Friday, May 4, 2012

«አሁን ደግሞ ገፍተው፤ ገፍተው ማንን ይሆን የሚወረውሩት?»

                                                                      (by dejebirhan)
አንድ ሰሞን የዘመድኩን በቀለ ትኩሳት  «በደጀሰላምና አንድ አድርገን» እንዲሁም በሌሎቹ ውርንጭላ ብሎጎች ሳይቀር፤  ይሄ ነው የተዋህዶ ልጅ፣ ሲኦልም ቢሆን ግባ፤ ውረድ ፣ ዘመድኩን  የአባ ቢላዋ ልጅ፣ ቆራጡ፤ እሳቱ፤ አንድ ለእናቱ፤ ጀግናው ፣ ሰማእቱ ምኑ ቅጡ፤ ያልተባለ፣ ያልተወራ ነገር አልነበረም። ከወሬ አቀባባዮቹ ብሎጎች አንስቶ፤ የወሬ አቀባባዮቹ አስተያየት ሰጪዎች ሁላቸውም በአንድነት፤ በአንድ ጀምበር ዘመድኩንን አጽድቀው፣ እነሱንም የሰማእትነት ሲቃ በሚተናነቃቸው  አስተያየቶች ተዥጎድጉደው ድረ ገጾቹን በእንቶ ፈንቶ አቆሽሸው ዘመድኩንን ከእርቅ አጣልተው ሲያበቁ ለተመኙለት   የእነሱ  ሲኦል (በኛ በኩል ግን እስር ቤት) ዱለውት ሲያበቁና  ፋይሉ ተዘግቶ ወደ መዝገብ ቤት መልስ  ሲሆን አንድም አጨብጫቢ ቃሊቲ አብሮት ሳይወርድ ያ ሁሉ ጯሂ የራሱን ኑሮ ወደማሞቁ መመለሱን ታዝበን ተገርመናል፣ ምናልባትም ዘመድኩን ዛሬ ላይ ሆኖ የያኔውን ግፋ በለው ፤ዓይኑን ገልጦ ሲመለከት  ያን ሁሉ ጆፌ አሞራ እንደእኛው ታዝቦ  ምን እንደሚሰማው ስንገምት «ሰውን ማመን ቀብሮ ነው» በተለይም ማቅን ማመን ውሃ መጨበጥ ነው፤ ይል ይሆናል። ያም ሆነ ይህ ጥሩ የትምህርትና ነገሮችን የማመዛዘን ጊዜ እንደሚሆንለት አይጠረጠርም። በዚያ መጠቀም ሳይችል ቀርቶ በከሰሱኝ  ሰዎች ላይ ቂሜ አይበርድም በሚል  ስሜት  በቀል አርግዞ የሚወጣ ከሆነም ከርቸሌ ውስጥ በችግር ተወልውሎ በተዘጋጀ የልቡ አዳራሽ፤ ከደጅ ቆመው የሚጠብቁት የቂም መናፍስት ወዲያው ገብተው የከፋ ችግር ከሚያመጡበት በቀር እሱ የሚጎዳው ወይም የሚያመጣው አንዳች ነገር እንደማይኖር ከወዲሁ ማስገንዘቡ ተገቢ ነው። ለማንኛውም ቃሊቲ የማስተዋል፣ የመማርና የማገናዘብ ጊዜ እንዲሆንለት ምኞታችን ነው።

 የዘመድኩንን ነገር ይህንን ያህል ካልን እነዚያ የፍርድ ቤቱ የመስመር  አራጋቢዎች ሁሉ ወደየት ሄዱ ወደሚለው እናምራ!
ደጀ ሰላምም ሆነ ታናሽ ወንድሙ ብሎግና ግልገሎቹ ብሎጎች ሁሉም ባንድነት ስለዘመድኩን አላየንም፣ አልሰማንም በሚል ስሜት ከረሱት በኋላ ሌላውን ባለተራ እንደዚሁ አይዞህ በርታ፤ሰማእቱ፣ ጀግናው፣ ማን እንዳንተ፣ ዘራፍ፣ እንዲህ ነው የተዋሕዶ ልጅ….. ወደሚል አዲስ የጩኸት መንደራቸው ተመልሰው በማስተጋባቱ ላይ ተጠምደው መቆየታቸውንም በአንክሮ ታዝበናል።
ከሳሙኤል ዘወገግ፣ እስከ ዝቋላ ደብረ ከዋክብት ድረስ አገር ይያዝ፣ አገር ይንቀል፣ ገንዘብ ይዋጣ፤ ዘመቻ እንውጣ፤ ውሃ ይሸጥ፣አስተዳደር ይለወጥ፣ መንግሥት አቃጠለ፤ ህጻናት ገደለ ወዘተ እሮሮና ጩኸት ወደማስተጋባቱ  ተዛውረው በተለመደ የቆሸሸ ልምዳቸው ከድረ ገጽ ላይ ተጥደው፤ በጎጋ አስተያየት ሰጪዎች አንድ ሺህ አንስተው፣ አንድ ሺህ ሲጥሉ እሳቱም ጠፋ፤ ነገሩም ተረሳ፤ ፋይሉም ተዘጋ።  እነሱ ያልጩሁት አይሰማም፤ እነሱ ያልደረሱበት መቅኖ የለውም የተባለ ይመስል፤ ተጮኸ፤ ተጯጯኸ። በጸረ መንግሥት ዘመቻቸው የተሳካ ወይም በማኅበረ ቅዱሳን ክንፍ አልባ መልአክነትና ፈጥኖ ደራሽነት የሰሩት ነገር ከሚኖር በቀር፤ የዝቋላ ገዳምም ሆነ የሳሙኤል ዘወገግ ገዳም ደን መቃጠል አዲስ ነገር እንዳልሆነ ሁላችንም የምናውቀው ጉዳይ ነው።

 ገዳማቱ የቃጠሎ አደጋ ሲደርስባቸው የገጽታ ግንባታና የጩኸት ጋጋታ ከማብዛት ይልቅ የሚበጀው ዘላቂ መፍትሄ መፈለግ ሆኖ ሳለ የአንድ ወቅትን ችግር ልክ ሰማይን እንደመደገፍ ቆጥሮ፤ መደገፉን እንደጨረሱ ሰማዩን መደገፍ ወትሮውንም ለማስመሰል እንጂ አቅም ኖሯቸው እንዳልሆነ ስንረዳ ምን ዓይነት አስመሳዮች ተፈለፈሉ ለማለት እንገደዳለን።
የኢህአዴግ መንግሥት ዲሞክራት ይሁን አምባ ገነን ፖለቲካዊ ማንነቱን ለመተንተን የዚህ ብሎግ ዓላማ ባይሆንም እንደመንግሥት አገር ሲቃጠል፤ ገዳም ሲፈርስ ዝም ብሎ የሚመለከትና  ከትንሹ መንግሥት ከማኅበረ ቅዱሳን ያነሰ  ድርሻ ይኖረዋል ብለን አናምንም።
ገዳማቱን የሚጠብቀው እግዚአብሔር መሆኑን ካመንን ዛሬ ጥበቃውን ያቆመ እስኪመስል ድረስ እኛ ባንጠብቅ ኖሮ የሚለው ከንቱ ዝማሬ የሚያስተምረን ነገር በእግዚአብሔር ላይ መመካት የማይችልና በችሎታው የሚተማመን ትውልድ መፈጠሩን ብቻ ነው።
እነ ደጀሰላምና ማቅ ባይኖሩም ገዳሞቹ ይኖራሉ፤ ድሮም ነበሩ። የሚገርመው ግን እኛ ፈጥነን ባንደርስ እንደዚህ ይሆን ነበር፤ መንግሥትማ ዝም ብሎ ተኝቷል፤ እኛ ንቁዎችና ፈጣን ደራሾች ነን የሚለው ትምክህት የእኛን አስፈላጊነት እወቁ፤ ተረዱ ለሚል ገጽታ ግንባታ ጥሩ አጋጣሚ ሆኖ ከማለፍ ውጪ ሌላ ፋይዳ የለውም።
 በእውነትና በቅን ልቡና ችግሩን ለመጋፈጥ በሃሳብ፤ በጉልበትና በገንዘብ የሚቻለውን ሁሉ ያደረጉ ምእመናትና ምእመናን እንዳሉ ሁሉ አጋጣሚውን በመጠቀም የጨለመ ስማቸውን ጥሩ ቀለም በመቀባት ጥቂት የመልክ ብርሃን ለመፈንጠቅ የተጠመዱ ማኅበራት እንዳሉ የምንደባበቀው ነገር አይደለም።።
እንዲህና እንደዚያ ሆኖ እንደ ዘመድኩን ፋይል ፤የአሰቦትና የዝቋላው ጉዳይ ሲዘጋ ደግሞ ክንፍ አልባ መልአኰቹ እየበረሩ ከዋልድባ በመድረስ ከማቅ እስከ ዳንኤል ክብረት፤ ከደጀ ሰላም እስከ አንድ አድርገን፤ ተቀጥላዎቹም ተጨምረው አዲሱንና ትኩሱን የስኳር ወሬ ወደማራገቡ መግባታቸውን ደግሞ ለመመልከት በቅተናል። አሁን አሁን ደግሞ የጦርነት ሰልፍ ወደ ገዳሙ እየተመመ እንደሆነ እየነገሩን ነው።
