Friday, April 6, 2012

ዘሪሁን ሙላቱ ከቡታጀራ፣ ዳንኤል ግርማ ከደሴ፣ "ቀኝ ኋላ ዙር" ተባሉ

                             የጽሁፉ ምንጭ፣ dejeselaam-dejeselaam.blogspot.com
በረጅም ምላስ እና በፈሪሳዊ ፍልስፍና ከሚታወቁት የ"ማኅበረ ቅዱሳን" ቀንደኛ ነውጠኞች መካከል ዘሪሁን ሙላቱ እና ዳንኤል ግርማ የተባሉት ግለሰቦች ከቡታጀራ እና ደሴ ከተሞች በመጡበት እግራቸው እንዲመለሱ መደረጉን ከየሥፍራው የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

ዘሪሁን ሙላቱ ከቡታጀራ የተባረረው ማንም ሳይወክለውና ሳይልከው ዓመታዊውን የመድኃኔዓለም በዓለ ንግሥ ተደግፎ ለራሱ ዝናና እና መልካም ገፅታ ግንባታ በማሰብ ዐውድ ምሕረት ላይ ለመስበክና "ኦርቶዶክስ መልስ አላት" በሚል ርዕስ ያሳተመውን ቪሲዲ ቸብችቦ ኪሱን በብር ለመሙላት አስልቶ ወደ ስፍራው በመሄዱ መሆኑን ውስጥ ዐዋቂ ምንጮቻችን አስታውቀዋል፡፡

ዘሪሁን ከወንድወሰን ጋር በመሆን "ሀገር-አማን" ብሎ ወደ ቡታጀራ የገሰገሰ ሲሆን፣ በትላንትናው ዕለት (መጋቢት 27 ቀን 2004 ዓ.ም) በቡታጀራ ደብረ ሠላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ተገኝቶ ዐውደ ምሕረት ላይ ወጥቶ ለመስበክ ዕድል እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ በሥፍራው የነበሩ የሀገረስብከቱ ሠራተኞች፣ የደብሩ አለቆችና የልዩ ልዩ ክፍል የሥራ ኃላፊዎች ማንነቱን ይጠይቁታል፡፡ ዘሪሁንም፣ "እኔ መምህር ዘሪሁን ሙላቱ" እባላለሁ በማለት ይጀምርና ስለ ራሱ ማንነትና አስተዋጽዖ አጉልቶና አግዝፎ መተንተን ይጀምራል፡፡ ካህናቱም "ለመሆኑ ይህንን ስትለን ተዘዋውረህ ለመስበክ የሚያስችልህ ፈቃድ አለህ ወይ"? ይሉታል፡፡ እርሱም በቀጥታ "የለኝም" ሳይላቸው ታዋቂ ሰባኪ ነኝ፤ ብዙ ቦታ ተገኝቼ አስተምሬአለሁ በማለት ቀጥተኛ መልስ መስጠት ሳይችል ይቀራል፡፡ "እሺ ወደዚህ ስትመጣ ማን እንደላከህ ልትነግረን ትችላለህ? ለዛሬ እዚህ መጥተህ እንድትሰብክ የተመደብክበት ወይም የታዘዝክበት ደብዳቤ ልታሳየን ትችላለህ"? ብለው ጠየቁት፡፡ እርሱም አንዱንም ጥያቄ በአግባቡ ሳይመልስላቸው ይቀራል፡፡ 

