Saturday, December 28, 2013

የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የደብር ሃላፊዎችና ሠራተኞች አዲሱን መዋቅር ተቃወሙ


(ደጀብርሃን) ሁሉን ዐቀፍ ጥናት ያልተደረገበትና በአናቱ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ላይ የለውጥ ሽፋን ሽብልቅ ሆኖ የገባው ማኅበረ ቅዱሳን ካህናቱንና የቤተ ክርስቲያኑን ላዕላይ አመራር ለሁለት እየሰነጠቀ ይገኛል። አባ ሉቃስን፤ አባ እስጢፋኖስንና ሌሎች የማኅበረ ቅዱሳን አገልጋይ ጳጳሳትን የያዘው ማኅበሩ ከጀርባ ሆኖ በቢሮው አርቅቆ ያመጣውንና በቤተ ክህነት መዋቅር ውስጥ የማንነት አሻራውን ለመትከል ታች ላይ እያለ የሚገኝ ሲሆን ቅዱስ ፓትርያርኩ ጉዳዩ እንዲጠናና ሁሉንም አሳታፊ እንዲሆን የነበራቸውን አቋም በማስለወጥ በጓሮ ያቀረበውን «የያብባል ገና» ፕሮጄክት በመደገፍ ላይ እንደሆኑ ውስጥ አዋቂ ምንጮቻችን መረጃውን አድርሰውናል። ሰሞኑን በፓትርያርኩ ቢሮ የከተመው ማኅበሩና አቀንቃኝ ጳጳሳቱ ለውጡን የሚቃወሙት ወገኖች በጣት እንደማይቆጠሩና ለዚያው ሌቦችና ዘራፊዎች ናቸው በማለት በማጠየም ላይ ተጠምዶ ሰንብቷል። ፓትርያርኩ ከዚህ በፊት የነበራቸው ሃሳብ ሁሉን አሳታፊ፤ አጠቃላይ የለውጥ እቅድ እንዲሆንና የቤተ ክርስቲያኒቱ አመራር የሚያወጣውና የሁሉንም ካህናት ሃሳብ ያካተተ ሊሆን እንደሚገባው የነበራቸውን አቋም ትተው ማኅበሩ እየተሯሯጠለት የሚገኘውን እቅድ እንዲደግፉ ሲወተውት ሰንብቶ ፓትርያርኩን የቀደመ ሃሳባቸውን አስጥሎ የራሱን እቅድ እንዳስጨበጠ መረጃችን አክሎ ገልጿል። ጉዳዩ እስከየት ይሄዳል? የሚለውን ወደፊት የምናየው ሆኖ አሁን ባለው ሁኔታ አለቆችን ለብቻ የነጠለ በሚመስል ስልት እየታከከ፤ የካህናቱን የስራ ዋስትና በመንጠቅ የራሱን አዲስ መዋቅር እየተከለ የሚገኘውን እንቅስቃሴ ማኅበረ ካህናቱ በዝምታ የሚያልፈው ከሆነ አሉታዊ ውጤቱ ለቤተ ክርስቲያኒቱም፤ ለሀገርም የሚተርፍ ይሆናል።
ይህንን በመቃወም የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት አስተዳዳሪዎችና ሠራተኞች እያቀረቡ ያለውን አቤቱታ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ዛሬ እንዲህ ዘግቦታል።
ዲግሪ ያላቸው በየአስተዳደሩ እንዲገቡ መደረጉ አግባብ አይደለምበኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የአዲስ አበባ ሃገረ ስብከት፣ ካለፈው ህዳር ወር ጀምሮ እያካሄደ ያለውን አዲስ የመተዳደሪያ ደንብ የማፅደቅ ሂደት እና መዋቅራዊ ለውጥ አጥብቀው እንደሚቃወሙ የሃገረ ስብከቱ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎችና ሠራተኞች ለቅዱስ ፓትሪያርኩና ለጠቅላይ ሚኒስትር /ቤት አስታወቁ፡፡ ቅሬታ አቅራቢዎቹ ለፅ/ቤቶቹ ባስገቡት ደብዳቤ፤ የሃገረ ስብከቱ አዲስ መተዳደሪያ ደንብ ሁሉም የቤተክርስቲያኒቱ ሊቃውንት ሳይሳተፉበት በጥቂት አመራሮች ብቻ የተቀረፀና በውይይት ያልዳበረ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ መተዳደሪያ ደንቡ ከነባሩ ህገ ቤተ ክርስቲያንና ከቃለ-አዋዲ ደንብ ጋር የሚጋጭና የሚጣረስ ነው ያሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ደንቡ፤ ነባሩን የቤተክርስቲያኒቱን ሠራተኛ በማፈናቀል በምትኩ ስለቤተ ክርስቲያን ትምህርት ምንም እውቀት የሌላቸውን ግለሠቦች በስመ ድግሪና ዲፕሎማ በመሠግሠግ የቤተክርስቲያኗን ሙሉ አስተዳደራዊ መዋቅር ለመቆጣጠር ያለመ ነውሲሉ ተቃውመዋል፡፡

አዲሱን መዋቅር ያዘጋጁት አካላት ማንነታቸው በግልፅ እንደማይታወቅ በደብዳቤያቸው የጠቀሡት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ የቤተክርስቲያኗ የመጨረሻ ስልጣን ያለውን ቅዱስ ፓትርያርክ ስልጣንን በመገደብ፣ ቤተክርስቲያኗ የእነዚህ አካላት ሠለባ እንዳትሆን ስጋት አለን ብለዋል፡፡ የቤተክርስቲያኒቱን ቃለ አዋዲ ያልጠበቀ ነው ያሉትን አዲሱን መተዳደሪያ ደንብ እንደማይቀበሉትም አስተዳዳሪዎቹ ገልፀዋል፡፡ ለቅሬታው መነሻ የሆነው ደንብ፣ ህግ በማርቀቅና በማዘጋጀት ከፍተኛ ልምድና እውቀት ባላቸው ገለልተኛ ምሁራንና የቤተክርስቲያኗ ሊቀ ሊቃውንት እንዲሰናዳ የጠየቁት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ህጉን አርቅቋል የተባለውን ማንነቱ ማህበር ፓትሪያርኩ እንዲያጣሩ ተጠይቀዋል፡፡አዲሱ ደንብ የካህናት ቅነሣ መርሃ ግብርም እንዳካተተ በግልፅ ተረድተናልያሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ድርጊቱ መንግስት ስራ አጥን ለመቀነስ የሚያደርገውን ጥረት የሚፃረር ነውሲሉ ያጣላሉት ሲሆን ብዙ ሊቃውንትን ከስራ በማፈናቀል ለችግር እና ለእንግልት የሚዳረግ በመሆኑ ህጉ መፅደቅ እንደሌለበት አሳስበዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ ማብራሪያ የጠየቅናቸው የፓትርያርኩ ልዩ /ቤት ሃላፊ አቶ ታምሩ አበራ የቅሬታ አቅራቢዎቹ ደብዳቤ ወደ /ቤት ሳይገባ በቀጥታ ለፓትርያሪኩ የደረሰ በመሆኑ በጉዳዩ ላይ ምላሽም ሆነ አስተያየት ለመስጠት እንደሚቸግራቸው ተናግረዋል፡፡ ቅሬታ አለን የሚሉ ወገኖች በተናጥል ከሚቀርቡ፣ ለቤተክርስቲያኗ ይጠቅማል የሚሉትን ኮሚቴ መርጠው ሃሣባቸውን በማደራጀት ቢያቀርቡ እንደሚሻል የጠቆሙት ሃላፊው፤ የእነሡ ሃሣብ ተቀባይነት ባያገኝም እንኳ በውይይት ለመተማመን ዝግጁ መሆን እንዳለባቸው ገልፀዋል፡፡

በከፊቾ ዞን የጽላት ዝርፊያና ቀበኞቹ "


ባለሃብቶች በእድሳት ስም ቤተ መቅደስ ዘልቀው ጽላት ይቀይራሉ" (የጽሁፍ ምንጭ፤ ጎልጉል የድረ ገጽ ጋዜጣ )
በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች ክልል በከፊቾ ዞን በጥንታዊ አድባራት ጽላት መዘረፉን እናውቃለን ያሉ ለጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ ገለጹ። የዜናው ምንጮች የዞኑ አገረ ስብከት በዞኑ በሚገኙ አድባራት ላይ ምርመራ እንዲያካሂድ ጠይቀዋል። ዝርፊያውን የሚያካሂዱት “ባለሃብቶች” መቀመጫቸውን አዲስ አበባና ጅማ ከተማ ያደረጉ የክልሉ ተወላጆች መሆናቸውን አስታውቀዋል። ነዋሪነታቸው ቦንጋና ጊምቦ እንደሆነ የሚገልጹት የዜናው ምንጮች “ቀበኞች” በማለት የሚጠሯቸውን የጽላት ዘራፊዎች የዝርፊያ ስልት ተናግረዋል። በመጀመሪያ እድሜ ጠገብ የሆኑትን አድባራት ይለያሉ። በቃፊሮቻቸው አማካይነት መረባቸውን ዘርግተው ሰዎችን ያጠምዳሉ። ህዝበ ክርስቲያን በሚሰበሰብበት ወቅትና ዓመታዊ የበዓላትን ቀን መርጠው በርዳታና በእድሳት ስም ውዳሴ ይቀበላሉ።
በዞኑ የሚገኙት አቢያተ ክርስቲያናት እድሜ ጠገብ በመሆናቸው በርካታ ጥንታዊ ቅርስም እንዳላቸው የሚጠቁሙት ክፍሎች “ያረጁትን አድባራት እናድሳለን በማለት ጥቁር ለምዳቸውን ለብሰው መቅደስ ውስጥ ይዘልቃሉ” በማለት የዝርፊያው ድራማ እንዴት እንደሚከናወን ያስረዳሉ።
ለሃይማኖታቸው የቀኑና የታመኑ የቤተ መቅደስ ጠባቂዎችና አገልጋዮች ሲያጋጥሟቸው መቅደስ ውስጥ ተመላልሰው በሚሰበስቡት መረጃ መሰረት አብረቅራቂ ሃሰተኛ ጽላት በመተካት ዝርፊያ እንደሚካሂዱ፣ ለዝርፊያ የሚመችና ስብናው የወደቀ አገልጋይ ሲያገኙም በግልጽ ያሻቸውን አድርገው ስርቆቱን እንደሚፈጽሙ የዜናው ሰዎች ያስረዳሉ። ድርጊቱ የቆየና ሰዎቹም የሚታወቁ እንደሆኑ የሚጠቁሙት እነዚሁ ክፍሎች፣ “ቀበኞቹ” ካላቸው የገንዘብ አቅም አንጻር እጃቸው ከወቅቱ ጉልበተኞችና የቤተ ክህነት ከፍተኛ አመራሮች ጋርም የጠበቀ ግንኙነት ሊኖራቸው እንደሚችል ከግምት በላይ አመላክተዋል። በዚህ ተነሳ “እንፈራለን፤ ፊት ለፊት ለመግጠምም እንቸገራለን” በማለት ለጎልጉል የአዲስ አበባ ዘጋቢ ምስጢራቸው እንዲጠበቅ አስጠንቅቀው መረጃውን ለመስጠት ችለዋል።
“ይህንን ዜና ጥቅማቸው የሚነካና ችግር ያለባቸው አካላት ዙሪያ ያሉ ጥቅመኞች ሊያስተባብሉት ይችሉ ይሆናል” ሲሉ ዜናው የሚያስደነግጣቸው ክፍሎች የሚወስዱትን የመጀመሪያ ርምጃ ያመላከቱት ተቆርቋሪዎች፣ “የእኛ ጥያቄ ግን ማጣራትና ምርመራ ተደርጎ ውጤቱ ከታወቀ በኋላ እውነታው እንዲረጋገጥ ነው” ብለዋል።
የዞኑ አገረ ስብከት ዛሬ ነገ ሳይል በተቀደሱ የማምለኪያ አድባራት ላይ የተፈጸመውንና እየተፈጸመ ያለውን ዝርፊያ የማጣራት ሃላፊነት እንዳለበት ያሳሰቡት ክፍሎች፣ ቀበኞቹ በርዳታ ስም እድሳት ባካሄዱባቸው አድባራት ላይ የሙከራ ምርመራ ቢደረግ ጥቆማው ምላሽ እንደሚያገኝም በርግጠኛነት ተናግረዋል።
በእድሳትና በርዳታ ስም መቅደስ በመዝለቅ ከሚከናወነው ዝርፊያ በተለየ በድርድር የሚካሄዱም ዝርፊያዎች ስለመኖራቸው ያመለከቱት ክፍሎች “ጉዳዩ እጅግ ጥንቃቄ የሚፈልግ በመሆኑ ስምና ቦታን ለይተን ለመጠቆም እንቸገራለን” ብለዋል። “መልዕክቱ ለቀበኞቹ፣ ለተባባሪዎቻቸውና የሚሰማ ተቆጣጣሪ አካል ካለ ለነሱ ነው” ሲሉም አክለዋል። በዞኑ ያሉ የህዝብ ወኪል እንደራሴዎችም በዚህ ጉዳይ ላይ ጥንቃቄ ወስደው እንዲሰሩ ጠይቀዋል።
“የቃል ኪዳን ጽላት ዘርፎ ከማነከስና ሰልሎ ከመሞት ውጪ ሌላ ዕድል የለም” ሲሉ ማስጠንቀቂያ ያስተላለፉት ተቆርቋሪ አዛውንቶች በ2005 መገባደጃ ላይ ዋሻ ውስጥ ተገኘ የተባለ ጽላት የት እንደገባ እንደማይታወቅ አመልክተዋል። ዜናው የመገናኛ ሰዎች ዘንድ ሁሉ ደርሶ እንደነበር፣ ነገር ግን በማይታወቅ ሁኔታ ተዳፍኖ መቅረቱ ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ አካላትን እስካሁን እንደሚከነክናቸው አመልክተዋል።

Friday, December 27, 2013

በመለኮቱ ቀናተኛ በሆነው በአምላካችን ስፍራ ያልተገለጸውን የመልአክ ስም በመጥቀስ ክብሩን ለሌላ አሳልፎ መስጠት ስህተት ነው!



