Wednesday, June 22, 2016

ማኅበረ ቅዱሳን ወንጌልን ማቆም ያልቻለው ለምንድነው?


ከዙፋን (ተስተካክሎ የቀረበ)
ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሰረተ 25 አመት ሞላው። ድርጅቱ ከተመሰረተ ጀምሮ የፕሮቴስታንት፣ የካቶሊክና ሌሎች የክርስትና ክፍሎች የወንጌል ስብከት በፊት ከነበራቸው ውስንነት በበለጠ ሲሰፉ እንጂ ሲጠፉ አልታየም።
 በተለይም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች የሆኑና ቤተክርስቲያኒቱ ከወንጌል ጋር አንዳንዴም ከወንጌል በላይ ስፍራ የምትሰጣቸው ትውፊቶች፣ ድርሳናት፣ ገድላት ከዚያም ባለፈ ልዩ ልዩ አስማትና ተረቶች የእግዚአብሔርን የክብር ስፍራ ወስደውና ጋርደው መገኘታቸውን ያስተዋሉና ከውስጥ የተነሱ የተሃድሶ እንቅስቃሴዎች ከነበሩበት ሁኔታ እየሰፉና እያደጉ መጥተዋል። ግንዛቤያቸውን በሁሉም ዘንድ በማዳረስ ረገድ ሰፊ ተቀባይነት በማግኘታቸው ከነበሩበት የተወሰነ ሁኔታ ወጥተው ዛሬ ከማኅበሩ የ25 ዓመታት ቁጥጥር ውጪ ናቸው። ማኅበሩ የተሐድሶ እንቅስቃሴን ለመጨፍለቅ ያልቆፈረው ጉድጓድ፣ ያልፈነቀለው ድንጋይ አልነበረም። ከንግድ ድርጅቶቹ የሚያገኘውን ግዙፍ ገንዘብ፣ የሰው ኃይልና ማቴሪያልም ጭምር ለዚህ ስራ ያውላል። በተሐድሶ ላይ ግንዛቤ ማስጨበጫ፣ ዐውደ ርእይ፣ ስብሰባ፣ ወርክሾኘ፣ በንግሥ በዓላት፣ በዐውደ ምሕረት፣ በፅሑፍ፣ በምስል ወዘተ ልዩ ልዩ መንገዶች ህዝቡን ያስተምራል፣ ያስጠነቅቃል ቪዲዮ ይበትናል፣ ካሴት ይለቃል፣ በራሪ ወረቀቶችን ያሰራጫል። በዩኒቨርሲቲዎች፣ በኮሌጆች፣ በሕጻናት፣ በወጣቶች፣ በጎልማሶች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት ባሉ ሰንበት ት/ ቤት ተማሪዎች ላይ ሥር ነቀል ለውጥ ለማምጣት ሰርቷል። ተጽእኖውና መልእክቱ ያልገባበት ቤት የለም። ተሐድሶ፣ ሃራጥቃ፣ መናፍቃን፣ የአውሬው ተከታዮች፣ ፀረ ማርያሞች፣ ጠላቶች፣ ነካሾች፣ ቡችሎች…ወዘተ ብዙ ስም አውጥቶ ለማስጠላት ሞክሯል። በስለላ፣ በክትትል፣ በጥርጠራና በድጋፍ አብሮት ያልቆመውን ሁሉ ስም እየለጠፈ በማባረርና በማስፈራራት ብዙ ቢጓዝም ትምህርተ ተሐድሶ ግን ሊቀንስ አልቻለም። ከዚህ ሁሉ ልፋት በኋላ በውጤቱም በ25 አመት በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ታይቶ በማታወቅ መልኩ 15 ሚሊዮን ህዝብ በላይ ከኦርቶዶክስ አካውንት ወደ ፕሮቴስታንት እምነት ጎርፏል።
ብዙ ሚሊዮን ኦርቶዶክሳዊያን ምእመናን፣ መምህራን፣ ሊቃውንት፣ ቀሳውስት፣ መነኮሳት፣ ጳጳሳት ሳይቀሩ ባሉበት ቤታቸው ሆነው የተሐድሶ እንቅስቃሴን ደጋፊና አራማጅ ሆነዋል። የተሐድሶ እንቅስቃሴ መጀመር ወደሌላ የእምነት ድርጅት የሚኮበልለውን ምዕመን ቁጥር መቀነስ ችሏል። ችግሩ ያለው ከኦርቶዶክስ መሠረታዊ አስተምህሮ ሳይሆን በጊዜ ብዛት በገቡ የስህተት ትምህርቶችና የፈጣሪን ሥፍራ የተረከቡ የክህደቶች አምልኰዎች የተነሳ መሆኑን ተሐድሶዎች ማሳወቅ በመቻላቸውና ይህንን ለማስወገድ ደግሞ እዚያው ሆኖ በማስተማርና በመለወጥ እንጂ በመኮብለል አለመሆኑን ብዙ በመሥራታቸው የተነሳ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ የሱን የኑፋቄ ጽዋ ለመጨለጥ ያልፈለጉት እዚያው ከሚቆዩ ይልቅ ኮብልለው የትም ገደል ቢገቡለት ይመርጣል። በጀትና ኃይል መድቦ ተሐድሶዎችን ከመከታተል ይልቅ ከበረት አስወጥቶ፣ በረቱ ውስጥ የቆዩለትን በጎች የራሱ የግል ንብረት አድርጎ ለመቆጣጠር ያመቸዋል። ያስቸገረውና ብዙ ድካሙን መና ያስቀረው ነገር የተሐድሶ ኃይል በእውቀት፣ በጥበብና በተዋሕዶ ቀደምት እውነት ሁሉን ማዳረስ መቻሉ ነው።
የማኅበረ ቅዱሳን ትልቁ ችግር ራሱን የእውነትና የእምነት ጫፍ አድርጎ መመልከቱ አንዱ ጉዳይ ሲሆን ሌላው ደግሞ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአስተምህሮ ጥግ ላይ ከማኅበረ ቅዱሳን ውጪ ያለው ለማስተማር መሞከር ማለት አፍን ማሞጥሞጥ እንደሆነ አድርጎ ማሰቡ ነው። እውነታው ግን በተሐድሶ ምሁራንና በማኅበረ ቅዱሳን መካከል ያለው የእውቀት ልዩነት የሰማይና የምድር ያህል የተራራቀ የመሆኑ ጉዳይ ነው። ተሐድሶ አዲሱን የወይን ጠጅ በአዲስ አቁማዳ ይቀመጥ ሲል ማኅበሩ ደግሞ በአሮጌው አቁማዳ አዲሱን የወይን ጠጅ ማስቀመጥ ይቻላል በሚለው የእምነት አስተሳሰብ ልዩነት የተነሳ በተደራጀ አቅምና ሥልጣን በሚያደርገው ሩጫ ተሐድሶን ማስቆም አልቻለም። ተሐድሶ የግለሰቦች አሳብ ሳይሆን የእግዚአብሔር አሰራር መገለጫ በመሆኑ ማንም ድርጅት በትግል ሊያቆመው አይችልም።
“ወልበስዎ ለሐዲስ ብእሲ ዘሐደሶ እግዚአብሔር በጽድቅ፣ ወበርትዕ፣ ወበንጽሕ” ኤፌ 4:24
“ለእውነትም በሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ” የሚለን እግዚአብሔር በቃሉ አማካይነት ነው። በተረታ--ተረትና በእንቶ ፈንቶ ጩኸት በመባከን ፈንታ የወንጌልን እውነት መጨበጥ፣ ባዶ ተስፋ ከሚያስጨብጡ ዝናብ አልቦ ደመናዎች ዝናብ ከመጠበቅ ይልቅ ባለቤቱ ራሱ የሕይወት ውሃ ምንጭ እኔ ነኝ ካለው እውነት ቃሉ በመጠጣት መርካት መቻል ማለት መታደስ፣ መለወጥ፣ አዲስ ሰው መሆን ማለት ነው። እግዚአብሔር ሁሉም ሰው እንዲታደስለት ይፈልጋል። የተሰራነው አንድ ጊዜ ተሞልቶ ፈፅሞ ከማይደክም የባትሪ ኃይል አይደለም።
“ወዘንተ ውስጥነሰ ይትሔደስ ኩሎ አሚረ”
“... የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል” 2ኛ ቆሮ 4:16 እንዳለው መታደስ በመንፈሳዊነት ኃይል እግዚአብሔር እንደሚወደው ሆኖ መሰራት ማለት ነው።
በዚህም የተነሳ ማኅበረ ቅዱሳን የሚታገለው የእግዚአብሔርን ሃሳብ ለማስቆም ነው። ነገር ግን እስካሁንም አልቻለም፣ ወደፊትም አይችልም። ምክንያቱም ተሐድሶ፣

1. የእግዚአብሔር ሃሳብ ነው።

 በመጨረሻው ዘመን የክርስቶስ ወንጌል በምድር ሁሉ ሊሰበክ ግድ ነው። ሉቃ 12:49 “በምድር ላይ እሳት ልጥል መጣሁ “ እንደሚለው ጌታ የጣለው እሳት ይነዳል እንጂ አይጠፋም። ሐዋ 5-38
  “ይህ አሳብ ከሰው እንደ ሆነ ይጠፋልና፤ ከእግዚአብሔር እንደሆነ ግን ታጠፉአቸው ዘንድ አይቻላችሁም፣ ከእግዚአብሔር ጋር ስትጣሉ እንዳትገኙ” እንዳለው ከእግዚአብሔር ስለሆነ ሊጠፉ አልቻሉም፣ አይጠፉምም ።

2. የአብርሖት (enlightenment) ዘመን በመሆኑ፣

ይህ ዘመን ትምህርት የተስፋፋበት ብዙዎች ከመሃይምነት ነጻ የወጡበት መረጃ የበዛበት ነው። የሰዎች መንፈሳዊ ረሃብ በማይረዱት ግእዝ የማያውቁትን ነገር ተቀብለው ወደቤት ከመሄድ ባለፈ መጽሐፍ ቅዱስና መንፈሳዊ ፅሑፎችን በማንበብ ማብራሪያና መልስ የሚፈልግበት ዘመን ነው። ትውልዱ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ልምምድን በመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ይፈትሻል። ለእምነቱ በቂ ማብራሪያ ይሻል። ያነጻጽራል። መጽሐፍ ቅዱስን በሞባይሉ አስጭኖ የትም ቦታ ያነባል። እንደ መጨረሻ ባለሥልጣን ቃልም ያየዋል። ከዚህ ቃል ጋር የሚጋጭ ወይም ለማስታረቅ የሚሞክርን ማንኛውንም ውሸት ለመቀበል አይፈልግም። ይህንን ዘመነ አብርሖት ከእውነት ጋር በመስማማት እንጂ በመሸፋፈን ወይም ትቀሰፋለህ፣ በሰይፍ ትቆረጣለህ በሚል ማስፈራራት ማስቆም አይቻልም።

3. ዛሬም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መዳንና ፈውስ ስላለ፣

 እግዚአብሔር በአንድ ቃልና በጸሎት በአንዴ መፈወስ ያቃተው ይመስል ለሥጋዊ ፈውስ ሸንኮራ፣ ጻድቃኔ፣ግሼን፣ሚጣቅ፣ ሺፈጅ፣ ኩክየለሽ፣ ግንድአንሳ፣ ከድንጋይ አጣብቅ፣ መሿለኪያ፣ መንከባለያ፣ ገልብጥ፣ ሰንጥቅ ወዘተ አዳዲስ የፈውስ መደብር እየፈጠሩ የአንዱ ወረት ሲያልቅ ሌላ እየፈለሰፉ ገንዘብ ጉልበት ጊዜ ጨርሶ መፍትሄ በማሳጣት ተራራ ለተራራ መንከራተት ስለሰለቸው ሰው ከዚህ እንግልት ማረፍ ፈልጓል። ከ 5 ትውልድ ወደ10 ትውልድ፣ ወደ 30 የማይጨበጥ ቃል ኪዳን ለመጨበጥ ሲያበላልጥ በክርስቶስ ላይ ብቻ አንዴ ታምኖ በመኖር ዕረፍትን ፈልጓል።

4. ትውልዱ ከሱስ መፈታትን ስለሚፈልግ

የጫት፣ የሲጋራ፣ የሺሻ፣ የሃሺሽና የመጠጥ ሱስ በየመንደሩ ብዙ ወጣቶችን ተብትቧል። ሴተኛ አዳሪነት፣ ስርቆትና ዝሙት አንገቱ ላይ ያሰረው ክር ወይም መስቀል ነፃ ሊያወጡት አልቻሉም። የጠለንጅ ወይም የጊዜዋ ቅጠል ማጫጫስ መፍትሄ አልሆኑትም።
 44 ታቦት ባነገሠ ማግሥት ከነበረበት ሕይወት ሊፈታ ባለመቻሉ ከተስፋ መቁረጥ የሚያድነውን ይፈልጋል። ይኼውም ያልተቀላቀለበት የእውነት ወንጌል መስማት መቻሉ ነው።
2 ቆሮንቶስ 4፣2
“ነገር ግን የሚያሳፍረውን ስውር ነገር ጥለናልና በተንኮል አንመላለስም፣ የእግዚአብሔርንም ቃል በውሸት አንቀላቅልም፤ እውነትን በመግለጥ ግን በእግዚአብሔር ፊት ለሰው ሕሊና ሁሉ ራሳችንን እናመሰግናለን”

5. ለሥራ ስለሚያነሳሳ፣

 እምነቱን ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ያስተካከለ ሁሉ ለበጎ ሥራ የተነሳሳ ሰው ነው። ከወንጌል ሥራን እንጂ ስንፍናን አይማርም። ዐባይን ብቻዋን እንድትጠቀም ግብጽ በሕዝባችን ላይ የጫነችው የስንክሳር የበዐላት ሸክሟን ከራሱ ላይ አራግፎ በመሥራት ራሱንና ወገኖቹን የሚጠቅም ትውልድ እንጂ ስለአባ እገሌ እያለ የሚለምን ዜጋ ሊኖር አይችልም። ትንሽ ሠርቶ ያገኛትን ደግሞ በፍትሃት ድግስ እያራገፈ፣ ብዙውን ጊዜ ደግሞ ዛሬ መልአከ እገሌ፣ ነገ አባ እገሌ፣ በዓታ፣ ጸአታ፣ ፍልሰታ፣ ልደታ፣ ግንቦታ፣ እያለ አበሻ ሥራ ቢሰራ የተለየ ቀሳፊ የተመደበበት ይመስል ዐዛሬ ቅጠል አልበጥስም” እያለ ይኖርበት ከነበረው ዘመን ተፈትቶ በዘመነ ተሐድሶ ነፃ እየወጣ የዕለት እንጀራውን ለማግኘት ሌሊትና ቀን እየሰራ ነው። በዐል ሳያከብር ፈረንጅ ያመረተውን ስንዴና ዘይት በእርዳታ የሚለምን በዐል አክባሪ እንደአበሻ ግብዝ የት ይገኛል?

ስለዚህ የዘመነ ተሐድሶ የክርስቶስን ወንጌል የሚቋቋም ማንም አይኖርም። የክርስቶስን ወንጌል የሚያቆም ከሰማይ በታች ምንም ዓይነት ኃይል ወይም ማኅበር የለም። ይሁን እንጂ ወርክሾፕ፣ ስልጠና ፣ አቅም ግንባታ፣ ሕንጻ ግንባታ፣ ኤግዚብሽን ግንባታ፣ ዐውደ ርእይ ወዘተ መደረጉ አይቀርም፣ ይኽ መደረጉ የእግዚአብሔርን የተሐድሶ ሐሳብ አያቆመውም። ማኅበረ ቅዱሳን የብር ኢዮቤልዩውን እንዲህ ካሳለፈ ዕድሜው ከሰጠው የወርቁን ደግሞ አመራሩ ራሱ ከኑፋቄ ወጥቶ ኢየሱስ ክርስቶስን ብቻ በማምለክ ያከብረው ዘንድ የእግዚአብሔር የተሐድሶ እቅድ መሆኑን አንጠራጠርም።

Wednesday, June 15, 2016

በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው!!


የቁልቁለት መንገድ ተጀምሯል!

ይህ ጽሑፍ በመጋቢት ወር 2004 በመካነ ጦማራችን ላይ የወጣ ነው። ደግመን ማውጣት ያስፈለገን፤ ሞት የሁሉም ሰው ጽዋ ቢሆንም ማኅበረ ቅዱሳን ፓትርያርክ ጳውሎስን በደጋፊ ጳጳሳቱ በኩል እስከሞት እያዋከበ መቆሚያና መቀመጫ እንዳያሳያቸው እነሆ ፓትርያርክ ማትያስን በተራቸው እስከሞት እየተዋጋ ለመቆየት መቁረጡ በዳበረ ልምዱ ሲሰራበት መቆየቱን ለማሳየት ነው። እንዲህ ብለናቸው ነበር። አንዳች ነገር ሳያደርጉ ሞት ወሰዳቸው፤ ማኅበሩም ሰፋለት። (አመኑንም አላመኑም ፓትርያርክ ጳውሎስ፤ አንድ ነገር አስረግጠን እንነግርዎታለን። በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው) ዛሬም ፓትርያርክ ማትያስን ለተመሳሳይ ጽዋ  በወከባና በአድማ እያንደረደረ ይገኛል። ማኅበሩ የሚተዳደርበት አዲስ ሕግ ሳይጸድቅ፤ በዐቃቤ መንበርና በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የሥልጣን ነጠቃውን ጀምሯል። ወደፊትስ?

በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ማኅበረ ቅዱሳን ከተራ ማኅበርነት ወደ ሀገረ ስብከትነት  አደገ። በዚህም የተነሳ ሲኖዶሱ ሙሉ በሙሉ በማኅበረ ቅዱሳን እጁን ተጠምዝዞ እንደሚሰራ አስመሰከረ። የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ተጠሪነቱ ለቅዱስ ሲኖዶስ ሆኖ  የየሀገረ ስብከቶቹ  ጠቅላይ ጽ/ቤት ሆኖ ያገለግላል። ይህ ጽ/ቤት ደግሞ የሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ በየ3 ዓመቱ በሚያደርገው ምርጫ በሚመድበው ሊቀጳጳስ ነው። እንግዲህ ማኅበረ ቅዱሳን ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና አሥኪያጅ ሆነ ማለት ራሱን የቻለ ሀ/ስብከት  ሆነ ማለት ነው። የጠቅላይ ቤተክህነቱ መምሪያዎች ሊያዙት አይችሉም። ከዚያም በላይ ቅዱስ ፓትርያርኩ ሊያዙት፤ ሊናገሩትና ሊቆጡት አይችሉም ማለት ነው። በቀጥታ በቅዱስ ሲኖዶስ በሚመደበው ሊቀጳጳስ በኩል ግንኙነቱ ከቅዱስ ሲኖዶሱ ጋር ብቻ ይሆናል ማለት ነው። እንዲህ ነው እንጂ ሹመት፤ መሾም ካልቀረ!! አንድ ማኅበር ባንድ ጊዜ እመር ብሎ አናት ላይ ፊጢጥ ብሎ ከመቀመጥ ወዲያ ሹመት ከወደየት ይገኛል? ከእንግዲህ  ከተቀመጠበት ደረጃ አንጻር ማኅበር መባሉ ዝቅ የሚያደርገው ስም ስለሆነ የቅዱሳን መምሪያ ወይም የወጣቶች ሀ/ስብከት እንዲባል ሲኖዶሱ በነካካው እጁ ስሙንም ማሻሻል ይገባዋል። ከዚያም አያይዞ ለዚሁ አዲስ ሀ/ስብከት አንድ ሊቀጳጳስ እንዲመድቡለትም ጥቆማውን እናቀርባለን። አንድ ነገር ታዘብን። ቤተክርስቲያኒቱ ሲኖዶስ የሚባል አካል እንደሌላት ተረዳን። በአንድ ተራ ማኅበር እየተመሩ የእሱን ጉዳይ ብቻ ሲያነሱና ሲጥሉ ሦስትና አራት ቀናት ስብሰባ መወዘፍን ምን ይሉታል? ስንት ስራ መስራት እየቻሉ ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ማውረድ እስኪያቅታቸው ድረስ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን አጀንዳ ይዞ መከራከርን እውነት ሰዎቹ በመንፈስ ቅዱስ ነው የሚመሩት እንድንል ያደርገናል። ይህ ማኅበር ባይኖር ኖሮ ስለምን ጉዳይ ሊሰበሰቡ ነበር፤፤
ይህ ማኅበር እስካሁን እየታዘዘ እንዳልቆየ የተጻፉለት ደብዳቤዎች አረጋጋጮች ናቸው። እሱ ራሱ አልቀበልም ብሎ በደብዳቤ አረጋግጧል። አንዴ ከኢህአዴግ፤ አንዴ ደግሞ ከተቃዋሚ ነኝ እያለ፤ ሌላ ጊዜ ከሀገር ቤቱ ሲኖዶስ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ ገለልተኛ እየመሰለ የተጓዘበትን ሁላችንም እናውቃለን። የወንድሞች ከሳሽና አሳዳጅ ስለመሆኑም ግፉን የቀመሱ ሁሉ ይመሰክራሉ። የተጓዘባቸውን ስልቶች ሁሉ ያጠናው መንግሥት ከሽብር አቀንቃኝ  ከሰለፊያ ጋር በአንድ ረድፍ አንዳስቀመጠው ነግሮናል። ስለሆነም አቡነ ጳውሎስ ይህንን የአድማና በጥቅም የተሳሰረ ውሳኔ አልፈርምም በማለት ውድቅ ሊያደርጉት ይገባል። ማኅበሩ አስቀድሞ ከሰለፊያ ተግባር ነጻ ስለመሆኑ ማረጋገጫ ማምጣት ይጠበቅበታል። ደጋፊዎቹ ጳጳሳትን በማስረጃና በሰው ምስክር ተጠንተው ብቁ ሆነው ያልተገኙ ካሉ ከማዕርጋቸው መሰናበት አለባቸው።  ቄስ የነበሩ፤ ልጆች የወለዱ፤ ቅምጥ ያላቸው እንዳሉ ይወራል፤ የአንዳንዶቹም ይታወቃል።  እየተሸፋፈነ መቀመጡ ለቤተክርስቲያን ጠንቅ የሆነ ውሳኔ ለማስወሰን ያልተመለሱ ሰዎች ስብስብ መሆኑ ከታየ ውሎ አድሯል።  ነውራቸውን ለመሸፈን እንኳን ከድመት አንሰዋል።
በአንድ ወቅት አባ ገብርኤል፤ አቶ ኢያሱ ተብለው ከማዕርጋቸው ተገፈው እንደነበረው፤ ማንነታቸው እንደገና ተመርምሮ  አስቸጋሪ በሆኑት ላይ ዛሬም ተመሳሳይ ውሳኔ ሊሰጥባቸው ይገባል። ጨከን ያለ የሥርዓት ማስከበር አካሄድ መውሰድ ካልተቻለ ሲኖዶሱን በነሱ በኩል እያወከ ነገ ፓትርያርክነቱን አስቀድሞ ከዚያም ቤተመንግሥቱን እንደሚረከብ የሚጠራጠር ካለ የማኅበሩን አካሄድ የማያውቅ ብቻ ነው። አመኑንም አላመኑም ፓትርያርክ ጳውሎስ፤ አንድ ነገር አስረግጠን እንነግርዎታለን። በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው። ከሆነለት ፓትርያርክነቱን ለሚታዘዝ  ሰው  ሰጥቶ ወደ ቤተመንግሥት ሰተት ብሎ ለመግባት ከጽዋ ማኅበርነት ወደ መምሪያ ተገዳዳሪነት፤ አሁን ደግሞ ወደ ሀገረ ስብከትነት ማደጉ ከምንም በላይ ማሳያ ነው።  ታዲያ ከእንግዲህ የቀረው ምንድነው? ይህ ሁሉ ለጽድቅ ነው እንዳይትሉንና እንዳንስቅ ጥቂት እዘኑልን። ነጋዴና  ሸቃጭ የሆነ  ቅዱስ ማኅበር  አራት ኪሎ የለም ። እያየነው በትንሽ በትንሹ የወጣው ይህ ሐረግ ቤተ ክህነቱን አንቆ ወዳሰበበት በመጓዝ ላይ ነው። እግዚአብሔር ለዚህ ክፉ ማኅበር አሳልፎ ከሰጠ በእውነትም ቤተክርስቲያኒቱ ለፈተናና ለውድቀት ተመርጣለች ማለት ነው። ተወደደም፤ ተጠላ ሲኖዶስ በየዓመቱ ያለህውከት ማለፍ አይችልም።
ሰውዬው «ሁሉን ለማየት መቆየት»እንዳለው የሚሆነውን ለማየት ከዕድሜው አይንፈገን!

