Showing posts with label ማብራሪያ. Show all posts
Showing posts with label ማብራሪያ. Show all posts

Wednesday, June 4, 2014

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ችግር፤ የአንድ ጤናማ ሰው የጤንነት መስተጓጎልን ይመስላል!


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከሚገጥሟት ፈተናዎች ሁሉ ከውስጧ እንደሚነሳው ፈተና የሚከፋ የለም። ቤተ ክርስቲያኒቱ የኢኮኖሚ አቅሟ እያደገና ውጫዊው ተግዳሮቶቿ እየገዘፉ በመጡ ቁጥር የውስጥ ፈተናዎቿ መቀነስ ሲገባቸው በተቃራኒው እንደአዲስ ቤተ ክርስቲያን ከመቼውም ጊዜ በላይ መከራዋ ገዝፎ መልህቅ መጣያ ወደብ እንዳጣች መርከብ በእስራ ምእቱ የአስተዳደር እክል የባህር ማእበል እየተናጠች ትገኛለች። ይህንን ውስጣዊ ፈተና በቅድሚያ አትኩሮ የሚመለከት ዓይን የሌለው ማንም ቢሆን ውጫዊ ተግዳሮቶቿን ለመመከት የሚያስችል አቅም በምንም ተአምር ሊኖረው አይችልም። ስለሆነም ውስጣዊ ፈተናዎቿን ለይቶ በማስቀመጥ ለመፍትሄውም መንገድ ማስቀመጥ ተገቢ ይሆናል። በዚሁ መሠረት ተለይተው መቀመጥ የሚገባቸውን አንኳር ችግሮች እንደታየን መጠን ለማስቀመጥ ወደድን።

ዋና ዋና ችግሮቿ፤

1/ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የሚችል በእውቀት፤ በልምድና በችሎታ የዳበረ ላዕላይ መዋቅር አለመኖሩ፤

2/ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ፤ ደንብና መመሪያ ጤናማ ሥራ የሚያሠራ ካለመሆኑም በላይ እንደአስፈላጊነቱ አለመሻሻሉ፤


3/ በልምድ፤ በባህልና በትውፊት እንጂ በወንጌል እውነት የታነጸና ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው ተከታይ ትውልድ መቅረጽ አለመቻሉ፤


በዋናነት የሚቀመጡ ናቸው ብለን እንገምታለን። ይህ ማለት አጠቃላይ ችግሮች እነዚህ ብቻ ናቸው ማለት ሳይሆን ዘርፈ ብዙ ችግሮቿ መነሻ የሚያደርጉት እነዚህ ሦስት ዐበይት የአንድ ሰው የሕይወት እስትንፋስን የማግኘት ያህል ህልውና ያላቸው ነጥቦች ናቸው የሚል እምነት አለን።
አንድ ሰው ሕልውና አለው የሚያሰኘው ነፍስና ሥጋው ሲዋሃድ ነው። ሥጋውም ሕይወት አለው የሚባለው አእምሮው፤ አጥንትና ጅማት ከውስጥ ሕዋሱ ጋር ተገቢ ሥራውን ማከናወን ሲችል መሆኑ ይታወቃል። ከዚህ ተነስተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ ሕይወት እንዳለው ሰው ለመቁጠር የሚያስችለን የቁመና መለኪያችን ዋና ዋና ችግሮች ከላይ በሦስት ልየታ ያስቀመጥናቸው ነጥቦች ናቸው። እንዴት? የሚለውን ቀጥለን እንመልከት።

1/ «ቤተ ክርስቲያኒቱ ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የሚችል በመንፈስ፤ በእውቀት፤ በልምድና በችሎታ የዳበረ ላዕላይ መዋቅር አለመኖሩ» የሚለው የጉድለት ነጥብ የአንድን ሰው የአእምሮ አስተሳሰብ ይወክላል። ሰውን ከሌላው እንስሳ የሚለየው ይህ አእምሮና ከአእምሮው የተያያዘው የጀርባው አጥንት በሚያስተላልፉት ኅብለ ሰረሰራዊ መዋቅር የተነሳ ነው። አእምሮ ካልሰራ ሰው ሊያሰኝ የሚችለውን የማንነት መገለጫዎችን ለመሥራት አይችልም። ስለዚህ በዚህ ደረጃ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአእምሮ ማዕርግ የተቀመጠው «ቅዱስ ሲኖዶስ» የሚባለው ክፍል ነው። ይህ ላዕላይ መዋቅር ህልውና እንዳለውና ምሉዕ ሰው ሊሰራ እንደሚገባው እንደባለ አእምሮ መስራት ካልቻለ ሌላው የሰውነት ክፍል በተገቢው መንገድ ሊሰራ አይችልም። ይህ የአንድ ጤናማ ሰው ዋና ማዕከል የሆነው አእምሮ በዚህ ሰዓት በተገቢው መንገድ እየሰራ አይደለም። ስለዚህ አካል የሆነችው ቤተክርስቲያን እክል ገጥሟታል ማለት ነው። እክሎቹ በምን በምን ይገለጻሉ? የሚለውን ጥያቄ በሌላ ጽሁፍ እንመለስበታለን። በጥቅሉ ግን እዚህ ላይ ማስገንዘብ የምንፈልገው ነገር አንድ ጤናማ ሰው እንዳለው አእምሮ መስራት ያለመቻል ችግሮች ነጸብራቅ የሚመሰለው «ቅዱስ ሲኖዶስ» ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ አለመቻሉና የመንፈሳዊነት ብቃት፤ የእውቀት፤ የልምድና የችሎታ ጉድለት ስለሚታይበት የቤተ ክርስቲያኒቱ አእምሮ ችግር ላይ መሆኑን እንረዳለን ማለት ነው። አእምሮ ካልሰራ፤ ሰው ጤናማ ሊሆን አይችልም። ይህ አእምሮና የኅብለ ሰረሰር መዋቅሩ የሚታከመው እንዴት ነው? ጤናማ ካልሆነ ቤተ ክርስቲያን ታማለች ማለት ነው።

2/  «የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ፤ ደንብና መመሪያ ጤናማ ሥራ የሚያሠራ ካለመሆኑም በላይ እንደአስፈላጊነቱ አለመሻሻሉ» የሚለው ነጥብ ምሳሌነቱን ወስደን ለአንድ እንደ ባለአእምሮ ጤናማ ሰው ግዘፈ አካል ብንወስድና ብንተረጉመው የሰውየውን ሥጋ የውስጥ አካሎቹን ያሳየናል። ሕግ፤ ደንብ፤ መመሪያና ሌሎች የማስፈጸሚያ ስልቶች ማለት «ልብ፤ ኩላሊት፤ ጉበት ወዘተ» ውስጣዊ የዝውውር ሕዋሳትን ይወክላል። ጤናማ አእምሮ የሌለው ሰው ካለበት ችግር በተጨማሪ ከእነዚህ ውስጣዊ አካላቱ ውስጥ በአንዱ ላይ ሌላ እክል ካለበት የሕመሙን መጠን የከፋ ያደርገዋል። ስለዚህ ሲኖዶሱ እንደባለ አእምሮ ፤ አእምሮውን ማሠራት አለመቻሉ እንዳለ ሆኖ በላይ የሰው ልጅ የሕልውና ክፍሎቹ እንደሆኑት የውስጥ አካላቱ ተጨማሪ እክል ዓይነት የሕግ፤ የደንብ፤ የመመሪያ ወይም የማስፈጸሚያ ስልቶች ዓይነትና መጠን ተገቢ የሥራ እንቅስቃሴ ማድረግ የሚያስችል ካልሆነ በሽታው አደገኛ ሁኔታ ውስጥ መሆኑን ለመረዳት አይከብድም። ከአእምሮው ላይ በተጨማሪ ከውስጥ ክፍሎቹ ባንዱ ላይ ችግር የገጠመውን አንድ ሰው እስኪ በዓይነ ልቡናዎ ይሳሉና ይመልከቱ! እጅግ አሳዛኝና አስጊ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኝ ለመረዳት የሚከብድዎ አይመስለንም። ቤተ ክርስቲያን አእምሮውን በታመመ አመራር ስር መሆኗ ሳያንስ ስራዋን በተገቢውን መንገድ የሚያስኬድላት የውስጥ አካላቷን መጠበቂያ ማዕቀፍ አለመኖሩ የችግሯን ውስብስብነት የሚያሳይ ይሆናል።

3/ በልምድ፤ በባህልና በትውፊት እንጂ በወንጌል እውነት የታነጸና ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው ተከታይ ትውልድ መቅረጽ አለመቻሉ፤ የሚለውን ደግሞ የአንድ ምሉዕ ሰው ወሳኝ የክፍል እንቅስቃሴ ምሳሌያዊ መገለጫ አድርገን ብንወስደው  ደም፤ አጥንት፤ ጅማትና ቆዳን ይወክልልናል። ሰውየው ግዘፍ እንዲነሳ የሚያደርጉት፤ እንቅስቃሴውን የሚወስኑትና የዑደት ዝውውሩን የሚያገናኙት እነዚህ ዋና የሰውነት ክፍሎቹ ናቸው። ቤተ ክርስቲያን ስንል የክርስቶስ ጉባዔ ምዕመናን ማለታችን እንደመሆኑ መጠን ለቤተ ክርስቲያን ኅልውና ደም፤ አጥንት፤ ጅማትና ቆዳ ሆኖ ያስተሳሰረው ይህ የመዘወሪያ አካል ንጹህ፤ ያልተበከለ፤ ያልተጣመመና ጤናማ የህንጻ ክፍል ካልሆነ ጉባዔ ቤተ ክርስቲያን ጤናማ ልትሆን በጭራሽ አትችልም። በነዚህ መሠረቶች ላይ የቆመው አካላዊ ህልውና የዝውውር ዑደቱ ከፈጣሪው በተቸረውና እፍ በተባለበት የሕይወት እስትንፋሱ በኩል አምላኩን በተገቢው ሊያመሰግን አለመቻሉ ጉባዔው የሚታወክ፤ የሚታመስ፤ በወሬ በሽታ የተጠመደ ይሆናል። በእድሜው መኖር በመቻሉና ነፍስያው አለመለየቷ ብቻውን አንድን ሰው ሕያው ሰው አያሰኘውም። በመንፈሱ የሞተ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ የለውም።
«በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና» ሮሜ 8፤14
በዚህም የተነሳ ጉባዔ አክሌሲያ እንደሆነ የሚታሰበው ትውልድ በልምድ፤ በባህል፤ በትውፊት ገመድ ተጠፍንጎ ከወንጌል እውነት ሳይታረቅና ፈሪሃ እግዚአብሔርን በልቡናው ሰሌዳ ላይ ሳይጽፍ ነገር ግን አንገቱ ላይ የመስቀልና ምስል አንጠልጥሎ የሚሳደብ፤ የሚዋሽ፤ የሚሰክር፤ የሚያጨስ፤የሚያመነዝር፤ የሚሰርቅ፤ እምነት የማይጣልበት የባህል እምነት ተከታይ ሆኖ የሚታየው የእውነትን ወንጌል በመጋት አሳድጎ የቃሉን አጥንት መጋጥ ወደሚያስችል ሰውነት ማድረስ ስላልተቻለ ነው። በእምነት ሳይሆን በሃይማኖት የኖረውም በልምድ እንጂ እውነት ስለገባው አይደለም።  «እውነት ባለበት በዚያ አርነት አለ» የተባለው አንገት ላይ መስቀል አንጠልጥሎ ነገር ግን ነጻ እንዳልወጣ ሰው የሥጋ ሥራ የሚሰራ ሰው ማለት አይደለም። ስለዚህ ትውልዱ በወንጌል ነጻ የመሆን የእውነት ቃል ተኮትኩቶና በቀደምት አባቶቹ አስተምህሮ ታንጾ ባለመኖሩ አርነት ያልወጣ ሰው የሚያደርገውን የሥጋ ሥራ እየፈጸመ  በስም ክርስቲያን እየተሰኘ የባህልና የልምድ ተከታይ ሆኖ እንዲኖር ተፈርዶበታል።  ከልምድና ከባህል መንፈስ ነጻ መውጣት አለበት።
2ኛ ቆሮንቶስ 3፥17  «ጌታ ግን መንፈስ ነው፤ የጌታም መንፈስ ባለበት በዚያ አርነት አለ»

ማጠቃለያ፤

አንድ ሰው ጤናማ የሚባለው አእምሮው፤ ኅብለ ሰረሰሩ፤ የውስጥ አካላቶቹ፤ ደም፤ ስጋ፤ አጥንትና ጅማቱ ተዋሕደው በጤንነት ሲገኙ ነው። ምሉዕ ሰው ሆኖ ሕይወት ያለው መንፈሳዊ ጤንነቱ የሚጠበቀው ደግሞ የነፍስያው ራስ የሆነው ፈጣሪውን ሲያውቅና በተገቢው መንገድ ሲያመልክ ብቻ ነው። ከእነዚህ ባንዱ ጉድለት ቢገኝ አደጋ ውስጥ መሆኑ እርግጥ ነው። ከዚህ ተነስተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችንን የሕይወት ኅልውና ስንመለከት ጤናማ ሁኔታ ውስጥ እንዳይደለች ከላይ ያነሳናቸው ነጥቦች ያስረዱናል። የተከታዮቿ ቁጥር ወደታች የማሽቆልቆሉ ምክንያት የበሽታውን ደረጃ ያሳየናል። የአስተዳደር ሰላም አለመኖር፤ የነበራት ክብርና ተደማጭነት ማነሱም የገጠማት የህመም ደረጃ አደገኛ መሆኑን ያስረዳናል። የመከፈፋሏ መነሻ፤ የመከባበር ድቀት፤ የነውር ገመና ማደግ፤ ዋልጌነት፤ የብክነትና የዝርፊያው የትየሌለነት የበሽታዋ ደረጃ ምን ያህል እንደገዘፈ ለማወቅ ምርምር አይጠይቀንም። ቤተ ክርስቲያኒቱ ያልጠፋችውም ከእግዚአብሔር ታጋሽነትና ለንስሐ የሚሆን እድሜ ከመስጠት አምላካዊ ባሕርይው የተነሳ ይመስለናል። እንደሚገባን ሆነን መልካም ፍሬ ካላፈራን ግን መቆረጣችን አይቀርም።
የፈለገውን ያህል ተኩራርተን የቀደመችቱ መንገድ እያልን ብንደሰኩር ከእግዚአብሔር አስቀድሞ የተቀበልነውንና የሰማውን ዛሬ ይዘን በተግባር ካልተገኘን ከያዝነው የቁልቁለት መንገድ አያድነንም።  በአንድ ወቅት በትንሹ እስያ ለነበረችውና በተመሳሳይ የቁልቁሊት መንገድ ላይ ለነበረችው ለሰርዴስ ቤተ ክርስቲያን በዮሐንስ በኩል መልእክት ደርሷት ነበር።  ነገር ግን መስማት ስላልቻለች እየወረደች ካለበት የቁልቁሊት መንገድ ወጥታ፤ ስህተቶቿን አርማ፤ በእውነት የጌታዋ መንገድ ላይ ለመጓዝ የሚያስችላትን የንስሐ እድሜ ባለመጠቀሟ ከ500 ዓመት በኋላ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመጥፋት በቅታለች። በፍርስራሾቿ ላይም የእስልምና አዛን የሚያስተጋባባት የታሪክ ቤተ ክርስቲያን ሆናለች። ከመሆኗ በፊት የተነገራት ቃል ይህ ነበር።
«እንግዲህ እንዴት እንደ ተቀበልህና እንደ ሰማህ አስብ፥ ጠብቀውም ንስሐም ግባ። እንግዲያስ ባትነቃ እንደ ሌባ እመጣብሃለሁ በማናቸውም ሰዓት እንድመጣብህ ከቶ አታውቅም» ዮሐ 3፤3
( በቀጣይ ጽሁፋችን  ዝርዝር ነገሮችን ለማየት እንሞክራለን)

Monday, April 14, 2014

«ማኅበረ ቅዱሳን አክራሪ ከሆነ እኔም አክራሪ ነኝ» የሚሉ ድምጾች ምነው በዙሳ?



የሚያከሩ እስኪበጠስ ያክርሩ፤ የማያከርና ተግባብቶ የሚኖር የት ይድረስ?
 
በአንድ ወቅት ዳንኤል ክብረት የተባለው ሰውዬ በእንቁ መጽሔት ላይ እንደተናገረው «ማኅበረ ቅዱሳን አክራሪ ሆኖ የገደለው ሰው የለም!» ብሎ ነበር። በዳንኤል አስተሳሰብ «አክራሪ» ማለት በሃይማኖተኝነት ሰበብ ሰው የመግደል ደረጃ ላይ ሲደረስ መሆኑ ነው። ከመግደል በመለስ ያለው ኃይልና ዛቻ፤ማሳደድ ተፈቅዷል ማለት ነው? ሌላው የማኅበረ ቅዱሳን የሜሪላንድ አፈቀላጤ ኤፍሬም እሸቴ ደግሞ «አክራሪ ሃይማኖተኛ መሆን ጥሩ ነው» ሲል ተመራጭነቱን በማሳየት የማኅበረ ቅዱሳንን የማክረር እንቅስቃሴ ተቀባይነት እንዲኖረው ለማድረግ ሲታትር ታይቷል።  አክራሪ በባህሪው እኔ ትክክል ነኝ ከሚል ጽንፍ ተነስቶ፤ የምለውን ተቀበሉኝ፤ እምቢ ካላችሁ ወግዱልኝ፤ አለበለዚያ እኔው በኃይል አስወግዳችኋለሁ በሚል ድምዳሜ የሚያበቃ አስተሳሰብ ነው።  አንዳንዶች አክራሪነት በዚህ ዘመን የተከሰተ አድርገው ሲመለከቱ ይታያል። ትርጉሙና የተግባራዊ እንቅስቃሴው ስፋትና ጥልቀት ተለይቶ ታወቀ እንጂ አክራሪነት ጥንትም ነበረ።  በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 9 ላይ እንደተመለከተው ኢየሱስ ለሐዋርያቱ እንደነገራቸው «አስቀድማችሁ ወደሰማርያ ከተማ ሂዱና፤ ጌታ ይመጣል ብላችሁ አስናድታችሁ ጠብቁኝ» ብሎ ባዘዛቸው ጊዜ የከተማይቱ ሰዎች መልዕክቱን እንዳልተቀበሉ ሐዋርያት ስለተመለከቱ «ጌታ ሆይ፥ ኤልያስ ደግሞ እንዳደረገ እሳት ከሰማይ ወርዶ ያጥፋቸው እንል ዘንድ ትወዳለህን?» ብለውታል።  ጌታ ግን፤ «የሰው ልጅ የሰውን ነፍስ ሊያድን እንጂ ሊያጠፋ አልመጣም» ብሏቸዋል።  አክራሪዎች ራሳቸውን የእግዚአብሔር ብቸኛ ወታደሮች አድርገው ራሳቸውን ያስቀምጣሉ። ስለዚህ እኛን ያልመሰለ ይጥፋ ባዮች ናቸው። አስተምሮ፤ ተከራክሮ መመለስ ስለማይችሉ አጭሩ መፍትሄ ማስወገድ ነው።
እንደዚሁ ሁሉ በፖለቲካው ከተሰማሩት ድረ ገጾች አንስቶ እስከጥቃቅኖቹ ብሎጎች ድረስ አንዱ ከአንዱ እየተቀባበሉ የማያውቁትን ማኅበር ለማሳወቅና ለሃይማኖት ማክረር እጅግ ጠቃሚ እንደሆነ የሚገልጹ ጽሁፎችን እስከማራገብ ድረስ ዘልቀዋል።  በፌስቡክና በትዊተር ገጾች «ማኅበረ ቅዱሳን አክራሪ ከተባለ እኔም አክራሪ ልባል» ከሚለው ድምጽ አንስቶ የማኅበረ ቅዱሳንን ዓርማ የሚያሳይ ግለ ስእል በመለጠፍ አጋርነታቸውን ለማሳየት የሞከሩ ብዙዎች ናቸው።  ሁሉንም ስንመለከት «አክራሪ ሃይማኖተኛ» መሆን አስፈላጊ እንደሆነና «እኛም የዚሁ ሰልፍ አባሪ ሆነን ለሃይማኖታችን አክራሪ ነን» የሚል ይዘት ያለው አቋም እየተንጸባረቀ መገኘቱን መገንዘብ ይቻላል። ሃይማኖተኛ ነን የሚሉቱ ወገኖች ያሉበትን ምክንያት ከማየታችን በፊት ፖለቲከኞቹ ነገሩን ለማስጮህ የፈለጉበትን ምክንያት እንመልከት።

