Wednesday, January 20, 2016

ተቀባይነት ያጣ እውነት!



ብዙ ብለናል፤ ብዙ ተብሏል።  ችግሩ ያለው የሚነገር እውነት አለመኖሩ ሳይሆን እውነቱን የሚቀበል መጥፋቱ ላይ ነው። ተቀባይነት ያጡ እውነቶችን መጽሐፍ ቅዱስን ዋቢ አድርገን እናቀርባለን።

1/ ታቦት

ታቦት ማለት ማደሪያ፤ማኅደር ማለት ነው።  ቃልኪዳናዊ አሠራሩም ከዚህ የሚከተለውን ይመስላል።
«እኔ እንደማሳይህ ሁሉ፥ እንደ ማደሪያው ምሳሌ እንደ ዕቃውም ሁሉ ምሳሌ፥ እንዲሁ ሥሩት። ከግራር እንጨትም ታቦትን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፥ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን። በውስጥና በውጭም በጥሩ ወርቅ ለብጠው፤ በእርሱም ላይ በዙሪያው የወርቅ አክሊል አድርግለት። አራት የወርቅ ቀለበቶችም አድርግለት፥ እነርሱንም በአራቱ እግሮቹ ላይ አኑር፤ በአንድ ወገን ሁለት ቀለበቶች፥ በሌላው ወገን ሁለት ቀለበቶች ይሁኑ። መሎጊያዎችንም ከግራር እንጨት ሥራ፥ በወርቅም ለብጣቸው። ለታቦቱ መሸከሚያ በታቦቱ ጐን ባሉት ቀለበቶች መሎጊያዎቹን አግባ። መሎጊያዎቹም በታቦቱ ቀለበቶች ውስጥ ይኑሩ፥ ከቶም አይውጡ። በታቦቱም ውስጥ እኔ የምሰጥህን ምስክር ታስቀምጣለህ። ከጥሩ ወርቅም ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ የስርየት መክደኛ ሥራ። ሁለት ኪሩቤል ከተቀጠቀጠ ወርቅ ሥራ፥ በስርየት መክደኛውም ላይ በሁለት ወገን ታደርጋቸዋለህ» ዘጸ 25፤10-18
ይህንን የእግዚአብሔር መመሪያ ያላሟላ ታቦት፤ ታቦት ሊባል አይችልም። ከዚህ የሚጨመርም፤ የሚቀነስም ከእግዚአብሔር  ቃል ያፈነገጠ ነው። ይህ አንዱ ታቦት ሁለቱን የምስክር ጽላቶች ይይዛል። ካህናቱ ሲሸከሙም በመሎጊያዎቹ ጽላቱ ውስጥ እንዳለ አራት ሰዎች በአንድ ጊዜ ይሸከሙታል እንጂ አናት ላይ ቁጢጥ የሚል ጽላት የለም። ይህ ያፈጠጠ ያገጠጠ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ነው። ይህ የእግዚአብሔር ቃል እንዲሻሻል የተነገረበት ጊዜ የለም። ዛሬ ታቦት የሚባለው ከየት የመጣ ነው? ዓላማው፤ አሰራሩ፤ እቅድና ግቡ ምንድነው? ብዙ ሰዎች ስለተከተሉት ወይም እድሜ ጠገብ ስለሆነ ውሸት መቼም ቢሆን እውነት ሊሆን አይችልም። ታቦትን የተመለከተ የእግዚአብሔር ዓላማ በዚህ ዘመን ለማንም አልተሰጠም።

2/ጽላት፤

 ጽላት ሁለቱ የኪዳን ሰሌዳዎች ናቸው። 10ቱ የእግዚአብሔር ትዕዛዛት የተጻፈባቸው ሰሌዳዎች ስለሆኑ ጽላት ተብለዋል። ሙሴ ጽላቶቹን ሊቀበል ሁለት ጊዜ ወደተራራ ወጥቷል። የመጀመሪያውን ጽላት የቀረጸውና በጣቱ የጻፈባቸው እግዚአብሔር ራሱ ነው። «እግዚአብሔርም ከሙሴ ጋር በሲና ተራራ የተናገረውን በፈጸመ ጊዜ በእግዚአብሔር ጣት የተጻፈባቸውን ከድንጋይ የሆኑ ሁለቱን የምስክር ጽላቶች ሰጠው» ዘጸ 31፤18
የመጀመሪያዎቹ ከተሰበሩ በኋላ ጽላቱን ከእብነ በረድ ዳግመኛ የቀረጸው ሙሴ ራሱ ሲሆን በላዩ ላይ ትዕዛዛቱን በጣቱ የጻፈባቸው ግን እግዚአብሔር ነው።
 «ሙሴን አለው፦ ሁለት የድንጋይ ጽላቶች እንደ ፊተኞች አድርገህ ጥረብ፤ በሰበርኻቸው በፊተኞቹ ጽላቶች የነበሩትን ቃሎች እጽፍባቸዋለሁ» ዘጸ 34፤1   ዘዳ10፤4
መጽሐፍ ቅዱስ ስለጽላት በተናገረበት የትኛውም አንቀጽ ውስጥ ሙሴ ጽላቶቹ ላይ ጻፈ የሚል ገጸ ንባብ የለም። ከእብነ በረድ አስመስለህ ቅረጽ የተባለውን ትዕዛዝ አንተው ጻፍባቸው የተባለ በማስመሰል ራሳቸው የሚጽፉባቸው ከየት በተገኘ ትዕዛዝ ነው? በወቅቱም ጽላቶቹ ላይ እግዚአብሔር ራሱ የጻፈባቸው ትዕዛዛት እንጂ ምስል ወይም ስዕል አይደለም። ይህስ ከማን የተገኘ ትምህርት ነው? ስንት ጽላት? ስንት ታቦትስ? እግዚአብሔር ሰጥቷል?