እነዚህ ጉዶች የሲኖዶስ ጉባዔ ሲቃረብ እንደ ለማዳ እንስሳ እየተቅለሰለሱ፤ የሌለ አቧራ በማራገፍ በአባቶች በኩል የራሳቸውን ጉዳይ ለማስፈጸም በነገር እንደሚተገትጓቸው ሁሉ  ምነው ታዲያ የዋልድባ ጉዳይ እንዴት እንዳንገበገባቸው፣ በለመዱት አቧራ  የማራገፍ ጥበብ ተጠግተው በማስረዳት አንዳች ነገር ሲኖዶሱ እንዲያደርግ ወይም ድምጹን እንዲያሰማ ያላደረጉ? ብለን ብንጠይቅ  ድሮውንም አባቶችን የሚቀርቡት ጉዳያቸውን ለማስፈጸምና ከፋፍሎ ለመያዝ እንጂ ሲኖዶሱ በመንፈስ ቅዱስ ይመራል ብለው ስለሚያምኑ እንዳልሆነ ይታወቃል። በአንድ ሰው ፤ ያውም በአባ ሠረቀ ብርሃን ላይ ያንን ያህል ዘመቻ በየድረ ገጾቻቸውና ብሎጎቻቸው ዜናና መግለጫ ሲሰሩ እንዳልነበሩ  በዋልድባም ይሁን በሌሎቹ ገዳማት ላይ ችግር ሲከሰት የሲኖዶሱና የወዳጆቻቸው ሊቃነ ጳጳሳት ዝምታ ትክክል አይደለም የሚል ዜና ምነው አልሰሩ?  ቢያንስ ቢያንስ ብጹእ ሥራ አስኪያጁ፤ እየተባሉ በየጊዜው የሚደሰኩሩላቸው ምነው በዋልድባ ጉዳይ ላይ ምን እንዳሉ አልነገሩን?
የእነዚህ ቡድኖች ምላስና ብእር እሺ ብለው በማይታዘዟቸው በአባ ፋኑኤል ላይ ብቻ ነው እንዴ የሚሾለው? የእሳቸው የአስተዳደር ድክመት ብቻ ነው እንዴ ከፊታቸው ተስሎ የሚታያቸው? ብለን ብንጠይቃቸው ጥያቄአችን ከተገቢ በላይ ተገቢ ነው።
 ዳሩ ግን ተንኰል እንጂ መልስ ስለሌላቸው ጥያቄውን በእንጥልጥል ትተነው እንለፍ።
«ሲፋጅ በማንኪያ፤ ሲቀዘቅዝ በእጅ» እንዲሉ እንጂ ማቅ ሆነ ደጀ ሰላም በአንድም ጳጳስ ላይ እምነት እንደሌላቸው አሳምረን  እናውቃለን። ያማ ባይሆን ኖሮ  ችግሩን የቤተክርስቲያን ጉዳይ አድርጎ ካመኑ በጳጳሳቱ ዝምታ ላይ በተነፈሱና ቢያንስ የቋሚ ሲኖዶስ አቋም በዋልድባ ጉዳይ በግልጽ አለመታየቱን በአስገራሚነቱ በገለጹልን ነበር።   ይህ የሚያሳየን ነገር ቢኖር ሁሉም ጯሂ ቡድን የሚራመደው ኋላና ፊቱን እየጠበቀ፣ የሆነ ጥግና ተገን ይዞ የሚያዋጣውን መዝኖ እንጂ ስለቤተክርስቲያን ግድ ብሎት ስለእውነት በአደባባይ ለመናገር ድፍረት ስላለው እንዳልሆነ ያረጋግጥልናል።
ሊቃነ ጳጳሳቱ የመንግሥትን አቋም ደግፈዋል ወይም ማኅበረ ቅዱሳንና ተላላኪዎቹ ብቻቸውን ተቃውመዋል።
አለበለዚያም ሊቃነ ጳጳሳቱ የመንግሥትን አሠራር ለመቃወም ድፍረት አጥተው፣በዝምታ ተውጠው ፤ ማኅበረ ቅዱሳን ግን ደፋር ሃይማኖተኛ ስለሆነ ከዋልድባ ሄዶ ጥናት ለማጥናት መገደዱን እንገምት? ብንል  ይህም እውነት አይመስልም፤ ምክንያቱም ማኅበረ ቅዱሳን ደፋር ሃይማኖተኛ ሆኖ የዋልድባ ጉዳይ የሚያንገበግበው ቢሆንማ ኖሮ የጳጳሳቱን  ዝምታ  ባላለፈና ከእኔ ቀድማችሁ ገዳሙን ልትጠብቁ ሲገባችሁ እኛን ልጆቻችሁን  ሜዳ ላይ ተዋችሁን ብሎ በተናገረ ነበር።
ጉዳዩ ወዲህ ነው። የሚያንገበግበው የቤተክርስቲያን ችግር ሳይሆን የራሱን ጉዳይ ከሚፈጽሙ ጳጳሳት ጋር ሳይላተም ጥጉን ይዞ በማለፍ ከጳጳሳቱ በላይ ለቤተክርስቲያን ደራሽ  መሆኑን ማሳየትን ስለፈለገ ብቻ ነው። ይህንንም ስውር ተልእኰውን በለፍላፊ ብሎጎቹ ገጽታውን  ሲገነባ መገኘቱ ያረጋግጥልናል። አለበለዚያማ እሱንና ልጆቹን  ከጳጳሳቱ የበለጠ ሊቀ ጳጳስ ያደረገውን ምክንያት በነገረን አለያም ጳጳሳቱ ስለገዳማቱ ከእሱ ያነሱበትን ጭብጥ ባስረዳን ነበር።
ሁሉንም  የሚያገናኛችሁ የቤተክርስቲያን ችግር ሳይሆን የየግላችውን ገመና በመሸፈን ጥቅሞቻችውን ማስጠበቅ ነው። እነዚያም ትልልቆቹ ዝም፤ እነዚህ ተቅለስላሾቹም ፤ ዝም።  ውስጣቸው ተቋስሎ ሳለ ጥቅሞቻቸውን ለማስጠበቅ ዝም!!