1/ ፖለቲከኞች ማኅበረ ቅዱሳንን የመደገፍ ምክንያት፤

ፖለቲከኛ ሃይማኖት የለውም ማለት ባይቻልም ሃይማኖተኛ ግን ፖለቲከኛ መሆን አይችልም። ፖለቲከኛ ሃይማኖት ሊኖረው የሚችለው ስለሃይማኖቱ አውቆና አምኖበት በመከተሉና እምነቱ የሚያዘውን ለመፈጸም እንደእግዚአብሔር ቃል ለመኖር ለራሱ ኪዳን የገባ ሳይሆን በውርስ ከቤተሰቦቹ የተረከበው ወይም በልምድ ሲከተለው ስለኖረ ራሱን ሃይማኖት እንዳለው አሳምኖ ሲያበቃ ከፖለቲካ የሚገኘውን የምድራዊ ሳይንስ ጫወታ የሚጫወት ሰው ነው።
 ምክንያቱም ፖለቲካ ባላጋራህ የሆነውን የሌላኛውን ሰው አመለካከትም ሆነ ተግባር በምትችለው መንገድ በልጠህ ወይም ጠልፈህ በመገኘት ምድራዊ ሥልጣንን መቆጣጠር ማለት ሲሆን ሃይማኖት ደግሞ የሰውን ልጅ ጠላትነት የማይቀበል፤ ባላጋራውም ሰይጣን ብቻ መሆኑ አምኖ ለእግዚአብሔር መንግሥት ሲል ሃይማኖታዊ መመሪያውን በመከተል ለማይታየው ሰማያዊ ሕይወት ሲል ከሚታየው ጠልፎ የመጣልና የመዋሸት ዓለም የጸዳ ማለት ነው። የዲሞክራሲ ጣሪያ ነክተናል ከሚሉት አንስቶ የነሱኑ መንገድ ተከትለናል እስከሚሉቱ ድረስ ሁሉም ፖለቲከኞች በፖለቲካል ቲዎሪ ከሚነገረው ታሪክ ባሻገር ማስመሰል፤ መዋሸት፤ ማታለል፤ ጠልፎ መጣል ወይም እውነተኛ መስሎ መታየት፤ ሀቀኛ፤ የህዝብ ወገንተኛ መሆንን መደስኮር በሁሉ ዘንድ መኖሩ በማስረጃ አስደግፎ መናገር ይቻላል።  በግርድፉ የተቀመጠውን የፖለቲካ ትርጉም ብንመለከት ለምድራዊ ስልጣን መታገል የመጨረሻ ግብ መሆኑ እውነት ነው።
« Politics is the activities associated with the governance of a country or other area, esp. the debate or conflict among individuals or parties having or hoping to achieve power»
« ፖለቲካ ከሀገራዊ ወይም ከክልላዊ የሕዝብ አስተዳደር ክንዋኔዎች ጋር በተዛመደና በተለይም በተቃርኖአዊ የእርስ በእርስ የሃሳብ ፍጭት የተነሳ ተስፋ በሚሰጥ የፓርቲዎች ስነ ሞገት ብልጫ አግኝቶ የስልጣን ኃይልን የመጨበጥ ግብ ያለው ነው»
ፖለቲካዊ ስልጣን ማለት ግን ለሃይማኖተኛ ጥቅም አይሰጥም፤ ወይም አይጎዳም ማለት አይደለም። እንደሚመራበት የፖለቲካ ርእዮት /አመለካከት/ ይወሰናል። ሃይማኖታዊ መንግሥት ባለበት ሀገር መንግሥቱ ለተመሰረተበት ሃይማኖት አብላጫውን ወይም ዋናውን አገልግሎት ይሰጣል። ሌሎች ሃይማኖቶች እንደመንግስታዊው ሃይማኖት እኩል መብት ሊኖራቸው አይችልም።  ሃይማኖት የለሽ መንግሥት ከሆነ ደግሞ ሁሉም ሃይማኖቶች የመንግስቱ ጠላቶች ነው። ሴኩላር/ ገለልተኛ/ የመንግስት አወቃቀር ባለበት ሀገር ደግሞ መንግስት በሃይማኖቶች ጉዳይ ጣልቃ እንደማይገባ ይደነግጋል። ጣልቃ የማይገባው ለሴኩላር መንግሥታዊ አወቃቀሩ ስጋት እስካልሆኑ ድረስ ብቻ ነው። እንደመንግሥታዊው የፖለቲካ አወቃቀር ሥርዓቱ ሃይማኖትን ሊጠቅም ወይም ሊጎዳው መቻሉ እርግጥ ነው። በኢትዮጵያ ታሪክ በአፄዎቹ፤ በደርግና በኢህአዴግ መካከል ባለው የፖለቲካ ርእዮት የተነሳ ፖለቲከኞቹ ሃይማኖትን የሚመለከቱበት መነጽር የተለያየ ነው። ሃይማኖትን በተለያየ መነጽር የሚያዩ ፖለቲከኞች፤ ሃይማኖተኞች ሊሆኑ አይችሉም።  ፖለቲከኞች የቆሙለትን የተለያየ የፖለቲካ ስርዓት ያገለግላሉ።  ፖለቲከኛ ሆኖ ሃይማኖተኛ ለመሆን ከባድ የሚሆነው ለዚህ ነው። ሃይማኖተኛ ሆኖ መዋሸት አይቻልም። ፖለቲከኛ  ስርአቱን እስከጠቀመ ድረስ ይዋሻል፤ የሌለ ተስፋ ይሰጣል።  አላስፈላጊ ወይም ጠቃሚ ካልሆነ ደግሞ ማስተባበያ ወይም ይቅርታ ሊጠየቅ ይችላል። ለሃይማኖተኛ ንስሀ እንጂ ማስተባበያ ወይም ይቅርታ የሚል የአደባባይ ዲስኩር የለም። ፖለቲከኛ ሃይማኖት ሊኖረው ቢችልም ሃይማኖተኛ ግን በጭራሽ ፖለቲከኛ መሆን አለመቻሉ እርግጥ ነው። ታዲያ የልምድ ሃይማኖት ያላቸው ነገር ግን ሃይማኖተኛ መሆን የማይችሉ ፖለቲከኞች ማኅበረ ቅዱሳን ሲነካ የሚጮሁት ለምንድነው? የሚለው ጥያቄ መመለስ አለበት። ዋናው ነጥብ «የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው» ከሚል የፖለቲካ ፍልስፍና የተነሳ ነው። 

 ሃይማኖት የሌላቸው /እምነት የለሾች/ ይሁኑ ማኅበረ ቅዱሳንን በልምድ የሚመሳሰሉ ባለሃይማኖቶች እና «ማኅበሩ ተነካ ማለት የእግዚአብሔር መንግሥት ተነካ» ባይ የዋሆች ሁሉም በአንድነት ውጥንቅጡ በወጣ አቋም ውስጥ ሆነው ለማኅበሩ ለመጮህ ሞክረዋል። የሚገርመው ደግሞ የማኅበረ ቅዱሳንን መጥፋት የሚመኙ እስላሞች ሳይቀሩ «የሃይማኖት ነጻነት ይከበር» በማለት ለማኅበሩ ያላቸውን ድጋፍ ለማሳየት መሞከራቸው ነው። ዋነኛ ዓላማቸው የሃይማኖት መከበር ስላሳሰባቸው ሳይሆን በእስልምና ጎራ ያሉ ታሳሪዎችን ድምጽ ከማኅበረ ቅዱሳን ጎራ ካሉት ጋር በማስተሳሰር ጉዳዩን ለማጦዝ ከመፈለግ የተነሳ ነው።  በዘመነ ኢህአዴግ እስልምና ተጨቁኗል ቢሉ ለሰሚው ግራ ነው።  በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ብቻ የእስላም መስጊድ ከቤተ ክርስቲያን ቁጥር የበለጠው በዘመነ ኢህአዴግ መሆኑ በጭራሽ ሊስተባበል የሚችል አይደለም።  ከአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ 16% ለሆነው የእስልምና ተከታይ 180 በላይ መስጊዶች ሲኖሩት 74% ከመቶው ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ያሉት አብያተ ክርስቲያናት ቁጥር 150 ገደማ ብቻ ነው። በኦርቶዶክስ ተጨቁነን ነበር የሚሉትን አቤቱታ እንደኢህአዴግ ያካካሰላቸው መንግስት ለእስላሞች የለም ማለት ይቻላል። በዘመነ ኢህአዴግ የተሰራው መስጊድ በሺህ ዘመናት ውስጥ ከተሰራው ይበልጣል።
 እንዳላት ተከታይ ብዛትና ሊኖራት እንደሚችለው የድርሻ ስፋት ድምጿ ያልተደመጠው ኦርቶዶክስ ናት ማለት ይቻላል። ከመንግሥታዊ ክፍል ያሉ፤ ፕሮቴስታንቱም፤ እስልምናውም፤ ኦርቶዶክሳዊ ነኝ የሚለው አሮጌ ፖለቲከኛው ሁሉንም ስንመለከት በግልጽም ይሁን በስውር ይህች ቤተ ክርስቲያን ለሀገሪቱ ባበረከተችው ከመጠቀምና በስሟ ከመነገድ በስተቀር ያደረጉላት አንዳችም ድጋፍ የለም። ላበረከተችው በጎ አስተዋጽኦ ዋጋ መስጠት በራሱ ትልቅ ነበር።

ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን «ልጠፋ ነው» እያለ ለሚያሰማው ጩኸት ፖለቲከኞቹን ያስተባበራቸው ኢህአዴግን እንደጋራ ጠላት ለመፈረጅ እንጂ በሃይማኖት ስለተሰሳሰሩ አይደለም። ኦርቶዶክስ እንድትጠፋ ሲሰሩ የቆዩ የቀድሞ መንግስት ፖለቲከኞች፤ የተለያዩ የሌኒናዊ ፓርቲ አባላትና ርዝራዦች ሳይቀሩ ለማኅበረ ቅዱሳን ሲጮሁ እያየን ነው። እውን ለኦርቶዶክስ አዝነው ነው? የቤተ ክርስቲያኒቱን ሃይማኖታዊ መሪዎች ከመግደል አንስቶ፤ ጣልቃ ገብቶ በመሾም፤ ሲኖዶሱን በመከፋፈልና በማዳከም ትልቅ ድርሻ ያላቸው እነዚህ ጮኸው የማይሰለቹ ፖለቲከኞች ትልቁን ድርሻ ይወስዳሉ። ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳንን ለመደገፍ መሞከራቸው ቤተ ክርስቲያኒቱን የማዳከም ቀጣይ ተግባራቸው ማሳያ ተደርጎ ከሚወሰድ በስተቀር ቤተ ክርስቲያኒቱ ከማኅበሩም ሆነ ከፖለቲከኞቹ ያተረፈችውም ምንም ነገር የለም።

2/ ሃይማኖተኞች የማኅበሩ ደጋፊዎች፤

ማኅበሩ ራሱ እንደሚለው ከሆነ 35,000 መደበኛ አባላትና 500,000 ተከታይ አባላት እንዳሉት ይነገራል። ያለውን የፋይናንስ አቅም በትክክል ባይናገርና ባናውቅም ቅሉ ከልዩ ልዩ የንግድ ተቋማት ገቢ ምንጮቹ የሚያገኘውን ካፒታል ሳንጨምር ከ35,000 አባላቱ ላይ ብቻ በግርድፉ ብንገምት በወርሃዊ መዋጮ መልክ 10 ብር ቢሰበስብ 350,000 ብር ወርሃዊና ከ500,000 ተከታይ አባላቱ ላይ ደግሞ ለልዩ ልዩ የማኅበሩ ልማታዊ ስራዎች ሰበብ በዓመታዊ ድጋፍ 10 ብር በነፍስ ወከፍ እንዲሰጡት ቢጠይቅና ካሉት ተከታይ አባላቱ መካከል 400,000 ያህሉ ለ10 ብር የድጋፍ ጥያቄው ምላሽ ቢሰጡ 4,000,000 ብር ያገኛል ማለት ነው። ከወርሃዊ  የአባልነት መዋጮ ገቢው ጋር በዓመት ሲሰላ ከ8 እስከ 9 ሚሊዮን ያላነሰ በዓመት ይሰበስባል ማለት ነው። ይህ ስሌት በመንፈሳዊ ጉዞ ሰበብ፤ በመጽሔት፤ በሆቴልና በሱቅ ሽያጭ፤ በካሴት፤ በሲዲ፤ በእርዳታ ጥሪ፤ ከበጎ አድራጎት፤ ከለጋሽ፤ ከቤት ኪራይ ወዘተ የሚገኘውን ግዙፍ ገቢ ሳይጨምር መሆኑ ታሳቢ ይደረግ።  ጆርጅ በርንስ እንዲህ ይላል። « Don't stay in bed, unless you can make money in bed»  «አልጋህ ላይ ሆነህ ገንዘብ ካላገኘህ በቀር አልጋህ ላይ አትቆይ» እንደማለት ነው። ይህ ብሂል የገባው ቅዱስ ማኅበር «መኒ» ይሰራል። «መኒ» የማይገዛው ስልጣን፤ ጉልበትና እውቀት በሌለበት ዘመን የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር አይባልም።

ይህ ማኅበር ከአንታርክቲካ በስተቀር በሁሉም ዓለማት ላይ ቢሮዎች አሉት። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ባለችበት ቦታ ሁሉ አለ። በሳንባዋ ይተነፍሳል፤ በደም ስሯም ይዘዋወራል። ነገር ግን መዋቅሩና የመዋቅሩ መረብ ማኅበረ ቅዱሳዊ ነው። አብዛኛው አባላቱና ደጋፊዎቹ አብረው የተሰለፉት ቤተ ክርስቲያኒቱን የደገፉና የረዱ እየመሰላቸው መሆኑ እርግጥ ነው። የቤተ ክርስቲያኒቱ አመራር ከዘመኑ ጋር መዘመን ባይችልና ባንቀላፋበት ቦታ ሁሉ ማኅበሩ እየተገኘ ከበሮ እየመታ፤ እየዘመረ አለሁልሽ እያለ ማኅበሩንና ቤተ ክርስቲያኒቱን ለይቶ የሚያይ ተከታይ ባይኖር አያስገርምም።  የሚገርመው እንመራሃለን የሚሉቱ የማኅበሩ ተመሪ ሆነው መገኘታቸው ነው።

ሀ/ ሊቃነ ጳጳሳቱ፤

ሊቃነ ጳጳሳቱን ማኅበሩ እንዴት አባል አድርጎ እንደሚይዝ ዝርዝር ውስጥ አንገባም። ነገር ግን ሊቃነ ጳጳሳቱ የሲኖዶስ አባልና በቤተ ክርስቲያኒቱ የአንዱ ሀገረ ስብከት ወይም ክፍል ተጠሪ ሆነው ሲያበቁ የማኅበሩን ዓላማ ተቀባይ፤ የማኅበሩ ጠበቃና ተከራካሪ ሲሆኑ ግርምት ይፈጥርብናል። ዋናው ጥያቄ የሚነሳውም ማኅበሩ የሲኖዶሱ ቅርንጫፍ መስሪያ ቤት ነው ወይ? ሊቃነ ጳጳሳቱ በሀገረ ስብከታቸው መሥራት ያልቻሉትን የሚሰራላቸው ወኪላቸው ነው ወይ?  ምን መስራት ያልቻሉትን፤ ምን መስራት እንዲችልላቸው፤ የትኛውንስ ጉዳይ እንዲያስፈጽም ውክልና ተሰጥቶታል?
 በማኅበሩ ስያሜና ቁመና እንዲሁም በሲኖዶስና በሊቃነ ጳጳሳት መካከል ያለው የሥልጣን፤ የደረጃ ክፍተት የሚለካው በምንድነው? የሚሉ ጥያቄዎች ግራ የሚያጋቡና ምላሻቸውንም በውል የሚያውቅ አለመኖሩ ጉዳዩን አስደማሚ ያደርገዋል።  ስለዚህ ጥርት ያለ መልስ የሌለው የአንድ ማኅበር ዓላማ በአእምሮአቸው የሰረጸ ነገር ግን የሲኖዶስ አባል ነን የሚሉ ሊቃነ ጳጳሳት በአንድም፤ በሌላ መንገድም የማኅበሩ ጉዳይ ፈጻሚ ሆነው መገኘታቸው እርግጥ ነው።

ለ/ ወጣት የሰንበት ት/ቤት አባላት፤ የጥምቀት ተመላሽ ማኅበር፤ የጉዞና መንፈሳዊ ማኅበራት፤

እነዚህ ወጣት ክፍሎች ከማኅበሩ ሰፊና ሁሉን አቀፍ እንቅስቃሴ አንጻር በቁጥጥር ስር መዋላቸው የግድ ነው። ደግሞም አስፈላጊ መሳሪዎች ናቸው። በአንድ በኩል በችግር ወቅት ለማንቀሳቀስ፤ በሌላ መልኩም በችግር ቀን ለመደበቅ ሊያገለግሉ ይችላሉ። መሰረታዊ የትጥቅ መሳሪያቸው ደግሞ «ቤተክርስቲያንን ከልዩ ልዩ ኃይሎች መጠበቅ» የሚል መንፈሳዊ መሰል ትጥቅ ሲሆን ወጣቶቹ ዓይናቸውን በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ በእምነት እንዲጥሉ በማድረግ ማኅበሩ ለሚፈልገው ዓላማ ማገልገል እንዲችሉ ተደርገው ይቀረጻሉ። ወጣቶቹ በእርግጥም ከልባዊ እምነት ተነስተው የሚከተሉ ስለሆነ ቤተ ክርስቲያንን እንደማገልገል እንጂ ማኅበሩን እንደመታዘዝ አይቆጥሩም ወይም ማኅበሩን ማገልገል የቤተ ክርስቲያኒቱን ፈቃድ እንደመፈጸም አድርገው እንዲያስቡ ተደርገዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ያሉ ሰንበት ተማሪዎች፤ የጥምቀት ተመላሽ ቡድኖችና የጉዞ ማኅበራት የማኅበሩ ታዛዥና ተጠባባቂ ኃይሎች ናቸው። የእነዚህ ማኅበራት አባል ሆኖ ማኅበረ ቅዱሳንን ማውገዝ ወይም መቃወም በጭራሽ አይታሰብም።

ሐ/ የመንግሥት ተቋማት አባሎቹ፤

ማኅበሩ ከሚያገኘው ሰፊ የፋይናንስ አቅም አኳያ አባላትን ለመመልመል መጠቀሙ እንዲሁም ከሚጓዝበት አደገኛ የስብከት ዘዴው አንጻር አእምሮአቸውን የመጠምዘዝ ስልት ረገድ በመንግሥታዊ ተቋማት ውስጥ ብዙ አባላትን ማደራጀት ችሏል። የማኅበሩን አቅም ማደራጀት ብቻ ሳይሆን አንድ አቅጣጫ ማየት እንዲችሉ ተደርገው የተቀረጹ የመንግሥታዊ ተቋማት አባላቱ በጣም ጠቃሚ ክፍሎቹ ናቸው።  በመንግሥት ጉዳይ እንደማይገቡ ማሳያዎቹ ናቸው። በሌላ መልኩም የመረጃ ምንጭ ሆነውም ያገለግላሉ። የየትኛውም የመንግሥት ተቋማት ሰራተኛ በየትኛውም ማኅበርና የእምነት ተቋም ውስጥ አባል የመሆን መብት ያለው መሆኑ ባይካድም የያዘውን የመንግስት ስራ ለማኅበሩ አገልግሎት ማዋል ግን ወንጀል ነው። ፖሊሳዊ ስልጣናቸውን በመጠቀም ለማኅበሩ አገልግሎት ተሰማርተው ያላግባብ ያሰሩ፤ የደበደቡ አሉ። ቤተ ክርስቲያኒቱ ስትጠይቃቸው ከመተባበር ይልቅ ማኅበሩ ሲጠራቸው አፋጣኝ ምላሽ የሚሰጡ የመንግሥታዊ ስልጣን አካላት መኖራቸው ማኅበሩ የቱን ያህል ስር እንደሰደደ ያሳያል። እነዚህ አካላት ከማኅበሩ ጎን በግልጽም፤ በስውርም መቆማቸው ነገሩን ከባድ ያደርገዋል።

3/ ማኅበሩ ራሱን ለማዳን የሚቀያይራቸው ስልቶች፤

ማኅበሩ የልዩ ልዩ ሰዎች ተዋጽኦ መሆኑ እንዳለ ሆኖ አመራሩ ራሱን ከወቅቱ የፖለቲካ ሙቀት ጋር በማስማማት የሚያደርጉት የጉዞ ስልት እጅግ የሚደነቅ ነው። ማኅበሩ ሃይማኖታዊ ድርጅት እንዳይደለ ይታወቃል። የድርጅት/ Organization/ ቅርጽ ያለው ነገር ግን በተቋምነት/ Institution/ ደረጃ የተደራጀ ይመስላል። ደግሞም በቤተ ክርስቲያን ስር ያለ የሰንበት ተማሪዎችም ማኅበር ለመምሰልም ይሞክራል። ምሁራን አመራሩ በሳል ስለሆኑ ከሰንበት ትምህርት ቤት ማደራጃ መምሪያ ስር ያወጡት አለምክንያት አይደለም። የሰንበት ት/ቤት በመባልና የሚንቀሳቀስበት ቅርጽ ተመሳሳይ ስላይደለ እንዳይበላሽበት ከመፈለግ የተነሳ የተዘየደ መላ መሆኑ ነው። ዛሬም ያ የማኅበሩ አመራር ኢህአዴግ ከገባበት የሙስሊሞች እንቅስቃሴ፤ ከምርጫ 2007 ዝግጅት እና የጥላቻ ፖለቲካ ካሰባሰባቸው ኃይሎች ጋር ያለበትን ክፍተት በመጠቀም ከመንግሥት ጋር ያለውን ልዩነት ለመጠቀም እየሰራ ይገኛል። በአንድ ወገን ስለማኅበሩ ጉዳይ እያስጮኸ ፤ በሌላ መልኩ ደግሞ ከጩኸቱ በሚገኘው የስውር ድምጽ ብዛት መንግሥት ወደያዘው ፤ልቀቀው እሰጥ አገባ እንዳይሄድ ባለበት በማስቆም ለመንግስት ፈቃዳት ሁሉ ታማኝ መሆኑን ለማሳየት በመሞከር ራሱን በማዳን ስልት ላይ ተጠምዷል። የቅዱሳን ማኅበር ሳይሆን ጠንካራ የፖለቲካ ቅዱሳን ያሉት ማኅበር ስለሆነ ሊደነቅ ይገባዋል።

4/ ማኅበሩና የመጨረሻ ውጤቱ፤

በትግርኛ የሚተረት አንድ ተረት አለ። «ወጮስ እንተገምጠልካዮ ወጮ» ይላሉ። «ብርድ ልብስን ብትገለብጠው ያው ብርድ ልብስ ነው» እንደማለት ነው። ያውም የደብረ ብርሃን ብርድልብስን ብትገለብጠው ያው ዥንጉርጉሩ  የደብረ ብርሃን ብርድ ልብስ ነው። የሰንበት ት/ቤት?/Sunday school/  ድርጅት? /organization/ ተቋም? /Institution/ የቱ እንደሆነ ማኅበረ ቅዱሳን እስካሁን የለየለት አይደለም። ነገር ግን ቅርጹንና መልኩን እንደእስስት እየቀያየረ 22 ዓመት ቆይቷል። ቤተ ክርስቲያኒቱ ለማኅበሩ ምኑ እንደሆነች ሲኖዶሱ በእርግጥ አያውቅም። ማኅበሩ ግን ቤተ ክርስቲያኒቱን እንዴት እንደሚጠቀምባት አሳምሮ ያውቃል። በጣም አደገኛና ስልታዊ ጉዞ የማድረግ ብቃት ያለው አመራር እንዳለው በጉዞው ላይ የሚያጋጥመውን ሳንካ ካለፈበት ተነስቶ መናገር ይቻላል። እውነተኛና ቅን የቤተ ክርስቲያን አባላት የሱም አባል መሆናቸው ሳይዘነጋ ማለት ነው። ነገር ግን ማኅበሩ  ቢደግፉት፤ ቢከተሉት፤ ቢጮኹለት፤ ቢታገሱት እንደ«የደብረ ብርሃን ብርድ ልብስ ቢገለብጡት ያው ብርድ ልብስ» ከመሆን የሚያልፍ አይደለም!!


Saturday, March 29, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን የሚፈርሰው በራሱ ተግባር ነው፤ ኢሕአዴግ ላለፉት 22 ዓመታት መቼ ነካው?



ይህ ህንጻ የማነው? የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን? የመንበረ ፓትርያርክ? የኢንቨስተር? የነጋዴ? የአስመጪና ላኪ?