3/ ምልጃና ማስታረቅ

«አማላጅ» የሚለው ቃል የተገኘው «ማለደ» ከሚል ግስ ሲሆን «ማለደ» ማለት ደግሞ «ለመነ» ወይም «ጸለየ» ማለት ይሆናል። « መማለድ ፤ ማማለድ… » ማለት  «መለመን ፣ ማስታረቅ» ሲሆን «አማላጅ» ደግሞ ይህን ተግባር የሚያከናውን ነው፡፡ ተግባሩ ደግሞ «ምልጃ» ይባላል፡፡
አዳም ከእግዚአብሔር ፊት በኮበለለ ጊዜ ወዴት ነህ? ሲባል እነሆ በዚህ ተሸሽጌአለሁ አለ።                         «እግዚአብሔር አምላክም አዳምን ጠርቶ፦ ወዴት ነህ? አለው።እርሱም አለ፦ በገነት ድምፅህን ሰማሁ፤ ዕራቁቴንም ስለ ሆንሁ ፈራሁ፥ ተሸሸግሁም» ዘፍ 3፤9-10
ይህ የኮበለለው ሰው፤ አዳም ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ነበረበት። መቼ? ማንስ? ያስታርቀዋል?
በዘመነ ብሉይ የማስታረቅ አገልግሎት የተሰጠው ለካህናቱ ወገን ብቻ ነበር። የኃጢአት ማስተሰሪያ መስዋዕትም ዕለት ዕለት ይቀርብ ነበር።
« ዕለት ዕለትም ስለ ማስተስረይ ለኃጢአት መሥዋዕት ወይፈኑን ታቀርባለህ፤ ማስተስረያም ባደረግህ ጊዜ መሠዊያውን ታነጻዋለህ ቅዱስም ይሆን ዘንድ ትቀባዋለህ» ዘጸ29፤36 ይህ የማስታረቅ አገልግሎት ፍጹማዊ አገልግሎት አይደለም። በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የተጋረደውን የጥል ግድግዳ ማፍረስ የማይችል ጊዜአዊ አገልግሎት ነበር። ስለዚህም በአዳምና በልጆቹ ላይ የእግዚአብሔር ቁጣ ነበረ። ይህ የበደል ቁጣ ሊመለስ የሚችለው ይህንን መሸከም የሚችል መስዋዕት ሲኖር ብቻ ነው። ለዚህም አገልግሎት ብቁ መሆን የሚችለው ደግሞ ከኃጢአት በቀር በሁሉ የተፈተነ ሊሆን ይገባዋል።
«ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም» ዕብ 4፤15
ስለዚህም ሰማያዊ ሊቀካህን ኢየሱስ ከእግዚአብሔር ፊት ለኮበለልነው ለአዳም ልጆች ሁሉ አስታራቂ መስዋዕት ሆነ። ይህንንም ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ አለ።«ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ»ኢሳ53፤12
ኢየሱስ ክርስቶስ አስታራቂና ማላጅ ባይሆን ኖሮ ሥጋ ከለበሰ ከሰው ልጅ ማንም ቢሆን የማስታረቅ አልገልግሎትን ሊፈጽም አይችልም ነበር። የክርስቶስ ኢየሱስን አስታራቂነት ልዩ የሚያደርገው የማማለድ ብቃቱ ብቻ ሳይሆን ዕለት ዕለት የሚደረገውን የማስታረቅ አገልግሎት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማስቀረት መቻሉ ነበር።
«ሊቀ ካህናትም ሁሉ ዕለት ዕለት እያገለገለ ኃጢአትን ሊያስወግዱ ከቶ የማይችሉትን እነዚያን መሥዋዕቶች ብዙ ጊዜ እያቀረበ ቆሞአል እርሱ ግን ስለ ኃጢአት አንድን መሥዋዕት ለዘላለም አቅርቦ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ» ዕብ 10፤11-12
ስለዚህ የኢየሱስ ክርስቶስ የማስታረቅ አገልግሎት አንዴ የተፈጸመ፤ ነገር ግን ዕለት ዕለት ወደእግዚአብሔር የሚመጡትን ሁሉ የሚያድን የዘላለም መስዋዕት ስለሆነ ዛሬ አዲስ የሚፈጸም የልመናና የማስታረቅ አገልግሎት የለም። አንዳንዶች ዛሬም የሚለምን ያለ የሚመስላቸው አሉ። አንዳንዶች ደግሞ አንዴ የፈጸመው አገልግሎት አብቅቷል፤ ከእንግዲህ አይሰራም የሚሉ አሉ።  አማላጅነትን ለሰዎች ያስረከቡ ሁሉ የክርስቶስን ዘላለማዊ ብቃት ይክዳሉ። በሌላ መልኩም የሰዎችን አማላጅነት ለመከላከል ሲሉ ኢየሱስን ዛሬም የሚማልድ አድርገው የሚስሉም አሉ። ሁለቱም ጽንፎች የኢየሱስን ማንነት ካለማወቅ የሚመነጭ አስተሳሰብ ነው።እውነቱ ግን ዕብራውያን መጽሐፍ እንዳለው፤
«እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤ እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል። ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤ እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና» ዕብ 7፤23-27
ስለዚህ በአጸደ ነፍስ ያሉ ቅዱሳን፤  ሰዎች ከበደል ወደ ጽድቅ፤ ከኃጢአት ወደቅድስና ሰዎች እንዲመለሱ ይማልዳሉ፤ ይለምናሉ ማለት ለኃጢአተኛው ምትክ ሆነው ያድኑታል ማለት አይደለም። አንዴ የተፈጸመው የማማለድና የማስታረቅ አገልግሎት በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው።