Sunday, December 15, 2013

የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማዊ ለውጥ ከላዕላይ መዋቅር ይመነጫል እንጂ ለአንድ ሀ/ስብከት ከማኅበረ ቅዱሳን ቢሮ አይደለም!


  • የማኅበረ ቅዱሳን ሩጫ ሀገረ ስብከት የመቆጣጠር ስልት እንጂ ዘረፈ ብዙ የቤተ ክርስቲያኒቱን ችግር ለመፍታት አያገለግልም።
  • ማኅበረ ካህናቱ ከማኅበረ ቅዱሳን አፈናና ስለላ ለመዳን መታገል ያለባቸው ዛሬ ነው!
  • ማኅበረ ቅዱሳን ራሱ ተቋማዊ ለውጥ የሚያስፈልገው ድርጅት ነው!
   ከዚህ ቀደም እንዳልነው ተቋማዊ ህዳሴና አስተዳደራዊ ለውጥ የሚያስፈልገው ለዘመናት ሲንከባለል የመጣውን አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ፈተናዎችና ተግዳሮቶችን  መነሻ ባደረገ መልኩ መሆን አለበት የሚለው ሃሳብ በመጀመሪያ ረድፍ የሚቀመጥ አጀንዳ ነው። ከላዕላይ መዋቅሩ ወይም ከዋልታው የለውጥ ተሐድሶ ባልተጀመረበትና ፈጽሞ ባልታሰበበት ሁኔታ በተናጠል የአንዱ ሀገረ ስብከት አጀንዳ እንደሆነ በመቁጠር በዚያ ዙሪያ መኮልኮል ውጤታማ ፍጻሜ ሊኖረው በፍጹም አይችልም።

 በተለይም ደግሞ ማኅበረ ቅዱሳን በተባለ አንጃ ተጠንስሶና የዲስኩር ውሃ ተሞልቶ ካህናቱ እንዲጠጡ በተዘጋጀው የስልጠና ወሬ የተነሳ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ለውጥ ይመጣል ማለት ዘበት ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ራሱ ተቋማዊ ለውጥ የሚያስፈልገው አፈንጋጭ ድርጅት ሆኖ ሳለ የሀገረ ስብከቱ እቅድ ነዳፊ፤ አሰልጣኝና «የያብባል ገና» ዜማ ደርዳሪ ሆኖ መሰየሙ አስገራሚ ነው። እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ላይከዱት በልጆቻቸው ስም ቃለ መሃላ የገቡለት ሊቀ ጳጳስ እስጢፋኖስ «ተቀመጥ በወንበሬ፤ ተናገር በከንፈሬ» ብለው ለማኅበሩ ያስረከቡትን ሀገረ ስብከት ማኅበረ ካህናቱ አሜን ይሁን፤ ይደረግልን ብለው መቀበላቸው ያሳዝናል። በጣፈጠና በለሰለሰ አማርኛ ነገ ብርሃን ሊወጣልህ ነው እያሉ በማደንዘዝ ላይ የተጠመዱት የማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች የአዲስ አበባን ችግር ከአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር በተለየ የመፍታት ምትሃታዊ ኃይል ስላላቸው ሳይሆን ማኅበረ ካህናቱ ማቅ የተባለውን ድርጅት ውስጣችን አናስገባም ብለው ለ21 ዓመት የታገሉትን ለመቋቋም ይቻለው ዘንድ ገሚሱን የስልጠናው ደጋፊና ገሚሱን የስልጠናው ተቃዋሚ አድርጎ ከፋፍሎ በመምታት እግሩን በመሃከል አደላድሎ ለመትከል ያለመ መሆኑን ሊጤን ይገባል።
  ማኅበረ ካህናቱ በቤተ ክርስቲያኒቱ አጠቃላይ መዋቅራዊና አስተዳደራዊ ለውጥ እንዲመጣ ካስፈለገ ከራሷ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንትና ምሁራን እንጂ ይህ ገንዘቡን በጓሮ እያደለበ፤ ስንት እንደነገደና ስንት እንዳተረፈ ካዝናው የማይታወቅ የመሰሪዎች ስብስብ ማኅበር በሚያረቀውና በሚያቀርበው የስልጠና መርሃ ግብር መሆን እንደሌለበት ማኅበረ ካህናቱ ሊገነዘብ ይገባል። የራሱን በጉያ ደብቆ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ካዝና ለመቆጣጠር እቅድና ትልም ማውጣቱ ድፍረት ብቻ ሳይሆን ጳጳሳቱ እስከደገፉት የሚከለክለው እንደሌለ ያሳየበት አጋጣሚ ነው።
  መዋቅራዊውን ለውጥ ከግቡ ለማድረስ አቅሙና እውቀቱ ካላቸው ከቅዱስ ፓትርያርኩና ከቅዱስ ሲኖዶስ መመንጨት አለበት። ከዚያም በተረፈ ቤተ ክርስቲያን ብትጠራቸው ይህንን ለመስራት ማገዝ የሚችሉ ቅን፤ የቤተ ክርስቲያናቸው ጉዳይ ግድ የሚላቸው፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ አሁን ያለችበት የአስተዳደር ጉድለት ዘወትር የሚያንገበግባቸው ኦርቶዶክሳውያን ምሁራን ሞልተዋል። ስለዚህ ነጋዴ የወጣቶች መንጋ ስኬት ያገኘ ስለመሰለው ብቻ ሀገረ ስብከቱን ልዘዘው፤ ልናዘው ብሎ ስለጠየቀ ሊፈቀድለት አይገባም። ደረጃውም፤ አቅሙም ስላይደለ ሀይ ሊባል የሚገባው ሰዓት ቢኖር አሁን ነው።

 ስለሆነም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ማኅበረ ካህናት የሆናችሁ ሁላችሁም ይህ ካዝናውን በጓሮ የደበቀ ማኅበር የናንተን የአገልግሎት ካዝና እንዲቆጣጠር ልትፈቅዱለት አይገባም። እርግጥ ነው፤ የብዙ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳደሮች ጉድለት፤ ብክነትና ምዝበራ አስቸጋሪ እየሆነ መጥቷል። በእኛ እምነት ይህ ችግር የሚቀረፈው የቤተ ክርስቲያኒቱ ላዕላይ መዋቅር የችግሩን አንገብጋቢነትና ስፋት በጥልቀት ተመልክቶ በቤተ ክርስቲያኒቱ ምሁራንና ሊቃውንት አስጠንቶ አጠቃላይ የለውጥ እንቅስቃሴ በማድረግ ብቻ እንደሆነ እናምናለን። ከዚህ ውጪ አንዱን ጫፍ ለማኅበረ ቅዱሳን አሳልፎ በመስጠት ለውጥ ሊመጣ ስለማይችል ማኅበረ ቅዱሳን ከቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ማሻሻል ጉዳይ እንዲወጣ መታገል ወቅቱ ዛሬ ነው።
በውስጥ ጉዳያችን ማኅበረ ቅዱሳን መግባት የለበትም ለማለት የማኅበረ ካህናቱ ድምጽ መሰማት ያለበት ዛሬ ነው።