 በል እንግዲህ ሁኔታህ እንደዚያ ከሆነ ማንነትህን ስለማናውቀው ዐውደ ምሕረቱን አንፈቅድልህም ይሉታል፡፡ እርሱም የጥያቄውን አቅጣጫ ይቀይርና "እሺ ዐውደ ምሕረቱን የማትሰጡኝ ከሆነ በቅርብ ያሳተምኩት ቪሲዲ አምጥቻለሁና ሕዝቡ እንዲገዛ ማስታወቂያ ንገሩልኝ" ይላቸዋል፡፡ እነርሱም ብልጠቱ ገብቷቸው "አንተ ማን ሆነህ ነው ያንተን ቪሲዲ የምናስተዋውቅልህ? ዐውደ ምሕረቱ የግለሰቦች ሸቀጥ መቸርቸሪያ አይደለም ከፈለግህ ከቅጥር ግቢው ራቅ ብለህ መሬት ላይ አንጥፈህ፣ ዘርግተህ በግልህ መሸጥ ትችላለህ" ብለው ይነግሩታል፡፡ በዚህ ሁኔታ ተሰፋ መቁረጥ ውስጥ የገባው ዘሪሁን ደረቱን ወጠር ያደርግና "እኔ እኮ ከአዲስ አበባ የመጣሁ ምርጥ የቤተክርስቲያን ልጅ ነኝ" በሚል ስሜት ኮስተር ብሎ ለማስፈራራት ይሞክራል፡፡ ካህናቱ የዋዛ አልነበሩምና ስማ የምንነግርህን እሺ ብለህ የማትቀበል ከሆነ ወደ ሀገረ ስብከታችን ሊቀጳጳስ ደውለን በፖሊስ አስይዘን ከመጠየቅ ውጪ አማራጭ የለንም ይሉታል፡፡ በዘሪሁን ሙላቱ ያደረው ሰይጣን ቅድስት አፎምያን (የሰኔ ድርሳነ ሚካኤልን ያንብቡ) ከተፈታተነው ሰይጣን ያነሰ አይደለምና "ሊቀጳጳስ የምትሉት (አንቱታው ቀርቶ) ይህ ሰው ማን ነው? ምን አገባው? እርሱ እኔን አያዘኝም" እያለ መደንፋት ይጀምራል፡፡ (ሥርዓተ ቤተክርስቲያን እንደሚያዘው፣ አንድ ኩታራ የመንደር ቸርቻሪ ቀርቶ ሊቀጳጳስ ቢሆን እንኳን፣ የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳሰ ሳይፈቅድለት በሌላው ሀገረ ስብከት ውስጥ ገብቶ ምንም ነገር ማድረግ አይችልም)፡፡ ሠላም ያልገዛውን ኃይል ይገዛዋልና፣ በዘሪሁን ሞገደኛነትና ማን አለብኝነት ግራ የተጋቡት ካህናት እንግዲህ የምንልህን እምቢ ብለህ የምታስቸግር ከሆነ  ሌላ አማራጭ የለምና ሕግ ይዳኘናል ብለው ፖሊስ መጥራት ይጀምራሉ፡፡ ዘሪሁንም የያዘው አቅጣጫ አላወጣ ማለቱን ሲረዳ ጭንቅላቱን እንደ ኤሊ ወደ ቅርፊቱ መልሶ፣ በኋላ ማርሽ አፈግፍጎ እግር አውጭኝ በማለት በመጣበት እግሩ ወደ አዲስ አባባ ለመፈርጠጥ መገደዱ ታውቋል፡፡

በተመሳሳይ ሁኔታም ዳንኤል ግርማ የተባለው የማኅበረ ቅዱሳን ምልምል ቅጥረኛ ወደ ደሴ ኪዳነ ምሕረት በመሄድ እሁድ መጋቢት 23 ቀን 2004 ዓ.ም  ዐውደ ምሕረት ላይ ቆሞ ለመስበክ ዕድል እንዲሰጠው ይጠይቃል፡፡ የደብሩ ሰበካ ጉባዔ አባላትና የስብከተ ወንጌል ኃላፊዎች እርሱ ማን እንደሆነ እና በቅድሚያ የቤተክርስቲያን ቅጥር ሠራተኛ ስለመሆኑ ማስረጃ እንዲያቀርብ ይጠይቁታል፡፡ እርሱም እንደዘሪሁን ይህንን ማስረጃ ማቅረብ አለመቻሉን ሲረዱ እንግዲያውስ ወደ እኛ ደብር መጥተህ እንድትሰብክ የታዘዝክበት የጠቅላይ ቤተክህነት ደብዳቤ አቅርብ ይሉታል፡፡ ይህንንም ማቅረብ አልቻለም፡፡ ኃላፊዎቹም መልሰው "በል አንተ፣ አጉራ ዘለል ሰባኪ ነህ ማለት ነው፤ ሌላውን አጉራ ዘለል ለማለት ይቀላችኋል መመሪያውን እየጣሳችሁ የምታስቸግሩ ግን እናንተው ራሳችሁ ናችሁ፡፡ ስለዚህ በመጣህበት እግርህ ተመለስ" ብለው  እንዳባረሩት ለማወቅ ተችሏል፡፡

ዘሪሁን ሙላቱ፣ ዳንኤል ክብረት፣ ዳንኤል ግርማ እና ዘመድኩነ በቀለ ራሳቸውን የማኅበረ ቅዱሳን አርበኛ አድርጎ በመሾም ቤተክርስቲያን ሳትወክላቸው ውስጥ ባሉ ተባባሪዎቻቸው በመታገዝ ገንዘብ እየከፈሉ ጭምር በልዩ ልዩ መድረኮች ማለትም በየመጽሔቱ፣ በየቴሌቪዥን ፕሮግራሙ እና በየዐውደ ምሕረቱ በመውጣት ለራሳቸው ክብርና ዝና ሌት ተቀን የሚለፉ መሆናቸው የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡

"ማኅበረ ቅዱሳን" እንደ ባህል የወሰደው ነገር ቢኖር ራሱን ከቤተክርስቲያን በላይ በማድረግ የሁሉንም ነገር ተቆጣጣሪና ስታንዳርድ አውጪ አድርጎ ማስቀመጥ ሲሆን "ደቀመዛሙርትህ እጃቸውን ሳይታጠቡ ለምን ይበላሉ? ይህች ሴት አመንዝራለች፣ በሰንበት ለምን ይፈውሳል"? በማለት እንደሚከስሱ ፈሪሳውያን የቤተክርስቲያንን ልጆች የሚሳድድ ሲሆን በሌሎች ልክ ያወጣው የአጉራ ዘለል (ቃሉ ከቤተክርስቲያን አባቶች መውጣት የሌለበት) መመሪያ መልሶ ራሱን አንቆ ይይዘው መጀመሩን ብዙዎች ታዝበዋል፡፡ በቡታጀራና በደሴ ያሉ ልዩ ልዩ ሥልጣነ ክህነት ያላቸው ኃላፊዎች መመሪያውን እንዲህ ሲያስጠብቁ፣ የሲኖዶስ አባል የሆኑት አቡነ ገብርኤል ራሳቸው ያወጡትን መመሪያ ራሳቸው በመጣስ አጉራ ዘለል ሰባክያንን ማለትም፣ ዘበነ ለማ፣ ዳንኤል ክብረትንና ምሕረተአብ አሰፋን  ያለ ጠቅላይ ቤተክህነት ፈቃድ በማንአለብኝነት ወደ ሀዋሳ ወስደው ከየካቲት 23 እስከ 25/2004 ዓ.ም ማሰበካቸው የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ 

ውድ የብሎጋችን ተከታታዮች፣ አንዳንድ ግለሰቦች "ወንጌል ይሰበክ እንጂ፣ ማን ሰበከ ማን"? ተብሎ ለምን ይጠየቃል የሚሉ የማዘናጊያ ጥያቄዎች ለዝግጅት ክፍላችን ያቀርባሉ፡፡ እንደ ብሎጋችን አቋም፡ መሠረቱ የወንጌል መሰበክ መሆኑን ብናምንበትም፣ ስለ ስብከት የወጣው መመሪያ ሁሉንም የቤተክርስቲያን ልጆች ሊመለከት ይገባል፡፡ አንዱ መመሪያ እንዲያከብር ሲገደድ ሌላው መመሪያ እንዲጥስ መደረግ የለበትም፡፡ ሁሉም እንደተሰጠው ፀጋ ያገልግል፡፡ ተንኮልና ሌላውን ጠልፎ የመጣል ሰይጣናዊ ባህል ከቤተክርስቲያናችን ሥሩ ተቆርጦ መጣል አለበት እንላለን፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት፣ ምሕረቱና ጥበቃው ከእኛ አይለይ!!!
አሜን!!!