Monday, June 13, 2016

"ፓ" ይላል ምዕመኑ!!!



«በዘውድአለም ታደሰ»
ነብይ ነኝ ባዩ የቤተክርስቲያን ደላላ!

ይሄ ሰውዬ "ጎሳ" ይባላል። በተለያየ ጊዜ የተለያዩ ቸርቾች ሲሰብክ አይቼዋለሁ። (ጎፋ መድሃኒአለም ፣ ዘፀአት ፣ FBI ፣ ወዘተ... ) የሚደክም አይነት ሰው አይደለም። ውሃ ሳይጎነጭ በተከታታይ ለሶስት ሰአታት የማውራት አቅም አለው! የምእመኑን ሳይኮ በልቶታል። ህዝቤን ምን እንደሚያስጮሀት ስለሚያውቅ አዳራሹን በጩኸት መናጥ ለነብይ ጎሣ ቀላል ነው!
ብዙ ግዜ ቸርቾች ይህን ሰውዬ ሚጋብዙት ገንዘብ ክፉኛ ሲያስፈልጋቸው ነው። ወይ መሬት ሊገዙ ሲያስቡ ... አሊያም የተሻለ አዳራሽ ሊከራዩ ሲፈልጉ ... ብቻ የሆነ የፈንድ ሬይዚንግ ጉዳይ ሲኖር ጎስሻን ይጠሩትና በዚያች ጮሌ ምላሱ የራሱንም ሆነ የሌሎች ሰዎችን ታሪክ እያጋነነ በመስበክ የዚህን ምስኪን ምእመን ኪስ ያራቁትላቸዋል!
«ነኝ ያልኩ ኮንትራክተር ነበርኩ፣ ነፍፍ መኪኖችና ብዙ ሰራተኞች ነበሩኝ፣ ጌታ ሲገባኝ ግን ንብረቶቼን ሸጬ ለቸርች ሰጠሁ» ብሎ ይጀምራል ተረት ተረቱን።
«ፓ» ይላል ምእመኑ!
«ከዛ ክፉኛ ተቸገርኩና፣ ምልስ ምቀምሰውን አጣሁ፣» ብሎ ለፅድቅ ሲል የከፈለውን መከራ እያጋነነ ያወራል!
«በከተማዋ ስሜ የተጠራ ኮንትራክተር እንዳልነበርኩ ምልስ ምቀምሰውን አጥቼ ተቸገርኩ» ሲል ረሃብን የሚያውቀው የዚህ ህዝብ አንጀት በሀዘኔታ ይላወሳል።
የሰዉን አቴንሽን ማግኘቱን ሲያረጋግጥ ታዲያ ... እንዴት ተአምራዊ በሆነ ሁኔታ እግዜር ሀብታም እንዳደረገው፣ እንዴት እንዳበለፀገው ትረካ በሚመስል ሁኔታ ያወራ ያወራና የህዝቡን አእምሮና ስሜት በሚገባ እንደተቆጣጠረ ሲረዳ እንዲህ ይላል ..
«ጌታ እንዲህ ሲል ተናግሮኛል» ብሎ ይጀምራል ነብይ ጎሳ። (ማን ነብይ እንዳረገው እንጃለቱ)
«ጌታ ዛሬ በዚህ አዳራሽ ውስጥ ያላችሁትን ሁላችሁን እባርካለሁ ብሎኛል» ሲል እቺ በረከቷን ከአርያም ሳይሆን መድረክ ላይ ከቆመው አረም የምትጠብቅ ምእመን አዳራሹን በጩኸት ታቀልጠዋለች! በጭብጨባው የሚሟሟቀው ጎሲሻም «አንዳንዶቻችሁ ከዚህ አዳራሽ ስትወጡ ከበረከታችሁ ጋር ትገናኛላችሁ» ሲል አዳራሹ በአንድ ድምፅ «አሜን» ይላል።
«አንዳንዶቻችሁ ደግሞ ቤታችሁ ስትገቡ በረከታችሁ ቁጭ ብሎ ይጠብቃችኋል»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ ስራ ቦታችሁ ላይ»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ የዛሬ ሳምንት»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ የዛሬ ወር»
«አሜን»
«እግዜር በተራራው ላይ ሙሴን ሲያገኘው በእጅህ ላይ ምን አለ? ብሎ ነው የጠየቀው ወገኖቼ። እግዜር እጃችን ላይ ባለ ነገር ነው ሚሰራው። ዛሬ በእጃችሁ ላይ ምን አለ?» ይላል ብልጣብልጡ ጎሳ!
ይሄ የዋህ ሁን ሲባል ሞኝ የሆነ ህዝብም እውነት መስሎት እጅና ኪሱን ያያል! ከዛማ በቃ አዋራው ይጨሳል .... ፒፕሉ በረከቱን በስጦታው ለመግዛት ይጋፋል! አዳሜ ወርቋን ከአንገቷ ላይ እየበጠሰች፣ ገንዘቧን ከቦርሳዋ እያራቆተች፣ ምንም የሌላት ደግሞ የእጅ ስልኳን ሳይቀር መባ እቃ ውስጥ እየጨመረች የማይፈፀም ትንቢት ታቅፋ እርቃኗን ከአዳራሹ ትወጣለች ... ልትባረክ ነዋ ሃሃሃሃ
ከላይ እንዳልኩት ነብይ ጎሳ ነብይነቱን ከየት እንዳገኘው ማንም አያውቅም። የሚያወራው ታሪክም እውነት ስለመሆኑ ምንም ማረጋገጫ የለም። ይህን ሰውዬ የሚጋብዙት ስግብግብ የቤተክርስቲያን አገልጋዮችም የሰውየው ምስክርነት እውነት የተፈፀመ ይሁን አይሁን ለማረጋገጥ ምንም አይነት ጥረት አያደርጉም! እነሱ ሚፈልጉት በሱ ጅንጀና የሚዘንበውን የገንዘብ ዶፍ ነው። የስብከቱ መለኪያ በሱ ስብከት አማካኝነት የገባው የገንዘብ መጠን ነው እንጂ የእግዚአብሔር ቃል አይደለም!
አሁን ቤተክርስቲያን በጎሳና ጎሳን በሚመስሉ መንፈሳዊ ደላሎች እየታመሰች የምትገኝበት ሰአት ላይ ትገኛለች። መፅሀፉ ጎሳንና መሰል አገልጋዮችን «ለመንጋው የማይራሩ» ይላቸዋል!
እንዲጠብቁት የተሰጣቸውን ምእመንና እረኛ የሆኑለትን መንጋ ስጋ እየበሉ ሰብተው ቆዳውን ገፍፈው ይለብሳሉ! በአስራትና በበኩራት፣ በመባና በፍቅር ስጦታ ስም፣ ገንዘቡ ወደካዝናቸው ይጋዝ እንጂ የገንዘቡ አመጣጥ እነሱን አያስጨንቃቸውም። በምእመኑ ፍራንክ ትልልቅ እቅዶች ያቅዳሉ፣ የህዝቡን መሶብ አራቁተው ሰማይ ጠቀስ ፎቆችን ይገነባሉ፣ በሊትር ሶስት ኪሎሜትር የሚሄዱ ላግዥሪ መኪኖችን ይነዳሉ። ይሄ ተስፈኛ ምእመን ግን ከሰማይ መና እየጠበቀ በደረቅ ምድረ በዳ ደረቅ ትንቢታቸው ታቅፎ ከቃዴስ ቃዴስ ሲንከራተት ይኖራል።
በአብዛኞቹ የወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያኖች ዘንድ ምድር ምድር የሚሸት ስብከት በዝቷል። ሰባኪው ሁሉ የ prosperity Gospel (የብልፅግና ወንጌል) አቀንቃኝ ሆኗል፣ ምእመኑም በረከቱን የሚለካው በምድራዊና ቁሳዊ ሀብት ብቻ ነው! «ሀገሬ በሰማይ ነው» አይነት ንግግሮች ከምእመኑ አንደበት መደመጥ አቁመዋል። ኢየሱስ የሞተው ለቼቭሮሌት መኪናና ለግራውንድ ፕላስ ስሪ ፎቅ ይመስል ወሬው ሁሉ ቤት ስለመስራትና ቤት ስለማፍረስ ሆኗል ... እንደ ዊነርስ ቻፕል አይነት ቸርቾችማ ወሬው ሁሉ ሱሪ ስለመቀየርና መኪና ስለመንዳት ከሆነ ቆየ። «በመንፈስ መኪና የመንዳት» ፕሮግራም ሁሉ ያካሂዳሉ አሉ! ሃሃሃ
ነብያቶች በዝተዋል። ነብይነት ግን ከሞተ ቆየ! ሰባኪዎችም አሸን ናቸው። ስብከት ግን ስልሳዎቹ ላይ ቆሟል! በየመድረኩ ተኳኩለው እንጣጥ እንጣጥ የሚሉ (ባለብዙ ሚስት ዘማሪዎች እልፍ ናቸው) መንፈሳዊ ማንነትን የሚያንፅ መዝሙር ግን ከመድረኩ ነጥፏል!
በፅድቅና በቅድስና የሚያገለግሉ አንዳንድ አገልጋዮች እንዳሉ አይጠፋኝም። ግን እነዚህ አገልጋዮች ከጎሳውያኑ ጋር ሲተያዩ በገምቦ ውስጥ እንዳሉ ጥቂት ጠብታዎች ናቸው! ስለዚህ ባህር ውስጥ እንዳሉ አይቆጠሩም። እኔ ማወራው ባህሩን ስለሞሉት የተበከሉ አሳዎች ነው!
 ቸርቾች በየመቶ ሜትሩ ከተማ ውስጥ ፈልተዋል። ደቀመዝሙር ማፍራት የማይችሉ ውሀ አልባ ምንጮች ናቸው እንጂ! ክርስቲያን ያልሆኑ የክርስቶስ ሰባኪዎችና ክርስቶስን የማያውቁ አገልጋዮች ይሄን ምስኪን ምእመን እንደአሻንጉሊት እየተጫወቱበት ነው! አገልግሎታቸው ያከበራቸውን ህዝብ በመናቅና በማስፈራራት ላይ የተመሰረተ ነው! «ለምን?» ብሎ ጥያቄ የሚያነሳ ሲመጣ «ጌታ በቀባው ላይ እጅህን አታንሳ» በማለት በጥቅስ ያስፈራሩታል። በፅድቅ ለማገልገል ከላይ እታች እያሉ የጅብ ድግሳቸው ላይ የማይሳተፉትን ንፁሀን ደግሞ የተለያየ ስም ጀርባቸው ላይ በመለጠፍ ከአገልግሎት ያግዷቸውና የሚከተላቸውን ምእመን ኑሮ እየቀሙ ይኖራሉ! ሳቁን መንትፈው ይስቃሉ! ደስታውን አራቁተው ይደሰታሉ! እውነትም ለመንጋው የማይራሩ ሆዳሞች!
ዘመኑ የባቢሎናውያኑን ዘመን ይመስላል። ትርምስ እንጂ መረጋጋት የለም! ጩኸት እንጂ መግባባት ጠፍቷል። ግራ የተጋቡ ባለራእዮችና ያልተማሩ አስተማሪዎች መሬት ባልረገጠ የትምህርት ወጀብ ህዝቡን እየናጡት ነው። በተቀየጠ ዶክትሪንና በስህተት አስተምህሮ ምእመኑን ከወንጌል አርቀው አይኑን በማሰር ወደቁልቁለት እየነዱት ነው! ነብያት ነን ባዮቹ ወንዝ በማያሻግር ትንቢት ሲወራጩ መድረኮቻችን ላይ ውለው ያድራሉ። ዝናብ የሌላቸው ደመናዎች በተራ ፉከራና ሽለላ የተሞሉ ፍሬ አልባ ደረቅ መሬቶች ናቸው!
በተለያዩ ቤተክርስቲያኖች እየተጋበዘ ህዝቡን የሚያራቁተው ደላላው ነብይ .... «ነብይ ጎሳም» ከላይ ለጠቀስኳቸው ሆዳም አገልጋዮች እውነተኛ ምልክት ሊሆን ይችላል ባይ ነኝ!