ስለቅዱሳን መላእክት ተራዳኢነትና አዳኝነት በዋናነት የሚቀርበው ጥቅስ እንዲሁም አንዳንዶች እንደመከላከያ ምሽግ የሚጠቀሙበት ቃል በመዝሙረ ዳዊት ላይ የተቀመጠው ይህ ቃል ነው።
“የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል።” መዝ. 33፡7 ይህ ጥቅስ የእግዚአብሔር ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔርን ለሚፈሩትና ለሚታዘዙ ሰዎች ተልከው እንደሚያግዙና እንደሚራዱ ያስረዳል። ምክንያቱም ቅዱሳን መላእክት ከስራቸው አንዱ ሰዎች ወደጽድቅና ቅድስና የመዳን መንገድ እንዲደርሱ በአምላካቸው ፈቃድ መፈጸም ነው።
 “ሁሉ መዳንን ይወርሱ ዘንድ ስላላቸው ለማገዝ የሚላኩ የሚያገለግሉም መናፍስት አይደሉምን?” ዕብ. 1፡14

  ቅዱሳን መላእክት ለምስጋናና ለተልእኮ የተፋጠኑ በመሆናቸው የጌታቸውን ትእዛዝ ተቀብለው እንደሚራዱና እንደሚያግዙ ቃሉ ስለሚናገር በዘመናት ውስጥ መላእክት በስምም ተገልጸው ይሁን በስም ሳይገለጹ ሰዎችን ሲያገለግሉ ኖረዋል። ከዚህ አንጻር በትንቢተ ዳንኤል ላይ የተጠቀሱትን ሶስቱን ወጣቶች እግዚአብሔር መልአኩ ገብርኤልን ልኮ አናንያ አዛርያ ሚሳኤልን ከእሳቱ ሊያድን እንደሚችል ብናምን ስህተት የለውም። ነገር ግን ሊያድን ይችላል ማለትና ስሙ ያልተገለጸውን ስም ሰጥቶ ሰለስቱ ደቂቅን ገብርኤል አድኗል ማለት ሁለት የተለያዩ ነገሮች ናቸው። ምክንያቱም ችግሩ የሚነሳው በነብዩ ዳንኤል የትንቢት መጽሐፍ ውስጥ  እንደምናነበው ወጣቶቹ ለጣኦት አንሰግድም በማለታቸው ከተጣሉበት እሳት ውስጥ ያዳናቸው ገብርኤል ነው የሚል ቃል በጭራሽ አለመኖሩ ነው። ከዚያም አልፎ ተርፎ የእሳቱ ወላፈን ቁመት 49 ክንድ እንደሆነም የሚሰበከው ተያያዥ ጉዳይ አለመጠቀሱም በተጨባጭ የሚረጋገጥ እውነት ስለሆነ ነው። 
ስለቅዱሳን መላእክት ተራዳኢነት ያለው የመጽሐፍ ቃል መንገድ እንዲስት ማድረጉ ሳያንስ ሰዎች ይህ ያልተፃፈውን ቃል እውነት አድርገን እንድንቀበል አጋዥና ደጋፊ ይሆኑናል የሚሉትን ለማግኘት በምክንያት ቁፋሮ በመድከም የተጻፈው ቃል ብቻውን ምሉዕ ነው በማለት አርፈው ባለመቀመጥ  ከቃሉ ጋር ያላቸው ግጭት እስከመጨረሻው መሆኑ ያሳዝናል።
  መጽሐፍ ቅዱስ ስለወላፈኑ ቁመት ያለው አንዳች ነገር አለመኖሩና ድርሳነ ገብርኤልም ሆነ ድርሳነ ሚካኤል የተባሉት መጻሕፍት የእሳቱ ቁመት 49 ክንድ ይረዝማል፤ ያዳንኳቸውም እኔ ገብርኤል ነኝ፤ እኔ ሚካኤል ነኝ በማለት እንዲናገሩ የተደረጉት እነዚህ መጻሕፍት ከየት የመጡ ናቸው ?ብለን ብንጠይቃቸው ተገቢ ይመስለናል። ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱሳችንን ስናገላብጥ መላእክቱ እኛ ነን ሲሉ ወይም እግዚአብሔር ለዳንኤል እነሱ ናቸው እያለ ሲናገር አናገኝምና ነው። 

 በዚህ ዘመን በየድርሳናቱ እንደምናነበው የእሳቱ ቁመት 49 ክንድ የሚለውና የተራዳው የመልአክ ስም ገብርኤል (በድርሳነ ገብርኤል)፤ ሚካኤል (በድርሳነ ሚካኤል) በማለት የጻፉት ዳንኤል ረስቶት ነው? ወይስ እግዚአብሔር ለዳንኤል ያልገለጸውን ቃል እነርሱ ጉድለት ስላገኙበት ለማሟላት ልዩ ፈቃድ ተቀብለው ይሆን ? 


    በሌላ መልኩ ከእግዚአብሔር ቃል ጋር ለመጣላት ቃል የገባ የሚመስለው ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ በድርሳነ ገብርኤል እንደተጻፈው ያዳነው ገብርኤል መልአክ ነው ቢልና ድርሳነ ሚካኤል ደግሞ ቅዱስ ሚካኤል ነው ቢል ችግር የለውም፤ ምክንያቱም ገብርኤል ባለበት ሚካኤል አለ፤ ሚካኤል ባለበትም ገብርኤል አለ በማለት የሁለቱን ድርሳናት ግጭት ለማስታረቅ በመሞከር መላእክቶቹ በጋራ ሆነው  የትም ስፍራ ለተልእኮ እንደሚሄዱ በመግለጽ የሌለ ታሪክ እያመጣ ሌላ ችግር ውስጥ ሲገባ መስተዋሉ ነገሩን አስገራሚ ያደርገዋል። 

ምክንያቱም እንደማኅበረ ቅዱሳን አባባል ይሁን ቢባል እንኳን ሰለስቱ ደቂቅ በተጣሉበት እሳት ውስጥ አምስት ሰዎች ሲመላለሱ በታዩ ነበር። ነገር ግን ሶስቱ ወጣቶችና ሌላ አንድ የሰውን ልጅ የሚመስል በድምሩ አራት ሰዎች እሳቱ ውስጥ እንደሚመላለሱ በአደባባይ ከመታየታቸው በስተቀር አምስት ሰዎች እሳቱ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ እናያለን የሚል ቃል መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አናገኝም።  ምናልባት አንዱ መልአክ ገብርኤልም፤ አልፎ አልፎም ሚካኤል እየሆነ ራሱን ይለዋውጣል ካልተባለ በስተቀር በሁለቱ ድርሳናት ላይ ያለው የእኔነት ጥያቄ በማኅበረ ቅዱሳን አሸማጋይነት ፈጽሞ የሚታረቁበት ሁኔታ ከቶ ሊኖር አይችልም። 
ያልታዩ አምስት ሰዎችን እሳቱ ውስጥ እንዳሉ በመቁጠር፤ ስማቸው ያልተገለጸ መላእክቶችንና ሁለቱን ድርሳናት በማኅበረ ቅዱሳን ሽምግልና ከእግዚአብሔር ቃል አንጻር መቼም ላይስማሙ የተጻፉ ናቸው። ምክንያቱም እግዚአብሔር ካልተናገረ በቃ አልተናገረም ነው እንጂ የሰው ቃል የጭማሪ ማሻሻያ አያስፈልገውም። ከተናገረ ደግሞ የተናገረው እውነት: መቼም ቢሆን ለዘለዓለም እውነት ሆኖ ይኖራል።
  መላእክት የእግዚአብሔርን ቃል ፈጻሚዎች ስለሆኑ ይራዱናል፤ ያግዙናል ማለት አንድ ነገር ነው። ይህንን የሚያስረዳ የእግዚአብሔር ቃል ማረጋገጫ ስላለን እንቀበላለን። ይሁን እንጂ ጉድለትና ስህተት በሌለበት በእግዚአብሔር ቃል ላይ ስሜቶቻችን እያስገባን በመተርጎም እግዚአብሔር ያደረገውን ድንቅ ስራ እጹብ እያልን እንዳናመሰግነው ዓይናችንን ወዳልተገለጹ መላእክት እንድንወረውር ማድረግ ደግሞ ሌላ ነገር ስለሆነ በዚህ አንስማማም። ሰውን ወደስህተት መምራት በደል እንደሆነ እንናገራለን። እግዚአብሔር ማን መሆኑን ሳይገልጽ የተወው የስራው ባለቤት እሱን እንድናመሰግነውና ስለድንቅ ስራው እንድናደንቀው እንጂ ማንነቱ ያልተገለጸውን፤ በትርጉም ሽፋን ስም ሰጥተን እኛ በጎደለው እንድንሞላው አይደለም። ክብሩን ላልተገለጸ መልአክ መስጠት ኃጢአት ስለሆነ ስለስቱ ደቂቅን ያዳናቸው እግዚአብሔር ነው በማለት ምስጋናውን ከእቶኑ ያድነናል ብለው እንደመሰከሩት ሶስቱ ወጣቶች ለእግዚአብሔር መልሰን ስላልተገለጸው መልአክ በተናገርነው ደግሞ  ንስሐ ልንገባ ይገባል። ገብርኤልን ጠቅሶ ልኮ ያዳነ ቢሆንም እንኳን አዳነ ተብሎ የሚመሰገነው እግዚአብሔር ነው እንጂ መልአኩ አይደለም፡፡  መልአኩም እኔን አመስግኑኝ አይልም። እንደዚህ አይነት ምስጋና መቀበል የሚፈልገው የወደቀው መልአክ እንጂ ከቅዱሳን መላእክቱ አንዱም አድርጉልኝ ሲሉ አናገኝም።
  ለዮሐንስ በራእዩ የተናገረው እንዲህ ሲል ቅዱሱን መልአክ እናገኛለን። «ልሰግድለትም በእግሩ ፊት ተደፋሁ። እርሱም፦ እንዳታደርገው ተጠንቀቅ፤ ከአንተ ጋር የኢየሱስም ምስክር ካላቸው ከወንድሞችህ ጋር አብሬ ባሪያ ነኝ፤ ለእግዚአብሔር ስገድ፤ የኢየሱስ ምስክር የትንቢት መንፈስ ነውና አለኝ» (ራእይ 19፤10)
 እኛ ገብርኤል ወይም ሚካኤል የሚል የተጻፈ የለም ስንል መጽሐፍ ቅዱስ የነገረን ይበቃናል፤ የሌለ ታሪክ በቃሉ ላይ አንጨምር በማለት እንጂ ቅዱሳን መላእክቱ ከአምላካቸው በሚወጣ ትእዛዝ አይራዱም ወይም አያግዙም ከማለት አንጻር እንዳልሆነ መታወቅ አለበት። ምስጋና ሁሉ፤ ሁሉን ማድረግ ለሚችል ለእግዚአብሔር ብቻ ይሁን እንላለን። ይሁን እንጂ «እናንተን የተቀበለ እኔን ይቀበላል» ማቴ 10፤40 በሚለው ቃል ስር ተጠልለው ለመላእክቱ የምናቀርበው ምስጋና ጌታችንን ማመስገናችን ነው በማለት መከራከር የሚሹ ወገኖች ቢኖሩም ምስጋና ውዳሴውን ለእነሱ አድርጉ: እኔ በተዘዋዋሪ እቀበላለሁ የሚል ቃል የለም። የተላኩትን የምንቀበለው የላካቸውን ስናውቅ ነው።


