Sunday, June 24, 2012

ዘረኛ ያልሆነ ማን ነው?


Naod ቤተሥላሴ
www. naodlive.com

ዘረኝነት፤ ብሔርተኝነት፤ ጎሰኝነት፤ ጎጠኝነት፤ መንደርተኝነት፤ ቡድነኝነትየሚባሉ ነገሮች ሁሉ የፍርደ ገምድልነት (Injustice, prejudice) መጀመርያዎች እና መገለጫዎች ናቸው ብል ብዙ የተሳሳትኩ አይመስለኝም፡፡ ከዚህ ቀጥዬ የማነሳው ጥያቄ ግን ከላይ በርዕሱ የጠቀኩትን ጥያቄ ነው፡፡ ዘረኛ፤መንደርተኛ... ያልሆነ ማን ነው?

ከቤተክርስቲያን ስወጣ፤ አንድ ጓደኛዬ፤ ከሆነ ከማላውቀው ልጅ ጋር አብሮ ወደ እኔ ሲመጣ አየሁት፡፡ ከዚያ ‹‹ተዋወቀው፤ የአዲስ አበባ ልጅ ነው!›› አለኝ፡፡ የአዲስ አበባ ልጅ ካልሆነ ከእኔ ጋር መተዋወቅ የለበትም? አንተ ራስህ የአዲስ አበባ ልጅ ሳትሆን ተዋውቄህ የለም? ብዬ ልገስጸው ከጅዬ ነበር፡፡ ግን ያው ጨዋ ነኝና…‹‹የጎረቤቴ ልጅ ካልሆነ አልተዋወቀውም›› ብዬ ቀልጄ እንግዳውን ተዋወቅኩት፡፡ የፈራሁት ግን አልቀረም


ከተዋወቅኩት ልጅ ጋር ያለኝ ጠባያዊም ሆነ ልማዳዊ የጋራ ነገር ‹‹አዲስ አበባ መወለድ ብቻ›› ሆኖ ቀረ፡፡ ኮከባችንም፤ ጨረቃችንም፤ ቅዠታችንም የማይገጥም ሆነና ትውውቃችንን Abort አደረግነው፡፡ ይሄ ገጠመኝ እስከዛሬ ትዝ የሚለኝ ያለ ምክንያት አይደለም፡፡

በትግሬዎች ዘረኝነት የሚንገፈገፉ ነገር ግን ራሳቸው ከራሳቸው መንደር ከመጣ በቀር ሌላ ጓደኛ የሌላቸው ብዙ ሰዎች ስለማይ ነው፡፡ ባለፈው የጊዮርጊስ ጽዋ ያላቸው ጎረቤቶች አገኘሁና፤ ማኀበር ልገባ ቋመጥኩ /ጠላ ስለምወድ፡)/ በጽዋው ዕለት አባላቱ ሁሉ በተገኙበት ተጋብዤ ሄድኩ ‹‹ከጎንደሬ በቀር አንድም ሌላ የሰው ዘር የለበትም››፡፡ ይሄ ግን the tip of the iceberg ነው፡፡ በሃይማኖተኞች ውስጥ ያለው መንደርተኝነት ከፖለቲካው የበለጠ ስር የሰደደ፤ ስብከትም፤ ስዕለትም፤ ጸሎትም የማያጠፋው ደዌ ነው፡፡

አንዳንዴ ኢትዮጵያዊ ከኢትዮጵያዊ የሚፈላለገው፤ የመንደሩን ኢትዮጵያዊ እስኪያገኝ ድረስ ይመስላል፡፡ አሁን እኒህ ሰዎች፤ እንደ መለስ ዜናዊ ስልጣን ቢይዙ፤ በራሳቸው መንገድ ጎጠኛ መሆናቸው ይቀራል? 20 ጓደኞቹ ውስጥ 19 የመንደሩ ልጆች የሆነ ሰው፤ መርጦ የሚሄድበት ቤተክርስቲያን እንኳን የመንደሩ ልጆች ወደ መሰረቱት ወይ ወደ ሚበዙበት /ክን የሆነ ሰው፤ ስለ መለስ ዜናዊ ጎጠኝነት፤ ስለ ኦነግ ብሔርተኝነት ማማረር ይገባዋልን? በትግሬዎችስ ዘረኝነት መብከንከንስ ይገባዋል? ፈረንጆችስ ከጥቁሮች እየሸሹ፤ ከብጤ ፈረንጆች ጋር ብቻ ለመጎዳኘት የሚያደርጉትን ጥረት ‹‹ዘረኝነት›› ብሎ መኮነንስ ይገባዋልን? በእኔ ሚዛን ራሱ ዘረኛ ነው፡፡

በእርግጥ፤ ብዙ የጋራ ታሪክ እና ባህል፤ ቋንቋና ለዛ ከምንጋራው ሰው ጋር መወዳጀት ቀላል እና ተፈጥሮአዊ ነገር ነው፡፡ ዘመድ ከዘመዱይባል የለ፡፡ ቢሆንም! ቢሆንም! እኛ የምናደርገውን ያንኑ ነገር ሌሎች ሲያደርጉት ‹‹ዘረኝነት›› ማለት ትክክል አይደለም፡፡ ከዘር፤ ከመንደርየተሻለ የጥብቅ ወዳጅነት ምክንያት፤ የመተማመን ዋስትና፤ የትውውቅ ሰበብ የሌለ ይመስል፤ ሰፈሬ፤ መንደሬማለት ትክክል አይደለም፡፡

ዘርን፤ መንደርንወዘተ ከቁጥር የማያስገቡ፤ ሌላ ብዙ ጥሩ እና በቂ የወዳጅነት ሰበቦች፤ የመተማመን ምክንያቶች አሉ ባይ ነኝ፡፡ ለምሳሌሙያ፤ የኑሮ ዘይቤ፤ አስተሳሰብ፤ ገጠመኝ፤ ርእዮተ ዓለም ወዘተእኒህ ሰበቦች፤ ዘርና መንደር ካልነካቸው አይጸኑም ካልተባለ በቀር!