እቀጥላለሁ!‎

Saturday, June 4, 2016

ማኅበረ ቅዱሳን አሁን የቤተ ክርስቲያን፤ ቆይቶ የመንግሥት መጥበሻ ምድጃ ነው!


በታሪክ አጋጣሚ የደርግን መውደቅና ግርግርን ተተግኖ የተፈጠረው ማኅበረ ቅዱሳን የመጥበሻ ምድጃ ከሆነ እነሆ 23 ዓመታት አለፉት። ብዙዎችን በትኗን፤ አሳዷል። ዳግም እንዳይመለሱ በማድረግ እንደተዋጊ በሬ እየበጠበጠ ከበረት አስወጥቷል። በማወቅም ይሁን ባለማወቅ አፋፍተው ያሳደጉትን አቡነ ጳውሎስን ሳይቀር በአድማ የመጥበሻ እሳት እየለበለበ እስከመቃብር ሸኝቷል። የአሁኑን ፓትርያርክ የአቡነ ማትያስን ወንበር በተሾሙ ሰሞን ለመረከብ ተፍ ተፍ ብሎ ሳይሳካለት ቢቀር በተለመደ የመጥበሻ ምድጃው ላይ አስቀምጦ ላለፉት 3 ዓመታት  በአድማው ግሪል / GRILL/ እየጠበሰ ይገኛል።

ፓትርያርክ ማትያስ ብቻቸውን ሆነው ይህንን መጥበሻ ምድጃ ሊያስወግዱ ብዙ ታግለዋል። ነውራም ጳጳሳቱ እዳ በደላቸው በዚህ ማኅበር የኃጢአት መዝገብ ላይ ስለሰፈረ ከፓትርያርኩ በተጻራሪ ቆመው ውግንናቸው ለማኅበሩ ሆኖ ታይቷል። የማኅበሩ ሥፍራ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የት ነው? በሚለው ነጥብ ላይ ጥያቄ ያላቸው ፓትርያርክ ማትያስ ድርሻውን፤ አቅሙንና ተጠሪነቱን የሚወስን አዲስ መተዳደሪያ ደንብ እንዲወጣለት ያደረጉት ተጋድሎ ላይ ውሃ በመቸለስ የሲኖዶስ ጉባዔ በመጣ ቁጥር የሚያጨቃጭቅ አጀንዳ እያስገባ ሲሾልክ ቆይቷል። ዘንድሮም ይህን የቤት ሥራ ሰጥቶ በአንድ አጀንዳ ላይ ለ4 ቀናት ካጨቃጨቀ በኋላ የሲኖዶስ አባል የሆነው የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር መፍትሄ አስምጦ ሊገላግላቸው ችሏል። ይህ ሁሉ የሆነው በማኅበሩና በጉዳይ ፈጻሚ ጳጳሳቱ የተነሳ ነው።

የእንደራሴ መኖር አለመኖር ለማኅበረ ቅዱሳን አሳሳቢው አይደለም። ነገር ግን በዘንድሮው ጉባዔ ላይ ማንሳት ያስፈለገው የራሱ ስሌት ስላለው እንጂ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ድክመት ከሱ መኖር በላይ አስቸጋሪ ፍጡር ስለመጣ አይደለም። በዚህም የተነሳ በአቅም ማነስ ሰበብ ፓትርያርኩን አሸመድምዶ በማስቀመጥ ለ3 ዓመታት ያህል እሳት ካነደዱበት ሥጋት ነጻ ለመውጣት የተያዘ መላ ከመሆን አይዘልም። ከዚህም በፊት እንዳልነው ጳጳሳቱ በሀገረ ስብከታቸው መሥራት ያልቻሉትን የመንፈሳዊና ሥጋዊ የልማት ሥራዎች  እንደራሴው እየዞረ የሚሰራላቸው አለመሆኑንም በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል። ማኅበረ ቅዱሳን እስካለ ድረስ ታዛዥ ያልሆነ የትኛውም የቤተ ክርስቲያኒቱ ባለሥልጣን  ማኅበሩ ባዘጋጀው መጥበሻ ላይ ይጣዳል። ምርጫቸው ከማኅበሩ ጋር መቆም አለያም በተጻራሪ ሆነው ለመጥበሻው ራሳቸውን ከማዘጋጀት የግድ ነው። አባ ሳዊሮስ ከአዲስ አበባ ማኅበረ ካህናት ጋር ቆመው ማኅበሩን ሲያጋልጡ ምድጃውን አዘጋጅቶ መጥበስ ሲጀምር እጃቸውን አንስተው ለማኅበሩ ለማስረከብ መገደዳቸውን አይተናል። አባ ፋኑኤል ማኅበሩ የሌለበት ቦታ የት ሄጄ ልሥራ? እንዳላሉ ሁሉ ምርኮኝነታቸውን ካረጋገጡ በኋላ ግን ከማኅበሩ መጥበሻ ግሪል ላይ ወርደው እረፍት ሊያገኙ ችለዋል። ሌሎቹ ግን የሚደርስባቸውን እሳት አስቀድመው ስለሚያውቁ ቃላቸውን አክብረው የጫናቸውን በማራገፍ ግንቦትና ጥቅምት በመጣ ቁጥር በማኅበሩ አጀንዳ አስፈጻሚነታቸው ቀጥለዋል።

 ማኅበረ ቅዱሳን በስመ ተሐድሶና ሙሰኛ ነጠላ ዜማው የፈጃቸውና ያቃጠላቸው ካህናት ቁጥራቸው ብዙ ነው። ስለቅድስናና መንፈሳዊ ንጽህና በዋለበት ያልዋለ የዋልጌዎች ስብስብ ይህ ማኅበር ስም እያጠፋ ያሳደዳቸው፤ ስለኃጢአታቸው ንስሐ የሚገቡበትን በር እየዘጋ ተስፋ በማስቆረጥ ያስወጣቸው የትየለሌ ናቸው። የሚገርመው ግን ነውራም ጳጳሳቱን በቅድስና ካባ ሸፍኖ ለአገልግሎቱ የሚጠቀምባቸው የከባቴ አበሳ ተፈጥሮ ስላለው ሳይሆን እስካለገለገሉት ድረስ ብቻ ነው። እያንዳንዱ የማኅበሩ አባል በተለይም አመራሩ እነአቡነ እገሌ እስከምን ድረስ የጉስቁልና ባሕር ውስጥ እንደሰጠሙ እያወቀ በስምምነት አብሮ ይሰራል። ነገር ግን ከማኅበሩ አቋም ካፈነገጡ ከዚህ በፊት እንዳደረገው የእዳ ደብዳቤአቸውን ከማንበብ አይመለስም። ይህ በተግባር የተረጋገጠ እውነት ነው።

አንዳንዶች ማኅበሩን የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር ብቻ አድርገው ያያሉ። ነገር ግን ማኅበሩ  እንደግብጹ የሙስሊም ወንድማማቾች ማኅበር በፖለቲካው መድረክም የረቀቀ ተልእኮ ያለው ማኅበር ነው። በአባልነት ያቀፋቸው ሚኒስትሮች፤ ከፍተኛ ባለሥልጣኖች፤ ሥራ አስኪያጆች፤ ፖሊሶች፤ ዳኞች፤ የሕዝብ አገልግሎት ሠራተኞች፤ መምህራንና ተማሪዎች፤ የሙያ ማኅበራት፤ በ44 አኅጉረ ስብከት ውስጥ ያሉ ሚሊዮኖች የሰንበት ት/ቤት አባላት፤ የጥምቀት ተመላሽ ተጠባባቂ ጦር የመሳሰሉትን በአባልነት እየመለመለ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም የራሱን ዶክትሪን በመጋት ማኅበረ ቅዱሳን፤ ማኅበረ ቅዱሳን ካሰኛቸው ውሎ አድሯል። ዛሬ ከሲኖዶስ ወይም ከፓትርያርኩ በላይ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ተቆርቋሪና ጠባቂ ከማኅበሩ በላይ የለም የሚለው አስተሳሰብ በእያንዳንዱ ሰው አእምሮ ውስጥ እንዲሰርጽ በሰፊው ተሰርቷል። ዘመናዊ የክርስቲያን ብራዘር ሁድ ማለት ማኅበረ ቅዱሳን ነው።

ሌላው የማኅበሩ ተንኮል አሁን ካሉት ታማኝና ታዛዥ ጳጳሳት በተጨማሪ ከእንግዲህ የሚሾሙ ኤጲስ ቆጶሳት በራሱ መስፈርት የተመለመሉና ወደፊት ችግር እንደማይፈጥሩ የተረጋገጠላቸው ብቻ እንዲሆኑ ይፈልጋል። እነዚህ የማኅበሩ እጩ ኤጲስቆጶሳት ያለፈ ታሪካቸው የቱንም ቢመስል አሳሳቢ አይደለም። ተቀባይነታቸው አርአያነት ባለው ሁኔታ ቢሆንም፤ ባይሆንም ለማኅበሩ አስጊ እስካልሆኑ ድረስ እንዲመረጡ አጥብቆ ይሰራል። ነገር ግን በተቃራኒ ማኅበሩን የሚፋለሙ ከሆነ እንደአባ ሠረቀብርሃን ወ/ሳሙኤልን የመሳሰሉት በልዩ ልዩ ስምና ወንጀል በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ እጃቸውን ካልሰጡ በስተቀር ለእጩነት ሊቀርቡ አይችሉም።

በአጠቃላይ ማኅበሩ በታሪክ አጋጣሚ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የተገኘ መጥበሻ ምድጃ ነው። በዚህ ምድጃ ዲያቆናት፤ ቀሳውስት፤ መነኮሳት ተጠብሰዋል። ሰባኪያነ ወንጌልና አስተዳዳሪዎች ተጠብሰዋል። ጳጳሳትና ፓትርያርኮች ተጠብሰዋል። እውነቱን እያወቁ ከመናገር ብዙዎች የተቆጠቡት ማኅበሩ መጥበሻው ላይ ከጣዳቸው የሚያወርዳቸው ስለሌለ ነው። ልክ እንደ መንግሥታዊ የስለላ መዋቅር የማኅበሩን ስም በተቃውሞ በአውቶቡስ፤ በታክሲ፤ በሬስቶራንት፤ በየካፌውና በሕዝብ መሰብሰበቢያ ቦታዎች መጥራት ከማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። መንግሥት ላይ ምን ዓይነት የአንኮበር መድኃኒት እንደተረጨበት ባናውቅም እሱም በፍርሃት ይሁን በድንዛዜ ፈዞ ቀርቷል።  እውነታው ግን ማኅበሩ ለየትኛውም ወገን መጥበሻ ምድጃ መሆኑ በተግባር የተረጋገጠ ነው።

Wednesday, June 1, 2016

«ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡት፤ ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡት?




አበው ዘይቤያዊ ምሳሌ ሲሰጡ፤ ፍሬ ነገሩን  ሊገልጥ የሚችል ጥሩ ኃይለ ቃል ይጠቀማሉ። በአንድ ዐረፍተ ነገር ብዙ ሐተታ ሊወጣው በሚችል መልኩ የጉዳዩን ብስለትና ጠጣርነት በደንብ ያሳዩበታል። ለዚህም ነው «ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡት፤ ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡት?» በማለት መሆን የማይገባው ነገር ሆኖ ቢገኝ መፍትሄው ግራ የሚያጋባ እንደሆነ ለማስረዳት ይፈለጉት። አዎ፤ በዘመነ አበው ምላጭ፤  እባጭ እንዲፈነዳ፤ የተቋጠረው መግል እንዲፈርጥ ይበጡበት ነበር። በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ዛሬም አልፎ፤ አልፎ ይሰራበታል።  ነገር ግን ምላጭ ራሱ ቢያብጥ በምን ይቆረጣል? ውሃስ ቢያንቅ በምን ማወራረድ ይቻላል? ግራ የሚያገባ ነገር ነው። መሆን የሌለበት ሆኖ ሲገኝ ያስገርማል፤ ያስደነግጣል፤ መፍትሄውም ሩቅ ይሆናል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየታየ ያለው ድርጊት የዚሁ ምሳሌ ተመሳሳይ ነገር ነው። በቤተ ክርስቲያኒቱ ታሪክ የቅዱስ ሲኖዶስ መንበር ከተመሠረተ ከ50 ዓመታት እጅግም ያልዘለለ ጊዜን ያስቆጠረ ቢሆንም በዚህ አጭር እድሜው 50 ጉድ አሳልፏል። ፓትርያርኳን አሳልፋ በመስጠት ለደርግ ጭዳ ማቅረቧም በማስረጃ የተረጋገጠ እውነት ነው። ፓትርያርክ አውርዳ ፓትርያርክ ሾማለች። ለሁለት የተከፈለ ሲኖዶስም የያዘችው በዚሁ አጭር እድሜዋ ነው። የሐዋርያትን መንበር ተረክቤአለሁ የምትለዋ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያት እንዳደረጉትና የራሱን ሥፍራ በለቀቀው በይሁዳ ምትክ እንደሾመችው ሐዋርያ በመንፈስ ቅዱስ ምርጫ እጣ ማጣጣል ሲገባት እንደፖለቲካ የካድሬ ምርጫ በሰውኛ አሳብና እንደተሰጣቸው ተልእኮ በሚመለመሉ ሰዎች ምርጫ መሾሟም የዚሁ የአጭር ዘመን ታሪኳ አንዱ ክፍል ነው። 