ከቤተ መንግስት ወደ አንድ ሰው የተላከ ስጦታን የሚቀበል ሰው፤ የተላከውን ሰው ማንነት አረጋግጦና በአክብሮት አስተናግዶ ለተደረገለት ስጦታ ግን ምስጋናና ውዳሴውን ለስጦታው ባለቤት ለቤተ መንግስቱ ክፍል ቢችል በጽሁፍ፤ ካልቻለም በቃል ያቀርባል እንጂ መልእክተኛውን ሰው ስለሰጠኸኝ ስለዚህ ስጦታ አመሰግንሃለሁ፤ ያደረክልኝን ውለታ መቼም አልረሳውም በማለት ለቤተ መንግስቱ ሊቀርብ የሚገባውን ምስጋና መንገድ ላይ በማስቀረት ለመልእክተኛው አያደርግም። ለመልእክተኛው ማድረጌ ለቤተ መንግስት እንዳደረኩ ይቆጠራል ቢል የስጦታውን ባለቤት ስጦታ መዘንጋት ይሆናል።

 ስለሆነም ለቅዱሳን መላእክት የምናከብራቸው አምላካቸውን ስለሚያውቁ፤ ለቃሉም ስለሚታዘዙ፤ ምስጋናና ውዳሴን ዘወትር ስለሚያቀርቡ፤ መልእክት ከዙፋኑ ሲደርሳቸው ለምህረት ይሁን ለመዐት ስለሚወጡ እንጂ እነሱ በተዐዝዞ ለሚያደርጉት ሁሉ ምስጋናና ውዳሴ የተገባቸው ተቀባዮች ስለሆኑ አይደለም።
«አሁንም እኔ ብቻዬን እኔ እንደ ሆንሁ፥ ከእኔም በቀር አምላክ እንደሌለ እዩ፤ እኔ እገድላለሁ፥ አድንማለሁ፤ እኔ እመታለሁ፥ እፈውስማለሁ፤ ከእጄም የሚያድን የለም» ዘዳ 32፤39  ይህንን ቃል አምናለሁ እያሉ መላእክቱን በስልጣናቸው አዳኝ አድርጎ ማስቀመጥ ብቻውን ገዢ ለሆነና ምስጋና የባህርይ ገንዘቡ በሆነው አምላክ ላይ የአምልኮ ምንዝርና መፈፀም ነው። አመንዝራ ቃል ኪዳን ከፈፀመላት ባለቤቱ ውጪ የሚደረግ ስርአተ አልበኝነት እንደሆነው ሁሉ፤ ምስጋናና ውዳሴ ከእግዚአብሔር ውጪ ለማንም እንዳናጋራ በእምነታችን ለአምላክ ቃል ኪዳን መግባታችንን በመዘንጋት እየቆረሱ ለሁሉም በማደል የምንፈጽመው የአምልኮ ስህተት ሁሉ ነው።


ሌላው አሳዛኝ ነገር እግዚአብሔር ከእልፍ አእላፋቱ መላእክቶቹ መካከል የትኛውን መልአክ፤ ለምን አገልግሎት እንደሚልክ ሳናውቅ በእኛ ጥሪ የሚመጣ ይመስል « እንደአናንያ፤ እንደአዛሪያ፤ እንደሚሳኤል፤ አድነን ገብርኤል» በማለት ከበሮ በመደለቅ ገብርኤል ራሱ እንዲመጣ መጥራታችን ነው። መላእክቱ ወደታዘዙበት ስፍራ ከምስጋና ከተማቸው የሚነሱት ከቅዱሱ መንበር ትእዛዝ ሲወጣ ብቻ ነው እንጂ ሰዎች ተሰብስበው በስም ስለጠሯቸው አይደለም።
«ቆርኔሌዎስም እንዲህ አለው፦ በዚች ሰዓት የዛሬ አራት ቀን የዘጠኝ ሰዓት ጸሎት በቤቴ እጸልይ ነበር፤ እነሆም፥ የሚያንጸባርቅ ልብስ የለበሰ ሰው በፊቴ ቆመና።ቆርኔሌዎስ ሆይ፥ በእግዚአብሔር ፊት ጸሎትህ ተሰማ ምጽዋትህም ታሰበ» (የሐዋ 10፤30-31) ላይ የተጻፈው ቃል የሚያስተምረን ሰዎች ፈቃደ እግዚአብሔርን በመፈጸም ስንጸና እኛ የማናውቀው ወይም በስም ያልተገለጸ መልአክ መልእክት ይዞልን በመምጣት ሊያግዘን እንደሚችል እንጂ ሚካኤል ና! ና! ወይም ገብርኤል ቶሎ ድረስ! ስላልን አይደለም። ምክንያቱም የእኛ የጥሪ ምኞትና የአምላክ ሃሳብ አንድ አይደለምና።

« ሰማይ ከምድር ከፍ እንደሚል፥ እንዲሁ መንገዴ ከመንገዳችሁ አሳቤም ከአሳባችሁ ከፍ ያለ ነው» ኢሳ 55፤9 የሚልም ቃል ተጽፎልናል።
 ስለዚህ እኛ አምላካችንን በጸሎትና በምስጋና ዘወትር ከፍ ከፍ  ከማድረግ ውጪ ይህኛው ፈጣን ነው፤ ያንኛው አዳኝ ነው እያልን በመጥራታችን መላእክቱ አያ እገሌ ስማችንን ጠርቷል፤ የእገሌ ደብር ፍሪዳ በስሜ አርዷልና ልሂድ፤ ልውረድ አይሉም።   ከመሰለንም ተሳስተናል።  ዘማሪው በመዝሙሩ  «መላእክቱ ሁሉ፥ አመስግኑት ሠራዊቱ ሁሉ፥ አመስግኑት» እንዳለው፤
«አየሁም፥ በዙፋኑም በእንስሶቹም በሽማግሌዎቹም ዙሪያ የብዙ መላእክትን ድምፅ ሰማሁ፤ ቍጥራቸውም አእላፋት ጊዜ አእላፋትና ሺህ ጊዜ ሺህ ነበር፥በታላቅም ድምፅ። የታረደው በግ ኃይልና ባለ ጠግነት ጥበብም ብርታትም ክብርም ምስጋናም በረከትም ሊቀበል ይገባዋል አሉ። በሰማይና በምድርም ከምድርም በታች በባሕርም ላይ ያለ ፍጥረት ሁሉ በእነርሱም ውስጥ ያለ ሁሉ። በረከትና ክብር ምስጋናም ኃይልም ከዘላለም እስከ ዘላለም በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው፥ ለበጉም ይሁን ሲሉ ሰማሁ» ራእይ 5፤11-13

ዘወትር ያመሰግኑታል።
ዝም ብሎ ሲጠራም ይሁን ሳይጠራ የትም የሚዞረውና ዓለምን በማሰስ ጊዜውን የሚፈጀው ሰይጣን ብቻ ነው። «እግዚአብሔርም ሰይጣንን፦ ከወዴት መጣህ? አለው። ሰይጣንም። ምድርን ሁሉ ዞርሁአት፥ በእርስዋም ተመላለስሁ ብሎ ለእግዚአብሔር መለሰ» ኢዮብ 1፤7
ስለዚህ እግዚአብሔር እንዴት እንደሚሰራ፤ በማን በኩል እንደሚሰራ፤ መቼ እንደሚሰራ ስለማናውቅ የመላእክቶችን ስም መጥራት አቁመን የእሱን ስም ብቻ ዘወትር በመጥራት እንጽና። በየትኛው መልአክና እንዴት እንደሚረዳን የሚያውቀው እሱ ብቻ ስለሆነ በተስፋ እንጠብቀው። የሚራዱንን መልእክተኞቹን እናከብራቸዋለን፤ እንወዳቸዋለን፤ በማንኛውም ስራ ግን ምስጋናና ውዳሴውን ለእሱ ብቻ እንሰጣለን።
በመለኮታዊ ሥልጣኑ ቀናተኛ ነውና። «ለሚወድዱኝ፥ ትእዛዜንም ለሚጠብቁ እስከ ሺህ ትውልድ ድረስ ምሕረትን የማደርግ እኔ እግዚአብሔር አምላክህ ቀናተኛ አምላክ ነኝና» ዘጸ20፤6 ያለን እግዚአብሔር ራሱ ነው።

Wednesday, December 25, 2013

ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ አባ ማቴዎስ በአሜሪካ ላለው የማኅበረ ቅዱሳን ክፍል ብዙ ቢጥሩም ፓትርያርኩ ከሊቀጳጳሱ ጋር ሁሉም ሊስማማ ይገባል በማለታቸው ድካማቸው ፍሬአማ ሳይሆን ቀርቷል!

አባ ማቴዎስ ከፓትርያርኩ ተነጥለው ወደናሽቪል በማቅናት ሐመረ ኖኅ ኪዳነ ምህረት ግቢ ሲደርሱ
  ወደአሜሪካ ካቀኑት ፓትርያርክ ጋር አብረው የተጓዙት አዲሱ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሥራ አስኪያጅ አባ ማቴዎስ በአሜሪካ ያለውን የማኅበረ ቅዱሳን ንዑስ ክፍል ከደረሰበት ጫናና አጣብቂኝ ለመታደግ ተስፋ መስጠታቸው ተሰምቷል። ጠቅላይ ስራ አስኪያጁ ከአዲስ አበባው የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጽ/ቤት በተቀበሉት መመሪያ መሠረት በካሊፎርኒያው አኅጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ በሊቀ ስዩማን ኃይለ ጊዮርጊስ አመራር የተነሳ የማቅ ቅርንጫፍ መተንፈሻና መላወሻ በማጣቱ ውጥረቱን ያረግቡላቸው ዘንድ የተነገራቸውን ተልእኮ ለመፈጸም አሜሪካ እንደደረሱ ደፋ ቀና ሲሉ መሰንበታቸው ከአካባቢው የደረሰን መረጃ አመልክቷል። እንደዘገባው ከሆነ ቢቻል ተስማምተው እንዲሰሩ በማግባባት ጊዜ ለመግዛት የሚቻልበትን ሁኔታ መፍጠር ፤ ባይቻል በማኅበረ ቅዱሳን የጥላቻ መዝገብ ላይ ከሰፈሩትና ቁጥር አንድ ባላንጣ ሆነው የተቆጠሩት ሊቀ ሥዩማን ኃ/ጊዮርጊስን ከስራ አስኪያጅነት ለማስነሳት ከአሜሪካው ጉዞአቸው በኋላ ዋና ስራቸው እንደሚሆን ቃል መግባታቸውን እንቅስቃሴውን ሲከታተሉ የነበሩ እማኞች ገልጸዋል።

 ስራ አስኪያጁ ወደአዲስ አበባ እንደተመለሱም ለአሜሪካው ማኅበረ ቅዱሳን ቅርንጫፍ ለመጀመሪያ ጊዜ እንደአንድ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋም ተቆጥሮ ደብዳቤ የጻፉለት ሲሆን ይህም የሚያሳየው ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግና ደንብ የሚተዳደር መሆኑን በማመልከት ሁኔታዎች ሰላማዊና ፍሬያማ ሆነው እንዲቀጥሉ ካስፈለገ ሊቀ ሥዩማን ኃይለ ጊዮርጊስ ካለበት ቦታ እንዲነሳ ለማስቻል መሆኑም ውስጠ አዋቂዎቹ ጠቁመዋል።
  በዚሁ መሰረት ከጉዞአቸው መልስ ለማኅበረ ቅዱሳን ያላቸውን ቁርጠኝነት ለማሳየትና የተቀበሉትን ተልእኮ ለመፈጸም በሚመስል መልኩ የአሜሪካው አኅጉረ ስብከት የስራ እንቅስቃሴ ሰላማዊና ተግባቦት የተሞላው ሆኖ እንዲቀጥል ካስፈለገ በብዙዎቹ ዘንድ እንደምክንያት የተቆጠሩት ሊቀ ሥዩማን ኃይለ ጊዮርጊስ ከቦታው ቢነሱ የተሻለ ነው በማለት  ለቅዱስ ፓትርያርኩና ለውጭ ግንኙነት የበላይ ኃላፊው ለብፁዕ አቡነ ገሪማ ያቀረቡ ቢሆንም ጥያቄያቸው ተቀባይነት ሳያገኝ መቅረቱም የደረሰን መረጃ አክሎ ገልጿል። ሀገረ ስብከቱ በአቡነ ፋኑኤል የሚመራ እንደመሆኑ መጠን ሥራ አስኪያጁ ይነሳልኝ የሚል ጥያቄ ከሊቀ ጳጳሱ ሳይቀርብ በውስጥ አስተዳደራቸው ጣልቃ እንደመግባት ስለሚቆጠር የሊቀ ሥዩማን ኃይለ ጊዮርጊስ ከቦታው መነሳት ለማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች ጉም እንደመዝገን ሆኖባቸዋል።