የሀገሬ ሰው «ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል» ይላል። ይህ አባባል ለሰሞነኛው የማኅበረ ቅዱሳን የጅቡ በላኝ ጩኸት ይስማማል። ኢህአዴግ ሊያጠፋኝ ነው ሲል በየግል ጋዜጣው ማስወራቱ 22 ዓመታት ኢህአዴግ በሚመራት ሀገር ውስጥ ያልነበረ ይመስላል። ሲነግድ፤ ሲያስነግድ፤ ሲሸጥ ሲለውጥ፤ከግብርና ታክስ ተከልሎ በሚሊዮኖች ብር ህንጻ ሲገነባ በሀገሪቱ ኢህአዴግ ያላየው ወይም የማያውቀው ይመስላል። ኢህአዴግ ማኅበረ ቅዱሳንን በአስማት ይሁን በምትሃት እስከዛሬ ሳያየው ቆይቶ አሁን ለማየት ዓይኑን ሲከፍት ማኅበረ ቅዱሳንን አገኘውና ሊበላው ስለሆነ ማኅበረ ቅዱሳን ኢህአዴግ ሊያጠፋኝ ለምን ፈለገ ሲል ለመጠየቅ የተገደደ ይመስላል። በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ያለው ተግባሬ ከማኅበረ ካህናቱ ጋር አጋጨኝ፤ በማያገባኝ አስተዳደር ውስጥ እጄን ሳስገባ ተገኘሁ እንዳይል ከመሬት ተነስቶ ኢህአዴግ ሊውጠኝ ነው ወደሚል ቅስቀሳ መግባቱን  ከመምረጡ በስተቀር በምድር ላይ ያለው እውነታ ግን የምርጫ ዘጠና ሰባት ውጤትና ተከትሎ የመጣው ፖለቲካዊ ቀውስ ስንቱን ፓርቲና የተቃዋሚ መሪዎች እየደፈጠጠ ሲያልፍ ማኅበረ ቅዱሳን ግን በቤተ ክርስቲያኒቱ ታዛ ተጠልሎ አልፏል። ኢህአዴግ ቢያጠፋው ኖሮ ያኔ ባጠፋው ነበር።
ከዚህ በፊት ማኅበሩ እንደጥራጊ አውጥቶ የጣለው ዳንኤል ክብረት ይህን ኢህአዴግ ሊበላኝ ነው የሚለውን የማኅበረ ቅዱሳንን ዘፈን እንዲህ ሲል በደጀሰላም ብሎግ ላይ አውጥቶ ነበር።
«እኔ እንደምገምተው የማኅበሩ አባላት መንግሥትን እንዲፈሩ እና እንዲጠሉ የሚፈልጉ አካላት በአመራሩ ውስጥ ሳይኖሩ አይ ቀርም፡፡ ምንጊዜም አንዳች ከባድ ነገር ሲነሣ መንግሥት እንዲህ ብሎናል፣ በዚህ ስብሰባው እንዲህ ብሏል፣ ሊዘጋን ነው፣ ሊያስረን ነው፣ ሊጨርሰን ነው ከማለት ያለፈ አንድም ቀን በጎ ነገር ስለ መንግሥት የማያነሡ አካላት አሉ»
 ስለዚህ ከዚህ አባባል ተነስተን ልንል የምንችለው ነገር ይህ መንግሥት ሊበላን ነው የሚለው ዜማ እንደስልት የተያዘና መንግሥት በአባላቱ ዘንድ እንዲጠላ የተዘየደ መሆኑ ነው። ከዚያም ባሻገር መሰሪ ስራውን ለመደበቅ ራሱን ጻድቅ አድርጎ በሌሎች ሰዎች ዘንድ ለመሳል የታቀደ ጥበብ ሲሆን ጻድቁ ማኅበረ ቅዱሳንን ኢህአዴግ ሊያጠፋው ስለሆነ ኦርቶዶክሳውያን የሆናችሁ ሁሉ የዚህን መንግሥት መሠሪነት ተመልከቱ ብሎ ክፉ ስዕል ለመስጠት የተፈለገ ብልጠት ነው።
እውነቱ ግን ማኅበረ ቅዱሳን ነጋዴ ድርጅት መሆኑ ማንም ያውቃል። የግል ይሁን የአክሲዮን ማኅበር መሆኑ ያልታወቀና የራሱን ሀብት የፈጠረ ተቋም ስለመሆኑም ስራው ምስክር ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ከንግድ ተቋማቱና ከልዩ ልዩ የገቢ ምንጮቹ ባሻገር የራሱ የሆኑ አባላት ያሉትና የአባልነት መዋጮ የሚሰበስብ ድርጅት ነው። ከዋናው ማዕከል ጀምሮ በቤተ ክርስቲያኒቱ ቁመት የራሱ የሆነ መዋቅርና  ራሱን የቻለ አደረጃጀት ያለው ነገር ግን አደረጃጀቱ በየትኛው የሀገሪቱ  የአደረጃጀት ፈቃድ ላይ እንደቆመ ያልታወቀ መሆኑም እርግጥ ነው። ይህንን የራሱ ተቋማዊ ኅልውና ያለውን ማኅበር በሀብቱ፤ በንግድ ተቋማቱ፤ በመዋቅራዊ አካላቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመቆጣጠርና የማዘዝ ምንም ሥልጣን የላትም።  በአንጻሩም ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስር ተሸፋፍኖ እንደመጠለሉ መጠን ቤተ ክርስቲያኒቱ በማኅበሩ ላይ የመቆጣጠርና የማዘዝ ሥልጣን እንዳላት ግምት ያለው በመሆኑ መንግሥት ይህን ድርጅት ነክቶት አያውቅም። ስለዚህ ይህንን ማኅበር ቤተ ክርስቲያኒቱም፤ መንግሥትም ሳይመለከቱት ከሁለት ወገን ቁጥጥር ነጻ ሆኖ 22 ዓመት ዘልቋል።
 «ለሁሉም ጊዜ አለው» እንዲሉ ሆኖ ማኅበሩን ማነህ? ምንድነህ? የት ነህ? ምን አለህ? ምን አገባህ? የሚሉ ካህናትና የአመራር አካላት ተባብረው በመነሳት መጠየቅ ሲጀምሩ ጥቂት ሟሳኞችና አሟሳኞች ወደሚል ሃሳብ ለመውረድ ተገዷል።  በምንም ደረጃ ያሉ ሰዎች ማኅበረ ቅዱሳንን መክሰስ መቻላቸው የማኅበሩን ማንነት ማሳያው ተግባሩ እንጂ ክሱ አይደለም።  እየተከሰሰ ያለው ማኅበር በተግባሩ ያልታወቀ ማኅበር ባለመሆኑ በሟሳኞችና አሟሳኞች የቃላት ጫወታ እየፈጸመ የቆየውን ሸፍጥ ሸፍኖ ማስቀረት አይቻልም።
ማኅበረ ቅዱሳን በተግባር በሌለው ሥልጣንና መብት መናፍቃን ናቸው ያላቸውን ኢትዮጵያውያንን በራሱ ጥቁር መዝገብ አስፍሮ አስደብድቧል፤ ሰልሏል፤ ስም አጥፍቷል፤ አስፈራርቷል፤ እንዲሰደዱ አድርጓል። ማኅበረ ቅዱሳን በቤተክርስቲያኒቱ ስም መጽሔትና መጻሕፍትን፤ ካሴትና ቪዲዮ፤ አልባሳትና ንዋየ ቅድሳትን ከታክስና ከቀረጥ ነጻ ሆኖ ነግዷል። የማኅበረ ቅዱሳን አቋም የሚቃወሙ ሁሉ ጠላቶቹ ናቸው። የሚደግፉት ደግሞ ጳጳሳቱ ሳይቀሩ ወንጀል ቢኖርባቸው እንኳን የቤተ ክርስቲያኒቱ ታማኝ አገልጋይ ተደርገው ዜና ይሰራላቸዋል፤ ሙገሳ ይሰጣቸዋል። አባ እስጢፋኖስን ማንሳት ይቻላል። ጠላቶቼ ከሚላቸውና ስማቸውን ሌሊትና ቀን ሲያጠፋቸው ከቆዩት ጳጳሳት ውስጥ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ እና ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ደግሞ የጥላቻ የአፍ መፍቻው ናቸው። ሌሎቹም ፈርተው አንገታቸውን ደፍተውለታል። የተገዳደረውን አንገት ያስደፋል፤ አለያም ቀና ካለ አንገቱን ይሰብራል።  ሌላው ቀርቶ ሲያመሰግናቸው የነበሩትን አዲሱን ፓትርያርክ ጠላቶቼ የሚላቸውን ሰዎች ሲቀጣ በቆየበት መልኩ በስም ማጥፋት ቅጣት ናዳውን እያወረደባቸው ይገኛል። ለራሱ ኅልውና ብቻ የሚጨነቅ፤ ካልመሰለው ደግሞ ሲያወድሳቸው ለነበሩት ሳይቀር ግድ የሌለው ማኅበር ስለመሆኑ ከድርጊቱ ተነስቶ መናገር ይቻላል።  ወትሮውንም ሸፋጭ ነጋዴ ገንዘቡን እንጂ ወዳጅና እውነት በእሱ ዘንድ ዋጋ የሌላቸው ስለሆኑ የሚያስበው ጊዜያዊ ትርፉን ብቻ ነው። በዚህ ዙሪያ ማኅበሩ አሸንቅጥሮ የጣለውና ለተቀበለው የእጅ መንሻ በውጪ እንዳለ የሚለፈልፈው ዳንኤል ክብረት ማኅበሩ ስለግለሰቦችና ስለቤተ ክርስቲያኒቱ ደንታ ቢስ እንደሆነ ያጋለጠው እንዲህ ሲል ነበር።
«ዲያቆን በጋሻው ማስተማር የጀመረው መቼ ነው? ማኅበሩ በነዲያቆን በጋሻው ላይ ሃሳብ ዛሬ መሠንዘር ለምን ጀመረ? በጋሻው ለቤተ ክርስቲያን አደጋ ነው ብሎ ስላሰበ አይደለም፡፡ በጋሻው ማኅበረ ቅዱሳንን በተመለከተ ስለ ተናገረ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ምንም ያልተናገረው ማኅበር ስሙ ሲነሣ ቤተ ክርስቲያን ተነካች ብሎ ተነሣ፡፡ ማኅበሩ አቡነ ጳውሎስን በተመለከተ የተለየ አቋም መያዝ የጀመረው መቼ ነው? «እርሳቸው ማኅበሩን ሊያፈርሱ ነው» ብሎ መሥጋት ከጀመረ በኋላ፡፡ አባ ሠረቀንም ቢሆ ንኮ ዛሬ ዛሬ በእምነት ችግር ይከሳቸዋል እንጂ፣ ከእርሳቸው ጋር ያለው ዋናው ችግሩ ማኅበሩ መነካቱ ነው፡፡ አባ ሠረቀ ማኅበረ ቅዱሳንን ሳይነኩ የፈለጉትን ቢሆኑ ኖሮ አይናገራቸውም ነበር፡፡ ባለፈው ጊዜ በቅዱስ ሲኖዶስ ላይ ችግር ሲፈጠር፣ ዝምታን መርጦ የነበረው አመራር የመንግሥት አካላት ከቤተ ክህነቱ ባለሥልጣናት ጋር ሆነው ስለ ማኅበሩ ሲያወያዩት ግን አገር ይያዝልኝ አለ፡፡ የአዋሳ ምእመናንን ችግር በዝምታ ያለፈው አመራር አባ ሠረቀ አንዳች ነገር ተናገሩ ብሎ ድምፁን አሰምቶ ተናገረ፡፡ እነዚህ እና መሰል ሁኔታዎች አመራሩ የሚቆረቁረው ማኅበሩ ሲነካ እንጂ ቤተ ክርስቲያኒቱ ስትነካ አለመሆኑን ያመለክታሉ» ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን ከራሱ በላይ ማንንም እንደማይወድ እርግጥ ነው።
ማኅበረ ቅዱሳን በፖለቲካው ዙሪያ ከምርጫ 97 በፊትም ሆነ በኋላ ስላለው ሁኔታ መንግሥት በቂ መረጃ እንዳለው ይሰማል። በዚህ ዙሪያ መንግሥት ያለውን መረጃ እስኪያወጣ ድረስ የምንለው ነገር የለም። ነገር ግን ማኅበሩ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሲያምሳት መቆየቱን፤ እጁን እያስገባ ሲኖዶሱን ሳይቀር እንደሚጠመዝዝ እናውቃለን። ማኅበሩ ደፋርና የልብ ልብ የተሰማው አንዳንድ የሲኖዶስ አባላት ተጠግቶ የጉባዔ ሃሳብ በራሱ መንገድ እስከመጠምዘዝ የመድረሱን አቅም እየለካ በመሄዱ ነው። ዛሬ ላይ ያ ነገር የለም። ፓትርያርክ ማትያስ ለዚህ የማኅበሩ ሃሳብ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ገና አንድ ዓመት ሳይሞላቸው ከኢህአዴግ ጋር ተመሳጥረው ሊያጠፉኝ ነው እያለ ስም ወደማጥፋት ወርዷል። በተቃራኒው ደግሞ ማንም እንደማያጠፋው በሚገልጽ ጀብደኝነቱ ፓትርያርክ ጳውሎስም እንደዚሁ ሊያጠፉኝ ሞክረው እንደማያዋጣቸው አውቀው አጃቸውን ከእኔ ላይ ለማንሳት ተገደዋል በማለት ለፓትርያርክ ማትያስ የማስጠንቀቂያ ማስታወቂያ እየሰራ ይገኛል። እጅዎን ከእኔ ላይ የማንሳትን ጉዳይ ችላ ሳይሉ ከቀድሞው ፓትርያርክ ትምህርት ውሰዱ በማለት ማሳሰቢያ እየሰጠ መሆኑ ነው። የሚፈራው ከተገኘ ጥሩ ጀብደኝነት ነው፤ ነገር ግን ባለቀ ጊዜ ማላዘን ዋጋ የለውም። ማኅበረ ቅዱሳን ቤተክርስቲያኒቱ ስንት ችግር ባለባት ሰዓት ራሱ ችግር ፈጣሪ ሆኖ ካለቦታው የተገኘ ማኅበር ስለሆነ ተገቢ ቦታውን መያዝ ካለበት ሰዓቱ አሁን ነው። ማኅበረ ካህናቱና የቤተ ክርስቲያኒቱ አመራር አባላት ጠንክሮ መታገል የሚገባችሁ ወቅት ቢኖር ዛሬ ነው። ማኅበሩ ቁጭ ብሎ አዋጭ የሆነውን መንገድ መቅረጽ ካለበት ቶሎ ብሎ ይህንኑ እንዲፈጽም ምክር እንለግሰዋለን። የአክሲዮን ማኅበር፤ የሃይማኖት ተቋም፤ በጎ አድራጊ ድርጅት ወይም የተሻለ ነው ብሎ የደረሰበትን ውሳኔ ወደተግባር መቀየር ካለበት ቀኑ ሳይመሽ በብርሃኑ ይሆን ዘንድ ልናሳስበው እንወዳለን። ሲሆን ዘንድሮ፤ ካልሆነም በቀጣዩ ዓመት፤ ቢረዝም፤ ቢረዝም አንድ ቀን ማኅበረ ቅዱሳን ከቤተ ክርስቲያኒቱ ጉያ እንደመዥገር የተጣበቀበት ቀን እንደሚያበቃ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል። ምክንያቱም ማኅበሩና ተግባሩ፤ ካህናቱና አስተዳደሩ መቼም ቢሆን አሁን ባለው መንገድ አብረው መጓዝ አይችሉምና ነው።  ከዚህ ሁሉ ፓትርያርኩም፤ ካህናቱም፤ አመራሮችም፤ መንግሥትም ይህንን ማኅበር ቦታ የማስያዙን ጉዳይ ችላ ሊሉት አይገባም። ማኅበረ ቅዱሳን ሳይኖር ቤተ ክርስቲያን ነበረች፤ ማኅበረ ቅዱሳን ሳይኖርም ትኖራለች!!!  «ማኅበረ ቅዱሳን ከሌለ ቤተ ክርስቲያን ትጠፋለች» የሚለው ራሱ ማኅበረ ቅዱሳን ብቻ ነው።

Saturday, February 15, 2014

ፓትርያርኩ ማኅበረ ቅዱሳን የጠራውን ሀገራዊ የሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ጉባዔ ማገዳቸው ትክክል ነው!!


«መታገድ» የሚለውን ቃል በአሉታዊ ምልከታ ለማራገብ ካልተሞከረ በስተቀር ባለእባብ ዓርማው ማኅበረ ቅዱሳን የጠራውን ስብሰባ መታገድ በተመለከተ የሚያሳየው  የትርጓሜ እውነታ ግን በትክክለኛነቱ ተቀባይነት ያለው ውሳኔ ነው። ለዚህም ከበቂ በላይ ምክንያቶች አሉን።
1/ ማኅበረ ቅዱሳን የተባለውን ማኅበር ቤተ ክርስቲያኗ ያላቋቋመችውና ከብላቴ ጦር ምላሽ በጎ ፈቃደኞች የመሠረቱት ሲሆን የቤተ ክርስቲያኗ የውክልና ድርሻ ስለሌለው የትኛውንም የቤተ ክርስቲያን አባል በመጥራት መሰብሰብ አይችልም።
2/ ማኅበረ ቅዱሳን በጥቂት ደጋፊዎቹ ተነስቶ የሲኖዶስ አባል የሆኑትን ጳጳሳት በመጠምዘዝ፤ በማስፈራራትና በጥቅማ ጥቅም በማታለል ለራሱ ብቻ የሚጠቅመውን መተዳደሪያ ደንብ በማስጸደቅ ቤተ ክርስቲያንን ተለጥፎ በሕይወት ለመቆየት ከመቻሉ በስተቀር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንደልማት ማኅበር ወይም እንደ በጎ አድራጊ ድርጅት ወይም እንደመንፈሳዊ ተቋም የመሠረተችው አይደለም። ስለዚህ አሀዳዊትና ሐዋርያዊት በሆነችው የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሌላ ማኅበር ሊኖር ስለማይገባው ማኅበረ ቅዱሳን ማንንም የቤተ ክርስቲያን አባል በማደራጀት መንቀሳቀስ አይችልም።
3/ ቤተ ክርስቲያኒቱ ከቅዱስ ሲኖዶስ አንስቶ በሊቃነ ጳጳሳት የሚመራ የሀገረ ስብከት ጽ/ቤቶች በተዋረድ ያላት ተቋም ሆና ሳለ በሽብልቅ የገባው ማኅበር ይህንን የመዋቅር ሰንሰለት በጥሶ ለራሱ ዓላማና ግብ በመንፈሳዊ ካባ ተጠልሎ ስብሰባ የማካሄድ፤ የመጥራት፤ የማደራጀት፤ የመምራት ስልጣን የለውም።

4/ ማኅበረ ቅዱሳን በልማት ማኅበር ወይም በእርዳታ ድርጅት ወይም ራሱን በቻለ መንፈሳዊ ተቋምነት ወይም በሌላ መሰል ስያሜ የሀገሪቱ ሕግ በሚፈቅደው አግባብ እውቅና አግኝቶ የተፈቀደለትንና የሚችለውን ሀገራዊና መንፈሳዊ ዓላማ ከማከናወን በስተቀር በሲኖዶስና በማኅበር የሚመራ ሁለት አስተዳደር ቤተ ክርስቲያኒቱ መሸከም የለባትም። ስለሆነም የፓትርያርኩ እግድ የስልጣን ተዋረድንና ኃላፊነትን ያገናዘበ በመሆኑ ትክክለኛ ውሳኔ ነው።
5/ ለወደፊትም ቢሆን ቁርጡ በታወቀ ቁመና የማኅበረ ቅዱሳን ማንነት መታወቅ አለበት። ስለሆነም እጅ እየጠመዘዘ ያስጸደቀው መተዳደሪያ ደንብ ቀሪ ሆኖ በራሱ ግዘፈ አካል፤

   ሀ/ በሰንበት ትምህርት ቤቶች አወቃቀር የቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ማኅበር ለመሆን ከፈለገ ያለውንና ያፈራውን ሀብትና ንብረት ለቤተ ክርስቲያኒቱ በማስረከብ ለሰንበት ተማሪዎች በተሰጠው የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማዊ መመሪያ መሰረት መተዳደር አለበት።
  ለ/ የሰንበት ትምህርት ቤቶችን ለማደራጀት በወጣው ህገ ደንብ የመተዳደር ፈቃደኝነቱ ከሌለው የአባልነት ምልመላ፤ የገንዘብ አቅምን የማጎልበት፤ አስተዳደራዊ መዋቅሩን የመዘርጋትና የማንነት አቅም ማጎለበቱ ከቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ውጪ የመሆን አዝማሚያ እንዳለው እያየን ነውና ሀገሪቱ በምትሰጠው መብት በፍትህ ሚኒስትር ተመዝግቦ ሊንቀሳቀስ ይገባዋልና ቅዱስ ፓትርያርኩ የጀመሩትን መልክ የማስያዝ ጅማሮ ከፍጻሜ እንዲያደርሱ እንጠይቃለን።

Saturday, January 18, 2014

የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት በ1994 እና በ1995 ዓ/ም በአንጻራዊነት የተሻለ የአስተዳደር ዘመን ነበረው!



ከመሪጌታ ይኄይስ ተአምኖ፤  ኩቤክ- ካናዳ

እንዲህ እንደዛሬው ሳይሆን የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅ ማለት በሀ/ስብከቱ ውስጥ የፈለገውን ማድረግ የሚችል ሹመኛ ማለት ነው። ከ1992 ዓ/ም  ጥቂት ቀደም ብሎ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የሊቀ ካህናት ብርሃኑ ገ/አማኑኤል ሥራ አስኪያጅነትና (ነፍሱን ይማረውና) የዮሐንስ ዋለ ዘመን እንዳበቃ፤ ከቤተ ክህነቱ ሙያ ውጪ የሌላ ሙያ ባለቤት ያልሆኑትና የተለየ ሥራ እንዳላቸው የማናውቅላቸው ነገር ግን በአድዋና በመቀሌ  ትልቅ ኢንቨስትመንት ያላቸው አለቃ መኮነን ገ/መድኅን የሥራ አስኪያጅነቱን ኃላፊነት ከተረከቡ በኋላ ሙስናው ያለማስታወቂያ መደበኛ የስራ መስክ ሆኖ እንደነበር የምናውቅ ሰዎች የምንዘነጋው አይመስለኝም።

  እንደዚያም ሆኖ አለቃ መኮነን ገ/መድኅን ጎበዝ የአስተዳደር ሰው ናቸው። በዚያ ላይም ባመኑበት ጉዳይ ደፋርና ወደኋላ የማያፈገፍጉ ጠንካራ ሰው ስለመሆናቸውም መጥቀሱ ተገቢ ይመስለኛል። በወቅቱ ፀሀፊ የነበረውና አሁን በአሜሪካ በታክሲ ሾፌርነት የሚሰራው ክነፈ ርግብ ሐጎስ ፈጣንና ከዓይን ላይ የሚነጥቅ ቀልጣፋ እንደመሆኑ መጠን የሚበቃውን ገንዘብ መሰብሰብ ችሎ እንደነበር የምናውቅ እናስታውሳለን። እንደዛሬው የጉቦው የጨረታ መነሻ ዋጋው ከፍ ሳይል በፊት ለጉቦው በተሰጠው የሀ/ስብከቱ ምሥጢራዊ መጠሪያ ሥም ማለትም «ሥላሴ ስንት ናቸው? ከተባለ መልሱ «አንድም ሦስትም ናቸው» ማለት ሲተረጎም ክፍያው ከአንድ ሺህ እስከሦስት ሺህ ይደርሳል ማለት ሲሆን «አምስቱ አዕማደ ምሥጢር» ከተባለ ደግሞ «እስከ አምስት ሺህ»፤ ሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ከተባለ ደግሞ « እስከ ሰባት ሺህ ብር» ጉቦ ይጠየቃል ወይም ይከፈላል ማለት ነበር። ዛሬን ወደኋላ መለስ ብዬ ሳየው በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ሽፋን የጉቦ መቀበያ ተመንን በቁጥር የማስቀመጥ መጥፎ ልምድ መነሻው እምነትን ለገንዘብ የማዋል ምሥጢራዊ ክህደትና ማላገጥ እየተስፋፋ የመምጣቱ ምልክት መሆኑን ያመላከተ እንደነበር ነው። እምነት ከሰዎች ውስጥ እየጠፋ በመጣ ቁጥር እምነቱ ለሥም መጠሪያ ይሆንና በተግባር ግን ወደሸቀጥነት ይለወጣል ማለት ነው። ጌታችንንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በቤተ መቅደሱ ደጃፍ ሲሸጡና ሲለውጡ የነበሩትን በሃይማኖት ስም የመጡ ነገር ግን እምነቱን የመሸቀጫ መድረክ ያደረጉትን ሰዎች የገለጸበት መንገድ ተመሳሳይ ነበር። 

«የአይሁድ ፋሲካም ቀርቦ ነበር፥ ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ።በመቅደስም በሬዎችንና በጎችን ርግቦችንም የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ፤ የገመድም ጅራፍ አበጅቶ ሁሉን በጎችንም በሬዎችንም ከመቅደስ አወጣቸው፥ የለዋጮችንም ገንዘብ አፈሰሰ ገበታዎቻቸውንም ገለበጠ፥ ርግብ ሻጪዎችንም። ይህን ከዚህ ውሰዱ፤ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት አላቸው።ደቀ መዛሙርቱም። የቤትህ ቅናት ይበላኛል ተብሎ እንደ ተጻፈ አሰቡ» ዮሐ2፤13-17 

ዕለተ ፋሲካ ቀርቦ ሳለ የሃይማኖት ሰዎች ሸቀጥ በመቅደሱ ደጃፍ ከትንሿ እርግብ እስከ ትልቁ በሬ ድረስ ሲሸጥ እንደነበር ቅዱስ ወንጌል ይነግረናል። ዛሬም እንደ ቃሉ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የነዋይ ፋሲካቸውን የሚያከብሩ ሞልተዋል። ከነጋዴውና ሸቃጩ ማኅበረ ቅዱሳን አንስቶ በሥራ አሥኪያጅነት ዘመናቸው ባርከውና ቀድሰው ጉቦውን ያስፋፉት አባ እስጢፋኖስ፤ ታሪክ ራሱን ይደግማል እንዲሉ ዛሬም ቤተ መቅደሱ ደጃፍ ላይ ተኮልኩለው አዋጭ ያሉትን የጥናትና ስትራቴጂ ገበያ ዘርግተው ለመሸጥ እያስማሙ መገኘታቸው ብዙም ላያስገርም ይችላል። በእምነት ሥም በዐደባባይ መሸጥ፤ መለወጥ ሲያያዝ የመጣ ነውና ብዙም ግር አያሰኝም።  ዛሬም ድረስ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ውስጥ ሸቃጮቹ መልካቸውን እየለዋወጡ መነገዳቸውን አላቆሙም። «የቤትህ ቅናት በላኝ» ለማለት በመጀመሪያ የንግድ ሂሳቡን ዘግቶ ወደኋላ የሚጎትተውን ብዙ ሀብት ትቶ ሊመጣ ይገባል እንጂ ስሜትና አፍን አስተባብሮ ነፍስያን በማባበል ማንንም ማታለል እንደማቻል ግን እንነግራቸዋለን።

«እርሱም በመንገድ ሲወጣ አንድ ሰው ወደ እርሱ ሮጦ ተንበረከከለትና። ቸር መምህር ሆይ፥ የዘላለም ሕይወትን እወርስ ዘንድ ምን ላድርግ? ብሎ ጠየቀው። ኢየሱስም፦ ስለ ምን ቸር ትለኛለህ? ከአንዱ ከእግዚአብሔር በቀር ቸር ማንም የለም።ትእዛዛትን ታውቃለህ፤ አታመንዝር፥ አትግደል፥ አትስረቅ፥ በሐሰት አትመስክር፥ አታታልል፥ አባትህንና እናትህን አክብር አለው። እርሱም መልሶ፦ መምህር ሆይ፥ ይህን ሁሉ ከሕፃንነቴ ጀምሬ ጠብቄአለሁ አለው። ኢየሱስም ወደ እርሱ ተመልክቶ ወደደውና። አንድ ነገር ጐደለህ፤ ሂድ፥ ያለህን ሁሉ ሽጠህ ለድሆች ስጥ፥ በሰማይም መዝገብ ታገኛለህ፥ መስቀሉንም ተሸክመህ ና፥ ተከተለኝ አለው። ነገር ግን ስለዚህ ነገር ፊቱ ጠቈረ፥ ብዙ ንብረት ነበረውና እያዘነም ሄደ» ማር 10፤17-22

ሀብትና ንብረታቸውን እያከማቹ «የቤትህ ቅናት በላኝ» ቢሉ ሁሉን ዐዋቂ ፈጣሪን ቀርቶ በዓይን የምናያቸው እኛን ሊታልሉ ከቶ አይችሉም። የገነቡትን የመኖሪያ ቤት ለቤተ ክርስቲያናቸው ይስጡ፤ ከመቅደሱ ደጃፍ የተገተረውንም ህንጻ የተወደደ መስዋዕት እንዲሆንላቸው ለቤተ መቅደስ መባዕ ይስጡና ስለ ቤቱ ቅናቱ   ይንገሩን። ያኔም ምሳሌ የሚሆነውን ሥራቸውን ዐይተን እንደነዚህ ዓይነቶቹን ቤተ ክርስቲያን ትፈልጋቸዋለች ብለን ምስክርነታችንን እንሰጣቸዋለን።
   ከዚያ ባሻገር የወጣቱን ሀብታም ታህል  «አታመንዝር፤ አትስረቅ፤ አታታልል፤ በሀሰት አትመስክር» የሚለውን ትዕዛዛት ከህጻንነታቸው ጀምረው ማክበር ስለመቻላቸው አፋቸውን ሞልተው ለመናገር የማይችሉ «የቤተ መቅደሱ ቅናት በላኝ» ቢሉ ማን ያምናቸዋል? ሌላው ቀርቶ ማኅበረ ቅዱሳን  የቤተ መቅደሱን ደጃፍ ሰናዖር ህንጻውን መባዕ አድርጎ ሊሰጥ ይቅርና ቤተ ክርስቲያን ሂሳብህን ኦዲት ታድርግህ፤ በቤተክህነቱም ሰነድ ገቢህን ሰብስብ፤ ሲባል በሕጋዊ የውጭ ኦዲተር አስመርምሬአለሁና የምሰጣችሁ ወረቀት በቂያችሁ ነው በማለት አቅሙም፤ ሥልጣኑም የላችሁም በማለት ማናናቁ ብቻ የማንነቱ ምሥክር ነውና ወቅታዊውን ችግር ተመልክቶ የራስን አጀንዳ ማስፈጸም አግባብ አይደለም።
  ወደ ርዕሰ ጉዳያችን ስንመለስ በ1994 ዓ/ም  አለቃ መኮነን ገ/መድኅን የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅነቱን ጨርሰው ለስድስት ወር ገደማ የወረቀት ራስጌና ግርጌ የማይለዩት፤ የማኅጸንቱ ልጅ ሥራ አስኪያጅነቱ እንደለቀቁ፤ በወቅቱ ከአሜሪካ የተመለሱት አባ ተከስተ ብርሃን ወ/ሳሙኤል / በኋላም አባ ሳሙኤል ሊቀ ጳጳስ/ መረከባቸው ይታወሳል።  ፀሀፊ የነበረው ክነፈ ርግብ ሐጎስም የዞረ ሂሳቡን በአባ ማኅጸንቱ በማስጨረስና የሚሸመጥጠውን ጨራርሶ በአጋጣሚ ያገኛትን ኢትዮጵያዊ አሜሪካዊትን አግብቶ ወደአሜሪካ ኮበለለ።
   አባ ተከስተ ብርሃን የወቅቱ ሥራ አስኪያጅ ሆነው በትኩስና ባልተበረዘ ስሜት በሀ/ስብከቱ ውስጥ ተንሰራፍቶ የነበረውን ሙስናና ቤተሰባዊ ተቋም ለመናድ ጊዜ አልፈጀባቸውም። የካህናት አስተዳደሩን መጋቤ ሃይማኖት ጸገየን፤ የትምህርትና ስብከተ ወንጌል ኃላፊውን ርዕሰ ደብር መሀሪን፤ የአስተዳደር መምሪያ ኃላፊውን (ነፍሱን ይማረውና) ኃይሉ ማርቆስን፤ ከወረዳ ቤተ ክህነት ወደ ፀሀፊነት የተዛወሩት አፈ መምህር ገ/ዮሐንስን፤ ከብዙ ድካምና ጥረት በኋላ ደ,ግሞ ወ/ሮ ሣራ ገ/ሥላሴን፤ ወ/ሮ ኢትዮጵያ ክፍሌን የመሳሰሉትን የማይገፉ ተራሮች አንድ በአንድ ለመናድ በመቻላቸው ትልቅ ስም ለመገንባትና በበታቾቻቸው ላይም የማይቻሉ ሰው የመሆናቸውን ተፅዕኖ ማሳደር ችለው ነበር።
 ከላይ የተዘረዘሩት ሰዎች በአንድም ሆነ፤ በሌላም ምክንያት ከበላይ ባለሥልጣናት በተለይም (ነፍሳቸውን ይማርና) ከወቅቱ ፓትርያርክ ከአቡነ ጳውሎስ ጋር ግንኙነት የነበራቸው ስለነበሩ እንደዚህ ዓይነቶቹን ሰዎች ከያዙበት ስኳር ከሆነ ሥልጣን ላይ ማስነሳት የሚታሰብ ባለመሆኑ የአባ ተከስተ ብርሃን ወ/ሳሙኤል ግንባር እድለኛ ስለነበር ይሆናል ወይም በበላይ አካል በኩል ተሰሚነት ያገኙ እንደነበሩ መገመት ይቻላል።  ይህም የስምና የኃይል ግንባታ ብቃት በበታቾቻቸው ላይ ፍርሃት በማንገሱ ትእዛዞቻቸው ሁሉ ተፈጻሚ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል። 
በእርግጥም ቀደም ብሎ ከእነ አባ ኃ/ማርያም ዘመንና ከወዲህም በእነ ሊቀ ካህናት ብርሃኑና ዮሐንስ ዋለ በኋላም በአለቃ መኮንንና ክነፈ ርግብ ሐጎስ አስተዳደር ጊዜያት ውስጥ ሀ/ስብከቱ ተጨመላልቆ ስለነበር የአባ ተከስተ ብርሃን ወ/ሳሙኤል አዲስ የአወቃቀር መንፈስ ተስፋን መፈንጠቁ የሚጠበቅ ነው።  ደግሞም ከእነድክመቶቹ በወቅቱ የአዲሱ ሥራ አስኪያጅ ቀናና ትኩስ መንፈስ ብዙ ድጋፍ ከካህናቱ ወገን አግኝቶም ነበር።
  መረን የለሽ የግል ጋዜጦች የቤተ ክህነቱን ገመና ሳይዙ የሚወጡበት ቀን አለ ለማለት አይቻልም ነበር። ይህም በብዙ መልኩ ቀንሶ የተገኘው በአባ ተከስተ ብርሃን ሥራ አስኪያጅነት ወቅት ለመሆኑ የሚዘነጋ አይደለም። በተለይም በ1994 እና በ1995 ዓ/ም በይበልጥም አባ ተከስተ ብርሃን የሊቀ ጳጳስነቱን ሥልጣን ከማግኘታቸው በፊት የነበረው የሀ/ስብከቱ አስተዳደር በአንጻራዊነት ሲታይ በሀ/ስብከቱ ታሪክ ከመቼውም ጊዜ የተሻለ እንደነበር አይካድም። የዚህ ጽሁፍ አቅራቢም ይህንኑ ይመሰክራል።


 አባ ሳሙኤል ሊቀ ጳጳስ ከሆኑም በኋላ ጥቂት ለማስቀጠል ሞከረው ነበር። ነገር ግን ቀደም ሲል የነበራቸውን የመልካም ስራ መንፈሳቸውን ማን እንደቀማቸው ሳይታወቅ፤ በፓትርያርክ ጳውሎስ ፊት የነበራቸውንም ግርማ ሞገስ እየሸረሸረ የወሰደው ነገር ሳይገለጥ ሀ/ስብከቱን ማስተዳደር ትተዋል በሚባል ደረጃ ወደ መርሳት ደርሰው ነበር። ምናልባትም ሥራ የአስኪያጅነቱን ዘመን የተጠቀሙት ወደሥልጣን የመሸጋገሪያ ስልት አድርገውት ይሆን? የሚል ጥያቄ የሚያስነሳው ሥራ አስኪያጅ ሳሉ ከነበሩበት ዘመን የተሻለ ሥልጣን ሲይዙ የበለጠ መስራት እየቻሉ ለመስራት አለመፈለጋቸው ፍንጭ ሊሰጠን ይችላል። ከዚያም በላይ አብረውአቸው የሚውሉትንና የሚወርዱትን ሰዎች ማንነት ስንመለከት በወቅቱ በትክክለኛ የኅሊናቸው መስመር ላይ እንዳልነበሩ ያረጋገጠ ማረጋገጥ ችለናል።

  ከሀ/ስብከቱ ሽያጭ ክፍል ተነስቶ ወደሥራ አስኪያጅነት ያደገው መሪጌታ መኩሪያ ደሳለኝ ከያዘው በኋላ የሀ/ስብከቱ የአስተዳደር ዘመን ሳይሆን የሞት ዘመኑ ሆኖ ተተክቷል። የተገነባው መልካም አወቃቀርና አስተዳደር እምጥ ይግባ ስምጥ ሳይታወቅ በአፍ ጢሙ ተደፋቷል። በተመሳሳይ መልኩ ሊቀ ጳጳስ ሳሙኤል መተንፈሻ እስኪያጡ ድረስ ከረቫት ባሰሩ አሸርጋጅ ፀሐፊዎች፤ ራሳቸውን ባልሰበኩ ሰባኪዎች፤ በሙዳየ ምጽዋት ገልባጭ አስተዳዳሪዎች ተከበው በውዳሴ ከንቱ መከራቸውን ያዩ ነበር። ሃይማኖት የለሹ ዘሪሁን ሙላቱ (ዛሬም በየመድረኩ ሃይማኖት እንዳለው ሰው ያናፋል) ቀኝ እጃቸው ሆኖ አለሁልዎ ሲላቸው መጨረሻውን ለማየት እንመኝ ነበር። የዛሬው የቦሌ መድኃኔ ዓለም ፀሀፊ ሰሎሞን በቀለ የካዝናውን ቀበኛ አይጥ ይዘው ሲጓዙ ለተመለከተ አጀብ የሚያሰኝ ነበር። የባሌ ጎባው አጭበርባሪ ሰሎሞን ቶልቻ (ቄስ ነኝ ይላል)፤  የቅድስት ማርያሙ ሰንበት ተማሪ ሡራፌል ወንድሙ (እሱም አሁን አሜሪካ ገብቶ ቄስ ነኝ ይላል) የመሳሰሉት ሁሉ እንደበረዶ ናዳ የሚሟሙ ወዳጆችን አፍርተው አይተን የሚቀልጡበትን ቀን ስንጠባበቅ ነበር።

  ጉዳይ የሚፈጸመው በስልክ ወደመሆን ተቀይሯል። በጉድ ሙዳዩ አባ አብርሃም በኩል የሚቀርቡ ተቀጣሪዎች ውጤታማ መሆናቸውም የታየበት ወቅት ነበር። ባለ ጉዳይ፤ ጉዳይ የለሽ ሆኗል። የአድባራትና ገዳማት ምዝበራ ከመቼውም ጊዜ በላይ ገኗል። ከስራ የሚባረር፤ አላግባብ የሚዛወር፤ ከደረጃው የሚወርድ በርክቷል። ፍርድ ቤቶችን የቤተ ክህነት አቤቱታ አሰልችቶታል። ብዙ ችግሮችና የሥልጣን ሽኩቻዎች ተበራክተው የሀ/ስብከቱ አስተዳደር ግብዓተ መሬቱ ሊፈጸም ሲል ከአባ ጳውሎስ ጋር የጠለቀ ክርክር ሲነሳ ጎራው ይለይ ጀመረ። ዘመቻው ሁሉ ፈልቶ፤ ገንፍሎና ቀዝቅዞ የሆነው ሁሉ ሆነ።  በተለያየ ጊዜ ከሀ/ስብከቱ ያስቀየሯቸው ሰዎች አባ ሳሙኤልን መዋጋት ዛሬ ነው በማለት ጦር ሰበቁ። አየር ላይ የተንሳፈፉት እነአባ ዕዝራ በጀት መደቡ። እነኤልዛቤል እጅጋየሁም እንደጉዲት ተፋለሙ። አባ ሳሙኤልም ብቻቸውን ቀርተው፤ ብቻቸውን ተዋግተው ዘለቁ። ሁሉም ጥጉን ይዞ «ያመኑት ፈረስ በደንደስ» እንዲሉ ያመኗቸው ሁሉ ከዱ። አባ ሳሙኤል ሀ/ስብከታቸውን በአግባቡ የአስተዳደር ማዕከላዊነት ይዘውት ቢሆን ኖሮ አንድ ጊዜ ለዐራት፤ ሌላ ላንድ ሲጠቀለልና ሲፈታ ባልኖረም ነበር። እንደጀመሩት ለመጨረስ አልቻሉም።

  ዛሬስ? ዛሬ ያለፈውን ስህተት ሲደገም ማየት የባሰ ያሳምማል። አባ እስጢፋኖስ ያንን ስህተት እየደገሙት ነው። ማኅበረ ቅዱሳንና ተላላኪዎቹ ከኋላ ሆነው ሀ/ስብከቱን እያስተዳደሩት መገኘታቸው እርግጥ ነው። እኛ የምንለው ራሳችሁን ሁኑ ነው። ሌሎችን ተደግፋችሁ የራሳችሁን ገመና ለአጋልጦ ገላጭ አትስጡ ነው። እውነት መናገር ካስፈለገ ካህናቱ የማንንም አባቶች ገመና አደባባይ ማውጣት አይፈልጉም፤ አይወዱምም። ችግሩ ያለው ከራሳቸው ከባለገመናዎቹ ሲሆን ገመናቸውን እንደድመት ሽፍን አድርገው መያዝ ያቅታቸውና ያለቦታቸው ተገኝተው እንዲገለጥላቸው አርፎ የተኛውን ካህን በግድ ይነካኩታል።  አፄ ቴዎድሮስን እልክ ያጋባቸውና እስከሞት ያደረሳቸው የካህን አድማ ነው። አባ እስጢፋኖስም አዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ያለማኅበረ ቅዱሳን ውሻል ማስተዳደር አልቻሉበትም። በእልኽ ቤት አይገነባምና በእልኸኝነት ሁሉን ከግብ አደርሳለሁ ማለቱን ትተው ሀ/ስብከትን ለቀው አንዱን፤ ጅማዎትን ለዚያውም ከቻሉ እስኪ እሱኑ በደንብ ያስተዳድሩ ምክሬ ነው!!

Monday, January 13, 2014

ጦርነቱ በማጣጣር ላይ ባለው የማኅበረ ቅዱሳን አልሞት ባይነትና እጁን ለመስጠት በተዘጋጀው የቤተ ክህነት ባለሥልጣናት መካከል ነው!!!



እንደወትሮው ስለማኅበረ ቅዱሳን የምናትተው ሰፊ ጽሁፍ የለንም። ማኅበሩ እያጣጣረ ነው። ለጊዜው ትንሽ መቆየቱ የእድገት መጨረሻውን አያስቀጥለውም።  ይሁን እንጂ ይህ የብላቴ ትራፊ «አንዲት ጥይት ወይም ሞት» በማለት የጥንት ቃል ኪዳኑን ለማደስ እየተንፈራገጠ ነው።
ለዚህም በመሞትና በመዳን መካከል እየተንፈራገጠ ያለው ማኅበረ ቅዱሳን ራሱን ለማዳን እየታገለ ይገኛል። ለመዳን የሚያደርጋቸውን ትግሎች በአጭር በአጭሩ በነጥብ ሲቀመጡ ይህንን ይመስላሉ።


1/ በሙስናና በአስተዳደር ብልሹነት ሊጠየቁ የሚገባቸው አስተዳዳሪዎችና ፀሐፊዎች አዲሱን ስልቴን እየተቃወሙት ነው በማለት ራሱን ደብቆ ለቤተ ክህነት የለውጥ ማሻሻያ ህግ አያስፈልጋትም የተባለ አስመስሎ ማሳየት ይፈልጋል።

2/ ህጉ ከየትምና ከማንም ይመንጭ ለቤተ ክህነት ስለማስፈለጉ ብቻ እንተማመን በማለት የሕጉን ምንጭ ማንነት እንዳይገለጥ በአስፈላጊነቱ ስር ሸሽጎ ለማስቀጠል ይፈልጋል።

3/ ከአባ አማቴዎስ፤ ከአባ ሉቃስ፤ ከአባ እስጢፋኖስ እና ለጊዜው ስማቸው መጥቀስ ከማንፈልጋቸው ሌሎች ጳጳሳት ጀርባ ተጭኖ የህጉን አስፈላጊነትን በማጦዝ ሲኖዶሳዊ ለማስመሰል በትጋት ይሰራል።

4/ ስለህጉ እጹብ ድንቅነትና ትንግርታዊነት በመረጃ መረብና በስመ ነጻ ሚዲያ ጋዜጦች ላይ በመለፈፍ የምርጫ ዓይነት ቅስቀሳውን በህዝብ ውስጥ በማስረጽና በጳጳሳቱ መካከል የወደፊት በል  ዘመቻውን ለማስቀጠል  ድፍረት የሚሆናቸውን ኃይል በማስታጠቅ ላይ ተጠምዷል።

5/  በካህናት ሽፋን፤  የጥምቀት ተመላሾችንና የተወሰኑ አባላት ምእመናኑን በማሰለፍ በፓትርያርኩ ላይ ጫና በማሳደር የሰማይ ተሰበረ ሽብሩን በመንዛት ላይ ላይ ይገኛል።
እነዚህ ከብዙ በጥቂቱ የተዘረዘሩት እስትንፋሱን የማስቀጠል ዘመቻው ጊዜ ከሚገዛለት በስተቀር በፍጹም ሊታደጉት አይችሉም። ምክንያቶቹ፤
ሀ/ በቤተ ክህነት አጠቃላይ መዋቅራዊ ማሻሻያና የለውጥ እስትራቴጂ ጥናት አስፈላጊነትን የተቃወመና የሚቃወም ማንም የለም። ሊቃወምም አይችልም።

ለ/ የለውጥ ጥናቱ መምጣት ያለበት  ከሲኖዶስ ውስጥ የሚመነጭ ሆኖ በሊቃውንቱ፤ በምሁራኑ፤ በካህናቱ፤ በአዋቂዎቹና በህግ ባለሙያዎች የሚዘጋጅ እንጂ ከማኅበረ ቅዱሳን ጡንቻ ነጻ የመሆን አቅምና ጠባይ በሌላቸው አባ እስጢፋኖስ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ላይ የማዘዝ ስልጣንን ያገኙትን አጋጣሚ በመጠቀም  ዓላማን የማስፈጸም ግብ ሊሆን አይችልም።

ሐ/ በመሰረቱ ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያኒቷ ምኗም አይደለም። ቤተ ክርስቲያን ነጋዴ አይደለችም። እሱ ግን የሚታይ የሚጨበጥ የንግድ ተቋም ያለው ግልጽ ነጋዴና አትራፊ ድርጅት ነው። በዐውደ ምሕረቷ ላይ የሚነግድ ይህ ድርጅት የንግድ ጠረጴዛው መገልበጥ አለበት። በጅራፍም ሊባረር የተገባው ነው። ስለዚህ በምንም ዓይነት መልኩ ወርቅና አልማዝ አቅርቤአለሁ ቢል ተቀባይነት ሊኖረው አይችልም።

መ/ ማኅበረ ቅዱሳንን የሚደግፉ ሊቃነ ጳጳሳት በግልጽ ቋንቋ ስንናገር፤

ሀ/ በቤተ ክርስቲያኗ ሕግና ደንብ መሰረት ለጵጵስና የሚያበቃ ሥነ ምግባር በጭራሽ የሌላቸው ናቸው።

ለ/ በዘር ፖለቲካ የተለከፉና ኢህአዴግ እንደጉም ተኖ፤ እንደጢስ በኖ  ይጠፋ ዘንድና  የራሳቸውን ሥርወ ቤተ ክህነት ለመትከል የሚናፍቁ ናቸው።  ከዚህ የወጣ  ደጋፊ የለውም።
በተለይ አባ እስጢፋኖስ ለማኅበሩ ጥብቅና የመቆማቸው ነገር በፍቅሩ ስለተቃጠሉ አይደለም።  ጵጵስና ስሙና ታሪኩ ክብር ያጣው ጸሊማን አርጋብ በምግባር /ጥቋቁር እርግቦች/ የሆኑ ቦታውን ከወረሩት በኋላ ነው። አባ እስጢፋኖስ ኮተቤ ያሰሩት የሚሊዮን ብሮች ግምት ቤታቸው የተሰራው በደመወዛቸው ነው?  መነኩሴ እናቱም አባቱም ቤተ ክርስቲያን ናት ስለሚባል እስኪ ለቤተ ክርስቲያን የውርስ ኑዛዜ ይስጡ!!
ስለዚህ እስትራቴጂ፤ ጥናት፤ ስብሰባ፤ ተቃውሞ፤ ስነ ምግባር፤ ሙሰኛ ወዘተ በሚሉ የቃላት ማደናገሪያ ቤተ ክህነቱ እጁ ሲጠመዘዝ አሜን ማለት የለበትም። አካፋን አካፋ ማለት የሚገባው ወቅት ቢኖር አሁን ነው። ቤተ ክህነት ችግሮቿን ታውቃለች። ለችግሮቿም መፍትሄ ማመንጨት አይሳናትም። የወላድ መካንም አይደለችም። ስለዚህ በፓትርያርኩ አመራር ከራሷ ልጆች በወጣ ህግ ለችግሮቿ መፍትሄ መስጠት አለባት እንጂ በማመልከቻና በደጋፊ ብዛት መጠምዘዝ አይቻልም። 
የማኅበረ ቅዱሳን ስፍራው መናገር ካስፈለገ ሼር ካምፓኒ/ የአክሲዮን ማኅበር መሆን ብቻ ነው። አዲዮስ ማኅበረ ቅዱሳን ከማለት ውጪ በዚህ ማኅበር ስንታመስ መቆየት ያብቃ!!  በዚህ ማኅበር ዙሪያ ከቤተ መንግሥቱ የተሰማውን መረጃ በሌላ ጽሁፍ ይዘን እንመለሳለን።

Thursday, January 2, 2014

ከፈረሱ ጋሪው የቀደመበት በማኅበረ ቅዱሳን የቀረበው የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት አዲሱ ጥናት!



ማኅበረ ቅዱሳን ባልታጠበ እጁ የመቅደሱን አገልግሎት ለመናኘትና የአስተዳደሩን ወንበር ለመጨበጥ ላይ ታች ማለት የጀመረው ገና አቡነ ጳውሎስን ገፍቶ እስከሞት ድረስ ከመታገሉ አስቀድሞ ነው። ተላላኪ ጳጳሳቱን ካሰማራ በኋላ በአዋጅ ባለባቸው ህመም ሳቢያ እንደሞቱ የሚነገርላቸው እና በውስጥ አዋቂዎች ደግሞ ከህመሙ ባሻገር የሰው እጅም አለበት የሚለውን  የስውር አካሄድን ይትበሃል የተመለከተ የአቡነ ጳውሎስ ኅልፈት  ከመድረሱ በፊት ማኅበሩ ራሱን ከሰንበት ት/ቤቶች መምሪያ ነጻ በማውጣት በቀጥታ ተጠሪነቱ ለሲኖዶሱና ለሥራ አስኪያጁ እንዲሆን ነጋሪት አስመታ። ከዚህ አዋጅ በኋላ ማኅበረ ቅዱሳን የማይደፈር፤ የማይነካ የቤተ ክህነቱ አንበሳ ሆነ።  በግንቦቱ የ2004 ዓ/ም  ሲኖዶስ ላይ ይህንን አስወስኖ ድል በድል በሆነበት ዋዜማ ሟቹን ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እንዲህ ብለን ነግረናቸው ነበር።
«አመኑንም አላመኑም ፓትርያርክ ጳውሎስ፤አንድ ነገር አስረግጠን እንነግርዎታለን። በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው» ብለን ነበር። [1]
እንዳልነውም ይህንን ከተናገርን ከሁለት ወራት በኋላ አቡነ ጳውሎስ ወደማያልፈው ዓለም ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ሄዱ። ነብይ ስለሆንን ወይም ከሰው የተለየ ራእይ ስለመጣልን አልነበረም። በወቅቱ የነበረው የማኅበሩና በገዛ እጃቸው ጰጵሰው የጥላቻ ፈረስ ያሰገራቸው ጳጳሳት አካሄድ ጤናማ ስላልነበር አንድ ነገር ሊመጣ እንዳለ ይጠቁመን ነበርና ነው። ያልነውም ሆነ። ማኅበሩም ተደላድሎ ቤተ ክህነቱን ያዘ። ከእንግዲህ ምን ቀረው ማለት ነው? ቤተ መንግሥቱ? በዚህ ዙሪያ በሌላ ርእስ እንመለስበታለን።

 አሁን አንድ ነገር እዚህ ላይ አስረግጠን በመናገር ወደርእሰ ጉዳያችን እናምራ።
ጳጳሳቱ አንድም በራስ የመተማመን ጉድለት ባመጣው ፍርሃት ለማኅበሩ አጎብድደዋል፤ በሌላም አንድ ምክንያት ግለ ነውራቸውን አደባባይ እንዳያወጣ የበደል ምርኮኝነታቸውን አስበው ራሳቸውን ለማኅበረ ቅዱሳን አሳልፈው ሰጥተዋል። ይሁን እንጂ፤
«አመናችሁም፤ አላመናችሁም እናንተም የአባ ጳውሎስን የጥላቻ ጽዋ ከማኅበረ ቅዱሳን ዋንጫ በተራችሁና በሰዓቱ ትጎነጫላችሁ። ወደማይቀረውም ሞት ተራ በተራ በጊዜአችሁም፤ አለጊዜአችሁም ትሸኛላችሁ፤ በሕይወት እያለን ይህንን የማኅበረ ቅዱሳንን ሚዛን ስትቀበሉ እናያለን፤ ያኔ ደግሞ እንደዚህ ብለናችሁ ነበር እንላለን» ይህም ደግሞ በቅርቡ ይጀምራል»
ከአቡነ ጳውሎስ ሞት በኋላ ሲኖዶስ ማለት ማኅበረ ቅዱሳን ነው። ቀንደኛ የማኅበሩ መዘውሮች ደግሞ አፍንጫና ጆሮ በመቁረጥ በራሱ የተአምር መጽሐፍ ላይ የተመሰከረለት የዘርዓ ያዕቆብ ደቀመዛሙርት ናቸው። በእርግጥ የማኅበሩን እርጥባን እየተቀበሉ በመናጆነት የሚያገለግሉ የሉም ማለት አይደለም። እነዚህ የዘርዓ ያዕቆብ ጉዶች በረቀቀ ስልት ቤተ ክህነቱን በእጃቸው አድርገዋል። ዋነኛ መፈክራቸው ቤተ ክህነትን « በገንዘባችን፤ በጉልበታችን፤ በእውቀታችን እናገለግላለን» ነው። ገንዘባቸውን  እንደሆነ ቤተ ክህነት በጭራሽ አታውቀውም። ጉልበታቸውንም  ቢሆን እንደአበራ ሞላ በአካባቢ ጽዳት ተሰማርተው ወይም  ጥቃቅንና አነስተኛ አቋቁመው ስራ አጥ ካህናቱን ወደስራ ሲያስገቡ አላየንም። እውቀታቸውን ግን እነሆ ለአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ባቀረቡት ጥናት ሽፋን የቁጥጥር መረባቸውን ሲዘረጉ አይተናል። ይህም የረጅም ጊዜ ህልማቸውን እውን ያደረጉበት እውቀት በመሆኑ ቤተ ክህነት የጀመረችው የቁልቁለት መንገድ ነው ብሎ መናገር ይቻላል። መጨረሻውም እንደማያምር ጀማሪውን አይቶ መተንበይ አይከብድም። ይህንን እንድንል የሚያደርጉን ምክንያቶች አሉ። በጥቂቱ እንያቸው።
1/ የፕሮጀክት ጥናቱ አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግሮችን የዳሰሰ መሆን ነበረበት። የችግሮቹን መግፍኢ ምክንያቶች፤ ያስከተሉት ውጤትና የመፍትሄ መንገዶችን ያመላከተ ሊሆን ይገባዋል።  የጥናቱ ዝርዝር ሁሉንም አሳታፊ በሆነ ውይይት ዳብሮ ለመፍትሄና አፈጻጸም በሚያመች መልኩ ተዘጋጅቶ አተገባበሩ ግን ለናሙና በተመረጠ አንዱ ሀ/ስብከት መሆን በተገባው ነበር እንላለን። እየሆነ ያለው ግን ማኅበሩ በሚነዳቸው ጳጳስ ፈቃጅነትና ማኅበሩ በሚዘውረው ቋሚ ሲኖዶስ ይሁንታ ከማኅበሩ ቤተ ክህነቷን የመቆጣጠር ምኞት ተፈብርኮ አዲስ አበባ ላይ የመዋቅር ብረዛ ችካል መትከል ተጀመረ።
2/ በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግሮች ላይ ሊደረግ የሚገባው ሁለ ገብ ጥናት የቤተ ክርስቲያኒቱን አባላት፤ ሊቃውንት፤ ምሁራን፤ የሕግ አዋቂዎች፤  ጋዜጠኞች፤ ስልጣን ያላቸው ከፍተኛ ሹማምንት፤ የዩኒቨርሲቲ ምሁራን ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱ መሪዎች የተካተቱበትና የቤተ ክርስቲያኒቱ እድገትና ልማት የሚመለከታቸው ሁሉ ተቀናጅተው ይህን የማስተባባር ኃላፊነት ቢቻል በአንድ ሊቀ ጳጳስ የሚመራ ራሱን የቻለ ክፍል ተዋቅሮ መካሄድ በተገባው ነበር። ጋኖች አለቁና ማኅበረ ቅዱሳን አርቃቂ ሆኖ ጳጳሳቱ ከየትም ይምጣ እንጂ እንቀበላለን ብለው አረፉ። በማፈሪያዎች ዘመን የሚያሳፍር ነገር የለምና ብዙም አያስገርምም።
3/ ቤተ ክርስቲያኒቱ በሥጋዊ ወመንፈሳዊ አገልግሎቷ የሚጠበቅባትን ያህል እየተራመደች እንዳይደለ እርግጥ ነው። በአብዛኛው ውጫዊ ምክንያቶች እንደሆነ ተደርጎ ቢወሰድም፤ ለድክመቷ በዋናነት መነሳት ያለበት ከውስጧ ባለው ጉድለት መሆኑን ማወቅ ተገቢ ነው። ሲኖዶስና የሲኖዶስ የሕግ አመራር የዘመኑን የቤተ ክርስቲያን ሁኔታ የተመለከተ ስለመሆኑ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያኒቱ አጠቃላይ የመዋቅር ዝርጋታው፤ አተገባበሩ፤ መመሪያውና ደንቦቿ ሁሉ ችግሮቿን የቃኙ፤ መፍትሄ ማምጣት የሚችሉና የሚያራምዱ አይደሉም። ቃለ ዓዋዲ የተባለው ደንብ በምንም መልኩ የዛሬይቱን ቤተ ክርስቲያን የማስተዳደር አቅም የሌለው ስለመሆኑ በማስረጃ አስደግፎ መናገር ይቻላል። ስለሆነም አጠቃላይ ጥናት ያስፈልጋል ሲባል ይህንን የተመለከተ መሆን ስላለበት ጭምር ነው። አንዱን ጥሎ አንዱን በማንጠልጠል የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ችግር ለብቻው ለመፍታት በፍጹም አይቻልም። የጳጳሳቱ ስሜትና የማኅበረ ቅዱሳን መንቀዥቀዥ ችግሩን ከማወሳሰብ በስተቀር የችግሩን ሰንኮፍ በፍጹም አይነቅልም።
4/ እስካሁን ያልተነገረለትና ሊነገርም ያልተወደደው የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር መንፈሳዊ ብልጽግናዋን የተመለከተው ክፍል ነው። በእርግጥ የአፄ ዘርዓያዕቆብ ትራፊዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥንታዊነትና ሐዋርያዊ አስተምህሮዋን የበረዘ የብርሃን ወረደልን ደብረ ብርሃናዊ ዜማ በጭራሽ እንዲነካ አይፈልጉም። የአባ እስጢፋኖስና ደቀ መዛሙርቱ የአፍንጫና ጆሮ መቆረጥን ተገቢነት ዛሬም እንደታመነበት እንዲቀጥል ይፈልጋሉ። ቤተ ክርስቲያኒቱ መከራን የተቀበለችበትን የክርስቶስን ወንጌል ወደጎን ገፍተው አለያም ወንጌሉን ጨብጠናል ለማለት ብቻ መሳ መሳ የሚራመዱት ተረት፤ እንቆቅልሽና አልፎ ተርፎም ክህደት ያለባቸው አስተምህሮዎች በጥናቱ ውስጥ በመካተት እርምት ሊወሰድባቸው የሚገባቸውን በቃለ እግዚአብሔር ሚዛንነት የመለየት ስራ ፈጽሞ ሊታለፍ የማይገባው ነው። ዘመናዊው አስተዳደር ያለመንፈሳዊ ልማት በጭራሽ አይታሰብም።
 የሰይጣን መነኮሰ ክህደትና እርምት ሲነገር ለምን ይሄ ተነክቶ በማለት ጸጉራቸው እንደጃርት እሾክ ከሚቆመው መካከል ማኅበረ ቅዱሳን አንዱ ነው። ይህ የተረት አባት የሆነ ማኅበር ነው እንግዲህ ሕግ አርቃቂ የሆነልን። ስለዚህ በወርቅ የቃለ ወንጌል ወራጅና ቋሚ ዐምድ የተተከለችው ቤተ ክርስቲያን በዘመናት ውስጥ ማንም ሳይፈቅድላቸው ገብተው የሸረሪት ድራቸውን ያደሩባት የዘመን እራፊዎች ጸድተው መገኘቷ አገልግሎቷን ምሉዕ፤ ክብሯንም በሚጠሏት ላይ ሳይቀር ከፍ ከፍ እንድትል ያደርጋታል። ደርግም፤ ኢህአዴግም ገፉን እያሉ ማልቀስ መነሻው የቀደመ መንፈሳዊ ክብሯ ስለቀነሰ ካልሆነ ሲያቦኩንና ሲጋግሩን አናይም ነበር።
ስለሆነም ከላይ ባየናቸው አራት ዋና ዋና መግፍኢ ምክንያቶች የተነሳ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ላይ የቀረበው የማኅበረ ቅዱሳን ጥናት ተብዬ ከፈረሱ ጋሪው የቀደመበት ነው ማለት ይቻላል። በየግል ጋዜጣው የላኩትን ጽሁፍ መልሶ እንደአዲስ ግኝት በዜና መልክ ማቅረብ ወሬ ማብዛት የሚወድ የወፈፌ ስራ እንጂ የቤተ ክርስቲያን ችግር እንደሰጎን እንቁላል አትኩሮ የተመለከተ የመልካም ዘር ተስፈኛ አስተሳሰብ አይደለም። ስለዚህ ይንን ጋሪው ከፈረሱ የቀደመበትን ጥናት በየትም ይምጣ ቀልደኞችን ጥሎ ጋሪው ፈረሱን የሚጎትትበት አግባብ ቶሎ መፍትሄ ይሰጠው።
------------------------------------------------------

Sunday, December 15, 2013

የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማዊ ለውጥ ከላዕላይ መዋቅር ይመነጫል እንጂ ለአንድ ሀ/ስብከት ከማኅበረ ቅዱሳን ቢሮ አይደለም!


  • የማኅበረ ቅዱሳን ሩጫ ሀገረ ስብከት የመቆጣጠር ስልት እንጂ ዘረፈ ብዙ የቤተ ክርስቲያኒቱን ችግር ለመፍታት አያገለግልም።
  • ማኅበረ ካህናቱ ከማኅበረ ቅዱሳን አፈናና ስለላ ለመዳን መታገል ያለባቸው ዛሬ ነው!
  • ማኅበረ ቅዱሳን ራሱ ተቋማዊ ለውጥ የሚያስፈልገው ድርጅት ነው!
   ከዚህ ቀደም እንዳልነው ተቋማዊ ህዳሴና አስተዳደራዊ ለውጥ የሚያስፈልገው ለዘመናት ሲንከባለል የመጣውን አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ፈተናዎችና ተግዳሮቶችን  መነሻ ባደረገ መልኩ መሆን አለበት የሚለው ሃሳብ በመጀመሪያ ረድፍ የሚቀመጥ አጀንዳ ነው። ከላዕላይ መዋቅሩ ወይም ከዋልታው የለውጥ ተሐድሶ ባልተጀመረበትና ፈጽሞ ባልታሰበበት ሁኔታ በተናጠል የአንዱ ሀገረ ስብከት አጀንዳ እንደሆነ በመቁጠር በዚያ ዙሪያ መኮልኮል ውጤታማ ፍጻሜ ሊኖረው በፍጹም አይችልም።

 በተለይም ደግሞ ማኅበረ ቅዱሳን በተባለ አንጃ ተጠንስሶና የዲስኩር ውሃ ተሞልቶ ካህናቱ እንዲጠጡ በተዘጋጀው የስልጠና ወሬ የተነሳ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ለውጥ ይመጣል ማለት ዘበት ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ራሱ ተቋማዊ ለውጥ የሚያስፈልገው አፈንጋጭ ድርጅት ሆኖ ሳለ የሀገረ ስብከቱ እቅድ ነዳፊ፤ አሰልጣኝና «የያብባል ገና» ዜማ ደርዳሪ ሆኖ መሰየሙ አስገራሚ ነው። እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ላይከዱት በልጆቻቸው ስም ቃለ መሃላ የገቡለት ሊቀ ጳጳስ እስጢፋኖስ «ተቀመጥ በወንበሬ፤ ተናገር በከንፈሬ» ብለው ለማኅበሩ ያስረከቡትን ሀገረ ስብከት ማኅበረ ካህናቱ አሜን ይሁን፤ ይደረግልን ብለው መቀበላቸው ያሳዝናል። በጣፈጠና በለሰለሰ አማርኛ ነገ ብርሃን ሊወጣልህ ነው እያሉ በማደንዘዝ ላይ የተጠመዱት የማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች የአዲስ አበባን ችግር ከአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር በተለየ የመፍታት ምትሃታዊ ኃይል ስላላቸው ሳይሆን ማኅበረ ካህናቱ ማቅ የተባለውን ድርጅት ውስጣችን አናስገባም ብለው ለ21 ዓመት የታገሉትን ለመቋቋም ይቻለው ዘንድ ገሚሱን የስልጠናው ደጋፊና ገሚሱን የስልጠናው ተቃዋሚ አድርጎ ከፋፍሎ በመምታት እግሩን በመሃከል አደላድሎ ለመትከል ያለመ መሆኑን ሊጤን ይገባል።
  ማኅበረ ካህናቱ በቤተ ክርስቲያኒቱ አጠቃላይ መዋቅራዊና አስተዳደራዊ ለውጥ እንዲመጣ ካስፈለገ ከራሷ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንትና ምሁራን እንጂ ይህ ገንዘቡን በጓሮ እያደለበ፤ ስንት እንደነገደና ስንት እንዳተረፈ ካዝናው የማይታወቅ የመሰሪዎች ስብስብ ማኅበር በሚያረቀውና በሚያቀርበው የስልጠና መርሃ ግብር መሆን እንደሌለበት ማኅበረ ካህናቱ ሊገነዘብ ይገባል። የራሱን በጉያ ደብቆ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ካዝና ለመቆጣጠር እቅድና ትልም ማውጣቱ ድፍረት ብቻ ሳይሆን ጳጳሳቱ እስከደገፉት የሚከለክለው እንደሌለ ያሳየበት አጋጣሚ ነው።
  መዋቅራዊውን ለውጥ ከግቡ ለማድረስ አቅሙና እውቀቱ ካላቸው ከቅዱስ ፓትርያርኩና ከቅዱስ ሲኖዶስ መመንጨት አለበት። ከዚያም በተረፈ ቤተ ክርስቲያን ብትጠራቸው ይህንን ለመስራት ማገዝ የሚችሉ ቅን፤ የቤተ ክርስቲያናቸው ጉዳይ ግድ የሚላቸው፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ አሁን ያለችበት የአስተዳደር ጉድለት ዘወትር የሚያንገበግባቸው ኦርቶዶክሳውያን ምሁራን ሞልተዋል። ስለዚህ ነጋዴ የወጣቶች መንጋ ስኬት ያገኘ ስለመሰለው ብቻ ሀገረ ስብከቱን ልዘዘው፤ ልናዘው ብሎ ስለጠየቀ ሊፈቀድለት አይገባም። ደረጃውም፤ አቅሙም ስላይደለ ሀይ ሊባል የሚገባው ሰዓት ቢኖር አሁን ነው።

 ስለሆነም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ማኅበረ ካህናት የሆናችሁ ሁላችሁም ይህ ካዝናውን በጓሮ የደበቀ ማኅበር የናንተን የአገልግሎት ካዝና እንዲቆጣጠር ልትፈቅዱለት አይገባም። እርግጥ ነው፤ የብዙ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳደሮች ጉድለት፤ ብክነትና ምዝበራ አስቸጋሪ እየሆነ መጥቷል። በእኛ እምነት ይህ ችግር የሚቀረፈው የቤተ ክርስቲያኒቱ ላዕላይ መዋቅር የችግሩን አንገብጋቢነትና ስፋት በጥልቀት ተመልክቶ በቤተ ክርስቲያኒቱ ምሁራንና ሊቃውንት አስጠንቶ አጠቃላይ የለውጥ እንቅስቃሴ በማድረግ ብቻ እንደሆነ እናምናለን። ከዚህ ውጪ አንዱን ጫፍ ለማኅበረ ቅዱሳን አሳልፎ በመስጠት ለውጥ ሊመጣ ስለማይችል ማኅበረ ቅዱሳን ከቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ማሻሻል ጉዳይ እንዲወጣ መታገል ወቅቱ ዛሬ ነው።
በውስጥ ጉዳያችን ማኅበረ ቅዱሳን መግባት የለበትም ለማለት የማኅበረ ካህናቱ ድምጽ መሰማት ያለበት ዛሬ ነው።

Thursday, December 12, 2013

የማኅበረ ቅዱሳን መግነንና ብቀላ መሳ ለመሳ ናቸው፤ እንደጠዋት ጤዛም ቀትር ላይ ይጠፋሉ!


ነፍሳቸውን በአጸደ ቅዱሳን ያሳርፍልንና ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከዚህ ዓለም በሞት ከተለዩ በኋላ ማኅበረ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያኒቱን ያለውልና ፊርማ ተረክቧት እያስተዳደረ ይገኛል። አቡነ ጳውሎስ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ይህንን መሠሪ ማኅበር ከመነሻው የደገፉት ሲሆን ውሎ አድሮ አካሄዱን አይተው የእድሜ ዘመኑን ለማሳጠር ብዙ ቢጥሩም ማኅበሩ ስር ሰዶ፤ የራሱን ጳጳሳት በመመልመል የሲኖዶሱን እኩሌታ መቆጣጠር የቻለበት ደረጃ ላይ ደርሶ ስለነበር ጥቂት ከማንገዳገድ ውጪ ሊጥሉት ሳይችሉ ቀርተው ወደማይቀረው ሞት ሄደዋል።
  አበው «የጠሉት ይወርሳል፤ የፈሩት ይደርሳል» እንዲሉ ይህንን ማኅበር የጠላነውን ያህል ሳይዳከም፤ የፈራነው ቤተ ክርስቲያኒቱን የመረከብ የረጅም ጊዜ ህልሙ እውን እያደረገ መገኘቱን ስንመለከት መጨረሻውስ? ብለን እስክንጠይቅ ድረስ መደመማችን አልቀረም። ምናልባት ቤተ ክህነቱን እንደወረሰ ቤተ መንግሥቱንም ይረከብ ይሆን? ይህንንም እንጠይቃለን። ማኅበሩን ስለመጥላት ስንናገር ሰውኛ ጥላቻ ሳይሆን  እንዴት አንድ ተራ ማኅበር፤ ለዚያውም በጦር ካምፕና በዝሙት መስዋእት ተመስርቶ ሁለት ሺህ ዘመን የዘለቀችውን ቤተ ክርስቲያን ተረክቦ በእጁ ያደርጋታል ከሚል መንፈሳዊ ቁጭትና መሸሻውም ይሁን መገኛው ከንስሐ ሥፍራ መሆን ሲገባው ዐመጽ ወልዶት፤ ዐመጽ ያሳደገው ማኅበር እዚህ መድረሱ አስገራሚም አስደማሚም ከመሆኑ የተነሳ ነው። አንዳንዶች ይህ ማኅበር እንደቴዎዳስ ዘግብጽ ቶሎ ያልጠፋው እግዚአብሔር ስለተከለው ነው በማለት ከእግዚአብሔር ፈቃድ ጋር በማስተሳሰር ሊያሳምኑን ይከጅላሉ። ናቡከደነጾር ኢየሩሳሌምን አጥፍቶ፤ ሕዝቡን 70 ዘመን በባርነት የገዛው ናቡከደነጾር እግዚአብሔርን ያመልክ ስለነበር ሳይሆን የእግዚአብሔር ሕዝብ የተባለው እስራኤል ከእግዚአብሔር አምልኮ ስላፈነገጠ መሆኑም እንዳይዘነጋ ማስረጃ እናቀርብላቸዋለን። ማኅበረ ቅዱሳን 21 ዓመት የመቆየቱ ምስጢርና ቤተ ክርስቲያኒቱን እስከማዘዝ የመድረሱ ነገር በቅድስናው ልክ እግዚአብሔር በመደሰቱ ነው ብለን አናስብም። በዚህ ርዕስ የማኅበረ ቅዱሳንን አነሳስ ትተን አሁን ያለበትን መንፈሳዊ መሰል ሕይወቱን ብንዘረዝር ውሎ ያሳድረናል። ሌላው ቀርቶ የማይታዘዙለትን ጳጳሳት እንዴት እንደሚያበሻቅጥና ሰጥ ለጥ ብለው የሚታዘዙለትን ደግሞ የቱንም ያህል አስነዋሪ ገመና ቢኖራቸው ምን ያህል እንደሚያንቆለጳጵሳቸው በመመልከት ስለማኅበሩ መናገር ይቻላል። «ከእነማን ጋር እንደምትውል ንገረኝና ማንነትህን ልንገርህ» ይባል የለ!

  አብዛኛዎቹ ጳጳሳትም ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ይህንን ማኅበር ቆመው ማውረድ እስኪያቅታቸው ድረስ በተዘዋዋሪ መንገድ ለዚህ ማኅበር የምርኮኝነት እጃቸውን ሰጥተዋል። በየሄዱበት ሀገረ ስብከት ወንበራቸውን ከኋላ የሚሾፍረው ይህ ማኅበር ሲሆን በተለይም ከአቡነ ጳውሎስ ሞት በኋላ በተጠናና በታወቀ ስልት እያደባ፤ ካህናቱንም ሳያስደነግጥ፤ በረቀቀ መንገድ አስተዳደሩን ተረክቦ የሁለት ተቋም አስተዳዳሪ ሆኖ ይገኛል። አንዱ  ቅዱስ የተባለው የሲኖዶስ መንበር ሲሆን ሁለተኛው በግልጽ የሚጠራበት የራሱ ማኅበር ተቋማዊ የንግድ አስተዳደር ነው። ለረጅም ጊዜ ባካበተው የስለላ ልምዱ መረጃዎችን ወደአንድ ቋት በመሰብሰብ እቅድና ትግበራውን በግልጽም በስውርም ያካሂዳል። ለዚህም ተጠቃሹ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አንዱ ነው።
  የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በሙስና፤ በአስተዳደር ብልሹነትና በንቅዘት ግንባር ቀደም ሀገረ ስብከት የመሆኑን ያህል ከፍተኛ የለውጥ እርምጃ የሚያስፈልገው ስለመሆኑ አያጠያይቅም።  እጃቸው በተጠመዘዘና በማኅበረ ቅዱሳን ሳንባ በሚተነፍሱት በአባ እስጢፋኖስ በኩል ለውጥ ይመጣል ብሎ መጠበቅ ግን «ላሞች ባልዋልሉበት ኩበት ለቀማ» ከመሆን የዘለለ ውጤት አይኖረውም ብቻ ሳይሆን የቤተ ክርስቲያኒቱን አናት ለማኅበረ ቅዱሳን አሳልፎ የመስጠት ሂደት መሆኑ ሊሰመርበት ይገባል።
  «የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በለውጥና ህዳሴ ጎዳና፤ ያብባል ገና» በሚለው የማኅበረ ቅዱሳን መፈክር ስር የተጠለለው የአስተዳደር ማሻሻል ትግበራ ሂደት ጥናቱ፤ እቅዱና አፈጻጸሙ ሙሉ በሙሉ እየተከናወነ ያለው በማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች በኩል ስለመሆኑ በግልጽ ይታወቃል። ዞሮ ዞሮ ሀገረ ስብከቱን ለማኅበረ ቅዱሳን እንቅስቃሴ አመቺ በሆነ መልኩ ማዋቀርና ሊመጣ የሚችልበትን ግልጽና ስውር ተቃውሞ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በመዝጋት «ማኅበረ ቅዱሳን፤ ማኅበረ ቅዱሳን» የሚል ድምጸትን የሚያስተጋባ አስተዳደርን መመስረት ዋነኛ ግቡ ስለመሆኑ የምንሰማቸው አቤቱታዎችና እንቅስቃሴዎች አመላካች ናቸው። በቅርቡ እንዳየነው ለማኅበረ ቅዱሳን በጎ አመለካከት የላቸውም የተባሉ ካህናትና ሰራተኞች በስመ ዝውውርና ሽግሽግ ሰበብ ዱላ እያረፈባቸው መገኘቱ አንዱ አስረጂ ነው። ለወደፊቱም በፍጥነት ሳያስደነግጡና ሳያስደነብሩ በማለሳለስ ተመሳሳዩን የበቀል ዱላ እያሳረፉ ለአዲሱ ለውጥና ህዳሴ ስለሆነ ሁላችሁም «ያብባል ገና»  በሚለው ዝማሬ ስር ተሰባሰቡ ማለቱን ይቀጥላል። አባ እስጢፋኖስ ከማኅበረ ቅዱሳን ጉያ ለመውጣት አቅሙም፤ ብቃቱም፤ ሞራሉም የላቸውም፤ ስለዚህ በቦታው እስካሉ ድረስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የጓሮ አስተዳዳሪ ማኅበረ ቅዱሳን ሆኖ መቀጠሉም አይቀሬ ነው። በባላ የተደገፈ ቤት ለጊዜው እንጂ በቀጣይነት ሊቆም አይችልም። የአባ እስጢፋኖስ የማኅበረ ቅዱሳን መዋቅራዊ ማሻሻያም የዚያው ተመሳሳይ ውጤት ከመሆን አይዘልም።  ምናልባትም የማኅበረ ቅዱሳን በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ውስጥ የማቡካት የመጋገር ጅማሮ የማኅበሩን ዕድሜ ቀጣይነት ወሳኝ ምዕራፍ ከፋች ሊሆን እንደሚችል ይገመታል። በሂደት የምናየውም ይሆናል።

ሌላው በተመሳሳይ መልኩ ማኅበረ ቅዱሳንን ካሰማሯቸው ታማኝ አገልጋዮች መካከል የሐዋሳው አቡነ ገብርኤል ተጠቃሽ ናቸው። እንዲያውም ማኅበሩ ራሱ በተደጋጋሚ እንደሚለፍፈው «ማኅበረ ቅዱሳን» ብለው የዳቦ ስሜን ያወጡልኝ አቡነ ገብርኤል ናቸው እያለ በሚጠራቸው የነፍስ አባቱ ቤትም ማዘዝ ከጀመረ ውሎ አድሯል። በተዘዋዋሪም ተጠያቂነት ካለብኝም ይህንን ስም የሸለሙኝ ሊሆን ይገባል በሚል ድምጸት ማኅበሩ ስሙንና አቡነ ገብርኤል ለአፍታም ከአፉ አይነጥልም።

አቡነ ገብርኤል እድሜ ለንስሐ የሰጣቸውን አምላክ ከማመስገን ይልቅ ይህንን ማኅበር በጌታ ምትክ ዘወትር ሲያወድሱት ይታያሉ። በአሜሪካ አደባባይ «የፍየል ወጠጤ፤ ልቡ ያበጠበት…………» ከሚለው የጸረ ኢህአዴግ  ሰላማዊ ሰልፍ አንስቶ በይቅርታ ይሁን በንስሐ ከኢህአዴግ ጋር የታረቁበት መንገድ ለጊዜው ባይታወቅም ሐዋሳ እስከደረሱበት ጊዜ ድረስ በየሄዱበት ሰላም አስፍነው እንደማያውቁ ግለ ታሪካቸው  ይናገራል። ሐዋሳ እንደገቡም የመጀመሪያ ስራቸው ምእመናኑን በመከፋፈል ገሚሱን በማስደንበር የማባረር ስራ አሐዱ ብለው የጀመሩ ሲሆን ከዚህ ጀርባም ያ ቁጭ ብለው የሰቀሉትና ቆመው ማውረድ ያቃታቸው የነፍስ ልጃቸው ማኅበሩ አብሯቸው ነበር።
  እነመጋቤ ሐዲስ በጋሻውን፤ ቀሲስ ትዝታውንና ሌሎቹንም ዘማርያን ነክሶ የያዘውን ማኅበር ደስ ለማሰኘት አባ ገብርኤል እስከመጨረሻው ድረስ ለማሳደድ አላቅማሙም። ደም እስኪፈስና አካል እስኪጎድል ድረስ ሐዋሳን የጦርነት አውድማ ለማድረግም ወደኋላ አላሉም። ማኅበሩ ካዘዘ ሕንድ ውቅያኖስ ውስጥም ከመግባት እንደማይመለሱ ይታወቃል። እንዲያው ተሸፋፍኖ ይቅር ብለን እንጂ አባ ገብርኤል ምን የማያደርጉት ነገር አለ? ከዚህ በደል ለመገላገል ደግሞ ያላቸው ብቸኛው አማራጭ ንስሐ መግባት ሳይሆን ያንን ከነከሰ የማይለቅ ማኅበር እስከመጨረሻው ማገልገል ብቻ ነው። ሰሞኑን በእርቅ ሰበብ ከተጣሏቸው ምእመናን ጋር በመታረቅ አቡነ ገብርኤል ተስማምተውና አካባቢውን መስለው ለማደር ቢፈልጉም ያ ማኅበር ከኋላቸው ሆኖ «አይሆንም፤ አይደረግም» እያለ ሰቅዞ ይዟቸዋል። በተለይም የጥሉ አስኳል ተደርገው በማኅበሩ የብቀላ መዝገብ ላይ የሰፈሩት እነ በጋሻው ይቅርታ ይደረግልን የሚል ማመልከቻ ያቅርቡ እያለ መገኘቱ የሁከቱ ባለቤት ማን እንደነበረ በግልጽ እያሳየ ይገኛል። በዳይና ተበዳይ ማን እንደሆነ የመመርመር ሳይሆን ጉዳዩን በእርቅ የመፍታት ጥረት ላይ ነገሩን ለማደፍረስ የሚደረገው የማኅበሩ ሩጫ አስገራሚም አሳዛኝም ያደርገዋል።  በጋሻው «የበደላችሁኝን ሁሉ ይቅር ብያለው» ማለቱ ሲሰማ ማኅበሩ በተገላቢጦሽ «በድያችኋለሁና ይቅር በሉኝ» ሊል ይገባል በማለት ላይ መጠመዱ ሳያንስ ማኅበሩ በዚህ መካከል የሚጨምረው የተንኮል ቅርቃር ደግሞ «በጋሻው ሃይማኖታዊ ሕጸጽ ስላለበት ጉዳዩ በይቅርታ አያልቅም» የሚል መሆኑ ነው።

«የበደሉንን ይቅር እንደምንል» ጌታ ያስተማረን ጸሎት ነው። በጋሻው ይህንን በማለቱ ተቀባይነት የለውም ማለት ምን ማለት ነው? በግልባጩ በጋሻው በድሎናል የሚል ካለም ይህንን ቃል መልሶ በመጠቀም «የበደሉንን ይቅር እንደምንል» ማለት በጋሻው በድሎናል፤ ግን ይቅር ብለነዋል ማለት የክርስትና መገለጫ እንጂ የትንሽነት ወይም የተጠቂነት ስሜት ማንጸባረቂያ አይደለም። ይሁን እንጂ ማኅበሩ « የበደልኩ እኔ ነኝ፤ ይቅር በሉኝ» የሚል ልመና ሊቀርብልን ይገባል ሲል ይደመጣል። እንዲያማ ቢሆን ኖሮ እኛ የሰው ልጆች  ወደ እግዚአብሔር የማቅረብ የበደለኛነት ጥያቄ እያለብን  የተበደለው አምላክ በደላችንን ይቅር ሊለን ሥጋ ለብሶ ባልመጣ ነበር እንደማለት ነው።  «ጠላቶች ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ከታረቅን፥ ይልቁንም ከታረቅን በኋላ በሕይወቱ እንድናለን» ሮሜ 5፤10
ለጸሎትም በቆማችሁ ጊዜ፥ በሰማያት ያለው አባታችሁ ደግሞ ኃጢአታችሁን ይቅር እንዲላችሁ፥ በማንም ላይ አንዳች ቢኖርባችሁ ይቅር በሉት» ማር 11፤25
እርስ በርሳችሁ ትዕግሥትን አድርጉ፥ ማንም በባልንጀራው ላይ የሚነቅፈው ነገር ካለው፥ ይቅር ተባባሉ። ክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ እናንተ ደግሞ እንዲሁ አድርጉ» ቆላስ 3፤13

ዳሩ ግን ይህ ተበቃይ ማኅበር የጠላቸው ሰዎች መንበርከካቸውንና እጃቸውን በመሸነፍ ስለማስረከባቸው የማረጋገጫ ቃል ካላገኘ በቀር «የበደሉንን ይቅር ብለናል« የሚለው ቃል አያረካኝም እያለ ይገኛል። የወንጌልን ቃል የማይቀበል ይህን መናፍቅ ማኅበር ደርሶ የወንጌል ቃል ተቆርቋሪ ሆኖ በመታየት ሌሎችን የሃይማኖት ሕጸጽ አለባቸው በማለት አለማፈሩ ያስገርማል። የእነ ደብተራ ገለፈትን መጽሐፍ እንጂ ማኅበረ ቅዱሳንና ወንጌል የትም እንደማይተዋወቁ እርግጥ ነው። መናፍቁና ጸረ ወንጌሉ ማኅበር ተግባር የሚመሰክርበትን የወንጌል ቃል ተቃርኖ እየተናገረ ስለወንጌል የመናገር ብቃቱም፤ እውቀቱም የለውም። ዳሩ ግን «ጊዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ ይሰብራል» እንዲሉ ባሰረጋቸው መነኮሳቱ በኩል ጳጳሳት ሆነው ስለተገኙ ብቻ  ቤተ ክርስቲያኒቱን በእነሱ እጅ በመጥፎ አጋጣሚ እያሾራት መገኘቱ ያሳዝናል። እነ አባ ሉቃስን በመሳሰሉ አድር ብዬዎች በኩል መለመላዋን የተገኘችውን ቤተ ክርስቲያን ለጊዜው ተረክቧት ማኅበሩ እያስተዳደረ ነው። «የበደሉንን ይቅር እንደምንል በደላችንን ሁሉ ይቅር በለን» ማለት የክርስትና ጸሎት ነበር። ይህንን ማለት ግን የአላዋቂዎች ጸሎት ተደርጎ ተቆጥሯል። ዳሩ ግን ሥልጣን እውቀትን በተካበት ዘመን ወንጌል ሥፍራ እንደሌለው እውነት ነው። ይሁን እንጂ የወንጌል እውነት በሥልጣንና በገንዘብ ተቀብሮ ሊቀር አይችልም። ከማኅበረ ቅዱሳን አገልጋይ ጳጳሳትና ከማኅበሩም በላይ ሥልጣንና ኃይል የነበራቸውም እንኳን በታሪክ ውስጥ የወንጌልን እውነት ቀብረው ሊያስቀሩ አልተቻላቸውም። ወንጌል በኃይልና በሥልጣን ሊነሳ ሲፈልግ ቦታውን ግሳንግስ ይወረዋል። በውሸት መካከል የወጣ እውነት ሕይወትን የመስጠት ኃይል የሚኖረው ያኔ ነውና።
  የማኅበሩ እንዲህ መገስገስና በየስፍራው  እያየነው የመንገስ ጉዳይ የጥዋት ጤዛን ያሳየናል። ፀሐይ ሲወጣ ጤዛ ባለበት አይገኝም። ዛሬ ለእግዚአብሔር ያለመመቸታችንና ስለኃጢአታችን በፊቱ ያለመውደቃችን ምክንያት እንጂ ንስሐ ገብተን፤ መልካሙን ዘመን እንዲያመጣልን ከልብ ከጸለይን ብላቴን ላይ የተፈለፈለው ማኅበር እንደጥዋት ጤዛ ቢያለጨልጭም ቀትር ላይ ተመልሰን እንደማናገኘው እርግጠኞች ነን። ለዚህ ጸሎት አንድ ኤልያስ በመካከላችን እንደማይጠፋም እናውቃለን። በሰው ላይ እየፈረደ፤ ራሱን ለንግድ አሳልፎ የሚሰጥ ለጊዜው እንጂ ከቆመበት መውደቁ አይቀርም። ይልቅ ራሱን ለንስሐ ቢያዘጋጅ ይበጀዋል።

«እግዚአብሔርን ደጅ ጥና፥ መንገዱንም ጠብቅ፥ ምድርንም ትወርስ ዘንድ ከፍ ከፍ ያደርግሃል ኃጢአተኞችም ሲጠፉ ታያለህ። ኃጥአን ከፍ ከፍ ብሎ እንደ ሊባኖስ ዝግባም ለምልሞ አየሁት። ብመለስ ግን አጣሁት ፈለግሁት ቦታውንም አላገኘሁም። ቅንነትን ጠብቅ፥ ጽድቅንም እይ ለሰላም ሰው ቅሬታ አለውና። በደለኞች በአንድነት ይጠፋሉ። የኃጢአተኞች ቅሬታ ይጠፋል» መዝ 37፤34-38

 

Tuesday, November 19, 2013

አርቲስት አቦነሽ አድነው፡- ከዘፋኝነት ወደ ዘማሪነት ክፍል -፩-

በዲ/ን ኒቆዲሞስ ዕርቅ ይሁን  ~nikodimos.wise7@gmail.com

ከሰሞኑን ለረጅም ዓመታት በዘፋኝነት ምናውቃት ተወዳጇ አርቲስት አቦነሽ አድነው ከዘፋኝነት ዓለም ተፋትቻለሁ ስትል ‹‹ክብሬ ነህ!›› የሚል የመዝሙር አልበም ለክርስቲያኑ ዓለም በማበርከት ወደዘማርያኑ ጎራ ተቀላቅላለች፡፡ ይህን ‹‹ክብሬ ነህ!›› በሚል ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚገኘውን ፍቅርን፣ ሕይወትንና ተስፋን ያወጀችበትን የአርቲስቷን መዝሙሮች ለማድመጥ ዕድሉን አግኝቼ ነበር፡፡ አርቲስት አቦነሽ ከዚህ በፊት ‹‹በባላገሩ›› አልበሟ ጥልቅ የሆነ የኢትዮጵያዊነት መንፈስ፣ ታላቅ ታሪክ፣ ገናና ሥልጣኔ፣ ቅርስና ባህል በማድነቅ ማቀንቀኗን ብዙዎቻችን እናስታውሳለን ብዬ እገምታለሁ፡፡ እንዲሁም አርቲስቷ በእምነቷ የሃይማኖት ትምህርት፣ መንፈሳዊ የአምልኮ ሥርዓትና ትውፊት እየተደመመች ‹‹ቤተ ክርስቲያን ሄደሽ ወንጌል ተማሪ›› ይለኛል በማለት ያዜመችው ‹‹ባላገሩ›› የሚለው ተወዳጅ ዜማዋ በአርቲስቷ ልብ ውስጥ ቀድሞውኑ ለዓመታት ሲንቀለቀል የነበረ አንዳንች የመንፈሳዊ ሕይወት ናፍቆትና ቅናአት እንደነበራት ያሳየ ነው ብል ብዙም ያጋነንኩ አይመስለኝም፡፡
ይህ የአርቲስቷ የልብ ናፍቆትና መንፈሳዊ ቅናአት ዛሬ ሙሉ በሙሉ ዕውን ሆኖአል እያለች ያለ ይመስላል አርቲስት አቦነሽ አድነው፡፡ ይህ የአቦነሽ ውሳኔና ከዘፋኝነት ወደ ዘማሪዎቹ ጎራ የመቀላቀል አጋጣሚ ምናልባትም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ን የቅርብ ታሪክ ብዙም ያልተለመደና እንግዳ ነገር ይመስለኛል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ ከዘፋኝነት ወደ ዘማሪነት በሚል ማዕቀፍ ውስጥ ብዙም በአቀንቃኝነቷ የማናውቃት የቀድሞዋ ዘፋኝ ዘማሪት ዘርፌ ከበደ ልትጠቀስ ትችል ይሆናል፡፡
ከዚህ ውጪ ሙሉ በሙሉ ከዘፈን ዓለም ወደ መዝሙር ዓለም ፊታቸውን የመለሱ አቀንቃኞቻችንን እንጥቅስ ቢባል የፕሮቴስታንቱ ዓለም አንጋፋ ኢትዮጵያውያን አርቲስቶችን በመማረክ ደረጃ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀስ ይመስለኛል፡፡ ለአብነትም በኢትዮጵያ ዘመናዊ ሙዚቃ ታሪክ ውስጥ በ1970ዎቹ፣ 80ዎቹ በኢትዮጵያ ሙዚቃ ውስጥ ከነገሡትና እስካሁንም ድረስ ትልቅ ዝና፣ ስምና ተወዳጅነት ካላቸው ድምፃውያን መካከል ስማቸው በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰው ሙሉቀን መለሰና ሒሩት በቀለ የፕሮቴስታንቱን ዓለም የተቀላቀሉ የመቼም ጊዜም ተወዳጅ አርቲስቶቻችን ናቸው፡፡
በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የቅርብ ዘመን ታሪክ በእጄ ላይ ባለው መረጃ መሠረት ምናልባትም ለመጀመሪያ ጊዜ አንድ ታዋቂና አንጋፋ አርቲስት ወደ ዘማሪነት ጎራ ስትቀላቀል አርቲስት አቦነሽ አድነው የመጀመሪያዋ ትመስለኛለች፡፡ ወደ አርቲስት አቦነሽ ከዘፋኝነት ወደ ዘማሪነት ስለተቀላቀለችባቸው የመዝሙሮቿ መልዕክትና አጭር ዳሰሳ ከማለፌ በፊት ግን ዘፈንና ዘፋኝነት አስመልክቶ ያሉትን የተሳሳቱ አመላካከቶችና ትርጓሜዎች ለማጥራት ይመቸን ዘንድ ጥቂት ቁም ነገሮችን ለማንሳት እፈልጋለሁ፡፡
ዘፈንና ዘፋኝነትን በመንፈሳዊው ዓለም እንዴት ይታያሉ
 ዘፈን ወይም ዘፋኝነት እስካሁንም ድረስ በበርካታ ክርስቲያኖች መካከል የመለያየትና የክርክር ርእስ ሆኖ ለዓመታት ዘልቋል፡፡ በአንዳንዶች ዘንድም ዘፈን ወይም ዘፋኝነት እንደ ትልቅ ኃጢአት ተቆጥሮ የተረገመበትንና የተወገዘበትን በርካታ አጋጣሚዎችን ታዝበናል፤ አልፎ አልፎ እንደምናስተውለውም አሁንም ድረስ ውግዘቱና እርግማኑ ያቆመ አይመስልም፡፡ እነዚሁ ዘፈንና ዘፋኝነትን አጥብቀው የሚጠሉና የሚኮንኑ ወገኖች ለዚህ አቋማቸው እንደ መነሻ አድርገው የሚወስዱት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን የገላትያ ፭፣፳፩ መልዕክቱን ነው፡፡ እንዲህ ይነበባል፡-
‹‹የሥጋ ፍሬም የተገለጸ ነው፣ እነርሱም መግደል፣ ስካር፣ ዘፋኝነት … አስቀድሜ እንዳልኩ እነዚህን የሚያደርጉ ሁሉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም፡፡›› በዚህ ጥቅስ ላይ በመመርኰዝ ‹‹ዘፈን የተወገዘ ነገር ነው፣ ዘፋኞችም በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ዕድል ፈንታ የላቸውም፡፡›› በማለት ብዙዎች ክርስቲያኖች ባሕላዊ ጨዋታና ማንኛውም ለእግዚአብሔር ክብር ከሚቀርብ መዝሙር ውጭ የሆነ ሙዚቃ ሁሉ ኃጢአት ነው የሚል አቋም ሲያራምዱ ይሰማል፡፡
በዚህ ዘፈንና ዘፋኝነትን በተመለከተ በሚነሡ የክርክር ሐሳቦች ላይ በአንድ ወቅት የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤ/ን አባትና የሥነ መለኮት ምሁር የሆኑት ዶ/ር አባ ዳንኤል ‹‹ዘፈን ኃጢአት ነውን?›› በሚል ርእስ ባስነበቡት አጭር መጣጥፋቸው ያነሷቸውን ሐሳቦች እዚህ ላይ ደግሜ ማንሳት ጠቃሚ ይመስለኛል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ዘፈንና ዘፋኝነት ሲያወግዝ ስለየትኛው ዓይነት ዘፈንና ዘፋኝነት እያወራ እንዳለ ከመናገራችን በፊት ይላሉ ዶ/ር አባ ዳንኤል፡- ‹‹ዘፈን በምንልበት ጊዜ በአእምሮአችን የሚመጣው ምንድን ነው? በቴሌቪዥን ወይም በሬዲዮ የሚቀርቡት ድምፃውያንና የሚያጅባቸው የተወዛዋዦች ቡድን እንዲሁም የሚያጅባቸው የሙዚቃ መሳሪያ ነውን? ወይስ ወደ ሲኦል የሚወስድ አስፈሪ ኃጢአት ነው? በፊታችን የሚደቀነው … የዚህስ ምክንያቱ ምን ይሆን በማለት ይጠይቃሉ፡፡››
‹‹ሙዚቃ የነፍስ ቋንቋ፣ የፈጣሪ ልዩ ጸጋ፣ የሰው ልጅ ፍቅርን፣ ውበትን፣ ጥበብን የሚገልጽበት ረቂቅ ቋንቋ፣ ጣፋጭ ዜማ ናት …፡፡›› ተብላ የተበየነችውን ሙዚቃን ሐዋርያው ያወገዘበት ትክክለኛ ምክንያቱ ምን ይሆን? በእርግጥስ ቅዱስ ጳውሎስ የተቃወመው ከላይ የገለጽነውን ዓይነት ሙዚቃ ይሆን? እሱን ‹‹ከመግደል፣ ከስካርና ከቅናት፣ ከመናፍቅነትና ከምቀኝነት›› ጋር እንዴት ሊደምረው ይችላል?! ወደ ትክክለኛው ምላሽና ብያኔ ለመድረስ የቅዱስ ጳውሎስ መልእክቶችም ሆኑ ሌሎች የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት በመጀመሪያ የተጻፉት በግሪክ ቋንቋ ስለሆነ ‹‹ዘፋኝነት›› በሚል ቃል የተተረጐመው የትኛው የግሪክ ቃል መሆኑን በጥንቃቄና በሚገባ መርምሮ ማየት ያስፈልጋል ይላሉ ዶ/ር አባ ዳንኤል፡፡
ቅዱስ ጳውሎስ በግሪክ ቋንቋ ‹‹ኮማይ›› ብሎ ያስቀመጠውም ቃል የአማርኛ መጽሐፈ ቅዱስ (የ፲፱፻፶፬ እና የ፲፱፻፸፪ ዓ.ም. ትርጉም) በዘፋኝነት ይተረጉመዋል፡፡ እርግጥ ቅዱስ ጳውሎስ በሚያወግዘው ድርጊት ውስጥ ዘፈንና ሙዚቃ ይኖራል፡፡ ነገር ግን ‹‹ኮማይ›› የሚለው ቃል ከላይ በተጠቀሰው ዘፈን የሚፈታ አይደለም፡፡ ‹‹ኮማይ›› ከልቅ ግብረ ሥጋ ግንኙነት ጋር የሚገናኝ ትርጉም አለው፡፡ ሰዎች ለጣዖት አምልኮ እየበሉና እየጠጡ የሚፈፅሙትን ሕገ ወጥ የዝሙት ኃጢአትን ያመለክታል፡፡ ይህም በሮማውያንና በግሪካውያን ዘንድ ይፈፀም እንደነበር የታሪክ ድርሳናት ይጠቁማሉ፡፡ እንግዲህ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ይህንን ከዘፈን ጋር ተያይዞ የሚፈጸመውን ልቅ ርኩሰት የሚያደርጉ ሰዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም›› ያለበትም ምክንያት አሁን መረዳት እንችላለን፡፡›
ለዚህ ተጨማሪ ማረጋገጫ ከፈለግን የእንግሊዘኛ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞችን መመልከት እንችላለን፡፡ እንግሊዝኛው “ኮማይ” የሚለውን ቃል ‹‹Orgy›› ብሎ ይፈታዋል፡፡ በአንጻሩ በቴሌቪዥን ወይም በሬዲዮ የሚቀርበው ዘፈን ‹‹Song›› የሚባል ይመስለኛል፡፡ በመጨረሻም በአዎንታዊ ትርጉሙ በዘፈን ተፈጥሮን፣ ታሪክን፣ ውበትን፣ ፍቅርን፣ መልካም ነገሮችን ማድነቅ እንደምንችል እናውቃለን፡፡ ያን ደግሞ እግዚአብሔር የሚቃወመው አይመስለኝም፡፡ ስለ ወንድና ሴት ፍቅር መዝፈን ኃጢአት ከሆነ ‹‹መኃልየ መኃልይ ዘሰለሞን›› የተባለውን መጽሐፍ ምን ልንለው ነው?! እሱ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነው፡፡ በየትኛውም ደረጃ ብንተረጉመው በቀጥታም ሆነ በተምሳሌነት የወንድና የሴት ፍቅርን ይገልጻል፡፡
እንግዲህ አስቀድመን ከመፍረዳችን በፊት ምን ዓይነት ዘፈን ብለን መለየት ያስፈልገናል፡፡ ወደ ኃጢአት ይመራል ወይስ ትምህርታዊ መልእክት አለው? ብለን መለየትም ያስፈልጋል፡፡ በ፻፲፰፸፱ ዓ.ም የታተመው የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ በገላትያ ፭፣፳፩ ላይ ‹‹ዘፋኝነት›› ተብሎ የተተረጐመውን ቃል ‹‹ማሶልሶል›› በሚል ቃል ነው የሚተረጉመው፡፡ ሊፈጠር ከሚችለው የምሥጢር መዛባትና የትርጉም አሻሚነት የሚያድን ቃል ይሆን? ወይስ ‹‹መስከር›› የሚለው ቃል ከሁሉም ይሻል ይሆን፡፡ ምክንያቱም የግሪኩ ቃል ቅጥ ማጣትንና መስከርን ይገልጻልና፡፡ በመሠረቱ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው የግዕዙ አዲስ ኪዳን ገላትያ ምዕራፍ ፭ ላይ ዘፋኝነትን ‹‹ስክረት›› እንጂ ‹‹ዘፈን›› ብሎ አይደለም የሚተረጉመው፡፡
የቃላቱን ትርጉም ለማመዛዘን ይረዳን ዘንድ እስቲ የተለያዩ መዝገበ ቃላት ስለ ዘፈን የሰጡትን ትርጓሜዎች ወይም ፍቺዎች እንመልከት፡፡ ስለ ዘፈን የደስታ ተ/ወልድ መዝገበ ቃላት እንዲህ ይላል፡- ዘፈነ፡- ‹‹አቀነቀነ፣ አወረደ፣ ግጥም ገጠመ፣ አዜመ፣ አንጐራጐረ፣ ዘለለ፣ ተረገረገ›› በማለት ሲፈታው የአማርኛ የመጽሐፍ ቅድስ መዝገበ ቃላት ደግሞ ዘፈንን እንዲህ ይተረጉመዋል፡-
‹‹በቅኔና በግጥም ከልዩ ልዩ መሣሪያ ጋር እየተቀነባበረ የሚቀርብ የደስታ ምልክት በልደት ቀን (ኢዮብ ፳፩፣፲፩-፲፪፣ ማቴ. ፲፬፣፮) በሠርግ ቀን (ኤር. ፴፩፣፬ ማቴ.፲፩፣፲፯) በድል በዓል ቀን (ዘጸ. ፳፣፳፩፣ ምሳ. ፲፩፣፴፬፣ ፩ሳሙ. ፲፰፣፮) በመንፈሳዊ በዓል ቀን (፪ሳሙ. ፮፣፲፬)፡፡ ከዚህም ሌላ በልዩ ልዩ የደስታ ቀን ይዘፈናል (ሉቃ. ፲፭፣፳፭)፡፡ በእስራኤል የአምልኮት ሥርዓት ዘፈን (ማኅሌት) ትልቅ ቦታ ይይዝ ነበር፡፡ (መዝ. ፻፵፱፣፫/፻፶፣፬)፡፡ ነገር ግን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ባዕድ አምልኮትንና ዝሙትን የሚያስከትል ዘፈን አልተፈቀደም (ዘዳ. ፴፪፣፮-፲፱፣ ማር. ፮፣፳፩-፳፪)፡፡ እዚሁ ላይ ሐዋርያት ዘፈን የማይገባ መሆኑን ተናግረዋል ይላል፡፡ ነገር ግን ሐዋርያት ምን ዓይነት ዘፈን እንደተቃወሙ አልገለጹም፡፡ አብዛኛዎቹ ጥቅሶች ተቀባይነት ስላለው ዘፈን እንደገለጹ ግን እናስተውል፡፡
ይህ በዘፈንና በዘፋኝነት ዙሪያ ያለው የትርጉም መዛባት የፈጠረውን መደናገርና የትርጓሜ ስህተት ላይ ይህን ያህል ለማየት ከሞከርን፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያለን አንድ ታሪክ ብቻ በማንሳት ሐሳቤን ለማጠናከር ልሞክር፡፡ የክርስትና ሃይማኖት ታሪክ እንደሚነግረን ጌታችን ኢየሱሰ ክርስቶስ፣ እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምና ሐዋርያቱ ዘፍንና ባህላዊ ጨዋታዎች ወደሚስተናገድበት የአይሁድ ሠርግ ላይ ለመታደም እንደሄዱ ወንጌላውያኑ ጽፈውልናል፡፡
ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር የመጣው በአይሁድ ባሕል ውስጥ ተወልዶና አድጎ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡ በዚያ ባሕል የተቃወማቸው ነገሮች እንዳሉ ሁሉ የተቀበላቸውም ነበሩ፡፡ በአይሁድ ሠርግ ላይ ባሕላዊ ውዝዋዜ እንደነበረ ይታወቃል፤ ብሉይ ኪዳንም ሆነ አዲስ ኪዳን ከሠርግ ጋር ስለሚገናኝ ሙዚቃና ጨዋታ ይናገራል፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ ሠርግ ላይ የተገኘው ኢየሱስ በሠርጉ ላይ የነበረውን ዘፈንና ባህላዊ ጨዋታ ተቃውሟል የሚል ንባብ ግን የለም፡፡
በመሠረቱ ይላሉ ዶ/ር አባ ዳንኤል ‹‹ዘፈን ኃጢአትን ነውን›› በሚለው ጽሑፋቸው በመሠረቱ፡- ‹‹ባሕል የሰው ልጅን ከእንስሳት የሚለይ ትልቅ ስጦታ ነው፡፡ ማንኛውም ባሕል በክርስቶስ ወንጌል ትምህርት የሚገመገምና የሚፈተን ሲሆን አስፈላጊነቱን ማመን ግን የግድ ይሆናል፡፡ ጌታችንም በቃና ዘገሊላ ሠርግ ላይ ሲታደም የሠርግ ዘፈን አልነበረም ለማለት አዳጋች ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃልን ስናነብ ስለአይሁድ ባሕል ብዙ ነገር እናገኛለን፡፡ ብሉይና አዲስ ኪዳንን ለመረዳትም ይህንኑ የአይሁድ ባሕል ማጥናት ሊጠቅመን ይችላል፡፡ እንግዲህ እግዚአብሔር እራሱ በአንድ ዘመን በነበረ ባሕል፣ ቋንቋና ሥልጣኔ አማካኝነት መናገሩን አንዘንጋ፡፡›› በማለት ይደመድማሉ ዶ/ር አባ ዳንኤል፡፡
ወደ አገራችን ስንመጣ እንደ የጉራጌኛ፣ የኦሮምኛ፣ የትግርኛ፣ የአማርኛ፣ የወላይትኛ ወዘተ… ባሕላዊ ጨዋታዎችን መመልከትና መሳተፍ ክፋቱ ምንድን ነው፣ የተፈጥሮን ውበትን፣ ታሪክን፣ ፍቅርን፣ ጥበብን፣ ውበትን፣ እውነትን፣ ፍትሕን፣ ነጻነትን፣ ማኅበራዊ መስተጋብርን የሚያወድሱ ዜማዎችን ማቀንቀንም ሆነ ማድመጥ ችግሩ ምኑ ላይ ነው ብለን ልንጠይቅ እንችላለን፡፡ በዚያ ዘፈን፣ ባህላዊ ጨዋታዎችና ውዝዋዜ ከአሥርቱ ትእዛዛት የትኛውን እናፈርሳለን? ከየትኛውስ በደል ሊመደብ ይችላል? ከመግደል ወይስ ከመስረቅ በሐሰት ከመመስከር ወይም ከማመንዘር?

ዜማና መዝሙር በኢትዮጵያ ቤ/ን ታሪክ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ዓለም ገና ስለ ሙዚቃና የዜማ ምሥጢር ማወቅና መነጋገር ከመጀመሩ ከብዙ መቶ ዓመታት በፊትና ጥልቅ የሆነ መንፈሳዊ ዜማ ድርሰት፣ ቀመርና ምልክቶች ምን መሆኑን ሳይደርስበት በፊት በታላቁ ሊቅና ማሕሌታይ በቅዱስ ያሬድ አማካይነት የሰማያዊ ዜማ ባለቤት ለመሆን የበቃች ጥንታዊትና ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ይህን እውነታ በኖርዌይ ትሮንድሄም እ.ኤ.አ በ2007 ዓ.ም. በተካሄደው በ፲፮ኛው ዓለም አቀፍ ኢትዮጵያ ጥናት ኮንፈረንስ ላይ ‹‹The Significance of St. Yared’s Music in the Age of Globalization›› በሚል ርእስ ጥናታዊ ወረቀት ያቀረበው በአሜሪካ ኮሎምቢያ የኦሃዮ ዩኒቨርስቲ ምሁሩ ሊቀ ዲያቆን ክፍሌ አሰፋ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ዜማ ያለውን ረቂቅነትንና ልዩ ውበቱን ሲገልጽ፡-
‹‹የቅዱስ ያሬድ/የኢትዮጵያ ቤ/ን ዜማ እጅግ ጥንታዊ፣ ጥልቅ፣ ከመንፈስና ከነፍስ በሚመነጭ ፍሰትና ልዩ ጥበብ የተፈጥሮን የለሆሳስ ድምፅና የፍቅርን ልዩና ረቂቅ ዜማ የሚያስቃኝ ሰማያዊና ሕያው መንፈሳዊ ዜማ ነው፡፡›› በተጨማሪም ክፍሌ አሰፋ በዚሁ የጥናት ሥራው ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ን ጥንታዊ ዜማ ከእግዚአብሔር ፍጥረታት (ከተፈጥሮ) ጋር በእጅጉ የጠበቀ ምሥጢርና ትስስር እንዳለው የሚከተለውን ሐሳብ ያክላል፡-
‹‹Ethiopian liturgical music is quite unique; those who listen carefully will recognize the haunting sounds of mother nature.›› ይህ ለሺሕ ዓመታት የዘለቀው የቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ ዜማና የአምልኮተ እግዚአብሔር ሥርዓት ዛሬ ዛሬ እየተበረዘ ነው የሚሉ ታዛቢዎችን በብዛት እያስተናገደ ነው፡፡
በተለይ በዘመናችን ወጣት ዘማሪያን እያወጧቸው ያሉ መዝሙሮች በአብዛኛው ምድራዊ ምኞቶችና ፍላጎቶች ላይ የሙጥኝ ያሉ፣ የጌታችንና መድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የመስቀሉን ውለታና ፍቅር ኃላፊና ጠፊ በኾነ ምድራዊ ሀብትና ክብር የሚያነጻጽርና የሚለካ፣ በአብዛኛው ገበያ ተኮር የሆኑ፣ በእጅጉ ዓለማዊነት ያየለባቸው፣ ለጸሎትና ለተመስጦ እንዲሁም ልዩ ምሥጢር ላለው ሰማያዊና ዘላለማዊ ሕይወት መንፈስንና ነፍስን ወደወዲያኛው ዓለም ለማሻገር አቅም የሚያነሳቸው፣ ደካማና ልፍስፍስ ናቸው … የሚሉ ብርቱ ትችቶችን እያሰተናገዱ ይገኛል፡፡
ለዚህ በቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ ምሁራን ዘንድ ዘማሪዎቻችን ከቅዱስ ያሬድ ዜማ እየወጡ ነው፣ የመዝሙሮቻቸው ግጥሞችም መንፈሳዊ ምሥጢር የማይንጸባረቅባቸው፣ ግልብና የይድረስ የይድረስ እየሆኑ ናቸው የሚለው ትችት የተጋነነና እውነታውን የሳተ ነው የሚሉ አንዳንዶች የራሳቸውን የመከራከሪያ ሐሳብ እንዲህ ሲሉ ያቀርባሉ፡፡ የቅዱስ ያሬድ መንፈሳዊ ዜማ፡- ልዩ፣ ሰማያዊና ረቂቅ ቢሆንም ከእርሱ ወዲያ በተለያዩ ጊዜያት የተነሡ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት የእርሱን ዜማ አመስጥረውና አራቀው እንደተጠበቡበትና በአዲስ የምስጋና ዜማና ሰማያዊ ቅኔ አምላካቸውን በመላእክት ሥርዓት እንዳመሰገኑት፣ እንዳወደሱትና እንዳመለኩት አጥብቀው ይሞግታሉ፡፡
ለአብነትም ያህል ይላሉ እነዚሁ ተከራካሪዎች በቤተ ክርስቲያናችን የቅዳሴ ዜማ ታሪክ የደብረ ዓባይ፣ የሰደል ኩላ፣ የአዲስ አበባ ዜማ … ተብለው የሚጠሩ የቅዳሴ ዜማዎች መኖራቸውን እንደ መረጃ በመጥቀስ ከቅዱስ ያሬድ ዜማ ወጥታችኋል የሚለው መከራከሪያ ውኃ የሚያነሳ አይደለም፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን ሀብት የኾነው የቅዱስ ያሬድ ዜማ በተለያዩ ዘመናት በተነሡ አባቶቻችን መሠረታዊ ይዘቱን ሣይለቅ መሻሻል ተደርጎበታል፡፡ እንዲሁም በቤተ ክርስቲያናችን የማሕሌት ስርዓት እንኳን እውቁ የ፲፱ኛው መቶ ክ/ዘመን ኢትዮጵያዊው ምሁር አለቃ ገብረ ሃና ለልጃቸው ለተክሌ በመኖሪያ አካባቢያቸው ያሉ ሸንበቆና ደንገል በንፋስ አማካኝነት የሚያደርጉትን ውዝዋዜ በማየት ያስተማሩት የአቋቋም ሥርዓት ‹‹የተክሌ አቋቋም›› በሚል የቤተ ክርስቲያናችን ሀብት ሆኗል፡፡
በተጨማሪም ይላሉ እነዚሁ አስተያየት ሰጪዎች የጎንደር አቋቋም፣ አስደማሚው የጎጃሙ አጫብርና ቆሜም የማሕሌት ሥርዓት ሌላው የምንኮራበት መንፈሳዊ የቤተ ክርስቲያናችን ሀብታት ናቸው፡፡ ስለሆነም ከቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓትና ትውፊት ሳናፈነግጥ በቅዱስ ያሬድ ጥልቅና መንፈሳዊ ዜማ እየተመሰጥንና እየተደነቅን ዛሬም ወደፊትም ደግሞም ለዘላለም በአባታችን ቅዱስ ያሬድ መንፈስ አዲስ ዜማ፣ ልዩ የምስጋና ቅኔን ለአምላካችን እናመጣለን፣ እንሠዋለን ሲሉ ይደመጣሉ፡፡
እንደውም ይህ ዘመን ይላሉ እነዚሁ ተከራካሪዎች በቤተ ክርስቲያኒቱ የቅርብ ታሪክ ዘመናት ውስጥ ‹‹የመዝሙር አብዮት›› የተከሰተበት ተብሎ ሊጠራ የሚችል ነው ሲሉ የእውቁን የቅኔ መምህርና ሰባኪ ወንጌል መጋቢ ሐዲስ መምህር እሸቱ አለማየሁን አገላለጽ በመዋስ ይህ አዲስ ‹‹የዝማሬ አብዮት›› ብዙዎችን የቤተ ክርስቲያኒቱን ምእመናኖች፣ ወጣቶችን እየማረከና አርቲስቶቻችንም ከዘፈን ዓለም ወደ ዘማሪነት ክብር እያፈለሰ ያለ የለውጥ ሂደት ነው ሲሉ በኩራት ሲናገሩ ይደመጣሉ፡፡
ስለሆነም ይህ በቤተ ክርስቲያኒቱ የተከሰተው ‹‹አዲስ፣ ልዩ የምስጋና፣ የዝማሬ ቅኔ ማዕበል›› እንደ ዘርፌ ከበደ ያሉትንና አሁንም ደግሞ ታዋቂዋን አርቲስት አቦነሽ አድነውን ወደ ዘማርያኑ ጎራ እንዲቀላቀሉ ያስቻለ ነው፡፡ ስለሆነም ይህ ሰማያዊ ቅኔ፣ ይህ ልዩ መንፈሳዊ ምስጋና ገና ብዙዎችን ወደ እናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይጠራል፣ ያፈልሳል ሲሉ ይናገራሉ፡፡
ምናልባት በዚህ የመዝሙሮቻችን ዜማና ግጥሞችና እንዲሁም ተያያዥ ጉዳዮች ላይ እየተካሄዱ ላሉ ክርክሮችና ሙግቶች፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ያሉ የዜማ ሊቃውንትና ምሁራን የጠራ አቋምና ግንዛቤ ይኖረን ዘንድ የሚያስችል ሙያዊ የሆነ ትንታኔ ሊሰጡበት ይችላሉ ብዬ እገምታለሁ፡፡ እኔ ግን የተነሣሁበትን ‹‹አርቲስት አቦነሽ አድነው ከዘፋኝነት ወደ ዘማሪነት›› በሚል ርእስ የጀመርኩትን አዲሱን የአቦነሽ አድነውን መዝሙሮች አጭር ዳሰሳ በዛሬው ጽሑፌ ላካትተው አልቻልኩም፡፡ በቀጣይ ጽሑፌ አርቲስቷ በዝማሬዎቿ ያነሳቻቸውን መንፈሳዊ መልእክቶችና የግጥሞቹን ይዘት በተመለከተ የሚያትተውን መጣጥፌን በቀጣይ ሳምንት እንደምመለስበት ቃል በመግባት ልሰናበት፡፡

ሰናይ ሳምንት!!

Tuesday, October 15, 2013

«እስኪ በቁጣ ሳይኾን በጥሞና ነገሩን አስተውሉት!»

(ይህ ጽሁፍ በአባ ሰላማ መካነ ድር ላይ አንድ አስተያየት ሰጪ ያቀረበው ሲሆን ስለማኅበረ ቅዱሳን ወቅታዊ ሁኔታ በአጭሩ ስለገለጸ ማቅረቡን ወደነዋል።)

የማኅበረ ቅዱሳንና ደጋፊዎቹ ትልቁ ችግር ይኽ ይመስለኛል፡፡ አንደኛ፣ የነገረ መለኮት ዕውቀት የላቸውም፡፡ ኹለተኛ፣ ራሳቸውን የቤተክርስቲያን ወታደሮች አድርገው ይስላሉ፡፡ እነርሱ የቤተ ክርስቲያቱ ወታደሮች ናቸው የሚለውን ሐሳብ የተቀበለ ኹሉ ከእነርሱ ጋር የማይተባበር ኹሉ የቤተ ክርስቲያን ጠላት ነው የሚለውን አቀንቅኖት መቀበሉ አይቀርለትም፡፡ “ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን ጠበቃ ነው! የቤተ ክርስቲያኒቱ የመከላከያ ሠራዊት ነው!” የሚለው ዐረፍተ ነገር በራሱ የጽንፈኝነት ወጥመድ አለበት፡፡ ምክንያቱም ጠበቃ የምንፈልገው የተጠቂነት ፍርኀት ሲኖርብን ነውና፡፡ ምናልባት ይኽ ነገሮችን ጥቁር ወይም ነጭ ብቻ ናቸው ከሚለው ጽንፈኝነት ከሰፈነበት ባህላችን የተወለደ ይመስለኛል፡፡ አለማወቅ ላይ ፍርኀት ሲጨመርበት ጽንፈኝነት መወለዱ አይቀርም፡፡ (ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን “ምስክሮቼ ናችኹ፡፡” እንጂ “ጠበቆቼ ናችኹ፡፡” አላለም፡፡)
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት አላስተዋለው እንደኾነ እንጃ እንጂ የተናገረው ነገር የማኅበረ ቅዱሳንን ጽንፈኝነት በደንብ ያሳያል፡፡ ማኅበሩንም በመንግሥት በደንብ ሊያስመታው ይችላል፡፡ እኛ የምንለውን የማይሉ፣ በእኛ ቅኝት ያላቀነቀኑ ኹሉ የቤተ ክርስቲያኒቷን ህልውና ለማጥፋት የሚታገሉ ናቸው ከማለት በላይ ጽንፈኝነት አለን? ዳንኤል ይኽን በማለቱ የማኅበሩን እውነተኛ ማንነት ዐደባባይ አውጥቶታል፡፡ ጽንፈኛ ደግሞ ከራሱ ውጪ ማንንም ለመስማት ፈቃደኛ አይደለም፡፡

Friday, October 11, 2013

«የማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች የሰሞኑ የአዞ እንባ የማኅበረ ቅዱሳንን ማንነት አይለውጠውም»


አንዳንዶች ማኅበረ ቅዱሳንን ስናነሳ ለምን ተነክቶ በሚል ቁጣ ወባ እንደያዘው ሰው ይንዘፈዘፋሉ። በእርግጥ በማኅበሩ የድንዛዜ መንፈስ የተወጉ ሰዎች እንደዚያ በመሆናቸው ከያዛቸው የወባ ዛር የሚያድን ምሕረት እንዲመጣላቸው እንመኝላቸዋለን እንጂ አንፈርድባቸውም። ሌላው ቀርቶ ማኅበሩ ራሱ ከእውነት ጋር ታርቆና ራሱን በንስሐ ለውጦ ከስለላና ከከሳሽነት ማፊያዊ ሥራ ተላቆ ቤተ ክርስቲያኒቱን ለራሱ አቋም ከመጠምዘዝ ቢታቀብ ሁላችንም አብረነው በቆምን ነበር።  ከወንጌል እውነት ጋር እየተላተመ በተረት ዋሻ ሥር አናቱን ቀብሮ ከኔ ወዲያ ለቤተ ክርስቲያን ጠበቃ የለም ከሚለው ትምክህት ቢወጣ እንዴት ባማረበት ነበር። ዳሩ ግን ማኅበረ ቅዱሳን ገና ከመሠረቱ የቆመበት የህልውናው መንፈስ በደምና በማስመሰል በመሆኑ ከዚያ አቋሙ ፈቀቅ ይላል ተብሎ አይታሰብም። ጉዳዩ የታጠቀው የእልህና የበቀል መንፈስ እስኪያጠፋው ድረስ አይለቀውምና ሄዶ ሄዶ መጨረሻው እስከዚያው ድረስ መሆኑን ደጋግመን ስንለው ቆይተናል። ያ ሰዓት የደረሰበት መሆኑን ያሸተተው ይህ ማኅበር በቀንደኛ ሰዎቹ በኩል የአዞ እንባውን ማፍሰስ ጀምሯል።

 ከማኅበሩ ቀንደኛና ተላላኪ ሰዎቹ መካከል ታደሰ ወርቁ፤ ዳንኤል ክብረት፤አባ ኃይለማርያም( የጵጵስና ተስፈኛው)፤ ሐራ ዘተዋሕዶና አንድ አድርገን ብሎጎች የመሳሰሉት ሁሉ እየተቀባበሉ የቃጠሎው እሳት የደረሰባቸው ያህል የአድኑን ጩኸታቸውን ሲያሰሙ እያየን ነው። የሁሉም ጩኸት በአጭር ቃል ሲገለጽ በክርስትና አክራሪነት ቦታ የለውም ወይም ለማኅበረ ቅዱሳን ይህንን የመሳሰለ ስም ሊጣበቅበት ተገቢ አይደለም የሚል ድምጸትን የያዘ ሆኖ አግኝተናል። ይሁን እንጂ ሰዎቹ በገደል ማሚቱ ድምጻቸው እየተቀባበሉ እውነታውን ለማዳፈን ቢፈልጉም እውነቱ በማስረጃ ሊገለጥ ይገባዋልና በዚህ ዙሪያ ጥቂት የምንለው አለን። ይከተሉን።

1/ ክርስትና፤

ክርስትና ክርስቶስ የሞተለት እምነት ስለሆነ ከሚሞቱለት በስተቀር ሌሎችን ሊገድሉለት፤ ሊደበድቡበትና ሊያሳድዱበት የተገባው ስላይደለ በእርግጥም ክርስትና ወግ አጥባቂነት፤ አክራሪነትና፤ ጽንፈኝነትና አይመለከተውም።

Monday, July 22, 2013

የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ጉዞና ልምላሜ የተለየው ዛፍ አንድ ናቸው!

አዲስ አበባ የሀገሪቱ ርእሰ መዲና እንደመሆኗ መጠን የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት በገንዘብ፤ በባለሙያና በሠራተኛ አቅም ትልቁ ሀገረ ስብከት ነው። በዚህ ሦስት ተቋማዊ አቅም በአግባቡ መጠቀም ከተቻለ ለሌሎች ሀገረ ስብከቶች የሚተርፍ በቂ ኃይል ያለው ሀ/ስብከት ነው። የርእሰ መዲናይቱ ሀ/ስብከት እንደመሆኑ መጠን የተሻለ ሥራ፤ ክፍያና ኑሮ ለማግኘት ከገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን የሚፈልሰው አገልጋይ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል። የሚያሳዝነው ግን አዲስ አበባ ከተማ ከተኛችበት እየነቃች እዚህም እዚያም ጉች ጉች ብለው የሚታዩት ግንባታዎችና የተዘረጉ መንገዶች ለአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ለውጥ ምን እንደሚመስል ለማየት የሚያስችል ዐይን እንዲኖረው የፈየደለት ነገር አለመኖሩ ነው። የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት አስተዳደር ወደኋላ መሄድ ከጀመረ ዓመታት ተቆጥረዋል። ዛሬም የሚታይበት አንዳች እንቅስቃሴ የለም። ለውጥ የሂደት ክስተታዊ ግዴታ ቢሆንም ይህ አመክንዮ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ለምን እንዳልጎበኘው ግራ ያጋባናል። ምናልባት እንደ ቀንድ አውጣ የዐርባ ዓመት እንቅልፉን አልጨረሰ ይሆን? ጊዜ ደግሞ ታክሲ አይደለም። ጊዜ ሲሄድ ባለበት ከሚቆመው ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት በስተቀር።
የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ተቋማዊ የኋሊዮሽ መንገድ ስንገመግም ቤተክርስቲያኒቱ የት እንዳለች ፍንጭ ሊሰጠን ይችላል። እነማን ቤተ ክርስቲያኒቱን እየመሯት እንዳሉ ያመላክተናልም። በሌላ ቋንቋ ቤተ ክርስቲያኒቱን የ40 ዓመት የቀንድ ዐውጣ እንቅልፍ ውስጥ እንደገባች የተቀመጡባት ሰዎች አመራር ይጠቁመናል። ዋልታ የሌለው ጣሪያ በአናቱ ዝናብ ማስገባቱ አይቀርምና ለጣሪያው መበስበስ የአናቱ ክፍተት ምክንያት ከመሆኑ ውጪ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል? የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት መበስበስ የላይኛው ጣሪያ የመበስበሱ ምልክት ተደርጎ ቢወሰድ አያስኬደንም ትላላችሁ?
የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን የበሰበሰ ጣሪያ ለመጠጋገን ብዙ ተሞክሯል። መጽሐፉ እንደተናገረው በአሮጌው አቁማዳ ላይ አዲስ ለመጣፍ እየተሞከረ መበጣጠሱን የከፋ አደረገው እንጂ የተቀየረ አንዳች ነገር የለም። በእነ እገሌ ዘመን የነበረው አስተዳደር ጥሩ ነበር እንዳንል የሁሉም ዘመን ችግር በመጠን ከሚበላለጥ በስተቀር በይዘቱ አንድ ነው። በእርግጥ ይዘቱ መጠኑንና ዓይነቱን ጨምሮ ዛሬ ሀ/ስብከት ሳይሆን «ኃላፊነቱ የተወሰነ የነጣቂዎች ማኅበር» ወደመሆን በመሸጋገሩ ከድሮዎቹ አስተዳደር ዛሬ የከፋ ደረጃ ላይ መድረሱ እውነት ነው። አንዱን ሾሞ አምሮቱ ሲጠረቃ ሌላ ያልጠረቃ በመሾም ችግሩን በማባባስ በኩል ያ! ያልታደለው ሲኖዶስ ለሀ/ስብከቱ ውድቀት ትልቁን ድርሻ ይወስዳል። ምክንያቱም ሲኖዶሱ ያልጠረቃውን በጠረቃው አመራር በማለዋወጥ ካልዘሩበት የሚያጭዱ ነጣቂዎችን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በማኅበር አደራጅቶ ባልለቀቃቸውም ነበር። 

ለዚህ ጥሩ ማሳያ የሚሆነን ንቡረ እድ መምህር ገ/ማርያም ገ/ሥላሴ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ እያሉ አውድማውን ሳያሄዱ የተመረተውን ዝም ብለው የሚቅሙ አጋሰሶችን አፍ በመዝጋታቸው ብቻ በእህል በሎች ክስ ባላባረሯቸውም ነበር። የሆነው እውነታ ግን ጠርጎ በሎችን መረን ለቆ፤ «ሊሰራ የማይወድ አይብላ» ብለው የታገሉትን ጠንካራ ሰው ባላባረረም ነበር። ድሮስ ጠርጎ በልን ሊታደግ የሚችለው ከጠርጎ በል በቀር ማን ሊሆን ይችላል?
የንቡረ እድ ገ/ማርያም ገ/ሥላሴ ወንጀል የቤተ ክርስቲያኒቱን ሙዳየ ምጽዋት ዘረፋ ማስቆም መቻላቸው ነበር። ከ200 ሺህ ብር በላይ ተቆጥሮ የማያውቀው የመንበረ መንግሥት ቅ/ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ  ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ የተቆጠረው በንቡረ እድ ገ/ማርያም ክትትል መሆኑ ታሪክ መዝግቦታል። የሌሎቹም አድባራት ሙዳየ ምጽዋት ሣጥኖች እየተዘቀዘቁ ከመገልበጥ የተረፉት በኚሁ ሰው አስተዳደር ዘመን ስለመሆኑ ገልባጮቹ ሳይሆን አገልጋይ ካህናቱ የሚናገሩት እውነታ ነው። ምን ያደርጋል ታዲያ? እውነተኛና ሀቀኛ እርሟ የሆነችው ቤተ ክርስቲያን ንብረ እድ ገ/ማርያምን ከአዲስ አበባ ወደሽሬ  በመወርወር ሲኖዶሱ ቁጭቱን ተወጣባቸው። ገልባጮችንም አስደስቷል። አባ ገ/ማርያም ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት መነሳታቸውን የሰሙ ምሽት ሙዳየ ምጽዋት ገልባጮች ሻምፓኝ ሲራጩ ማደራቸው ተሰምቷል። እንግዲህ ይህ ክፍል ነው በመበደሉ ምክንያት ሲኖዶሱ በነፍሱ የደረሰለት። አሳዛኝ ዘመን?
ዛሬ ደግሞ በፓትርያርክ ማትያስ ምርጫ ላይ የአንበሳውን ድርሻ የወሰዱት አባ እስጢፋኖስ ለፈጸሙት የታማኝነት አገልግሎት ከፓትርያርኩ በገጸበረከትነት የቀረበላቸው ስጦታ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሲሆን በፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስነት ሽፋን ተዝቆ የማያልቀውን ካዝና የድርሻቸውን እንዲናኙ  ተመድበው እነሆ ከመነሻው በስመ ሥልጠና ሽፋን ተረክበው እያመሱት ይገኛሉ። የሚያሳዝነው ደግሞ ገና ምኑንም ሳይጀምሩ አባ እስጢፋኖስ አድባራቱን ገንዘብ አዋጡና ወደ ሀገረ ስብከቱ ገቢ አድርጉ እያሉ ሥልጠና በተባለው አሰልቺ መድረክ ላይ ነጋ ጠባ መጮሃቸው ነው። አዋጡ ማለት ምን ማለት ነው? ፐርሰት ክፈሉ ነው? ወይስ የሀ/ስብከቱ ጽ/ቤት የሚጦራቸው ድኩማን አሉት? ጥያቄውን ለአቡኑ እንተውና ከአዋጡ ጭቅጨቃቸው የምንረዳው እውነታ ቢኖር ሀ/ስብከቱ ዛሬም ፈውስ የራቀው መሆኑን ነው። ሥልጠና በተባለው የጩኸት መድረክ ላይ ሥልጠናውን የሚካፈሉት እነዚያው የቤተ ክርስቲያንን ሙዳየ ምጽዋት የሚገለብጡ ሰዎች መሆናቸውን ስናይ አቡኑ አዲስ ነገር መጀመራቸውን በማሳየት በቀደመው ጎዳና ለመሄድ ያቀዱት ስላለመሆኑ የሚያሳምን አንዳች  ሥር ነቀል ተቋማዊ ለውