Monday, May 5, 2014

«ኢየሱስ ለእኔ እንዲህ ነው፤ ለእናንተስ?»



የኦሪቱ የኃጢአት ማስተስርያ
ኢየሱስ በኔ ኃጢአት ምትክ ሞቶ ሕይወትን ይሰጠኝ ዘንድ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከ ህያው በግ ነው።
ዮሐንስ ወንጌላዊ እንዲህ ሲል እንደተናገረ;
 «በነገው ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፦ እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ» ዮሐ 1፤29

እስራኤል ዘሥጋ የተባሉት የብሉይ ኪዳን ሕዝቦች እግዚአብሔር ከሰጣቸው ተስፋ መካከል አንዱ ኃጢአት ቢሰሩ ወይም ቢበድሉ ከዚህ መንጻት የሚችሉበትን መንገድ  አሳይቷቸው ነበር።  ይኼውም
 «ማናቸውም ሰው ቢበድል፥ ሳያውቅም ለእግዚአብሔር በተቀደሰው በማናቸውም ነገር ኃጢአትን ቢሠራ፥ ለበደል መሥዋዕት ለእግዚአብሔር ከመንጋ ነውር የሌለበትን አውራ በግ ያቀርባል እንደ ግምጋሜህ መጠን በብር ሰቅል እንደ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን ለበደል መሥዋዕት ያቀርበዋል» ዘሌ 5፤15
ኃጢአተኛው ይህንን የኃጢአት ወይም የበደል መስዋዕት በታዘዘው ደንብ መሠረት ለሊቀ ካህናቱ ካቀረበ በኋላ እጁን በመስዋእቱ ላይ ጭኖ ከጸለየለት በኋላ ኃጢአተኛው ለሰራው ኃጢአት ምትክ ማስተሰርያ ሆኖ አንገቱን ይቆለምመዋል። ከደሙም የመሰዊያ ግድግዳው ላይ ይረጨዋል። ያን ጊዜም የኃጢአት መስዋዕት ሆኖ ኃጢአተኛው ከሰራው ኃጢአት ነጻ ሆኖ ይመለስ ነበር።
 ይህ ከኃጢአት ለመንጻት የሚደረግ የመስዋዕት ስርዓት ኃጢአት በሰሩ ቁጥር መቅረብ የሚገባውና ኃጢአተኞች ሁሉም ለየራሳቸው ያለማቋረጥ ለማቅረብ የሚገደዱበት የመንጻት ደንብ ነበር።  ይህን መስዋዕት ሁልጊዜ ለመፈጸም ያስገደደው ምክንያት ሊቀካህኑም ሆነ የሚሰዋው በግ  ዘላለማዊ ስላልነበሩና ብቃት ስለሚጎላቸው ነበር።   ሊቀካህኑ ለራሱ መስዋዕት እንዲያቀርብ ይገደዳል። በጉም  ነውር እንዳይኖርበት ጥንቃቄ ይደረግበታል።  እንደዚያም ሆኖ ፍጹም ማዳን አይችሉም።
  
«ሊቀ ካህናት ሁሉ ስለ ኃጢአት መባንና መስዋዕትን ሊያቀርብ ከሰው ተመርጦ ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ ስለ ሰው ይሾማልና፤እርሱ ራሱም ደግሞ ድካምን ስለሚለብስ፥ ላልተማሩትና ለሚስቱት ሊራራላቸው ይችላል፤በዚህም ምክንያት ስለ ሕዝብ እንደሚያቀርብ እንዲሁ ስለ ራሱ ደግሞ መስዋዕትን ስለ ኃጢአት ሊያቀርብ ይገባዋል» ዕብ 5፤1-3

ስለዚህ ይህንን ኪዳን በማስቀረት እግዚአብሔር አዲስ ቃል ኪዳን ለመግባት ወዷል። በዚሁ መሠረት እነዚህን አምስት ነጥቦች የሚያሟላ ነው ፤
1/ ኃጢአትን የሚያስተሰርየው ሊቀ ካህን በሞት የሚሸነፍ መሆን የለበትም።

2/ ሊቀ ካህኑ በመሐላ የተሾመ መሆን አለበት።

3/ ለራሱ መስዋዕት ማቅረብ የማይገባው ንጹህ መሆን አለበት።

4/ ሊቀ ካህኑ እንደኦሪቱ በግ የሚያቀርብ ሳይሆን ራሱ ለኃጢአተኛው በግ ሆኖ መሰዋት አለበት።

5/ ኃጢአተኛው ወደሞተለት ሊቀካህን በመቅረብ መናዘዝ እንጂ ስለኃጢአቱ በግ ማቅረብ አይጠበቅበትም።
ስለዚህ ይህንን የሚያሟላ መስዋዕት እግዚአብሔር አብ ልጁን ወደምድር ልኳል። እሱም ሰው የሆነው ኢየሱስ ነው። 
«ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ ማንም የለም፥ እርሱም በሰማይ የሚኖረው የሰው ልጅ ነው» ዮሐ 3፤13 
ኢየሱስ በመሃላ የተሾመ ዘላለማዊ ሊቀካህን ስለሆነ ዛሬ ሌላ ሊቀካህን የለንም። የኦሪቱ የኃጢአት መስዋዕት በግ ከኃጢአት ያነጻ ነበር። የአዲስ ኪዳኑ የእግዚአብሔር በግ ደግሞ ላመኑበት ለዘለዓለም ያድናል። ከዚህ ውጪ የመዳን መንገድ ለሰው ልጅ አልተሰራም። ኢየሱስም «መንገዱ እኔ ነኝ» ያለውም ለዚህ ነው። ሌላ የመዳኛና የመጽናኛ መንገድ በጭራሽ በዚህ ምድር በሌላ በማንም የለም።

«እነርሱም ያለ መሐላ ካህናት ሆነዋልና፤ እርሱ ግን፦ ጌታ። አንተ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘላለም ካህን ነህ ብሎ ማለ አይጸጸትም ብሎ በተናገረለት ከመሐላ ጋር ካህን ሆኖአልና ያለ መሐላ ካህን እንዳልሆነ መጠን፥እንዲሁ ኢየሱስ ለሚሻል ኪዳን ዋስ ሆኖአል።እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል።ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና።» ዕብ 7፤20-27
ስለዚህ ኢየሱስ በሞቱ ሞቴን ያሸነፈ፤ የሕይወቴ ቤዛና በሥጋ የተገለጠ የእግዚአብሔር ልጅ ነው። በእርሱም አዳኝነት አምናለሁ። «በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው»  ዮሐ 3፤36 እንዳለው የዘላለምን ሕይወት በሞቱ በኩል አግኝቻለሁ። ከሌላ ከማንም የድኅነትን ተስፋ አልጠብቅም። በኃጢአት ብወድቅ የምነጻው፤ የምነሳው በእሱ ብቻ ነው። የምለምነው፤ የምጠይቀው፤ የምማጸነው እሱን ብቻ ነው። በሩ እሱ ስለሆነም «አንኳኩ ይከፈትላችኋል» በማለት የሰጠኝ የመዳን ተስፋ የማይለወጥ ነውና። ኢየሱስ ለእኔ እንዲህ ነው። እናንተስ የመዳናችሁን ተስፋ የምትጠባበቁት ከእነማን ነው?