 በአንድ ስብሰባ ላይ ማቆች የከሳሽና የተከሳሽ የክርክር መድረክ ሳይቸግራቸው ከፍተው ኃይለ ጊዮርጊስን እናዋርዳለን ብለው የጀመሩት እነያሬድ ገብረ መድኅንና እሸቱን የመሳሰሉ የማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች ከሥራ አስኪያጁ በቀረበባቸው የመልስ ምት መሰረት ያሬድ በጋብቻ ላይ ጋብቻ የፈጸመ ሆኖ ሳለ ቀሲስ ብሎ እንደሚጠራ፤ እሸቱ በፖሊስ በቀረበበት ማስረጃ የብዙ ሴቶችን ድንግልና ማጥፋቱ ተዘግቦ ሳለ ቀሲስ እሸቱ መባሉ አግባብ እንዳልሆነ፤ ይህም በሰውና በሰነድ ማስረጃ እንደሚረጋገጥ ሲገለጽባቸው በጉባዔው ላይ በሃፍረት ተሸማቀው የሚገቡበት እንደጠፋቸው የዓይን እማኞች ገልጸዋል።  ምሰሶ የሚያክል ኃጢአታቸው የራሳቸውን እንዳያዩ የጋረደ ዓይናቸውን ገልጠው የሥራ አስኪያጁን ኃጢአት ለመደርደርና በጉባዔው መካከል ለማዋረድ ቢፈልጉም የቀረበባቸው ምት ጨርቃቸውን ጥለው እስኪሄዱ ድረስ ቀልባቸውን የገፈፈ ነበር። እነዚህ የማኅበረ ቅዱሳን ጉዶች በጫሩት እሳት ከመለብለባቸው የተነሳ ከዚያ ወዲህ በያሉበት ድምጻቸውን አጥፍተዋል። እድለኛ ቢሆኑና ንስሐ ቢገቡ የውሸት ቅስናቸውን መልሰው እግዚአብሔር በሰጣቸው የመዳን ጸጋ ሰርተው ቢኖሩ ምንኛ ባማረላቸው ነበር!!
  ዳሩ ግን የማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች በንስሐ የተፉትን ኃጢአት መልሶ ለመላስ እንደማይቸገሩ የብዙዎች አባላቱ የተገለጠ ነውር በአደባባይ ይጮሃል።
ቀሲስ? ያሬድ።

እንግዲህ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ከእንደዚህ ዓይነቶቹ የማቅ ደጋፊዎች ጋር ነው ጥንቃቄና ስልት በተሞላበት አካሄድ ማንም ሳያውቅባቸው ግንኙነት በማድረግ በምድረ አሜሪካ የሰነበቱት።
  ከዚሁ ጋር ተያይዞ ለስልታዊ እርምጃቸው ብዙ የሚጠነቀቁትና በረቂቅ አካሄዳቸው የሚታወቁት አባ ማቴዎስ በአሜሪካ ቆይታቸው በካሊፎርኒያው አኅጉረ ስብከት ሥልጣነ ክህነቱ የታገደው የማኅበረ ቅዱሳን አጫፋሪ እንደሆነ የሚነገርለት የዶ/ር መስፍንን ቤተ ክርስቲያን መጎብኘታቸው የታወቀ ሲሆን ከማኅበሩ አባላትና ከአንዳንድ የፖለቲካ ሽታ ካላቸው ሰዎች ጋር ያደረጉት ውይይት በመቅረፀ ድምጽ መረጃው መያዙም ታውቋል። አባ ማቴዎስ በወያኔ/ኢህአዴግ አገዛዝ መማረራቸውን በመግለጽ ሁኔታዎች በዚህ ከቀጠሉ  ወደአሜሪካ መጥተው ከመኖር ውጪ ሌላ አማራጭ እንደሌላቸው መናገራቸውም የደረሰን መረጃ ያስረዳል። ምናልባትም  ለፓትርያርክነት የነበራቸውን ህልም ያጨለመባቸው ያለፈው የውድድር ሜዳ ቀድሞ በተዘጋጀ ስሌት በመጠናቀቁ የተነሳ ወደፊትም ኢህአዴግ እስካለ ተስፋ የለኝም ከሚል እሳቤ የተነሳ ሁኔታዎች ካላመቹ ወደአሜሪካ ለማቅናት ማሰባቸው ላያስገርም እንደሚችልም  ተነግሯል።

Saturday, December 21, 2013

(ሰበር ዜና) የአዲስ አበባ አድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፤ ፀሐፊዎችና አጠቃላይ ማኅበረ ካህናቱ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ አቤቱታቸውን አቀረቡ!


     ስድስት ገጽ የያዘው የማኅበረ ካህናቱ አቤቱታ በግልባጭ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት፤ ለፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን፤ ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትርና ለሚመለከታቸው ክፍሎች ሁሉ ገቢ መደረጉን ለማወቅ ተችሏል!
         (ደብዳቤውን ከታች አቅርበንላችኋል)
        ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያኒቱ ሲኖዶስ አይደለም በማለት ያሳሰቡ ሲሆን ይህ ተረፈ ደርግና በቤተ ክርስቲያን ታዛ የተጠለለ ነጋዴ ድርጅት የመጨረሻ እልባት ሊሰጠው የሚገባው ወቅት አሁን ነው በማለት ጠየቁ!
        ማኅበረ ቅዱሳንና ታማኝ አገልጋዮቻቸው ሊቃነ ጳጳሳት በሚፈጥሩት ሁከት ቤተ ክርስቲያናችን እየታመሰች መቀጠሏ ማቆም አለበት በማለት ድምጻቸውን ሲያሰሙ ውለዋል!
        የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ችግር ከአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር ጋር በሲኖዶስ የሚታይና የአስተዳደር ለውጥ ለማድረግም ሲኖዶሱ በሚሰጠው መመሪያ በምሁራን ልጆችዋ፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ በሕግ አዋቂዎች፤ በአስተዳደርና በማኔጅመንት እውቀትና ልምድ ባላቸው አባላት ሰፊ ጊዜ ተሰጥቶት በሚቀርብ የማሻሻያ ረቂቅ ደንብ እንጂ ቤተ ክርስቲያኒቱ ሀብትና ንብረቴን መቆጣጠር አትችልም ባለ ዐመጸኛ ቡድን መሆን ስለማይገባው ቅዱስ ፓትርያርኩ አስቸኳይ መፍትሄ ይስጡን በማለት ተጠይቀዋል!
        21 ዓመት የተሸከምነውን ይህን ማኅበር ከእንግዲህ ተሸክመን በዚህ ዓይነት መልኩ ለመዝለቅ ስለማንችል መንግሥት አንድ እልባት እንዲሰጠን እንጮሃለን ብለዋል! በቃ የሚባልበት ወቅት ቢኖር አሁን ነው ያሉት ተሰብሰባዎቹ ወደፊት በዚህ ማኅበር ምክንያት ለሚመጣው ጉዳት ኃላፊነቱን አንወስድም ሲሉ ያላቸውን ፍርሃትም አሳስበዋል!
        ቅዱስ ፓትርያርኩም ጉዳዩን በቀላሉ እንደማይመለከቱትና መፍትሄም እንደሚሰጡ ቃል የገቡላቸው ሲሆን ማኅበረ ካህናቱ ያላቸውን ችግር ለመፍታትና ለመነጋገር የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አዳራሽ ክፍት ሆኖ እንደሚያገለግላቸው ገልጸውላቸዋል!
     ከታች የቀረበው ጽሁፍና ማመልከቻ ለቅዱስ ፓትርያርኩ በጠቅላይ ቤተክህነቱ አዳራሽ የቀረበ የማኅበረ ካህናቱ ፊርማና አቤቱታ ነው።
                       ዐቢይ ዜና

ማኅበረ ቅዱሳን በአዲሱ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት መዋቅራዊ ለውጥ ምክንያት እየደረሰበት ያለው ተቋሞ ተጋግሎ ቀጥሏል፡፡ በየሆቴሉ በድብቅ ይሰበሰባሉ ሲባሉ የቆዩት የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት አለቆች በገሀድ በጠቅላይ ቤተክህነት አዳራሽ ተሰብስበው ፓትርያርኩንና አንዳድ የማኅበሩን ደጋፊ ሊቃነ ጳጳሳት አስጠነቀቁ፡፡ ጥያቄዎቻችን ምላሽ የማያገኙ ከሆነ የቤተክርስቲያኒቱ አስተዳደር በጥቁር ራስ (መነኮሳት ባልሆኑ) ሰዎች እንዲካሄድ በሕጋዊ መልኩ እንደሚጠይቁ አስረድተዋል፡፡
የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት ሰራተኞች ቤተክርስቲያኒቱ የአሰራር ለውጥ እንደሚያስፈልጋት አምነው ለውጡ ሁለንተናዊና መላውን የቤተክህነቱ ክፍል ሊያቅፍ እንደሚገባ ሕጉም ከዋናው ከሕገ ቤተክርስቲያን መጀመር እንዳለበትና በየደረጃው ደንቦችና መመሪያዎች ሊወጡ እንደሚገባው አስረድተው ይህንን የሚሰራው አካልም ከቅዱስ ሲኖዶስ፣ ከሊቃውንት ጉባዔ፣ በየደረጃው ከሚገኙ የቤተክርስቲያኒቱ መዋቅር ሰራተኞች ፣ ከገለልተኛ ባለሙያዎች ምእመናንና የሰንበት ት/ቤት ተወካዮች በተወጣጣ ኮሚቴ መሰራት እንደሚገባው አስምረውበታል፡፡
ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ጥያቄያችሁ በቀላሉ የሚታይ አይደለም ትኩረት ይፈልጋል  በማለት ኮሚቴ እንዲቋቋም ፈቅደዋል በቤተክህነቱ አዳራሽ መሰብሰብ እንደሚችሉ አረጋግጠውላቸዋል፡፡ስብሰባው ያበሳጫቸው አቡነ እስጢፋኖስ ግለቱ ከብዷቸው ወደ አሜሪካ እንደሚሄዱ ተናግረዋል፡፡
ጥናቱ ግልጽነት የጎደለውና ቤተክርስቲያኗን ለአንድ ማኅበር ድብቅ ዓላማ እና ፍላጎት አጋልጦ የሰጠ በመሆኑ፣ የካህናት ቅነሳ በሚል አገልጋዮችን የሚበትን ፣ ቤተክርስቲያኒቱ ያሏትን ሊቃውንት ያላካተተ በመሆኑ፣ የሰንበት ትምህርት ቤትን በማዳከም በአጥቢያ ቤተክርስቲያናት ብዙ ማኅበር እንዲደራጅና ሕጋዊ እንዲሆን በማድረግ በወጣቱ ዘንድ መከፋፈል የሚፈጥር በመሆኑ እንደማይቀበሉት  አስታውቀዋል፡፡    ማኅበረ ቅዱሳን  በጥቅምቱ የሰበካ ጉባዔ ምልአተ ስብሰባ በተወሰነው መሠረት  የ55 ሚሊዮን የቤተክርስቲያኗ ምእመናን ካህናትና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች በወሰኑትባ በአቋም መግለጫ ባጸኑት ውሳኔ  መሠረት  ሀብትና ንብረቱን እንዲያሳውቅና በቤተክርስቲያኗ አሰራር መሠረት በሕጋዊ ሞዴሎች እንዲጠቀም ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ለቅዱስ ፓትርያርኩ በ 5000 ሰራተኞች ፊርማ በቀረበውና ለመንግሥት አካላት ግልባጭ በተደረገው ደብዳቤ ተጠይቋል፡፡
በማኅበረ ቅዱሳን በተዘጋጀውና ለአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከት ብቻ እንዲተገበር በታለመው የመዋቅራዊ ጥናት ምክንያት  በሀገረ ስብከቱ ሥር በሚገኙ አድባራትና ገዳማት ሠራተኞችና በማኅበረ ቅዱሳን መካከል ያለው አለመግባባት ቀጥሏል፡፡ መዋቅራዊ ጥናቱን ይቃወማሉ የሚባሉት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአድባራት ሰራተኞች ባሳለፍነው ሳምንት ረቡዕ ወደ ጠቅላይ ቤተክህነት በማምራት ቅዱስ ፓትርያርኩንና ብፁአን ሊቃነ ጳጳሳትን አነጋግረዋል፡፡ የአቋም መግለጫቸውንም ለፓትርያርኩ ሰጥተዋል፡፡ በመድረኩ ማኅበረ ቅዱሳን አንድ የቤተክርስቲያን አካል ሆኖ እያለ ለመላዋ ቤተክርስቲያን መመሪያ አውጪ መሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ ሥልጣን ወዴት ነው ያለው እንዳስባላቸው ተሰብሳቢዎቹ ለፓትርያርኩ አስረድተዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን እራሱ ለቃለ አዋዲውና ለሕገ ቤተክርስቲያን ሳይገዛ እንዴት ሕግ አውጪ ሊሆን ቻለ? የሚል ጥያቄ አንስተዋል፡፡ መመሪያ የሚያስፈልግ በመሆኑ ከሕገ ቤተክርስቲያን ጀምሮ በየደረጃው መመሪያና ደንብ እንዲወጣና ይህንንም አንድ ማኅበር ሳይሆን የቤተክርስቲያኒቱ መዋቅር ውስጥ ያሉ እና ገለልተኛ አካላት ሊያዘጋጁት ይገባል ብለዋል፡፡ ተሰብሳቢዎቹ ማኅበሩ መዋቅራዊ ጥናቱን ለምን በድብቅ መስራት አስፈለገው፣ ሊቃውንት ለምን እንዲሳተፉ አልተፈለገም የሚሉ ጥያቄዎች ተነስተዋል፡፡ ለጥያቄዎቹ መልስ በሚሰጥበት ወቅት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የማኅበሩ የኢዲቶሪያል ኮሚቴ አባል ስለ መዋቅሩ አስፈላጊነት ለመግለጽ የሞከሩ ሲሆን አቡነ እስጢፋኖስ ግን ስለ ጥናቱ ብዙም መረጃ እንደሌላቸውና አንዳንዱንም ከተሰብሳቢው ወገን እንደሰሙ በመግለጽ እርስ በእርሱ የተምተታ መልስ ሰጥተዋል፡፡ መመሪያውና ጥናቱን ወድቆ ብናገኘውስ ምን ችግር አለው ሲሉ ምንጩን ለመደበቅ ሞክረዋል፡፡ ተሰብሳቢዎቹ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥያቄያቸውን ማይመልስ ከሆነ የቤተክርስቲያኒቱ አስተዳደር በጥቁር ራስ (መነኮሳት ባልሆኑ) ሰዎች እንዲካሄድ በሕጋዊ መልኩ እንደሚጠይቁ አስረድተዋል፡፡ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ የተሰብሳቢዎቹ ጥያቄ አግባብ የሆነና በትኩረት መታየት እንዳለበት አስረድተው ከተሰብሳቢዎቹ ጉዳዩን የሚከታተል 15 ዐቢይ ኮሚቴ እና 20 ንዑሳን ኮሚቴዎች አስመርጠው በጠቅላይ ቤተክህነት አዳራሽ በመሰብሰብ ጉዳዩን በይበልጥ በትኩረት እንዲያጠኑ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ለጊዜው እንዲቋረጥ ብፁአን አባቶች ሀሳብ የሰጡበት የመዋቅራዊ ጥናት ስብሰባ በአቡ እስጢፋኖስ ትእዛዝ እንደቀጠለ ሲሆን የሥልጠናው መሪ ማኅበረ ቅዱሳኑ አቶ ታደሰ ፍስሐ በሥልጠናው ተሳታፊዎች እናንተ እነማን ናችሁ? ከሊቃውንትስ ማንን ይዛችሁ ነው የምትሰሩት በሚል ለተነሳላቸው ጥያቁ በደፈናው የቤተክርስቲያን ልጆች ነን ከሊቃውንትም ታላቁን ሊቅ አቡነ እስጢፋኖስን ይዘን ነው የምንሰራው በማለት ምላሽ ሲሰጡ አዳራሹ በስላቅ ሳቅ ደምቋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን ሠራተኛ አቶ ደስታን በሥልጠናው ሥፍራ በወሬ አቀባይነት መድቦ በሬኒ ካፊና ሬስቶራንት የምሳ እና የሻይ እየተከፈለው አንዳንድ መረጃዎችን ለማኅበሩ ሥውር ብሎጎች እንዲያቀብል መድቦታል፡፡ የአዲሱ ሚካኤል ሰንበት ትምህርት ቤት አባል የነበረውና ወደ ቤተክህነት እቃ ሊያደርስ ተልኮ በድንገት ሠራተኛ የሆነው አሁንም በጠ/ቤተ ክህነቱ ገዳማት አስተዳደር ተጧሪ ሆኖ ደመወዝ የሚበላውን ይህንን ጨዋ የአድባራት እና ገዳማት አለቆችንንና ሰራተኞችን ስም በማጥፋት ተግባሩ ማኅበሩ አንቱታን ቸሮታል፡፡ በተጨማሪ እነ ጳውሎስ መልክአ ሥላሴም በዚሁ ተግባር በመሳተፍ ከቤተክህነቱ አደባባይ መዋል ከጀመሩ ሰነባብተዋል፡፡ 



