ከጳጳሳቱ ጋር ተላትሞ ችግር ከማባባስ ይልቅ ተመራጭ የሆነለት ነገር የስኳሩን  ጉዳይ በህዝቡ መካከል ስኳር አድርጎ በማቅረብ ለጦርነት ክተት ወደሚል ዘመቻ መጠመድ እንደአማራጭ መወሰድን ነው። ሰማእትነት እንዳያመልጥህ ወደሚል ጥበብ መሸጋገሩን መርጠዋል። ድረ ገጾቹና ብሎጎቹም ይህንኑ ትኩስ ዜና፤ሰበር ዜና እያሉ ወደማስተገባቱ አምርተዋል። ይህ እንግዲህ የዋሁን ምእመን ወደጦር አውድማ በመንዳት ቢቻል ስለህዝቡ ብዛት መንግሥት ፍርሃት አድሮበት ስራውን እንዲያቆም፤ ከዚያም ተጽእኖ ፈጣሪ ነን ብሎ ራስን ለመካብ አለያም መንግሥት በታጠቀው ኃይል ምእመኑን ለመጨፍለቅ እርምጃ ቢወስድ መንግሥት የራሱን ሕዝቦች ፈጀ ብሎ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘትና ተነስ፤ታጠቅ፤ ሃይማኖት የሚሽር መንግሥት መጥቶብሃልና ተዋጋ ለማለት ካልሆነ በስተቀር ዱላ በእጁ የያዘ ምእመናን ይህንን ብልጥ መንግሥት ይገዳደረዋል ተብሎ እንዳልሆነ ይታወቃል።  ገድሎ ይሁን አስሮ የሚያደርገውን አድርጎ መንግሥት ሲያበቃ በሥራው ቢቀጥል አለቅላቂ ብሎጎችና አባታቸው ማቅ ዘመድኩንን ሲኦል ከትተው አላየንም፤ አልሰማንም እንዳሉት፤ ሕዝቡን አስፈጅተው አላየንም፤ አልሰማንም እንደሚሉ ይጠበቃል። ይሁን እንጂ ይህ ጥበብ  በመጨረሻ የሚያዋጣ ነው ብለን አናስብም።

ጳጳሳቱን ማንቃት ማደራጀት ሳይሆንላቸው ሲቀር  ሕዝቡን ስለዋልድባ ንቃ ተደራጅ በማለት ወደእሳት ለመግፋት መሞከራችሁ አሳዛኝ ነው። መንግሥት የስኳር ፋብሪካ ዓላማውን በፍርሃት አቋረጠ ከሚል ፖለቲካዊ ኪሳራ ለመዳን ቢችል በማግባባት፤ ባይሆንለት በማሰር ወይም በማስፈራራት ሊቀጥል ይችላል። ያኔ ነገር ሁሉ መቋጫ ሲያገኝ ምን ልትሉ ይሆን? ሌላ የሁከት መድረክ ፈጥራችሁ ስትጮሁ እንደዚሁ እናይ ይሆናል።
እስከዚያው ገፍታችሁ፤ ገፍታችሁ ዘመድኩንን የእነሱ ሲኦላችሁ እንደወረወራችሁት፤ አሁን ደግሞ ስለስኳሩ ገፍታችሁ ገፍታችሁ ማንን ይሆን የምትወረውሩት? ምእመናኑን ነዋ!
  ይህ ፎቶ የሚያሳየው ያንን ነው።

ለሁሉም  የሚሆነውን ጊዜ ይስጠን እናያለን።