Wednesday, April 4, 2012

እኛ ጦጣ ነን?

የኛ አርኪዮሎጂስቶች ‹‹ጦጣ›› ከሚፈልጉ…

naodlive@gmail.com


አርኪዮሎጂስቶች ተግተው የሚፈልጉት ነገር ቢኖር ቅሪተ አጽም ነው፡፡ ከቻሉ የሰው ለማግኘት ይሞክራሉ፤ ካልሆነላቸው የእንስሳ አጽም፤ ካጡ ደግሞ የዕጽዋት ቅሪት፤ በጣም ከተቸገሩ ደግሞ የጥንት ሰው መገልገያ ሊሆኑ ይችላሉ ያሏቸውን ስለታም ድንጋዮችና ሸክላዎች ይፈልጋሉ፡፡
የብዙዎቹ ኢትዮጵያውያን አርኪዬሎጂስቶች ሕልም ግን ሉሲን የሚቀድም የጦጣ አጽም ማግኘት ነው፡፡ ሉሲን ያገኛትም ፈረንጅ ስለሆነ ደስተኛ አይደሉም ስለዚህ የ‹‹ሀበሻን ጦጣ›› ራሱ ሀበሻ እንዲያገኝ ይፈልጋሉ፡፡ በቅርቡ ሀበሻ ተመራማሪዎች ያገኙት ቅሪተ አጽምም የተሞገሰውም የሉሲን የዕድሜ ሪከርድ ስለሰበረ እና …ነው፡፡

ይሄ ሁሉ ልፋት ግን አንድ ነገር ለማረጋገጥ ነው? እኛ ሰዎች ከጦጣ መምጣታችንን!
ሰው ከጦጣ ሊመጣ አይችልም ብዬ ለመሞገት አልፈልግም፡፡ ምን አገባኝ! የሚያምን ይመን፤ የማያምንም አለማመኑን  ይመን፡፡ እኔን የሚያሳስበኝ! ጦጣ ስንፈልግ እንደ ጦጣ ማሰብ የመጀመራችን ነገር ነው?
ያ ጦጣ፤ የመጀመሪያው ጦጣ፤ ኢትዮጵያ ብቻ መገኘቱ ነገር ለምን ጥሩ ዜና እንደሚሆን ግን አይገባኝም!፡፡ ለምን አሜሪካ አይገኝም? ለምን ዩሮፕ አይገኝም? …..አረ… ኢትዮጵያ የሰው ልጅ ምንጭ ስለሆነች ነው! አይደል?፡፡ የሰው ልጅ ምንጭ ጦጣ ከሆነ፤ ያ ጦጣም ኢትዮጵያ ብቻ ከተገኘ…ኢትዮጵያውያን ከሌላው የሰው ዘር ሁሉ ተለይተን ለጦጣ የቀረብን መሆናችን አይደል? እና ይሄ ምን ያኮራል? ያሳፍራል እንጂ፡፡ እንኳንም ዘንቦብን ...

 ባልማር ኖሮ ደንቆሮ! ትሉኝ ነበር፡፡ ግን አትሳሳቱ...እንደ እናንተም ባይሆን ተምሬያለሁ..በዝግመተ ለውጥ ሰው እና ባክቴሪያ እንዴት እንደሚመሳሰሉም ማውራትም እችላለሁ፡፡ ዋናው ችግሬ፤ ከመላምት ያልጸዳውን የዝግመተ ለውጥ ፍልስፍና መሞገት አይደለም፤ ለፍልስፍናው እኛ ያለን ‹‹ጦጣዊ›› አቀባበል እንጂ፡፡ በተለየይ አርኪዮሎጂስቶች፡፡
ዩሮፕ እና አሜሪካ ‹‹ጦጣ›› ቢያገኙ ምን የሚያደርጉ ይመስላችኋል? ‹‹የኛ አባት›› እያሉ የሚኮሩበት ይመስላችኋል? አትሞኙ! ሊሉ የሚችሉት ‹‹ከአፍሪካ በባርነት የተሰደደ፤ የጥንት ሰው ቅሪተ አጽም፤ ደቡብ አሜሪካ ጥጥ እርሻ ሜዳ ላይ ተገኘ የሚል ጽሑፍ ጽፈው ጆርናል ላይ ያትሙታል፡፡ከዚያ ሙዚየም አስቀምጠው ገንዘብ ይሰበስበቡበታል፤ ቢዝነስ ይሰሩበታል እንጂ! እንደ እኛ፤ አሀ! እኛም የጦጣ ቅርብ ዘመዶች ነን ለካ! ብለው አይኮሩበትም፡፡
ማስረጃ ከፈለጋችሁ፤ የሰውን ልጅ ዝግመተ ለውጥ ካርታ ተመልከቱ፡፡ በጄኔቲክ አድቫንስመንትም፤ በአርኪዮሎጂካል ምስክርም፤ ዘመናዊ ሰው ያለው ዩሮፕ እና አሜሪካ ነው፤ ኃላ ቀሩ እና ብዙ ኃላ ቀር ጂኖች ተሸክሞ ያለው ሕዝብ ማን ይመስላችኋል! ምሥራቅ አፍሪካ፡፡ ለምን! በሉሲ ምክንያት…ደስ ይበላችሁ! የጦጣ የቅርብ ዘመዶች ነን፤ ፈረንጆች ትክክል ናቸው፡፡