Sunday, December 15, 2013

የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማዊ ለውጥ ከላዕላይ መዋቅር ይመነጫል እንጂ ለአንድ ሀ/ስብከት ከማኅበረ ቅዱሳን ቢሮ አይደለም!


  • የማኅበረ ቅዱሳን ሩጫ ሀገረ ስብከት የመቆጣጠር ስልት እንጂ ዘረፈ ብዙ የቤተ ክርስቲያኒቱን ችግር ለመፍታት አያገለግልም።
  • ማኅበረ ካህናቱ ከማኅበረ ቅዱሳን አፈናና ስለላ ለመዳን መታገል ያለባቸው ዛሬ ነው!
  • ማኅበረ ቅዱሳን ራሱ ተቋማዊ ለውጥ የሚያስፈልገው ድርጅት ነው!
   ከዚህ ቀደም እንዳልነው ተቋማዊ ህዳሴና አስተዳደራዊ ለውጥ የሚያስፈልገው ለዘመናት ሲንከባለል የመጣውን አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ፈተናዎችና ተግዳሮቶችን  መነሻ ባደረገ መልኩ መሆን አለበት የሚለው ሃሳብ በመጀመሪያ ረድፍ የሚቀመጥ አጀንዳ ነው። ከላዕላይ መዋቅሩ ወይም ከዋልታው የለውጥ ተሐድሶ ባልተጀመረበትና ፈጽሞ ባልታሰበበት ሁኔታ በተናጠል የአንዱ ሀገረ ስብከት አጀንዳ እንደሆነ በመቁጠር በዚያ ዙሪያ መኮልኮል ውጤታማ ፍጻሜ ሊኖረው በፍጹም አይችልም።

 በተለይም ደግሞ ማኅበረ ቅዱሳን በተባለ አንጃ ተጠንስሶና የዲስኩር ውሃ ተሞልቶ ካህናቱ እንዲጠጡ በተዘጋጀው የስልጠና ወሬ የተነሳ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ለውጥ ይመጣል ማለት ዘበት ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ራሱ ተቋማዊ ለውጥ የሚያስፈልገው አፈንጋጭ ድርጅት ሆኖ ሳለ የሀገረ ስብከቱ እቅድ ነዳፊ፤ አሰልጣኝና «የያብባል ገና» ዜማ ደርዳሪ ሆኖ መሰየሙ አስገራሚ ነው። እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ላይከዱት በልጆቻቸው ስም ቃለ መሃላ የገቡለት ሊቀ ጳጳስ እስጢፋኖስ «ተቀመጥ በወንበሬ፤ ተናገር በከንፈሬ» ብለው ለማኅበሩ ያስረከቡትን ሀገረ ስብከት ማኅበረ ካህናቱ አሜን ይሁን፤ ይደረግልን ብለው መቀበላቸው ያሳዝናል። በጣፈጠና በለሰለሰ አማርኛ ነገ ብርሃን ሊወጣልህ ነው እያሉ በማደንዘዝ ላይ የተጠመዱት የማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች የአዲስ አበባን ችግር ከአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር በተለየ የመፍታት ምትሃታዊ ኃይል ስላላቸው ሳይሆን ማኅበረ ካህናቱ ማቅ የተባለውን ድርጅት ውስጣችን አናስገባም ብለው ለ21 ዓመት የታገሉትን ለመቋቋም ይቻለው ዘንድ ገሚሱን የስልጠናው ደጋፊና ገሚሱን የስልጠናው ተቃዋሚ አድርጎ ከፋፍሎ በመምታት እግሩን በመሃከል አደላድሎ ለመትከል ያለመ መሆኑን ሊጤን ይገባል።
  ማኅበረ ካህናቱ በቤተ ክርስቲያኒቱ አጠቃላይ መዋቅራዊና አስተዳደራዊ ለውጥ እንዲመጣ ካስፈለገ ከራሷ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንትና ምሁራን እንጂ ይህ ገንዘቡን በጓሮ እያደለበ፤ ስንት እንደነገደና ስንት እንዳተረፈ ካዝናው የማይታወቅ የመሰሪዎች ስብስብ ማኅበር በሚያረቀውና በሚያቀርበው የስልጠና መርሃ ግብር መሆን እንደሌለበት ማኅበረ ካህናቱ ሊገነዘብ ይገባል። የራሱን በጉያ ደብቆ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ካዝና ለመቆጣጠር እቅድና ትልም ማውጣቱ ድፍረት ብቻ ሳይሆን ጳጳሳቱ እስከደገፉት የሚከለክለው እንደሌለ ያሳየበት አጋጣሚ ነው።
  መዋቅራዊውን ለውጥ ከግቡ ለማድረስ አቅሙና እውቀቱ ካላቸው ከቅዱስ ፓትርያርኩና ከቅዱስ ሲኖዶስ መመንጨት አለበት። ከዚያም በተረፈ ቤተ ክርስቲያን ብትጠራቸው ይህንን ለመስራት ማገዝ የሚችሉ ቅን፤ የቤተ ክርስቲያናቸው ጉዳይ ግድ የሚላቸው፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ አሁን ያለችበት የአስተዳደር ጉድለት ዘወትር የሚያንገበግባቸው ኦርቶዶክሳውያን ምሁራን ሞልተዋል። ስለዚህ ነጋዴ የወጣቶች መንጋ ስኬት ያገኘ ስለመሰለው ብቻ ሀገረ ስብከቱን ልዘዘው፤ ልናዘው ብሎ ስለጠየቀ ሊፈቀድለት አይገባም። ደረጃውም፤ አቅሙም ስላይደለ ሀይ ሊባል የሚገባው ሰዓት ቢኖር አሁን ነው።

 ስለሆነም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ማኅበረ ካህናት የሆናችሁ ሁላችሁም ይህ ካዝናውን በጓሮ የደበቀ ማኅበር የናንተን የአገልግሎት ካዝና እንዲቆጣጠር ልትፈቅዱለት አይገባም። እርግጥ ነው፤ የብዙ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳደሮች ጉድለት፤ ብክነትና ምዝበራ አስቸጋሪ እየሆነ መጥቷል። በእኛ እምነት ይህ ችግር የሚቀረፈው የቤተ ክርስቲያኒቱ ላዕላይ መዋቅር የችግሩን አንገብጋቢነትና ስፋት በጥልቀት ተመልክቶ በቤተ ክርስቲያኒቱ ምሁራንና ሊቃውንት አስጠንቶ አጠቃላይ የለውጥ እንቅስቃሴ በማድረግ ብቻ እንደሆነ እናምናለን። ከዚህ ውጪ አንዱን ጫፍ ለማኅበረ ቅዱሳን አሳልፎ በመስጠት ለውጥ ሊመጣ ስለማይችል ማኅበረ ቅዱሳን ከቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ማሻሻል ጉዳይ እንዲወጣ መታገል ወቅቱ ዛሬ ነው።
በውስጥ ጉዳያችን ማኅበረ ቅዱሳን መግባት የለበትም ለማለት የማኅበረ ካህናቱ ድምጽ መሰማት ያለበት ዛሬ ነው።

Thursday, December 12, 2013

የማኅበረ ቅዱሳን መግነንና ብቀላ መሳ ለመሳ ናቸው፤ እንደጠዋት ጤዛም ቀትር ላይ ይጠፋሉ!


