Wednesday, December 25, 2013

ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ አባ ማቴዎስ በአሜሪካ ላለው የማኅበረ ቅዱሳን ክፍል ብዙ ቢጥሩም ፓትርያርኩ ከሊቀጳጳሱ ጋር ሁሉም ሊስማማ ይገባል በማለታቸው ድካማቸው ፍሬአማ ሳይሆን ቀርቷል!

አባ ማቴዎስ ከፓትርያርኩ ተነጥለው ወደናሽቪል በማቅናት ሐመረ ኖኅ ኪዳነ ምህረት ግቢ ሲደርሱ
  ወደአሜሪካ ካቀኑት ፓትርያርክ ጋር አብረው የተጓዙት አዲሱ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሥራ አስኪያጅ አባ ማቴዎስ በአሜሪካ ያለውን የማኅበረ ቅዱሳን ንዑስ ክፍል ከደረሰበት ጫናና አጣብቂኝ ለመታደግ ተስፋ መስጠታቸው ተሰምቷል። ጠቅላይ ስራ አስኪያጁ ከአዲስ አበባው የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጽ/ቤት በተቀበሉት መመሪያ መሠረት በካሊፎርኒያው አኅጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ በሊቀ ስዩማን ኃይለ ጊዮርጊስ አመራር የተነሳ የማቅ ቅርንጫፍ መተንፈሻና መላወሻ በማጣቱ ውጥረቱን ያረግቡላቸው ዘንድ የተነገራቸውን ተልእኮ ለመፈጸም አሜሪካ እንደደረሱ ደፋ ቀና ሲሉ መሰንበታቸው ከአካባቢው የደረሰን መረጃ አመልክቷል። እንደዘገባው ከሆነ ቢቻል ተስማምተው እንዲሰሩ በማግባባት ጊዜ ለመግዛት የሚቻልበትን ሁኔታ መፍጠር ፤ ባይቻል በማኅበረ ቅዱሳን የጥላቻ መዝገብ ላይ ከሰፈሩትና ቁጥር አንድ ባላንጣ ሆነው የተቆጠሩት ሊቀ ሥዩማን ኃ/ጊዮርጊስን ከስራ አስኪያጅነት ለማስነሳት ከአሜሪካው ጉዞአቸው በኋላ ዋና ስራቸው እንደሚሆን ቃል መግባታቸውን እንቅስቃሴውን ሲከታተሉ የነበሩ እማኞች ገልጸዋል።

 ስራ አስኪያጁ ወደአዲስ አበባ እንደተመለሱም ለአሜሪካው ማኅበረ ቅዱሳን ቅርንጫፍ ለመጀመሪያ ጊዜ እንደአንድ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋም ተቆጥሮ ደብዳቤ የጻፉለት ሲሆን ይህም የሚያሳየው ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግና ደንብ የሚተዳደር መሆኑን በማመልከት ሁኔታዎች ሰላማዊና ፍሬያማ ሆነው እንዲቀጥሉ ካስፈለገ ሊቀ ሥዩማን ኃይለ ጊዮርጊስ ካለበት ቦታ እንዲነሳ ለማስቻል መሆኑም ውስጠ አዋቂዎቹ ጠቁመዋል።
  በዚሁ መሰረት ከጉዞአቸው መልስ ለማኅበረ ቅዱሳን ያላቸውን ቁርጠኝነት ለማሳየትና የተቀበሉትን ተልእኮ ለመፈጸም በሚመስል መልኩ የአሜሪካው አኅጉረ ስብከት የስራ እንቅስቃሴ ሰላማዊና ተግባቦት የተሞላው ሆኖ እንዲቀጥል ካስፈለገ በብዙዎቹ ዘንድ እንደምክንያት የተቆጠሩት ሊቀ ሥዩማን ኃይለ ጊዮርጊስ ከቦታው ቢነሱ የተሻለ ነው በማለት  ለቅዱስ ፓትርያርኩና ለውጭ ግንኙነት የበላይ ኃላፊው ለብፁዕ አቡነ ገሪማ ያቀረቡ ቢሆንም ጥያቄያቸው ተቀባይነት ሳያገኝ መቅረቱም የደረሰን መረጃ አክሎ ገልጿል። ሀገረ ስብከቱ በአቡነ ፋኑኤል የሚመራ እንደመሆኑ መጠን ሥራ አስኪያጁ ይነሳልኝ የሚል ጥያቄ ከሊቀ ጳጳሱ ሳይቀርብ በውስጥ አስተዳደራቸው ጣልቃ እንደመግባት ስለሚቆጠር የሊቀ ሥዩማን ኃይለ ጊዮርጊስ ከቦታው መነሳት ለማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች ጉም እንደመዝገን ሆኖባቸዋል።