እና አጽም እየቆፈሩ፤ ከጦጣ ነው የመጣችሁት ለሚሉን፤ እንደውም ‹‹ቁርጥ ጦጣ ትመስላላችሁ›› ለሚሉን ሰዎች ማስረጃ ማቀበል፤ እስካሁን እንደጦጣ ከማሰብ እንዳልተላቀቅን ያመለክተኛል፡፡ የጦጣ እና የተማሪ ተረት ትዝ አይላችሁን? በቃ እንደዛ ነው ነገሩ፡፡ ሲያደርጉ አይተን ማድረግ እንጂ ሌላ ሙያ የለንም፡፡
በአርኪዮሎጂ ሳይንስ አምናለሁ፡፡ የማልስማማው፤ የእኛ ተመራማሪዎች፤ ለማግኘት በሚሞክሩት እና በማግኘታቸውም በሚኮሩበት ነገር  ነው፡፡ በነገራችን ላይ የኢትዮጵያ አርኪዮሎጂስቶች ዋና ተግባር ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? መቆፈር እና አጽሙን ከአፈር መለየት፤ ከዚያ ውጪ ያለውን የእውነት ሳይንስ ግን የሚጨርሱልን ግን ፈረንጆች ናቸው፡፡ጦጣ ምን ያውቃል፡፡
ያገኘነው ጦጣ እድሜው ስንት እንደሆነ፤ ቅሪተ አጽሙ የየትኛው ዓይነት ሰው እንደሆነ፤ በዝግመተ ለውጥ ውስጥ ስላለው ትርጉም የሚነግሩን እነርሱው ፈረንጆቹ ናቸው፡፡ በእርግጥ ሌላ ቁፋሮ እንድናካሂድላቸው፤ ጆርናል ላይ ስማችንን ይጽፋሉ አለያም ዶክተር፤ ማስተር የሚል ሰርተፍኬት ይሰጡናል፡፡
የኛ አርኪዮሎጂስቶች መቆፈር ካለባቸው፤ የላሊበላን እግር ቆፍረው፤ የፋሲለደስን እግር ቆፍረው፤ የአክሱምን እግር ቆፍረው…የኛ ሥልጣኔ ለምን እዚያ ላይ እንደቆመ ይንገሩን! የእነ ላሊበላን የሕንጻ መሳሪያዎች ያሳዩን፤ አባቶቻችን የአክሱምን ድንጋዮች ያጓጓዙበትን መኪና ያሳዩን! ስለ ዝግመተ ለውጥም ማውራት ከፈለጉ በእኛ እና በላሊበላ ትውልድ ስላለው ለውጥ ያብራሩልን! የጠፋውን ጂን ያፋልጉን!..እንጂ ከጦጣ እንዳልመጣን ሆዳችን እያወቀ፤ ከጦጣ መጣችሁ ለሚሉን ፈረንጆች ‹‹ከጦጣ መጥቼአለሁ! ካላመናችሁ ሀገሬ ያገኘሁትን ጦጣ እዩ!›› እያሉ አይጃጃሉብኝ፡፡ ከንቱ አርኪዮሎጂስቶች! ጦጣዎች!
እኔ መለስ ዜናዊ ቢሰማኝ ኖሮ! አርኪዮሎጂስቶችን ጦጣነታችንን ለማረጋገጥ ከሚለፉ፤ ሥልጣኔአችንን ቆፍረው እንዲያወጡ በጉልቤ! እዘዛቸው እለው ነበር፡፡ ወይም ፈረንጅ ቀጥሬ በፈረንጅ አስነግራቸው ነበር፡፡ ደግነቱ! መለስም አይሰማኝ! አርኪዮሎጂስቶችም ብሎጌን አያነቡ! ግልግል፡፡