽላት፤

 ጽላት ሁለቱ የኪዳን ሰሌዳዎች ናቸው። 10ቱ የእግዚአብሔር ትዕዛዛት የተጻፈባቸው ሰሌዳዎች ስለሆኑ ጽላት ተብለዋል። ሙሴ ጽላቶቹን ሊቀበል ሁለት ጊዜ ወደተራራ ወጥቷል። የመጀመሪያውን ጽላት የቀረጸውና በጣቱ የጻፈባቸው እግዚአብሔር ራሱ ነው። «እግዚአብሔርም ከሙሴ ጋር በሲና ተራራ የተናገረውን በፈጸመ ጊዜ በእግዚአብሔር ጣት የተጻፈባቸውን ከድንጋይ የሆኑ ሁለቱን የምስክር ጽላቶች ሰጠው» ዘጸ 31፤18
የመጀመሪያዎቹ ከተሰበሩ በኋላ ጽላቱን ከእብነ በረድ ዳግመኛ የቀረጸው ሙሴ ራሱ ሲሆን በላዩ ላይ ትዕዛዛቱን በጣቱ የጻፈባቸው ግን እግዚአብሔር ነው።
 «ሙሴን አለው፦ ሁለት የድንጋይ ጽላቶች እንደ ፊተኞች አድርገህ ጥረብ፤ በሰበርኻቸው በፊተኞቹ ጽላቶች የነበሩትን ቃሎች እጽፍባቸዋለሁ» ዘጸ 34፤1   ዘዳ10፤4
መጽሐፍ ቅዱስ ስለጽላት በተናገረበት የትኛውም አንቀጽ ውስጥ ሙሴ ጽላቶቹ ላይ ጻፈ የሚል ገጸ ንባብ የለም። ከእብነ በረድ አስመስለህ ቅረጽ የተባለውን ትዕዛዝ አንተው ጻፍባቸው የተባለ በማስመሰል ራሳቸው የሚጽፉባቸው ከየት በተገኘ ትዕዛዝ ነው? በወቅቱም ጽላቶቹ ላይ እግዚአብሔር ራሱ የጻፈባቸው ትዕዛዛት እንጂ ምስል ወይም ስዕል አይደለም። ይህስ ከማን የተገኘ ትምህርት ነው? ስንት ጽላት? ስንት ታቦትስ? እግዚአብሔር ሰጥቷል?

3/ ምልጃና ማስታረቅ

«አማላጅ» የሚለው ቃል የተገኘው «ማለደ» ከሚል ግስ ሲሆን «ማለደ» ማለት ደግሞ «ለመነ» ወይም «ጸለየ» ማለት ይሆናል። « መማለድ ፤ ማማለድ… » ማለት  «መለመን ፣ ማስታረቅ» ሲሆን «አማላጅ» ደግሞ ይህን ተግባር የሚያከናውን ነው፡፡ ተግባሩ ደግሞ «ምልጃ» ይባላል፡፡
አዳም ከእግዚአብሔር ፊት በኮበለለ ጊዜ ወዴት ነህ? ሲባል እነሆ በዚህ ተሸሽጌአለሁ አለ።                         «እግዚአብሔር አምላክም አዳምን ጠርቶ፦ ወዴት ነህ? አለው።እርሱም አለ፦ በገነት ድምፅህን ሰማሁ፤ ዕራቁቴንም ስለ ሆንሁ ፈራሁ፥ ተሸሸግሁም» ዘፍ 3፤9-10
ይህ የኮበለለው ሰው፤ አዳም ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ነበረበት። መቼ? ማንስ? ያስታርቀዋል?