 በአንድ ስብሰባ ላይ ማቆች የከሳሽና የተከሳሽ የክርክር መድረክ ሳይቸግራቸው ከፍተው ኃይለ ጊዮርጊስን እናዋርዳለን ብለው የጀመሩት እነያሬድ ገብረ መድኅንና እሸቱን የመሳሰሉ የማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች ከሥራ አስኪያጁ በቀረበባቸው የመልስ ምት መሰረት ያሬድ በጋብቻ ላይ ጋብቻ የፈጸመ ሆኖ ሳለ ቀሲስ ብሎ እንደሚጠራ፤ እሸቱ በፖሊስ በቀረበበት ማስረጃ የብዙ ሴቶችን ድንግልና ማጥፋቱ ተዘግቦ ሳለ ቀሲስ እሸቱ መባሉ አግባብ እንዳልሆነ፤ ይህም በሰውና በሰነድ ማስረጃ እንደሚረጋገጥ ሲገለጽባቸው በጉባዔው ላይ በሃፍረት ተሸማቀው የሚገቡበት እንደጠፋቸው የዓይን እማኞች ገልጸዋል።  ምሰሶ የሚያክል ኃጢአታቸው የራሳቸውን እንዳያዩ የጋረደ ዓይናቸውን ገልጠው የሥራ አስኪያጁን ኃጢአት ለመደርደርና በጉባዔው መካከል ለማዋረድ ቢፈልጉም የቀረበባቸው ምት ጨርቃቸውን ጥለው እስኪሄዱ ድረስ ቀልባቸውን የገፈፈ ነበር። እነዚህ የማኅበረ ቅዱሳን ጉዶች በጫሩት እሳት ከመለብለባቸው የተነሳ ከዚያ ወዲህ በያሉበት ድምጻቸውን አጥፍተዋል። እድለኛ ቢሆኑና ንስሐ ቢገቡ የውሸት ቅስናቸውን መልሰው እግዚአብሔር በሰጣቸው የመዳን ጸጋ ሰርተው ቢኖሩ ምንኛ ባማረላቸው ነበር!!
  ዳሩ ግን የማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች በንስሐ የተፉትን ኃጢአት መልሶ ለመላስ እንደማይቸገሩ የብዙዎች አባላቱ የተገለጠ ነውር በአደባባይ ይጮሃል።
ቀሲስ? ያሬድ።

እንግዲህ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ከእንደዚህ ዓይነቶቹ የማቅ ደጋፊዎች ጋር ነው ጥንቃቄና ስልት በተሞላበት አካሄድ ማንም ሳያውቅባቸው ግንኙነት በማድረግ በምድረ አሜሪካ የሰነበቱት።
  ከዚሁ ጋር ተያይዞ ለስልታዊ እርምጃቸው ብዙ የሚጠነቀቁትና በረቂቅ አካሄዳቸው የሚታወቁት አባ ማቴዎስ በአሜሪካ ቆይታቸው በካሊፎርኒያው አኅጉረ ስብከት ሥልጣነ ክህነቱ የታገደው የማኅበረ ቅዱሳን አጫፋሪ እንደሆነ የሚነገርለት የዶ/ር መስፍንን ቤተ ክርስቲያን መጎብኘታቸው የታወቀ ሲሆን ከማኅበሩ አባላትና ከአንዳንድ የፖለቲካ ሽታ ካላቸው ሰዎች ጋር ያደረጉት ውይይት በመቅረፀ ድምጽ መረጃው መያዙም ታውቋል። አባ ማቴዎስ በወያኔ/ኢህአዴግ አገዛዝ መማረራቸውን በመግለጽ ሁኔታዎች በዚህ ከቀጠሉ  ወደአሜሪካ መጥተው ከመኖር ውጪ ሌላ አማራጭ እንደሌላቸው መናገራቸውም የደረሰን መረጃ ያስረዳል። ምናልባትም  ለፓትርያርክነት የነበራቸውን ህልም ያጨለመባቸው ያለፈው የውድድር ሜዳ ቀድሞ በተዘጋጀ ስሌት በመጠናቀቁ የተነሳ ወደፊትም ኢህአዴግ እስካለ ተስፋ የለኝም ከሚል እሳቤ የተነሳ ሁኔታዎች ካላመቹ ወደአሜሪካ ለማቅናት ማሰባቸው ላያስገርም እንደሚችልም  ተነግሯል።