ነውርና ነቀፋ የሌለበት፤ ራሱንና ቤተሰቡን በአግባቡ ስለመምራቱ በምእመናንና ምእመናት የተመሰከረለት አገልጋይ ሰው ኤጲስ ቆጶስ እንዲሾም ቃለ ወንጌሉ ቢናገርም ከንባብና ከአንድምታው በዘለለ ተግባር ዳገቷ ቤተ ክርስቲያን ሆና ለሰሚ የሚቀፍ፤ ለሚያውቁት የሚያሳፍር ሹመት እየፈጸመች በመገኘቷ እነሆ ጥቅምትና ግንቦት በመጣ ቁጥር የዘራችውን እያጨደች ትገኛለች።
   «መልካም ዘር መልካም ፍሬ ያፈራል» እንዲል ወንጌል የዚህ ተቃራኒ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ስለመዘራቱ ደግሞ ፍሬውን ሲኖዶስ በመጣ ቁጥር ጭቅጭቅ፤ ንትርክ፤ ሁከትና አድማ ሲያስተናግድ ማየት የተለመደ ሆኗል። ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው ለትውልድ የፈውስና የምሕረት መልእክተኛ መሆን የሚገባው አካል ለራሱ ከፈውስም ሆነ ከምሕረት ስለራቀ መሆን በማይገባው ሁኔታ ውስጥ ይገኛል። 

«ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡታል፤ ውሃስ ቢያንቅ በምን ይውጡታል?» ማለት ይኼ ነው። ሰው በልቡ መታደስ ካልተለወጠና የማይሞተውን የሞት አሸናፊ ካልለበሰ አዲስ ፍጥረት እንደማይሆን ሐዋርያው በመልእክቱ ነግሮናል።  ካልተለወጠና የቀድሞ ግብሩን ካልተወ አሮጌነት ደግሞ አብሮት ያለው ማንነት በክፋትና በተንኮል ተግባር እየተገለጠ በዘመኑ ሁሉ ይቀጥላል። ዛሬም በሲኖዶስ ጉባዔ ላይ የሚታየው ችግር ሁሉ የውስጥ ማንነቱ ማሳያ መስታወት ነው። ሰው የሌለውን ውበት ከየትም ሊበደር አይችልም።
ሰሞኑን እየተካሄደ ባለው ሲኖዶስ (ቅዱስ ለማለት ይከብደኛል) ምክንያቱም ካልተወሻሸንና ሞራል እንጠብቅ ካልተባለ በስተቀር መንፈስ ቅዱስ የሁከትና የንትርክ አምላክ ስላይደለ ቅዱስ ለማለት ይከብዳል። በስብሰባው ላይ እየታየ ያለው ኢ-መንፈሳዊና ኢ-ሥነምግባራዊ ድርጊት ከስምና ከማዕርግ እድገት በስተቀር ያልተለወጠ ማንነት የተንጸባረቀበት እጅግ አሳፋሪና አሳዛኝ ክስተት የታየበት ስለሆነ ነው። 

 «ከእናንተ አንዱ ከባልንጀራው ጋር ሙግት ቢኖረው በቅዱሳን ፊት በመፋረድ ፋንታ በዓመፀኞች ፊት ሊፋረድ ይደፍራልን? ቅዱሳን በዓለም ላይ እንዲፈርዱ አታውቁምን? በዓለምስ ላይ ብትፈርዱ ከሁሉ ይልቅ ትንሽ ስለሚሆን ነገር ልትፈርዱ አትበቁምን?» 1ኛ ቆሮ 6፤1-2

በቅዱስ ስም ተሰብስቦ፤ በዓለማውያን ምናልባትም እግዚአብሔርን በማያውቁ ዐመጸኞች ፊት የጉባዔ ዳኝነት ከመጠየቅ ወዲያ ለሲኖዶስ ምን ሞት አለ? አሁን እውነት ሕይወት ያለው ሲኖዶስ የሚባል አካል አለ ማለት ነው? ይህ ሁሉ የሆነውና እየሆነ ያለው በሞተ አካል ውስጥ ያለው የሙት መንፈስ ፍሬውን እያፈራ በመገኘቱ የተነሳ ነው።  ለዚህም ነው ሐዋርያው ጳውሎስ፤

 «በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ። ከሄድሁ በኋላ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ተኩላዎች እንዲገቡባችሁ፥ ደቀ መዛሙርትንም ወደ ኋላቸው ይስቡ ዘንድ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ ሰዎች በመካከላችሁ እንዲነሡ እኔ አውቃለሁ» በማለት የተናገረው። የሐዋ 20፤28-30

መንጋው ተበትኗል፤ ለሚጠፋው በግ የሚራራ እረኛ የለም፤ ቤተመቅደሱ በርግብ ሻጮችና በለዋጮች ተሞልቷል፤ እርስ በእርሳቸው የሚነካከሱና የሚበላሉ ሆነዋል፤ ነገር ግን በሕይወት አለን ይላሉ። ለሥልጣን ሽሚያ፤ ለመፈንቅል፤ ለቡድን አሸናፊነት፤ ለማኅበር የበላይነት ይጋደላሉ።
 በየተመደቡበት ሀገረ ስብከት እንደነገሥታት የሚሰጣቸው ስግደት ሳይጎድል፤ እንደሰማያዊ ሹም ሆነው መታየታቸው ሳይጠፋ ምንም የሰሩትና ያለሙት በሌለበት ሁኔታ ዓይናቸው ሁል ጊዜ የሚያየው እዚያ ጣሪያ ላይ ነው። ጣሪያው ደካማ ይሁን ሰነፍ የሚያስቀምጠው አንድ ሰው ነው። ጣሪያው ላይ ሰው ሲቀመጥ ያልታገሉ ፈራህያን ዛሬ የሚያደቡት ምን ለማግኘት ነው? ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስበው? ተጨንቀው? በጭራሽ አይደለም።
 ጳጳሳቱ ሰው ከመቅጠርና ከማባረር ባለፈ ሚሊዮን ተከታዮቻቸውን አሰልፈው ትምህርት ቤት፤ ጤና ጣቢያ፤ የንጹህ መጠጥ ውሃ፤ የብሎኬት ማምረቻ፤ የእንጨት መሰንጠቂያ፤ የመስኖ ልማት፤ የልብስ ስፌት፤ የጧፍና ሻማ ማምረቻ፤ የአልባሳትና ቅርሳ ቅርስ ተቋም፤ የዶሮና የከብት እርባታ፤ የዳቦ መጋገሪያ፤ የካህናት ማሰልጠኛ፤ ኮሌጆች፤ ዩኒቨርሲቲዎች፤ የህጻናት ማሳደጊያ፤ የአረጋውያን መጦሪያ ለምን አያቋቁሙም? ለምን አይሰሩም? ማን ከለከላቸው?
ከ15 ሚሊዮን ያልበለጠ ተከታዮች ያሏት የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትና አድባራት በረሃውን ገነት ያደረጉት፤ ምርትና ሃብታቸው የተትረፈረፈው እንደእኛ ጳጳሳት በፎጣ በመሸፋፈን ሳይሆን በአጭር ታጥቀው ከእስላም ሰይፈኞች ጋር በመታገልና ተግተው በመስራታቸውና በማሰራታቸው ነው። ከላይ ከተዘረዘሩት ውስጥ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ያልሰራችው የልማት ስራ የለም።  በጀት ተመድቦላቸው፤ ባለሙያ ተቀጥሮላቸው ሳይሆን መነኮሳቱን፤ ካህናቱን፤ ምእመናኑን በማስተማርና በማሰልጠን በራስ አገዝ የልማት ተሳትፎ የተመሰረተ ነው።
 የኛዎቹ ለግንቦቱ ጉባዔ ከጥቅምት ጀምሮ ከመዶለትና ለጥቅምቱ ጉባዔ ደግሞ ከግንቦት ጀምሮ ሴራ ከመጎንጎን በስተቀር በሀገረ ስብከታቸው የልማት ርእይ፤ እቅድና ግብ በጭራሽ የላቸውም። ከሐውልት ምርቃት፤ ከቀብር ክፍያ፤ ከክርስትና፤ ከጋብቻ፤ ከፍትሃት፤ ከጸበል፤ ከሰበካ ጉባዔ አባልነት ወዘተ የሚሰበስቡትን ሚሊዮኖች ብር ለደመወዝና ለስራ ማስኬጂያ ከማዋል ባለፈ ተመልሶ ለሕዝቡ ልማት የዋለው ምን ያህሉ ነው? በደቡብ ክልል አካባቢ ያሉ የኦርቶዶክስ ምእመናን «እናንተ አምጡ እንጂ እንደሌሎቹ እንኩ አታውቁም» ማለታቸውን ስንሰማ የኛዎቹ መስጠትን ሳይማሩ አምጡን ከየት ለመዱት ያሰኛል።

    በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውድቀትና ማሽቆልቆል ተጠያቂዎቹ ጳጳሳቱ ናቸው። ለመንጋው መበተን፤ ለስርቆትና ሥነ ምግባር ጉድለት ኃላፊነቱን መውሰድ አለባቸው። የታጣው መሪ እንጂ  ለመመራት ፈቃደኛ፤ ለመስጠት እጁን የማይዘረጋ  ምእመን የለም። ደግሞስ እንደኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ምእመን እጁን የሚዘረጋ አለ እንዴ?
 በሀገረ ስብከታቸው ልማት ሳያሳዩ ወደላይ መንጠራራት ስንፍናቸውን እንጂ አዋቂነታቸውን አያመለክትም። ጳጳሳቱ ለድክመታቸው ምክንያት ፓትርያርኩ ላይ አመልካች ጣታቸውን ከመቀሰራቸው በፊት እኔ በሀገረ ስብከቴ ምን ሰራሁ? ብለው ራሳቸውን ይጠይቁ። ብዙዎቹን ጳጳሳት ከምንኩስና ጀምሮ ስለምናውቃቸው ስለማንነታቸው ነጋሪ አያሻንም። ከታች ጀምሮ ያልተገነባ ስብእናና ችሎታ ደረጃቸው ስላደገ ባንዴ አብሮ አይመነደግም። ቁም ነገሩ እንደእኛው ችሎታ የሚያጥራቸው ሰዎች መሆናቸው ሲሆን አሁን አለቃቸውን ማስቸገር ቀደም ሲል በአለቅነታቸው ካዳበሩት ችግር የተማሩት ብቸኛ እውቀት ይመስለኛል።  ከዚያ ባሻገር በልማታቸው ለሕዝቡ የመኖር ተስፋ ወይም በጸሎታቸው ለሀገር የሚተርፉ ሆነው 15 ሚሊዮን ሕዝባችንን ከድርቅ ሲታደጉ አላየንም። ከመንጋ ጳጳስ እንዴት አንድ ኤልያስ ይጥፋ? ተግባር እንጂ ስም አላልኩም።

በግንቦቱ ሲኖዶስ ተሰብስበው በፓትርያርክ ማትያስ የችሎታ ማነስ ላይ ከመሳለቅ አስቀድመው በራሳቸው የአቅም ማነስ ላይ ቢወያዩ የተሻለ ነበር። ምሳሌ እንስጥ፤  ከ1985 ዓ/ም ጀምሮ 23 ዓመት በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ጳጳስ ሆነው የቆዩት የአሁኑ አባ ጎርጎርዮስ፤ ሟቹ አቡነ ጎርጎርዮስ ከመሰረቱት የዝዋይ ካህናት ማሰልጠኛና የአትክልት ልማት ወዲህ ስንት ማሰልጠኛ አቋቋሙ? ስንት የልማት አውታር ተከሉ? እውነታው ምንም ነው። አባ ቄርሎስስ በሰሜን ወሎ ሀ/ስብከት ስንት የካህናት ማሰልጠኛ፤ ስንትስ የእደ ጥበብ ተቋም ተከሉ? ስንት የከብት ማድለቢና የዶሮ እርባታ አቋቋሙ? ማን እንዳያደርጉ ከለከላቸው? ሟቹ አባ ጳውሎስ ወይስ ሕያው አባ ማትያስ?

 በምሥራቅ ጎጃምና በምዕራብ ጎጃምስ ምን ተሰራ፤ በሰሜንና ደቡብ ጎንደር ሀ/ስብከትስ ምን ልማት ተቋቋመ? በአጭር ጊዜና በረጅም ጊዜ እቅዳችሁ ምን አሳካችሁ?  በደን ልማት ላይ ሕዝቡን በማስተባበር በዚህ ዓመት ስንት ሚሊዮን ችግኝ ለመትከል ተዘጋጅታችኋል?
እርግጥ ነው ጳጳሳቱ በሌላ የሥራ መስክ ላይ አልቦዘኑም። የግል ቤታቸውን ገንብተዋል፤ ዘመናዊ መኪና አስገዝተዋል። በባንክ ገንዘባቸውን አጭቀዋል። ዘመድ አዝማዳቸውን በየቤተ ክርስቲያናቱ ቀጥረዋል።  
በአንድ ወቅት መንግሥቱ ኃ/ማርያም ሚኒስትሮቹን ሰብስቦ « የምትነዱትን የመኪና ዓይነትና ብዛት፤ ያላችሁን ቤት፤ የምትውሉበትን፤ የምታድሩበትን ቦታና ጭምር ይኽ ሕዝብ ብታምኑም ፤ ባታምኑም አሳምሮ ያውቃል» ብሏቸው ነበር።  ሕዝብ ምን የማያውቀው አለ? ተከድኖ ይብሰል ብለነው እንጂ የኛዎቹን ስንቱን ጉድ እናውቃለን።
 አሁን እነሱ ምን ስለሆኑ ነው፤ እንደራሴ ይሾም የሚሉት?  እንደራሴ ምን ያድርግላቸው? መፈንቅለ ፓትርያርክ መሆኑ ነው ወይስ እንደራሴው በየሀገረ ስብከታቸው እየሄደ ት/ቤት ሊሰራላቸው ነው? ጉዳዩ ፓትርያርኩን ወደጎን አስቀምጦ ለጳጳሳቱና ለማኅበረ ቅዱሳን ያደረ ሰው ለማስቀመጥ እንደሆነ ሳይታለም የተፈታ ነው። እቅዱም የኃጢአታቸው ዐቃቤ ኃጢአት ከሆነው ከማኅበረ ቅዱሳን ሴራነት የዘለለ አይደለም።  የሚያሳዝነውና የሚያስገርመው ነገር የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር እንደራሴ ለመሾም ይችሉ ዘንድ እንዲያግዛቸው መለመናቸው ነው።
 የፖለቲካ ሰው ምን ማድረግ እንዳለባችሁ ቅዱስ በሚባለው ጉባዔያችሁ ተቀምጦ ሲነገራችሁ ከመስማት ሞት ይሻላችሁ ነበር። ዳሩ ግን የሞታችሁት ቀድሞ ነውና ይኼ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ውርደት ለእናንተ ግን ክብር ነው። ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር በጠሩት ጉባዔ ላይ አንድ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ተወካይ የተናገረውን ጠቅሼ ልቋጭ። «ፖለቲከኛው እጣን፤ እጣን ሲሸት፤ የሃይማኖት አባት ፖለቲካ፤ ፖለቲካ ሲሸት አስቸጋሪ ነው» ማለቱን አስታውሳለሁ።
አዎ፤«ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡት፤ ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡት?» እንዲሉ።