በዘመነ ብሉይ የማስታረቅ አገልግሎት የተሰጠው ለካህናቱ ወገን ብቻ ነበር። የኃጢአት ማስተሰሪያ መስዋዕትም ዕለት ዕለት ይቀርብ ነበር።
« ዕለት ዕለትም ስለ ማስተስረይ ለኃጢአት መሥዋዕት ወይፈኑን ታቀርባለህ፤ ማስተስረያም ባደረግህ ጊዜ መሠዊያውን ታነጻዋለህ ቅዱስም ይሆን ዘንድ ትቀባዋለህ» ዘጸ29፤36 ይህ የማስታረቅ አገልግሎት ፍጹማዊ አገልግሎት አይደለም። በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የተጋረደውን የጥል ግድግዳ ማፍረስ የማይችል ጊዜአዊ አገልግሎት ነበር። ስለዚህም በአዳምና በልጆቹ ላይ የእግዚአብሔር ቁጣ ነበረ። ይህ የበደል ቁጣ ሊመለስ የሚችለው ይህንን መሸከም የሚችል መስዋዕት ሲኖር ብቻ ነው። ለዚህም አገልግሎት ብቁ መሆን የሚችለው ደግሞ ከኃጢአት በቀር በሁሉ የተፈተነ ሊሆን ይገባዋል።
«ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም» ዕብ 4፤15
ስለዚህም ሰማያዊ ሊቀካህን ኢየሱስ ከእግዚአብሔር ፊት ለኮበለልነው ለአዳም ልጆች ሁሉ አስታራቂ መስዋዕት ሆነ። ይህንንም ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ አለ።«ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ»ኢሳ53፤12
ኢየሱስ ክርስቶስ አስታራቂና ማላጅ ባይሆን ኖሮ ሥጋ ከለበሰ ከሰው ልጅ ማንም ቢሆን የማስታረቅ አልገልግሎትን ሊፈጽም አይችልም ነበር። የክርስቶስ ኢየሱስን አስታራቂነት ልዩ የሚያደርገው የማማለድ ብቃቱ ብቻ ሳይሆን ዕለት ዕለት የሚደረገውን የማስታረቅ አገልግሎት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማስቀረት መቻሉ ነበር።
«ሊቀ ካህናትም ሁሉ ዕለት ዕለት እያገለገለ ኃጢአትን ሊያስወግዱ ከቶ የማይችሉትን እነዚያን መሥዋዕቶች ብዙ ጊዜ እያቀረበ ቆሞአል እርሱ ግን ስለ ኃጢአት አንድን መሥዋዕት ለዘላለም አቅርቦ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ» ዕብ 10፤11-12
ስለዚህ የኢየሱስ ክርስቶስ የማስታረቅ አገልግሎት አንዴ የተፈጸመ፤ ነገር ግን ዕለት ዕለት ወደእግዚአብሔር የሚመጡትን ሁሉ የሚያድን የዘላለም መስዋዕት ስለሆነ ዛሬ አዲስ የሚፈጸም የልመናና የማስታረቅ አገልግሎት የለም። አንዳንዶች ዛሬም የሚለምን ያለ የሚመስላቸው አሉ። አንዳንዶች ደግሞ አንዴ የፈጸመው አገልግሎት አብቅቷል፤ ከእንግዲህ አይሰራም የሚሉ አሉ።  አማላጅነትን ለሰዎች ያስረከቡ ሁሉ የክርስቶስን ዘላለማዊ ብቃት ይክዳሉ። በሌላ መልኩም የሰዎችን አማላጅነት ለመከላከል ሲሉ ኢየሱስን ዛሬም የሚማልድ አድርገው የሚስሉም አሉ። ሁለቱም ጽንፎች የኢየሱስን ማንነት ካለማወቅ የሚመነጭ አስተሳሰብ ነው።እውነቱ ግን ዕብራውያን መጽሐፍ እንዳለው፤
«እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤ እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል። ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤ እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና» ዕብ 7፤23-27
ስለዚህ በአጸደ ነፍስ ያሉ ቅዱሳን፤  ሰዎች ከበደል ወደ ጽድቅ፤ ከኃጢአት ወደቅድስና ሰዎች እንዲመለሱ ይማልዳሉ፤ ይለምናሉ ማለት ለኃጢአተኛው ምትክ ሆነው ያድኑታል ማለት አይደለም። አንዴ የተፈጸመው የማማለድና የማስታረቅ አገልግሎት በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው።

Friday, January 1, 2016

ስለአንዳንድ በኢ.ኦ.ተ.ቤ.ክ ላይ…ከአንዳንድ የኦሮሞ ጸሐፍት የተሰነዘሩ…ያስቀየሙኝ ክታቦች!!


