Monday, February 11, 2013

ምንኩስናና ወንጌል ይተዋወቃሉ?

በድንግልና ሕይወት እግዚአብሔርን ስለ ማገልገል መጽሐፍ ቅዱስ በሚገባ ያስተምራል። ማቴ 19፤10-  1ቆሮ 7፤25-39   ጥያቄው ግን «ድንግልናና ምንኩስና አንድ ናቸውን?» የሚለው ጥያቄ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ በድንግልና የኖሩና በድንግልናም ስለመኖር የተናገረበት መንፈስ መነኩሴ ስለመባሉ ምንም ያለው ነገር የለም። ምንኩስናን ደናግላን ብቻ ሳይሆኑ መአስባንም /ባለትዳሮችም/ የሚከተሉት ህግ ነው። ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ ስለደንግልና ከሚናገረው ሃሳብ ጋር የምንኩስና ህግ ምንም ግንኙነት እንደሌለው ነው።  ምንኩስና በጫካና በበረሃ ኑር የሚልን ልምምድ የሚያስተምር ሲሆን ወንጌል ግን ለእግዚአብሔር ቃል መስፋፋት ያለጋብቻ በድንግልና መኖር ጠቃሚ እንደሆነ እንጂ ወደጫካ መሄድ አስፈላጊ ስለመሆኑ አያስተምርም። 
ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ ድንግልናን የሚደግፈው፤


1/ በእግዚአብሔር ዘላለማዊ ጥሪ መሠረት ለአገልግሎት ራሳቸውን የለዩ ማለትም እግዚአብሔርን ለማገልገል ብለው ሃሳባቸውን በዚህ ዓለም የትዳር ፈተና /ሚስትና ልጆችን በመውለድ/ ምክንያት ልባቸው ተከፍሎ የእግዚአብሔር መንግሥት መስፋፋት ሥራ እንዳይተጓጎል የሚያደርጉት ውሳኔ ነው። /እንደሐዋርያው ጳውሎስ ማለት ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ ለወንጌል አገልግሎት የተለየና በድንግልና የኖረ ሰው እንጂ መነኩሴ አልነበረም/

2/  በተፈጥሮ ጃንደረባ የሆኑ ወይም ሰዎች ጃንደረባ ያደረጓቸው ከትዳርና ልጅ ከመውለድ ሕይወት ጋር የተራራቁ ስለሚሆኑ ራሳቸውን በድንግልና ሕይወት ውስጥ መኖር እንደሚችሉ ሲያገነዝበን ይታያል።


እንደመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ከዚህ ውጪ ሰዎች በድንግልና እንዲኖሩ የሚገደዱበት መንገድ የለም። ይሁን እንጂ ምንኩስና የሚባለው ሕግ ለደኅንነት፤ ለጽድቅና መንግሥተ ሰማያት ለመግባት ተብሎ በድንግልና መኖርን የሚሰብክ መንገድ ነው። ይህ መንገድ የሰዎች ህግ እንጂ የእግዚአብሔር ቃል መሠረትነት የሌለው ለጽድቅና ለመዳን የሚደረግበት የትግል መድረክ በመሆኑ በልዩ ልዩ ፈተናና ውድቀት ውስጥ የሚታለፍበት መንገድ መሆኑም እርግጥ ነው።  ይህም «የእግዚአብሔርን ጽድቅ ሳያውቁ የራሳቸውንም ጽድቅ ሊያቆሙ ሲፈልጉ፥ ለእግዚአብሔር ጽድቅ አልተገዙም» ያለው ቃል እንደተፈጸመ ያሳያል። ሮሜ 10፤3 ምክንያቱም ጽድቅ በክርስቶስ ደም የተሰጠንና በእምነት የምንቀበለው ስጦታ እንጂ እኛ በምናደርገው ተጋድሎ የሚገኝ አይደለም። በእምነት የተቀበለውን ጽድቅ  ሥራ ከመጠበቅ ውጪ በጥረት የሚመጣ አይደለም። ሮሜ 5፤16 ኤፌ 4፤24

 በኢትዮጵያ ውስጥ ይሁን በዓለም አቀፍ ሃይማኖቶች ውስጥ እየታየ ያለው የምንኩስና አስነዋሪና የፈቲው ውድቀቶች እየጎሉ በመምጣታቸው የተነሳ በትግል የማይወጡት መሆኑን መነሻም በትግል ጽድቅ ለመስራት የመሞከር ውጤት ነው። 
ዓለማውያኑን በመፈወስና ከእውነተኛው የእግዚአብሔር ቃል በማገናኘት ወደዘላለማዊው መንገድ መምራት የሚገባቸው ሰዎች ለመጽደቅ የተመረጠው መንገድ ምንኩስና ነው በማለታቸው ሰባኪና መምህር ጠፍቶ ዓለማውያኑ ከእውቀት ማነስ የተነሳ በኃጢአት ውስጥ በመኖር በመነኮሳቱ የጽድቅ ስራ ላይ የመዳን ተስፋ እንዳላቸው እንዲያስቡ ተደርገዋል። ዛሬም በመነኮሳቱ የቀደመ ሥራ ላይ ተስፋን በማድረግ አማልዱኝ የሚሉ ድምጾች የመብዛታቸው ምክንያት ይሄው ነው። ክንፍ የበቀለበት ቀን፤ እግር የተቆረጠበት እለት፤ መሬት የቀደዱበትና ሱራፌል የሆኑበት መዓልት እያሉ በየገዳማቱ እየዞሩ በጸሎትዎ ያስቡኝ፤ ጻድቁ አይርሱኝ የሚለው ልመና መሠረቱ መነኮሳቱ በሥራቸው ጸድቀው፤ያጸድቃሉ፤ እኔ ግን ኃጢአቴ ብዙ ስለሆነ የመዳን ተስፋዬ የመነመነ ነው ከሚል አስተሳሰብ የመነጨ እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል። የክርስትና ጽድቅ ክርስቶስ እንደሆነ የዝንጋዔ ልቡና በሕዝቡ ውስጥ ያሰረጸው ይህ ምንኩስና የሚሉት ፍልስፍና ነው። «ወንጌል ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ» ሲል የክርስቶስን የማዳን መንገድ የሚከተሉ ማለቱ እንጂ በመነኮሳት ተጋድሎ ላይ የሚንጠላጠሉ ማለቱ አልነበረም። ጽድቅ በሰው ልጆች ትግልና ውጣ ውረድ የሚመጣ ቢሆን ኖሮ ሐዋርያው « እንግዲህ በአንድ በደል ምክንያት ፍርድ ለኵነኔ ወደ ሰው ሁሉ እንደ መጣ እንዲሁም በአንድ ጽድቅ ምክንያት ስጦታው ሕይወትን ለማጽደቅ ወደ ሰው ሁሉ መጣ» ሮሜ 5፤18 ባላለም ነበር። 


የምንኩስና መስራቾች የ4ኛው ክ/ዘመን ግብጻውያን ሰዎች መሆናቸው እርግጥ ነው። እነዚህ ሰዎች ጀምረውታል ከመባሉ ከ4ኛው ክ/ዘመን በፊት በቤተክርቲያን ውስጥ እንዳልነበረ ይታወቃል። ድንግልናን በመከተል ይሁን መአስብነትን በመተው ከምንኩስና ሕግ ጋር የመስማማት መሠረቱ በአንዳንዶች በኩል የዓለማዊ አስተሳሰብ ወደቤተክርስቲያን በመግባቱ የፈጠረባቸውን ሃዘን ለመሸሽ፤ አንዳንዶቹም ዓለማዊው ኑሮ አስቸጋሪ ሲሆንባቸው ከዚህ ለመገላገል፤ ሌሎቹም የመኖር ተስፋቸው ሲሟጠጥ «ሄጄ እዚያው ልሙት» ከሚል አስተሳሰብ የተነሳ እንደሆነ ከምንኩስናው መጽሐፍ ስንረዳ ሰው ሰራሽነቱን ያጎላዋል።  ሥርዓቱን ቤተኛ ያደረጉት ሰዎች ተዋጽዖ «አባ በእንተ ነፍሱ፤ አባ በእንተ ከርሱና አባ በእንተ ልብሱ» ናቸው። የምንኩስና የሕይወት መገለጫዎች መሆናቸውን መናገሩ የምንኩስናን መሠረት ሰዋዊ ሥርዓት መሆኑን እንደማሳያ መውሰድ ይቻላል። ምንም እንኳን «አባ በእንተ ነፍሱ» የተባለው እጸድቅበታለሁ ብሎ ቢገባበትም ጽድቅ የሰው ልጆች ትግል ገጸ በረከት ስላይደለች ዓላማው መንገዱን የሳተ ከመሆን አያልፍም።

በመሠረቱ ምንኩስና የመጽሐፍ ቅዱሱ ድንግልናዊ ሕይወት መገለጫ  አይደለም። ከላይ እንደጠቆምነው ምንኩስና ባለትዳሮችም ትዳር በኋላ ሊከተሉት የሚችሉት መንገድ ስለሆነ ግንኙነት የለውም። ምንኩስና ከመጽሐፍ ቅዱሱ ቃል ጋር ራሱን በማስጠጋትና መንፈሳዊ ምስል በመቀባት ቤተክርስቲያን ውስጥ የተተከለ ሰው ሰራሽ ስርዓት ነው። የተፈጠረበት ዓመተ ምህረት እንደሚያስረዳው አመጣጡ ከቅዱሱ የእግዚአብሔር ቃል ይልቅ የግኖስቲኮች ጋር ሲስማማ ይገኛል። ውርርሱም ከሂንዱይዝም፤ ቡድሂዝምና ዞሮአስተራኒዝም ጋር ነው።  ምንኩስና የሚባለው ስርዓት በ4ኛው ክ/ዘመን ጀምሮ ሳይተከል ከክርስቶስ ልደት በፊት የነበረ ስርዓት ነው። ወንጌል ደግሞ አዲስ የሕይወት መንገድ እንጂ የቡድሂዝምን የምንኩስና ስርዓት አስፈጻሚ ባለመሆኑ አንድም ቦታ የዚህን ስርዓት ጠቃሚነትና አስፈላጊነት አልተናገረም። ስለሆነም ከክርስቶስ ልደት በፊት የነበረው ይህ ሥርዓት የክርስትናን መልክና ቅርጽ ይዞ በግብጽ በኩል ወደ ዓለም ሊሰራጭ በቅቷል።
 ይህች ግብጽ ለዓለም ያበረከተችው ይህንን ብቻ አይደለም። የእስላሙን መስራች መሐመድን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል አጣምመው ያስተማሩት መነኩሴ ግብጻዊ እንደነበሩ ታሪክ ይናገራል። የቶማስ ወንጌል፤ የማርያም መግደላዊት ወንጌል፤ የባርናባስ ወንጌል፤ የይሁዳ /ሰያጤ እግዚኡ/ ወንጌልን ጽፈው ለዓለም አበርክተዋል። እነዚህ መጻሕፍት እንደቤተክርስቲያን ቅዱሳት ባይቆጠሩም ለብዙዎች መሰናከያ ሆነዋል። ግብጻውያኑ ብዙ የክህደትና የፍልስፍና መጻሕፍት ምንጮችም ነበሩ። ከዚህ የተነሳ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ የነበረውን የምንኩስና ሥርዓት ጎትተው በማምጣት ክርስቲያናዊ መልክ ቀብተው በዓለም ቢያስፋፉት ብዙም አያስገርምም። አሳዛኙ ነገር ዓለሙ ሁሉ ይህንን ስርዓት መጽሐፍ ቅዱሳዊ አድርጎ በመቁጠር የወንጌል ዘመን አዲስ ግኝት አድርጎ በህግ መተግበሩ ነው።  
 የምንኩስና ሕግጋት የምሥራቃውያንን ሃይማኖቶች የተከተለ ስርዓት ነው። ቢጫ መልበስ፤ መቁጠሪያ መቁጠርና መሬት ላይ እየወደቁና እየተነሱ መስገድ ከክርስትና መምጣት 500 ዓመት በፊት ሲደረግ የመቆየቱ ነገር ዛሬም ይኼው ስርዓት ከክርስትናው ጋር በተመሳሳይ መልኩ ይከናወናል። እንጨት አለዝቦ፤ ቅርጽ ቀርጾ፤ በሚያስቡት የኅሊና ፍላጎት መልኩ መላእክትን፤ የሚያመልኩትን ጌታ ስእል ስሎ፤ እጣን ማጠንና ለእነሱም መስገድ የቡድሂዝም ቀደምት እምነት መሠረቶች ናቸው። ይህንኑ ድርጊት በክርስትናው ዓለም ያስፋፉት እነዚሁ የቡድሂዝምና ሂንዱይዝም ቅጂ ግብጻውያን መነኮሳት ስለመሆናቸው የድርጊቱ ተወራራሽነት አመላካች ነው። ቅድመ ክርስትና ሲመለክ የነበረው የሂንዲዎቹ የሎርድ ሺቫ ወይም ቪሽኑ ስእል ከክርስትና ብዙ ስእሎች የሚለየው የመስቀል ምልክት አለመያዙ ብቻ ነው።
                           የቡድሂዝም የሎርድ ቪዥኑ ስእልበቅዱሳን አማልክቱ ተከቦ

 ነገሮችን ለማስረዳት ወይም ለማስገንዘብ አንድን ቅርጽ ወይም ምስል መጠቀም ጥሩ ቢሆንም ወደአምልኮና ስግደት ቀይሮ አንዳች ነገር በእሱ በኩል እንዲከናወንልን መጠበቅ ግን የክርስትና ትምህርት አይደለም።

ጉዶ ሪኒ የተባለው ካቶሊካዊ ሰዓሊ በ1636 ዓ/ም በኅሊናው ቀርጾ በስእል ያስቀመጠው፤ አንድ የዘመኑን ባለጡንቻ ስፖርተኛ የሚመስል፤ ራሰ በራ ሰው እሱ ይሆናል ብሎ ያሰበው ሚካኤል መልአክ በላዩ ላይ ቆሞበት  የሳለው ስእል ዛሬ በገበያ ላይ በጣም ተፈላጊ ነው። ተፈላጊነቱም ክርስቲያን ነን የሚሉቱ ሰዎች ከፊት ለፊታቸው አስቀምጠው እየወደቁ በመነሳት በመስገድ ከምስሉ የመልስ ተስፋ መጠበቅ ሚካኤል ለሚሉት የራሳቸው ስሜት የሚያቀርቡት ልመና  እጅግ አሳዛኝ ነው። ይህ ሁሉ ሰባኪ የመጥፋቱና የእግዚአብሔር ቃል ለሰዎች ሁሉ በእውነት ያለመገለጡ ችግር መሆኑን ማንም አይክድም።  ሪኒ ራሱ ስእሉን የሳለው የችሎታውን ውጤት በማስመሰል ለማሳየት እንጂ እንዲሰገድበት ወይም ያየው እውነተኛ ነገር ሆኖ አልነበረም።

ጉዶ ሪኒ በ1636 ዓ/ም የሳለው ስእል

 በሌላ መልኩም ከኃጢአት የመጠበቅ ሕግጋት ማለትም ማኅተመ አፍ /signaculum oris/  ማኅተመ እድና /signaculum manum/  ማኅተመ ሕፅን /signaculum sinus/ የግኖስቲኮችና የምሥራቃውያን መለያዎች ናቸው። በተለይም የዘር ብልትን /signaculum sinus/ ወደሴት ብልት ከማቅረብ መጠበቅ ከኃጢአት መራቅ ነው የሚለው ፍልስፍና ውርሻው የቀደምት ሃይማኖቶች የፈጠራ ውጤት  በክርስትና ውስጥ ቢስፋፋም ይህንን ተፈጥሮአዊ ግዴታ ለመቆጣጠር መታገል አግባብ እንዳልሆነ በአስተምህሮው /መኑ የዐቁር እሳት ውስተ ሕጽኑ/  በብብቱ እሳትን ማን መሸከም ይችላል? ሲል በመጠየቅ መልስ ይፈልጋል። በእርግጥም እሳቱን መቆጣጠር ባለመቻሉ ህዝቡን እየፈጀ ይገኛል።

የሰዎቹ የህግ ሥርዓት ምንኩስና አመጣጡና ሂደቱ በብዙ በአጭሩ ከላይ የተቀመጠውን መምሰሉ እንደተጠበቀ ሆኖ ቤተክርስቲያን ላይ ያስቀመጠው ሌላው ለሸክም የሚከብደው ድንጋይ ሥርዓት ስልጣንን በተመለከተ ነው። ዓለምን አንፈልግም፤ ውጊያችን የሥጋችንን ተፈጥሮ በማዳከም መጽደቅ ነው ካሉ በኋላ በየትኛውም ዓለም የቤተክርስቲያንን ስልጣን ተቆጣጥረው ያሉት እነሱ የመሆናቸው ጉዳይ አስገራሚ ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ የቤተክርስቲያን መሪዎች ባለትዳር ኤጲስቆጶሳት መሆን እንዳለባቸው  በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ቢያስቀምጥም ይህን ቃል የዛሬዋ ቤተክርስቲያን በፍጹም የምትቀበለው ነገር አይደለም። እንኳን ከፍተኛው የሥልጣን እርከን ይቅርና ዋና ዋና አድባራት ሳይቀሩ የሚመሩት ትዳር ምናባቱ! ባሉ መነኮሳት መሆኑ የአደባባይ ምስጢር ነው። 
ከአመሠራረቱ ጀምሮ የወንጌል ተጻራሪ የሆነው ይህ ሥርዓት በአመራርም ይዞታ ከወንጌል ቃል በተጻራሪነቱ እንደጸና  ይገኛል። ቤተሰቡን መምራት የማይችል እንዴት ቤተክርስቲያንን መምራት ይችላል? ከሚል የሐዋርያው ቃል ተነስተን ሥልጣኑን ሁሉ ሰብስበው በእጃቸው ያደረጉ መነኮሳት እንዴት ቤተክርስቲያንን ሊመሩ እንደሚችሉ አይገባንም። ጳውሎስን ተሳስቶ ነው ያንን የጻፈው እስካላሉ ድረስ ቤተክርስቲያንን የመምራት ፍቃድና ብቃት እንደሌላቸው የእልከኝነትና የሥልጣን ምኞት ስካሮቻቸው ያስከተሉት ችግሮች አንዲቱን የክርስቶስ ቤተክርስቲያን በመከፋፈል ለትውልድ ተርፏል።

በአንድ ወቅት አንድ የቅድስት ሥላሴ ኮሌጅ ምሩቅ ወደአሜሪካ ለማቅናት መመንኮስ አለብህ ተብሎ የገዛውን ጨርቅ ደብረ ሊባኖስ ወስዶ አስመርቆ ካደረገው በኋላ የማይሄድበት ሁኔታ በመፈጠሩ ምክንያት መቅረቱን ሲያውቀው ጨርቁን አውልቆ ለደሃ መነኩሴ መመጽወቱ ይታወቃል።   ለምን እንደዚህ እንዳደረገ በቅርብ ሰዎቹ ሲነገር እንደሰማሁት ለቤተክህነቱ የእውቅና ቪዛ እንዲሆነኝ እንጂ ቢሳካልኝ እንኳን የአገልግሎት ዘመኑ የሚያበቃው አሜሪካ ኤርፖርት ላይ ነበር ማለቱም ተነግሯል።  ዛሬ ብዙዎች ስልጣን ለማግኘትና በቤተክህነቱ ወደውጪ ሀገር ለመሄድ ጭምር የሚመነኩሱ እንዳለ እርግጥ ነው።

በአጠቃላይ ምንኩስና የተመሰረተበት መንገድና ዓላማ መጽሐፍ ቅዱሳዊ አይደለም። ያስከተለውም መዘዝ ቆሜበታለሁ ከሚል መርህ ጋር የተቃረነ ነው። ቤተሰባዊ ዓምድን በኑራአቸው ውስጥ ያቆሙ፤ እግዚአብሔርን የመፍራት ሕይወት በኑሮአቸው የተከተሉ ቀሳውስት የመነኮሳቱ ደጅ ጠኚ የሚሆኑበት ምክንያት የእግዚአብሔርን ቃል ይጋፋል።

በድንግልና ሕይወት የመኖር መጽሐፍ ቅዱሳዊው ቃል ምንኩስና ከሚባለው የሂንዱይዝም ቅጂ ግብጻዊው ሥርዓት ጋር ምንም ግንኙነት የለውም። ለእግዚአብሔር መንግሥት አገልግሎት ራስን በድንግልና መለየትና ለጽድቅ ሲሉ መመንኮስ ሁለት የተለያዩ ነገሮች በመሆናቸው ዓላማና ግባቸው አንዱ በእግዚአብሔር ላይ መታመን ሲሆን ሌላኛው በራስ ትግል ላይ መተማመንን የሚያስተምር መሆኑ ነው። ማንም ለራሱ ነፍስና ለራሱ ጽድቅ ሲል መኖር አይችልም። በእምነት የምንኖረውና በሕይወትም ያለነው ስለእኛ በሞተልን በክርስቶስ ኢየሱስ የተነሳ እንጂ በእኛ ብርቱ ትግል አይደለም። «በሕይወትም ያሉት ስለ እነርሱ ለሞተውና ለተነሣው እንጂ ወደ ፊት ለራሳቸው እንዳይኖሩ ስለ ሁሉ ሞተ» 2ኛ ቆሮ 5፤15 ከዚህ የተነሳ ምንኩስና ስለማን የሚኖሩት ሕይወት ይሆን?
ሥርዓቱ ትክክል ያለመሆኑ ነጥቦች እመራበታለሁ የሚለውን ሕግ አያከብርም። የሌላውንም መብት ይጋፋል። ከሁሉም በበለጠ ተፈጥሮአዊ ሕግን የሚነቅፍና ወንጌልን የሚጻረር መንገድ ነው። ምንኩስናና ወንጌልም አይተዋወቁም።