ነፍሳቸውን በአጸደ ቅዱሳን ያሳርፍልንና ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከዚህ ዓለም በሞት ከተለዩ በኋላ ማኅበረ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያኒቱን ያለውልና ፊርማ ተረክቧት እያስተዳደረ ይገኛል። አቡነ ጳውሎስ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ይህንን መሠሪ ማኅበር ከመነሻው የደገፉት ሲሆን ውሎ አድሮ አካሄዱን አይተው የእድሜ ዘመኑን ለማሳጠር ብዙ ቢጥሩም ማኅበሩ ስር ሰዶ፤ የራሱን ጳጳሳት በመመልመል የሲኖዶሱን እኩሌታ መቆጣጠር የቻለበት ደረጃ ላይ ደርሶ ስለነበር ጥቂት ከማንገዳገድ ውጪ ሊጥሉት ሳይችሉ ቀርተው ወደማይቀረው ሞት ሄደዋል።
  አበው «የጠሉት ይወርሳል፤ የፈሩት ይደርሳል» እንዲሉ ይህንን ማኅበር የጠላነውን ያህል ሳይዳከም፤ የፈራነው ቤተ ክርስቲያኒቱን የመረከብ የረጅም ጊዜ ህልሙ እውን እያደረገ መገኘቱን ስንመለከት መጨረሻውስ? ብለን እስክንጠይቅ ድረስ መደመማችን አልቀረም። ምናልባት ቤተ ክህነቱን እንደወረሰ ቤተ መንግሥቱንም ይረከብ ይሆን? ይህንንም እንጠይቃለን። ማኅበሩን ስለመጥላት ስንናገር ሰውኛ ጥላቻ ሳይሆን  እንዴት አንድ ተራ ማኅበር፤ ለዚያውም በጦር ካምፕና በዝሙት መስዋእት ተመስርቶ ሁለት ሺህ ዘመን የዘለቀችውን ቤተ ክርስቲያን ተረክቦ በእጁ ያደርጋታል ከሚል መንፈሳዊ ቁጭትና መሸሻውም ይሁን መገኛው ከንስሐ ሥፍራ መሆን ሲገባው ዐመጽ ወልዶት፤ ዐመጽ ያሳደገው ማኅበር እዚህ መድረሱ አስገራሚም አስደማሚም ከመሆኑ የተነሳ ነው። አንዳንዶች ይህ ማኅበር እንደቴዎዳስ ዘግብጽ ቶሎ ያልጠፋው እግዚአብሔር ስለተከለው ነው በማለት ከእግዚአብሔር ፈቃድ ጋር በማስተሳሰር ሊያሳምኑን ይከጅላሉ። ናቡከደነጾር ኢየሩሳሌምን አጥፍቶ፤ ሕዝቡን 70 ዘመን በባርነት የገዛው ናቡከደነጾር እግዚአብሔርን ያመልክ ስለነበር ሳይሆን የእግዚአብሔር ሕዝብ የተባለው እስራኤል ከእግዚአብሔር አምልኮ ስላፈነገጠ መሆኑም እንዳይዘነጋ ማስረጃ እናቀርብላቸዋለን። ማኅበረ ቅዱሳን 21 ዓመት የመቆየቱ ምስጢርና ቤተ ክርስቲያኒቱን እስከማዘዝ የመድረሱ ነገር በቅድስናው ልክ እግዚአብሔር በመደሰቱ ነው ብለን አናስብም። በዚህ ርዕስ የማኅበረ ቅዱሳንን አነሳስ ትተን አሁን ያለበትን መንፈሳዊ መሰል ሕይወቱን ብንዘረዝር ውሎ ያሳድረናል። ሌላው ቀርቶ የማይታዘዙለትን ጳጳሳት እንዴት እንደሚያበሻቅጥና ሰጥ ለጥ ብለው የሚታዘዙለትን ደግሞ የቱንም ያህል አስነዋሪ ገመና ቢኖራቸው ምን ያህል እንደሚያንቆለጳጵሳቸው በመመልከት ስለማኅበሩ መናገር ይቻላል። «ከእነማን ጋር እንደምትውል ንገረኝና ማንነትህን ልንገርህ» ይባል የለ!

  አብዛኛዎቹ ጳጳሳትም ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ይህንን ማኅበር ቆመው ማውረድ እስኪያቅታቸው ድረስ በተዘዋዋሪ መንገድ ለዚህ ማኅበር የምርኮኝነት እጃቸውን ሰጥተዋል። በየሄዱበት ሀገረ ስብከት ወንበራቸውን ከኋላ የሚሾፍረው ይህ ማኅበር ሲሆን በተለይም ከአቡነ ጳውሎስ ሞት በኋላ በተጠናና በታወቀ ስልት እያደባ፤ ካህናቱንም ሳያስደነግጥ፤ በረቀቀ መንገድ አስተዳደሩን ተረክቦ የሁለት ተቋም አስተዳዳሪ ሆኖ ይገኛል። አንዱ  ቅዱስ የተባለው የሲኖዶስ መንበር ሲሆን ሁለተኛው በግልጽ የሚጠራበት የራሱ ማኅበር ተቋማዊ የንግድ አስተዳደር ነው። ለረጅም ጊዜ ባካበተው የስለላ ልምዱ መረጃዎችን ወደአንድ ቋት በመሰብሰብ እቅድና ትግበራውን በግልጽም በስውርም ያካሂዳል። ለዚህም ተጠቃሹ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አንዱ ነው።
  የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በሙስና፤ በአስተዳደር ብልሹነትና በንቅዘት ግንባር ቀደም ሀገረ ስብከት የመሆኑን ያህል ከፍተኛ የለውጥ እርምጃ የሚያስፈልገው ስለመሆኑ አያጠያይቅም።  እጃቸው በተጠመዘዘና በማኅበረ ቅዱሳን ሳንባ በሚተነፍሱት በአባ እስጢፋኖስ በኩል ለውጥ ይመጣል ብሎ መጠበቅ ግን «ላሞች ባልዋልሉበት ኩበት ለቀማ» ከመሆን የዘለለ ውጤት አይኖረውም ብቻ ሳይሆን የቤተ ክርስቲያኒቱን አናት ለማኅበረ ቅዱሳን አሳልፎ የመስጠት ሂደት መሆኑ ሊሰመርበት ይገባል።
  «የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በለውጥና ህዳሴ ጎዳና፤ ያብባል ገና» በሚለው የማኅበረ ቅዱሳን መፈክር ስር የተጠለለው የአስተዳደር ማሻሻል ትግበራ ሂደት ጥናቱ፤ እቅዱና አፈጻጸሙ ሙሉ በሙሉ እየተከናወነ ያለው በማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች በኩል ስለመሆኑ በግልጽ ይታወቃል። ዞሮ ዞሮ ሀገረ ስብከቱን ለማኅበረ ቅዱሳን እንቅስቃሴ አመቺ በሆነ መልኩ ማዋቀርና ሊመጣ የሚችልበትን ግልጽና ስውር ተቃውሞ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በመዝጋት «ማኅበረ ቅዱሳን፤ ማኅበረ ቅዱሳን» የሚል ድምጸትን የሚያስተጋባ አስተዳደርን መመስረት ዋነኛ ግቡ ስለመሆኑ የምንሰማቸው አቤቱታዎችና እንቅስቃሴዎች አመላካች ናቸው። በቅርቡ እንዳየነው ለማኅበረ ቅዱሳን በጎ አመለካከት የላቸውም የተባሉ ካህናትና ሰራተኞች በስመ ዝውውርና ሽግሽግ ሰበብ ዱላ እያረፈባቸው መገኘቱ አንዱ አስረጂ ነው። ለወደፊቱም በፍጥነት ሳያስደነግጡና ሳያስደነብሩ በማለሳለስ ተመሳሳዩን የበቀል ዱላ እያሳረፉ ለአዲሱ ለውጥና ህዳሴ ስለሆነ ሁላችሁም «ያብባል ገና»  በሚለው ዝማሬ ስር ተሰባሰቡ ማለቱን ይቀጥላል። አባ እስጢፋኖስ ከማኅበረ ቅዱሳን ጉያ ለመውጣት አቅሙም፤ ብቃቱም፤ ሞራሉም የላቸውም፤ ስለዚህ በቦታው እስካሉ ድረስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የጓሮ አስተዳዳሪ ማኅበረ ቅዱሳን ሆኖ መቀጠሉም አይቀሬ ነው። በባላ የተደገፈ ቤት ለጊዜው እንጂ በቀጣይነት ሊቆም አይችልም። የአባ እስጢፋኖስ የማኅበረ ቅዱሳን መዋቅራዊ ማሻሻያም የዚያው ተመሳሳይ ውጤት ከመሆን አይዘልም።  ምናልባትም የማኅበረ ቅዱሳን በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ውስጥ የማቡካት የመጋገር ጅማሮ የማኅበሩን ዕድሜ ቀጣይነት ወሳኝ ምዕራፍ ከፋች ሊሆን እንደሚችል ይገመታል። በሂደት የምናየውም ይሆናል።

ሌላው በተመሳሳይ መልኩ ማኅበረ ቅዱሳንን ካሰማሯቸው ታማኝ አገልጋዮች መካከል የሐዋሳው አቡነ ገብርኤል ተጠቃሽ ናቸው። እንዲያውም ማኅበሩ ራሱ በተደጋጋሚ እንደሚለፍፈው «ማኅበረ ቅዱሳን» ብለው የዳቦ ስሜን ያወጡልኝ አቡነ ገብርኤል ናቸው እያለ በሚጠራቸው የነፍስ አባቱ ቤትም ማዘዝ ከጀመረ ውሎ አድሯል። በተዘዋዋሪም ተጠያቂነት ካለብኝም ይህንን ስም የሸለሙኝ ሊሆን ይገባል በሚል ድምጸት ማኅበሩ ስሙንና አቡነ ገብርኤል ለአፍታም ከአፉ አይነጥልም።

አቡነ ገብርኤል እድሜ ለንስሐ የሰጣቸውን አምላክ ከማመስገን ይልቅ ይህንን ማኅበር በጌታ ምትክ ዘወትር ሲያወድሱት ይታያሉ። በአሜሪካ አደባባይ «የፍየል ወጠጤ፤ ልቡ ያበጠበት…………» ከሚለው የጸረ ኢህአዴግ  ሰላማዊ ሰልፍ አንስቶ በይቅርታ ይሁን በንስሐ ከኢህአዴግ ጋር የታረቁበት መንገድ ለጊዜው ባይታወቅም ሐዋሳ እስከደረሱበት ጊዜ ድረስ በየሄዱበት ሰላም አስፍነው እንደማያውቁ ግለ ታሪካቸው  ይናገራል። ሐዋሳ እንደገቡም የመጀመሪያ ስራቸው ምእመናኑን በመከፋፈል ገሚሱን በማስደንበር የማባረር ስራ አሐዱ ብለው የጀመሩ ሲሆን ከዚህ ጀርባም ያ ቁጭ ብለው የሰቀሉትና ቆመው ማውረድ ያቃታቸው የነፍስ ልጃቸው ማኅበሩ አብሯቸው ነበር።
  እነመጋቤ ሐዲስ በጋሻውን፤ ቀሲስ ትዝታውንና ሌሎቹንም ዘማርያን ነክሶ የያዘውን ማኅበር ደስ ለማሰኘት አባ ገብርኤል እስከመጨረሻው ድረስ ለማሳደድ አላቅማሙም። ደም እስኪፈስና አካል እስኪጎድል ድረስ ሐዋሳን የጦርነት አውድማ ለማድረግም ወደኋላ አላሉም። ማኅበሩ ካዘዘ ሕንድ ውቅያኖስ ውስጥም ከመግባት እንደማይመለሱ ይታወቃል። እንዲያው ተሸፋፍኖ ይቅር ብለን እንጂ አባ ገብርኤል ምን የማያደርጉት ነገር አለ? ከዚህ በደል ለመገላገል ደግሞ ያላቸው ብቸኛው አማራጭ ንስሐ መግባት ሳይሆን ያንን ከነከሰ የማይለቅ ማኅበር እስከመጨረሻው ማገልገል ብቻ ነው። ሰሞኑን በእርቅ ሰበብ ከተጣሏቸው ምእመናን ጋር በመታረቅ አቡነ ገብርኤል ተስማምተውና አካባቢውን መስለው ለማደር ቢፈልጉም ያ ማኅበር ከኋላቸው ሆኖ «አይሆንም፤ አይደረግም» እያለ ሰቅዞ ይዟቸዋል። በተለይም የጥሉ አስኳል ተደርገው በማኅበሩ የብቀላ መዝገብ ላይ የሰፈሩት እነ በጋሻው ይቅርታ ይደረግልን የሚል ማመልከቻ ያቅርቡ እያለ መገኘቱ የሁከቱ ባለቤት ማን እንደነበረ በግልጽ እያሳየ ይገኛል። በዳይና ተበዳይ ማን እንደሆነ የመመርመር ሳይሆን ጉዳዩን በእርቅ የመፍታት ጥረት ላይ ነገሩን ለማደፍረስ የሚደረገው የማኅበሩ ሩጫ አስገራሚም አሳዛኝም ያደርገዋል።  በጋሻው «የበደላችሁኝን ሁሉ ይቅር ብያለው» ማለቱ ሲሰማ ማኅበሩ በተገላቢጦሽ «በድያችኋለሁና ይቅር በሉኝ» ሊል ይገባል በማለት ላይ መጠመዱ ሳያንስ ማኅበሩ በዚህ መካከል የሚጨምረው የተንኮል ቅርቃር ደግሞ «በጋሻው ሃይማኖታዊ ሕጸጽ ስላለበት ጉዳዩ በይቅርታ አያልቅም» የሚል መሆኑ ነው።