 (በአማን ነጸረ ክፍል 4)

(7.1) ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃይለሥላሴ በጻፉት በመጀመሪያው ‹‹ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ›› መጽሐፋቸው ገጽ-137 ይሕንኑ ሁኔታ (የቶፋ ሥርዓት) በጥቁምታ ያመላክቱናል፤እንዲህ ሲሉ ‹‹በኢትዮጵያ የካሕናት ቁጥር እጅግ ብዙ ነው፡፡ለነዚሁም ሁሉ መንግሥት ከያውራጃው ከግማሽ እስከ አንድ ጋሻ መሬት ለእያንዳንዱ ካሕን ርስት እያደረገ ሰጥቷቸዋል፡፡ይኸውም ርስት እየሆነ የተሰጠው መሬት ለልጅ ልጅ የሚያልፍ [በመሆኑ] ቤተክርስቲያን ልታዝዝበት አትችልም፡፡በዚህም ላይ ከንጉሠ-ነገሥቱ ዠምሮ መሳፍንቱ መኳንንቱም ሌላውም እነሱን የመሰለው ሁሉ ወይዛዝርት እንኳ ሳይቀሩ የቤተክርስቲያን ገበዞች እየሆኑ ከ200 እስከ 700 ጋሻ መሬት ንጉሠ-ነገሥቱ ርስት እያደረገ ይሰጣቸዋል...›› በማለት ይዞታው በወሬ የኢኦተቤክ እየተባለ ስመ-ንብረቱ (title deed) ግን በተግባር በንጉሡ፣በመሳፍንትና ወይዛዝርት እጅ እንደነበረ፤እነዚህ መሳፍንትና ወይዛዝርት ሲያልፉም ልጆቻቸው የቤ/ክ ትምህርት ባይማሩም ‹ገበዝ› በሚል መጠሪያ ርስቱን ወርሰው ደሃ ካሕናትን እያስቀደሱ በስመ ተዋሕዶ የሚያደርጉትን ብዝበዛ (የቶፋ ሥርዓት) ስሙን ሳይጠሩ ያብራሩልናል፡፡
(7.2) በ1967 ዓ.ም የመሬት-ላራሹ ዐዋጅ ሲታቀድ በካሕናት እጅ እንደዜጋ የነበረውን መሬት ሁሉ በነባሩ ‹‹የሲሶ መሬት ይዞታ›› ትረካ አጠቃሎ የመውረስ አዝማሚያ አስፈርቶ ነበር፡፡ሁኔታው ያሳሰባቸው የጊዜው የኢኦተቤክ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ በ1967 ዓ.ም ለደርግ በጻፉት ደብዳቤ ተቃውሞአቸውን ሲገልጹ ‹‹...ተጋኖ ሲነገር የኖረው ጨርሶ ያልነበረ የመንግሥት ሥልጣን ድርሻና የሀገሪቱ ሲሶ መሬት ወሬ ፈጽሞ ተረት ቢሆንም ያው ያለው መጠነኛ ድጋፍ እስካሁን ድረስ ከመንግሥት ሲሰጣት ቆይቷል›› በማለት ‹‹ያው ያለው መጠነኛ ድጋፍ›› እንዲቀጥል ተማጽነው ነበር፡፡ፓትርያርኩ ጥያቄያቸውን በ7 ነጥቦች አብራርተው ነበር ያቀረቡት፡፡2ቱን ብቻ ልጥቀስላቸው ‹‹1ኛ. የኢትዮጵያ ገዳማት መሬት ያንድነት ማኅበር እንደ መሆኑ መጠን ይኸው በይዞታቸው ያለው የንፍሮ መሬታቸው በይዞታቸው ስር እንዲቆይ እንዲፈቀድላቸው፣እንዲሁም ‹በርሷ (በኢኦተቤክ) ስም ተይዘው ሌሎች ወገኖች ሲጠቀሙባቸው የኖሩ መሬቶች ቢወሰዱ የምትጎዳበት ባይኖርም› እስከ ዛሬ በቀጥታ ስትረዳባቸው የቆዩ አንዳንድ መሬቶች በይዞታዋ ስር እንዲቆዩላት፤2ኛ. በግብርና ስራ የሚተዳደሩ ካሕናት ሁሉ ካሕንነታቸው ኢትዮጵያዊ ማንነታቸውን ስለማይሽረው እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የመሬት ድርሻቸውን የማግኘት መብታቸው እንዳይዘነጋባቸው››ብለው ጠይቀው ነበር (መምህር ኪዳነማርያም ጌታሁን፡ገ.102)፡፡
(7.3) በደስታ ተክለወልድ የአማርኛ መዝገበ ቃላት ገጽ 1267 ‹‹ወኪል፣ምትክ፣ተጠሪ፣ገባሪ›› ተብሎ ስለተተረጎመው ‹‹ቶፍነት›› ሌላ ዋቢ እንቁጠር፡፡‹‹የኢኦተቤክ አስተዳደር በየዘመናቱ››የተሰኘው መጽሐፍ ደራሲ ብፁዕ አቡነ ገሪማ (ዶ/ር) ስለዚህ ጉዳይ ሲተርኩ ‹‹ለቤተክርስቲያን መግባት የሚገባውን የግብር ገንዘብ መሳፍንቱ፣መኳንንቱ፣ባላባቶችና ወይዛዝርት በግብዝና በእልቅና፣በመሪጌትነት፣በድብትርና፣በቅስና፣በዲቁና እና በልዩ ልዩ [የ]ክሕነት [አገልግሎት] ስም ርስት እየያዙ በግል እየተጠቀሙ በተወሰነ ክፍያ ወይም በቶፍነት ካሕናትን ያስገለግሉ ነበር›› ይሉናል፡፡አቡነ ገሪማ ታሪኩን ሲቀጥሉ ‹‹…የቤ/ክ መተዳደሪያ ብዛት ጎልቶ ከመታየቱ በቀር ለካሕናቱ መተዳደሪያ ይሆን ዘንድ የተፈቀደው ርስተ - ጉልት የሚሰጠው ጥቅም የአገልጋዮች ካሕናትን ችግር ከመሸፈን አኳያ በቂ አልነበረም፡፡…ከሚያጋጥሙት ችግሮች መካከል፡- ያልቀናውንና በረሃማውን መሬት እየሰጡ የለማውን መሬት መቀማት፣ለም የሆነውን መሬት በጠፍ መሬት መለወጥ፣የኩታ ገጠም አቀማመጥ ያለውን ርስት ወደ ግል ይዞታ ማስገባት…ይገኙበታል›› ይላሉ (አቡነ ገሪማ፡ገ.64-70)፡፡
(7.4) ከላይ ያለችውን የ“ቶፍነት” ሥርዓት ጽንሰ - ሐሳብ ለመረዳት ከመርስዔኀዘን ‹‹ትዝታዬ›› መጽሐፍ ገጽ-92 ማሳያ እንጨምር፡፡የድጓ መምህር የነበሩት ኣባታቸው ሲሞቱ የአባታቸውን መሬት ወርሰው እንደ ባለርስት መገበራቸው ቀርቶ እንዴት ወደ ቶፍነት እንደተሸጋገሩ ሲተርኩ ‹‹…እንግዲህ የምትገብረው በአባትህ ሥም አይደለም፣መሬቱ ለፊታውራሪ ጥላሁን ስለተሰጠ ሥመ - ርስቱ ተዛውሯል፤ሆኖም ለፊታውራሪ ጥላሁን በቶፍነት ልትገብር ትችላለህ…›› እንደተባሉ ይገልጻሉ፡፡ከመርስዔኀዘን አባባል እንደምንረዳው የመንግሥት ሹም የነበሩት ፊ/ሪ ጥላሁን ለድብትርና ተብሎ ለይስሙላ የተመደበውን ርስት ወርሰው ይዘው ደብተራውን (መርስዔኀዘንን) ‹‹ቶፋ›› አድርገዋቸዋል፡፡ታሪክ ግን ፊታውራሪ የያዙት ርስት ለስሙ የኢኦተቤክ ስለተባለ ብቻ ‹‹ሲሶ የቤተክሕነት ድርሻ›› ብላ ያልበላነውን ልታስተፋን ትጥራለች!!ቆዩማ ይቺን ታሪክ የሚሏትን ጉድ በጎጃምኛ ልስደባት ‹‹ኧግ!ይቦጭቅሽ!››
(7.5) ይሄን ሀቅ ጠጋ ብለው ያላዩልን እነ መኩሪያ ቡልቻ እና አባስ ሐጂም ነዋሪ ነባሪውን ስሑት የወሬ ጫፍ ይዘው <<...the clergy were....landlords,they owned Oromo peasants as Gabbars...>> ይሉናል!እርግጥ ይሕ በነአቶ አጽሜ ጸረ-ካሕናተ-ኦርቶዶክስ ጥላቻ ተከትቦ እስካሁን የሚናፈስ የታሪክ አረዳድ ኢህአዴጋውያንን ጨምሮ የብዙኃኑ ልሂቅ አረዳድ ስለሆነ እነ መኩሪያ ቡልቻንና አባስ ሐጂን ነጥሎ መውቀስ ኢ-ፍትሐዊ ሊሆን ይችላል፡፡በቁሳዊ ሀብትና በካሕናት ኑሮ ረገድ የዛሬዋ የኢኦተቤክ ያለችበትን ከቅድመ-1967 ዓ.ም የመሬት ዐዋጅ የተሻለ ኢኮኖሚያዊ አቅም ያስተዋለ ሰውማ በእርግጥም አቡነ ቴዎፍሎስ እንዳሉት በኦሮሚያም ሆነ በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች የሚተረከው ‹‹የሲሶ መሬት›› ድርሻ ‹‹ፈጽሞ ተረት›› እንደነበረ ይገለጽለታል፡፡እኛማ ትናንት በተወረሱባት ሕንጻዎች ምትክ ከደርግ የ5 ሚሊዮን ብር ምጽዋት ትጠብቅ የነበረች ቤ/ክ ዛሬ ገንዘብ አያያዟ ባያስደስተንም እንኳ በጀቷ ቢሊዮን መሻገሩን አይተናል፡፡እናም የትናቱ የተረት ተረት ‹‹ሲሶ ግዛት›› ከቶም አያቃዠንም!!አባቴ እንዲህ ይል ነበር ‹‹ድሮ ካሕን ስሙና ማዕረጉ ብዙ ነው፤በቤቱ ግን ሙሉ እንጀራ ቆርሶ የሚበላ ከስንት አንድ ነው፤በነገሥታቱ ከባቢ ካሉት በቀር ድሆችን ካሕናት የሚፈቅድ የለም፤ከነተረቱም ‹የካሕን ልጅ ስም ይጠግባል፤እንጀራ ግን አይጠግብም› ይባል ነበር፤መምህራኖቻችን የኖሩት ተማሪ ለምኖ እያበላቸው ነው፤አየ!፤ተውኝማ ልጄ!››
(7.6) ትውልዱ ባይገለጽለትም እኛ መከራና ስቃይ ከካሕናት ወላጆቻችን የወረስነው ‹ምድጃ የላቀን፤አመድ የወረሰን፤ደሃ የድሃ ልጆች› ወላጆቻችንን ዘበናይ ሁላ ተማርኩ ብሎ ‹‹ሲሶ-ሲሶ!›› እያለ በእንግሊዝኛ ሲዘባነንባቸው እንገረማለን፡፡በተሳልቆ ‹‹ኡኡቴ!ድንቄም ሲሶ!›› እንላለን፡፡ትናንት በነበሩ ብዙኃን ካሕናት ወላጆቻችን ያልተጠገበ ጥጋብ የዛሬዎቹ ሕያዋን ልጆቻቸው እንድንሸማቀቅ የሚሹትን የባለቅኔውን ድንቅ አባባል ተውሰን፡-
‹‹እስመ-እንዘ-ቦ፡ሕያወ፡እሞተ-ሥጋ፡ግዙፍ፣
ሞተ-ዮሴፍ፡አኃዊሁ፡ነገርዎ፡ለዮሴፍ፡፡››እንላቸዋለን--ለቀባሪው ማርዳት!!ሁሉን ትተን የታላላቆቹን ሊቃውንት የነክፍለ ዮሐንስ መራብና መታረዝ የሚያመላክቱና ቅኔያዊ ቁዘማዎቻቸውን የገለጹባቸውን ቅኔያት እንጠቃቅሳለን፡፡እንዲህ፡-
‹‹...ልብስየሂ፡ምንንት፡መንጦላእተ-ርኅቅት፡ነፍስ፣
እስመ-አነ፡ከመ-ዶርሆ፡እምላእለ-አብራክየ፡እለብስ፡፡››
እያሉ እኒያን የመሰሉ ሊቃውንት እርቃናቸውን እንኳ በቅጡ መሸፈን አቅቷቸው እንደ ዶሮ ከጉልበት በላይ ተራቁተው በ‹‹ሲሶ ግዛት››ተረት አእጽምቶቻቸው እረፍት ሲያጡ ከማየት የሚደርስብንን ሕማም በቅኔያቱ እናስታምማለን፡፡ደግሞም የዋድላው የኔታ ሲራክ ራሳቸውን ከአህያና በቅሎ ጋር እያነጻጸሩ የ30 ብር ዓመታዊ ደሞዝ ሰቆቃዊ አኗኗራቸውን፡-
‹‹አእዱግ፡ወበቅል፡እንዘ-ያወጽኡ፡ስልሳ፣
ሲራክ፡አምላከ-ዋድላ፡ተሰይጠ፤ለሠላሳ፡፡››
እያሉ የገለጹባቸውን ቅኔያት እያስታወስን እንግሊዝኛ ተናጋሪ ደባትሮቻችን ወደ ልባቸው ተመልሰው ሚዛኑን የጠበቀ ጽሑፍ እንዲያቀርቡል እንጸልያለን፡፡አንዳንዴም እንጎተጉታለን፡፡አልፎ አልፎም ሕመማቸው ሕመማችን መሆኑን ሳንስት በተጋነነ ቅሬታና ፍረጃ መስመር ሲለቅቁብን ከወዲህ የላላውን ለመወጠር ከወዲያ የተወጠረውን እንጎትታለን--እንዲህ እንዳሁኑ!
የላላው ይወጠር፤የተወጠረው ይርገብ፡፡ወይኩን ማዕከላዌ!አሜን!ይኹን፤ይደረግ!
፡፡፡፡፡፡፡፡በአማን ነጸረ፡፡መስከረም 2008 ዓ.ም፡፡፡፡፡፡፡፡
ማጣቀሻዎቼ!
ሀ. መጻሕፍት(ሃርድ ኮፒ)
1. ብፁዕ አቡነ ገሪማ (ዶ/ር)፣የኢኦተቤክ አስተዳደር በየዘመናቱ፣ጥቅምት 2000 ዓ.ም፣ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት
2. ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ(M.A)፣የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ታሪክ፣1986 ዓ.ም፣2ኛ እትም፣ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት
3. በኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንትና ጳጳሳት፣የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ከልደተ ክርስቶስ እስከ ፳፻(2000 ዓ.ም)፣በ2000 ዓ.ም፣ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት
4. አባ አንጦንዮስ አልቤርቶ (ዶ/ር) (ካፑቺን)፣የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ታሪክ በኢትዮጵያ፡ከብፁዕ አቡነ ጉሊየልሞ ማስያስ እስከ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ጃሮሶ (1841-1941 ዓ.ም)፣1993 ዓ.ም፣ንግድ ማተሚያ ድርጅት
5. ታቦር ዋሚ፣የውገና ድርሰቶችና የታሪክ እውነቶች፣በ2007 ዓ.ም፣3ኛ እትም፣አርቲስቲክ ማተሚያ ድርጅት
6. መርስዔኀዘን ወልደቂርቆስ፣ትዝታዬ፡ስለራሴ የማስታውሰው፣2002 ዓ.ም፣አስቴር ነጋ አሳታሚ ድርጅት፤ሮኆቦት አታሚዎች
7. ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ፣ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ (1ኛ መጽሐፍ)፣1965 ዓ.ም፣ብርሃንና ሰላም ወዳማዊ ኃይለሥላሴ ማተሚያ ቤት
8. አለቃ ተክለኢሱስ ዋቅጀራ (ሐተታ በዶ/ር ስርግው ገላው)፣የኢትዮጵያ ታሪክ፣2000ዓ.ም፣ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት
9. በቀለ ወልደማርያም አዴሎ፣የካፋ ሕዝቦችና መንግሥታት አጭር ታሪክ፣1996 ዓ.ም፣ሜጋ ማተሚያ ድርጅት
10. ዶናልድ ሌቪን (ትርጉም በሚሊዮን ነቅንቅ)፣ትልቋ ኢትዮጵያ፣2007 ዓ.ም፣አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ
11. ቅዱስ ያሬድ፣መጽሐፈ-ድጓ፣1988 ዓ.ም፣ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት
12. ከአባቶች ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ፣የውዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጉም፣1990 ዓ.ም፣ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት
13. የእጅ ጽሕፈት የግእዝ መማሪያ ግስ/መዝገበ-ቃላት(በራሴ ተቀድቶ የተማርኩበት)፡፡
14. እነ አለቃ አፈወርቅ ዘውዴ፣የግእዝ ቅኔያት የስነጥበብ ቅርስ-2፣1980 ዓ.ም፣ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት
15. መምህር ኪዳነማርያም ጌታሁን፣የሐሰት ምስክርነት፣1994 ዓ.ም፣ንግድ ማተሚያ ድርጅት
16. ሰሎሞን ጥላሁንና ሥምረት ገ/ማርያም፣ደማቆቹ፣2000ዓ.ም፣
17. ደስታ ተክለወልድ፣ዐዲስ ያማርኛ መዝገበ ቃላት፣1962 ዓ.ም፣አርቲስቲክ ማተሚያ ቤት
18. የኢትዮጵያ መጽሐፍቅዱስ ማኅበር፣የመጽሐፍቅዱስ መዝገበቃላት፣1992 ዓ.ም፣6ኛ እትም፣ባናዊ ማተሚያ ቤት
19. ላጵሶ ጌ.ድሌቦ (ዶ/ር)፣የኢትዮጵያ ረጅም ሕዝብና ታሪክ አንደኛ መጽሐፍ፣1982 ዓ.ም፣ንግድ ማተሚያ ድርጅት
ለ. የኢንተርኔት መጻሕፍት(ሶፍት ኮፒ) እና መጣጥፎች!
1. የመኩሪያ ቡልቻ፣የገመቹ መገርሳ እና የቶማስ ዚትልማንን ጽሑፎች ለማግኘት http://www.diva-portal.org/…/get/diva2:277262/FULLTEXT01.pdf
2. የመሐመድ ሐሰንን ጽሑፍ https://zelalemkibret.files.wordpress.com/…/jos-volume-7-nu…
3. የአባስ ሐጂን http://69.162.74.242/~iprenewi/r.php… ወይም http://69.162.74.242/~iprenewi/r.php…
4. በወለጋ ስለነበረው የሚሽኖች እንቅስቃሴ GILCHRIST, HORACE ERIC የጻፈው የ2ኛ ዲግሪ ማሙያ http://repository.lib.ncsu.edu/…/bits…/1840.16/844/1/etd.pdf
5. ፕ/ር ታምራት አማኑኤል የአለቃ ዐጽመጊዮርጊስን እና የነአለቃ ታዬ ታሪክ ጨምሮ የቀደምት ጸሐፍያንን ስራዎች ባጭሩ የዳሰሱበት መጽሐፍ http://www.ethioreaders.com/…/About-Ethiopian-Authors-Prof-…
6. ስለኦሮሞ ሕዝብ የሃይማኖት ተዋጽኦ https://en.wikipedia.org/wiki/Oromo_people#Religion
7. ‹‹ጋላ›› የሚለው ቃል በሶማሌ ሕዝብ ታሪክ ውስጥ ያለው የተለያየ ትርጉም https://www.yumpu.com/…/the-galla-myth-on-somali-history-or…
8. ስለ Krapf ሚሲዮናዊ ሕይወት https://en.wikipedia.org/wiki/Johann_Ludwig_Krapf
9. ‹‹ጋላ›› የሚለው ቃል ኬንያም ውስጥ በታሪክ መጻሕፍት ጥቅም ላይ ሲውል ስለመኖሩ የሚያሳይ ደብዳቤ http://yassinjumanotes.blogspot.com/…/stop-use-of-word-gall…
10. በዚች መዝሙር ላሳርግ Ethiopian Orthodox Mezmur in Afaan Oromo- Waldaa Qulqullootaa - Galanni Waaqayyoof haa ta'u https://www.youtube.com/watch?v=tER05f165A8
http://www.diva-portal.org/…/get/diva2:277262/FULLTEXT01.pdf