«የበደሉንን ይቅር እንደምንል» ጌታ ያስተማረን ጸሎት ነው። በጋሻው ይህንን በማለቱ ተቀባይነት የለውም ማለት ምን ማለት ነው? በግልባጩ በጋሻው በድሎናል የሚል ካለም ይህንን ቃል መልሶ በመጠቀም «የበደሉንን ይቅር እንደምንል» ማለት በጋሻው በድሎናል፤ ግን ይቅር ብለነዋል ማለት የክርስትና መገለጫ እንጂ የትንሽነት ወይም የተጠቂነት ስሜት ማንጸባረቂያ አይደለም። ይሁን እንጂ ማኅበሩ « የበደልኩ እኔ ነኝ፤ ይቅር በሉኝ» የሚል ልመና ሊቀርብልን ይገባል ሲል ይደመጣል። እንዲያማ ቢሆን ኖሮ እኛ የሰው ልጆች  ወደ እግዚአብሔር የማቅረብ የበደለኛነት ጥያቄ እያለብን  የተበደለው አምላክ በደላችንን ይቅር ሊለን ሥጋ ለብሶ ባልመጣ ነበር እንደማለት ነው።  «ጠላቶች ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ከታረቅን፥ ይልቁንም ከታረቅን በኋላ በሕይወቱ እንድናለን» ሮሜ 5፤10
ለጸሎትም በቆማችሁ ጊዜ፥ በሰማያት ያለው አባታችሁ ደግሞ ኃጢአታችሁን ይቅር እንዲላችሁ፥ በማንም ላይ አንዳች ቢኖርባችሁ ይቅር በሉት» ማር 11፤25
እርስ በርሳችሁ ትዕግሥትን አድርጉ፥ ማንም በባልንጀራው ላይ የሚነቅፈው ነገር ካለው፥ ይቅር ተባባሉ። ክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ እናንተ ደግሞ እንዲሁ አድርጉ» ቆላስ 3፤13

ዳሩ ግን ይህ ተበቃይ ማኅበር የጠላቸው ሰዎች መንበርከካቸውንና እጃቸውን በመሸነፍ ስለማስረከባቸው የማረጋገጫ ቃል ካላገኘ በቀር «የበደሉንን ይቅር ብለናል« የሚለው ቃል አያረካኝም እያለ ይገኛል። የወንጌልን ቃል የማይቀበል ይህን መናፍቅ ማኅበር ደርሶ የወንጌል ቃል ተቆርቋሪ ሆኖ በመታየት ሌሎችን የሃይማኖት ሕጸጽ አለባቸው በማለት አለማፈሩ ያስገርማል። የእነ ደብተራ ገለፈትን መጽሐፍ እንጂ ማኅበረ ቅዱሳንና ወንጌል የትም እንደማይተዋወቁ እርግጥ ነው። መናፍቁና ጸረ ወንጌሉ ማኅበር ተግባር የሚመሰክርበትን የወንጌል ቃል ተቃርኖ እየተናገረ ስለወንጌል የመናገር ብቃቱም፤ እውቀቱም የለውም። ዳሩ ግን «ጊዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ ይሰብራል» እንዲሉ ባሰረጋቸው መነኮሳቱ በኩል ጳጳሳት ሆነው ስለተገኙ ብቻ  ቤተ ክርስቲያኒቱን በእነሱ እጅ በመጥፎ አጋጣሚ እያሾራት መገኘቱ ያሳዝናል። እነ አባ ሉቃስን በመሳሰሉ አድር ብዬዎች በኩል መለመላዋን የተገኘችውን ቤተ ክርስቲያን ለጊዜው ተረክቧት ማኅበሩ እያስተዳደረ ነው። «የበደሉንን ይቅር እንደምንል በደላችንን ሁሉ ይቅር በለን» ማለት የክርስትና ጸሎት ነበር። ይህንን ማለት ግን የአላዋቂዎች ጸሎት ተደርጎ ተቆጥሯል። ዳሩ ግን ሥልጣን እውቀትን በተካበት ዘመን ወንጌል ሥፍራ እንደሌለው እውነት ነው። ይሁን እንጂ የወንጌል እውነት በሥልጣንና በገንዘብ ተቀብሮ ሊቀር አይችልም። ከማኅበረ ቅዱሳን አገልጋይ ጳጳሳትና ከማኅበሩም በላይ ሥልጣንና ኃይል የነበራቸውም እንኳን በታሪክ ውስጥ የወንጌልን እውነት ቀብረው ሊያስቀሩ አልተቻላቸውም። ወንጌል በኃይልና በሥልጣን ሊነሳ ሲፈልግ ቦታውን ግሳንግስ ይወረዋል። በውሸት መካከል የወጣ እውነት ሕይወትን የመስጠት ኃይል የሚኖረው ያኔ ነውና።
  የማኅበሩ እንዲህ መገስገስና በየስፍራው  እያየነው የመንገስ ጉዳይ የጥዋት ጤዛን ያሳየናል። ፀሐይ ሲወጣ ጤዛ ባለበት አይገኝም። ዛሬ ለእግዚአብሔር ያለመመቸታችንና ስለኃጢአታችን በፊቱ ያለመውደቃችን ምክንያት እንጂ ንስሐ ገብተን፤ መልካሙን ዘመን እንዲያመጣልን ከልብ ከጸለይን ብላቴን ላይ የተፈለፈለው ማኅበር እንደጥዋት ጤዛ ቢያለጨልጭም ቀትር ላይ ተመልሰን እንደማናገኘው እርግጠኞች ነን። ለዚህ ጸሎት አንድ ኤልያስ በመካከላችን እንደማይጠፋም እናውቃለን። በሰው ላይ እየፈረደ፤ ራሱን ለንግድ አሳልፎ የሚሰጥ ለጊዜው እንጂ ከቆመበት መውደቁ አይቀርም። ይልቅ ራሱን ለንስሐ ቢያዘጋጅ ይበጀዋል።

«እግዚአብሔርን ደጅ ጥና፥ መንገዱንም ጠብቅ፥ ምድርንም ትወርስ ዘንድ ከፍ ከፍ ያደርግሃል ኃጢአተኞችም ሲጠፉ ታያለህ። ኃጥአን ከፍ ከፍ ብሎ እንደ ሊባኖስ ዝግባም ለምልሞ አየሁት። ብመለስ ግን አጣሁት ፈለግሁት ቦታውንም አላገኘሁም። ቅንነትን ጠብቅ፥ ጽድቅንም እይ ለሰላም ሰው ቅሬታ አለውና። በደለኞች በአንድነት ይጠፋሉ። የኃጢአተኞች ቅሬታ ይጠፋል» መዝ 37፤34-38

 

Tuesday, December 10, 2013

ራሺያ የአሸባሪዎች መመሪያ ብላ የሰየመችው «ቁርአንን» በሀገሯ ቋንቋ ተተርጉሞ እንዳይገባ አገደች።


 
አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ እንደዘገበው፤ የራሺያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የአሸባሪዎች የሽብር መመሪያ ነው ያለውን ቁርአን ወደሀገሩ እንዳይገባ የእግድ ውሳኔ አሳለፈ። ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ በውሳኔው ላይ እንዳመለከተው ፤ አንድ መጽሐፍ ወደራሺያ ከመግባቱ በፊት ማኅበራዊ ኑሮን፤ የራሺያን ባህልና ወግ የማይጻረር መሆኑ ሳይመረመር በፊት መግባት ስለማይችል፤ ቁርአን የተባለው መጽሐፍ በሳዑዲ ዐረቢያ ውስጥ በራሺያው ዜጋ ኤልሚር ኩልየቭ በኩል ተተርጉሞ በነጻ ከታተመ በኋላ  ኮፒውን መርምረናል ያለው ፍርድ ቤቱ፤ ይህ መጽሐፍ እንደማንኛውም ሌሎች መጽሐፍ ውስጡ ተመርምሮ የተደረሰበት ጭብጥ እንደሚያስረዳው ትርጉሙ ወደራሺያ ምድር ቢገባ ሽብርን በማበረታታት፤ ጥላቻን በመዝራትና ባህልና ወጋችንን በማደፍረስ ሰላምና መረጋጋት እንዲጠፋ በማድረግ በኩል አሉታዊ ጎኑ የበረታ በመሆኑ እንዳይገባ የእግድ ውሳኔ አሳልፈንበታል ሲል በውሳኔው ላይ ፍርድ ቤቱ ገልጿል።
  በኤልሚር ኩልየቭ በኩል የተተረጎመው ይህ በስም «ቁርአን» የተባለው መጽሐፍ በፍርድ ቤቱ የታየው በየትኛውም የሃይማኖት መጽሐፍነቱ ሳይሆን እንደአንድ ተራ መጽሐፍ ሲሆን የተመረመረውም ይኸው መጽሐፍ ሊሰጥ እንደሚችለው ሀገራዊ ጠቀሜታ አንጻር መሆኑንም ፍርድ ቤቱ ሳይገልጽ አላለፈም።

 ስለሆነም መጽሐፉ ለሀገራቸው ከሚሰጠው ጥቅም ይልቅ ውስጡ ሲመረመር ከጥቅሙ ጉዳቱ ስለሚያመዝን ትርጉሙ ወደሀገር ውስጥ እንዳይገባ ያገደ ሲሆን ይህንን የፍርድ ቤት እግድ ተላልፎ የተገኘ ማንም ዜጋ ሽብርተኝነትን በማበረታታትና በማስፋፋት በሚያስጠይቀው የሀገሪቱ ሕግ መሠረት ተጠያቂ እንደሚሆንም ተገልጿል።
  ይህ «ቁርአን» የተባለው መጽሐፍ የዐረቢኛው ትርጉም በራሺያውያን ሙስሊሞች እጅ የሚገኝ ቢሆንም ከራሺያ ቋንቋ ውጭ ስላሉ ትርጉሞች የተባለ ነገር የለም።

የራሺያው ቋንቋ የቁርአን ትርጉም  በወደሀገሪቱ እንዳይገባ መታገዱን በመቃወም የራሺያው የሙስሊሞች ሙፍቲ ራቪል ጋይኑትዲን ለራሺያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን በጻፉት ደብዳቤ እንዳመለከቱት «ይህ እውቀት የጎደለውና ጸብ አጫሪ ውሳኔ እንደገና መታየት አለበት»  በማለት በኃይለ ቃል መግለጻቸውን «ኸፍ ፖስት» ጋዜጣ ዘግቧል።
  ጠቅላይ ሙፍቲው እንዳሳሰቡት « በጥቁር ባህር ወደብ ላይ ወደራሺያ ሊገባ የተዘጋጀው ይህ የቁርአን ትርጉም በአስቸኳይ መፍትሄ ካልተሰጠው፤ የእስላሞች መጽሐፍ ላይ የተወሰደ ውሳኔ አድርገን እንቆጥራለን» ሲሉ መናገራቸውም ተሰምቷል። አንድ ራሺያዊ ዜጋ ስለጉዳዩ በሰጠው አስተያየት እንደተናገረው « ራሺያ እስልምና ለሚፈልገው ማንኛውም ጉዳይ እንደውሻ ጭራዋን እየቆላች ለማስተናገድ የምትገደድበት ምክንያት የለም፤ እስልምና እዚያው ተፈጠርኩበት ካለው በሳዑዲ ምድር አርፎ ይቀመጥ፤ እንግድነት ከፈለገም እኛ ዜጎቹ በምንፈቅድለት መጠንና መንገድ ብቻ ሊስተናገድ ይገባዋል ሲል የገለጸ ሲሆን ምሬቱን በማከልም « ሳዑዲ ዐረቢያ ቁርአንን አሳትማ ወደራሺያ ስትልክ እንድንቀበልላት እንደምትፈልገው ሁሉ መጽሐፍ ቅዱስን በዐረብኛ ተርጉመን ወደሀገሯ እንድናስገባ በኦፊሴል ትፈቅድልናለች ወይ? ሲል ጠይቋል።

የራሺያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን የፍርድ ቤቱን ውሳኔ በተመለከተ ለሙፍቲው የሰጡት መልስ ምን እንደሆነ አልተዘገበም።

Saturday, December 7, 2013

መነኩሴው በግብረሰዶም ወንጀል በእስራት ተቀጡ



በአሸናፊ ደምሴ /ሰንደቅ ጋዜጣ፤ ህዳር 25 እትም/

ዐቃቤ ሕግ ለአካለ መጠን ባልደረሰ ታዳጊ ላይ የግብረ ሰዶም ጥቃት ፈፅመዋል ሲል ክስ የመሰረተባቸው የ33 ዓመቱ ተከሳሽ አባ ገብረፃዲቅ ወልደሩፋኤል በቀረበባቸው ማስረጃ ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 7ኛ ወንጀል ችሎት ህዳር 19 ቀን 2006 ዓ.ም ውሎ በ4 ዓመት ፅኑ እስራት የቅጣት ውሳኔ ሰጠ።
የፌዴራሉ ዐቃቤ ህግ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው፤ ተከሳሽ ከእርሱ ጋር ተመሳሳይ ፆታ ካለውና ዕድሜው ለአካለ መጠን ባልደረሰው ልጅ ላይ የግብረ ሰዶም ጥቃት ለመፈፀም አስበው ነሐሴ 22 ቀን 2005 ዓ.ም በግምት ከቀኑ 8፡00 ሲሆን፤ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 13/15 አካባቢ ልዩ ቦታው ዳንኤል ሆቴል ውስጥ ዕድሜው 15 ዓመት ከሆነው የግል ተበዳይ ጋር ግንኙነት ለማድረግ በመስማማት በሆቴሉ ሽንት ቤት ውስጥ ተከሳሽ አባ ገብረፃዲቅ ወልደሩፋኤል የግል ተበዳይን ካስገቡት በኋላ የግብረ ሰዶም ግንኙነት ሊፈፅሙ ሲል ሌሎች ግለሰቦች እየተከታተሏቸው መሆኑን ሲያውቁ ሱሪያቸውን አጥልቀው መሸሻቸውን ድርጊቱም በጅምር የተቋረጠ መሆኑን ያትታል። በመሆኑም ዐቃቤ ሕግ ተከሳሹ ለፈፀመው ለአካለ መጠን ባልደረሰ ልጅ ላይ የሚፈፀም የግብረ ሰዶም ጥቃት ለሥነ-ምግባር ተቃራኒ በሆነ ሌላ ድርጊት ሙከራ ወንጀል ክስ መስርቶባቸዋል።  
የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 7ኛ ወንጀል ችሎትም የጉዳዩን ግራና ቀኝ ሲመረምር ከቆየ በኋላ ተከሳሹ የዐቃቤ ሕግን ማስረጃዎች በሚገባ ማስተባበል ባለመቻሉ ጥፋተኛ ነው ሲል ብይን ሰጥቷል። ይህም በመሆኑ ባሳለፍነው ሐሙስ ህዳር 19 ቀን 2006 ዓ.ም በዋው ችሎት ተከሳሹ ጥፋተኛ ሆነው በተገኙበት ወንጀል በአራት አመት ፅኑ እስራትና ለአራት አመታት በሚዘልቅ የመምረጥ መመረጥ እና ከማንኛውም ህዝባዊ መብቱ እንደታገድ ቅጣት ተጥሎበታል።

Wednesday, December 4, 2013

አይ አበሻ! አበሻና ሆድ!

 
አይ አበሻ! አበሻና ሆድ፤
Posted on
by መስፍን ወልደ-ማርያም (Mesfin Wolde-Mariam)
ጥቅምት 2006


አበሻ ድግስ ይወዳል፤ ድግስ የሚወደው መብላትና ማብላት ስለሚወድ ነው፤ ለመብላት የአበሻ ምክንያቱ ብዙ ነው፤ ልጅ ተወለደ ብሎ መብላት ነው፤ ልጅ ክርስትና ተነሣ ብሎ መብላት ነው፤ ልጅ አገባ ብሎ መብላት ነው፤ ልጅ ሞተ ብሎ መብላት ነው፤ አበሻ ሰው ቀብሮ ሲመለስ በንፍሮ ይጀምርና ቀስ በቀስ ወደሌላው ይተላለፋል።
ሃይማኖትም ቢሆን ለመብላት ካልሆነ የነፍሱ ጉዳይማ በጣም ሩቅ ነው፤ ሕያዋን ለነገሥታት፣ ሙታን ለካህናት ይገብራሉ፤ በሚለው መመሪያ መሠረት
ግብር መቀበል ያለ ነው፤ ክርስቶስ ተወለደ መብላት ነው፤ ክርስቶስ ተጠመቀ መብላት ነው፤ ክርስቶስ ሞተና ተቀበረ መብላት ነው፤ ክርስቶስ ተነሣ መብላት ነው፤ ማርያም አረገች መብላት ነው።
ማኅበርም የሚጠጣው (የሚበላው ለማለት ነው፤) ለመብላት ነው፤ አምላክ በተለያዩ ስሞቹ፣ ቅድስት ማርያም በተለያዩ ስሞችዋ፣ መላእክት፣ ቅዱሳን፣ ሰማዕታት ሁሉ ለመብላትና ለማብላት ያገለግላሉ፤ ወደመንግሥተ ሰማያት ለመግባት አማላጅ ሊሆኑ የሚችሉ ሁሉ ማኅበር ለመብላት ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ፤ የሌሎች አገሮች ክርስቲያኖች በመብል አይመለሱም፤ ገበያቸው በጠገራ ብር ነው፤ ስለዚህም አብሮ መብላት ብሎ ነገር የለም።
አበሻ የሚበላው የመጣውን ሲቀበል ብቻ አይደለም፤ የሚሄደውን ሲሰናበትም  መብላት ይወዳል፤ ሞትም ቢሆን ለመብላት ምክንያት ነው፤ ቀብር ብሎ እዝን እያቀረቡ መብላት ነው፤ ሠልስት ብሎ መብላት ነው፤ ለሰባት መብላት ነው፤ ለዓርባው መብላት ነው፤ የሙት-ዓመት ደግሶ መብላት ነው፤ በቀብር ላይም  ቢሆን ለቅሶውም ‹‹ሆዴ! ሆዴ!›› ነው።
ለአበሻ ጾምም ቢሆን ለመብላት ነው፤ የጾም ትልቁ ምሥጢሩ ምግብ እንዲናፍቅ ለማድረግ ነው፤ የፍስኩ የተትረፈረፈ ምግብና ጥጋብ ባይኖር ማን ይጾማል? የለየላቸው ጠጪዎች በሁዳዴ መለኪያውንና ብርጭቆውን አርግፍ አድርገው የሚተውት ሲፈሰክ በናፍቆት ዊስኪውንና ቢራውን ለመጋት ነውኮ! ይህ ባይሆን አንድ ጊዜ ሞጣ ያየሁትየበግ ሌባ ለምን ይጦም ነበር? ታሪኩ እንዲህ ነው፤ በሞጣ አውሮጵላን ማረፊያ አንድ የበግ ቆዳ የያዘ ሰውዬ በፖሊሶች ይጠበቃል፤ እንደሰማሁት በግ ሰርቆ ጫካ ይወስድና ቆዳውን ገፎ ለመሸጥ ወደገበያ ሲሄድ ተይዞ ነው፤ የሁዳዴ ጾም ስለነበረ ሥጋውን ለማይጾሙ አውሬዎች ጫካ ውስጥ ጥሎ ነው! አሁን ይህ ሰውዬ የሚጾመው ሲፈሰክ ደህና አድርጎ በናፍቆት ለመብላት ካልሆነ ለሌላ ለምንድን ነው ሊባል ነው?
ሥራም ቢሆን ለመብል ነው፤ ከመኝታው ሲነሣ ጀምሮ እስኪተኛ ቢበላ ደስታውን አይችለውም፤ለገና፣ ለፋሲካ፣ ለእንቁጣጣሽና ለመስቀል ለገናና ለፋሲካ፣ ለእንቁጣጣሽና ለመስቀልም ከሌሊት ጀምሮ ከአንዱ ቤት አንዱ ቤት እየተዘዋወሩ በመብላት ቀኑ ያልፍ የለም እንዴ! በእውነት አበሻ መብላት የሚወደውን ያህል ማብላትም ይወዳል፤ ስሞት! ስቀበር! አፈር ስገባ! … ወዘተ. እየተባባለ የጠገበውን ሰው በቁንጣን እንዲሰቃይ ማድረግ የአበሻ ልዩ የፍቅር መግለጫ ነው! መጎራረስም አለ፤ ፍቅርና ጉርሻ ሲያስጨንቅ ነው እየተባለ ፍቅርና ሆድን ያያይዛል፤ አነጋገሩ አበሻ ለመብላት ያለውን እንጂ ፍቅርን አይገልጽም፤ ማሰጨነቅንና ፍቅርን ምን አገናኛቸው! አበሻ ሌላም ተረት አለው፤ የወለዱትን ካልሳሙለትና የሠሩትን ካልበሉለት ደስ አይለውም ይባላል፤ የልጅ ፍቅር ከምግብ ፍቅር ጋር ተስተካክሎ የቀረበ ይመስላል፤ ደሞም ብቻውን የበላ ብቻውን ይሞታል፤ ይላል፤ ጉድ ነው! ሲሞትም ተከተሉኝ የሚል ይመስላል!! ለነገሩማ ፍቅርምኮ አበሻ ዘንድ ምግብ ነው፤ ሆዴ! አንጀቴ! ጎንደሬዎች ሲያሳምሩት ደግሞ ራቴዋ! ይሉታል።
ዛሬ ዛሬ አበሻ ከማብላት ይልቅ ማጠጣት ይወዳል፤ እስቲ ሰዎች ሰብሰብ ብለው በሚጠጡበት ቦታ ብቅ በሉ፤ ያቺን የፈረደባትን ጉበት ለማቃጠል በአቦ፣ በሥላሴ የማይል የለም፤ ቸገረኝ ብሎ ገንዘብ የሚጠይቅ አይምጣ እንጂ ለማብላትና ለማጠጣት፣ ለአንድ ጥሪኝ ፈሳሽ አበሻ ቸር ነው፤ በላኤ ሰብስ በማርያም ስም አንድ ጥሪኝ ውሀ ሰጥቶ አይደለም እንዴ የበላው ሰው ሁሉ የተሰረዘለት? አበሻ በሆድ አይጨክንም።
ለአበሻ ምግብ ክቡር ነው፤ ስለዚህም ምንም ነገር ሲበላ ተቀምጦ ነው፤ ፈረንጅ ቂሉ በየመንገዱ እንደመጋዣ ያመነዥካል፤ በየመንገዱ ማመንዠክ ምግቡን ማዋረድ ነው፤ ከዚያም በላይ ቆመው ሲበሉ ወደጉልበት ይወርዳል ይላል፤ ለአበሻ ጨጉዋራና ጉልበት በቀጥታ የተገናኙ ናቸው፤ ሳይንሱ የሚለው ሌላ ቢሆንም አበሻ አበሻ ምን ቸገረው?
ለመሆኑ ከሆድ ጋር ያልተያያዘ ነገር አበሻ ምን አለው?  ነገርን በሆድህ ያዘው ምን ማለት ነው? ነገርን ማብላላት የማሰብ ምትክ መሆኑ ነው፤ ልጆች ሆነን አይጥ አበላሁት እንል ነበር፤ አሸነፍሁት ለማለት ነው፤ ዛሬም ቢሆን ቁማርተኞች በላሁ-ተበላሁ ይባላሉ፤ አይጥ ከማብላት ገንዘብ ወደማብላት ተለወጠ እንጂ ከሆድ አልወጣም፤
አበሻ በሆዱ የማይዘው ምን ነገር አለ? ፍቅርም፣ ጥላቻም በሆድ ነው፤ ቂምም በሆድ ነው፤ ምኞትም ፍላጎትም በሆድ ነው፤ ተስፋም በሆድ ነው፤ መጥኔ ይስጠው የአበሻ ሆድ! ሁሉን ከተናገሩት ሆድ ባዶ ይቀራል፤ አይ የአበሻ ሆድ! የነገር ስልቻ ከመሆኑ በላይ ነገር አልቆበት ‹‹ነገር እንዳይርበው(!)›› ጥንቃቄ ማድረግ አለበት! የአበሻ ሆድ እህል ቢያጣና ከእህል ባዶ ቢሆንም ከነገር ባዶ መሆን የለበትም፤ እህል ቢጠፋም ነገር አይጥፋ!
የአበሻና የሆድ ነገር በዚህ አያበቃም፤ አበሻ ሲያመው ቡዳ በልቶት ነው፤ ቆንጆውን ሁሉ ቡዳ ይበላዋል፤ ልብ በሉ ለአበሻ በዓይንም ይበላል ማለት ነው! አንዳንዴም ሲያመው መድኃኒቱ ምግብ ነው፤ ለሆድ ቁርጠት ብላበት፤ አበሻ ሲሞትም ለቅሶው ሁሉ ስለሆድ ነው፤ ‹‹የኔ ሆድ፣ ሆዴ እንዴት ይቻለው! ፋሲካን የት ልፈስክ?››
እስከናካቴው ‹‹ሆድ›› የሚባል ቃል ከአበሻ ቋንቋ ፈጽሞ ቢሰረዝ ቋንቋው ብቻ ሳይሆን አበሻም ጉድ ይፈላበታል፤ አእምሮ፣ ኅሊና የሚባሉትን ቃላት አበሻ አያውቃቸውም፤ ተግባራቸውንም ሁሉ ለሆድ ሰጥቶታል።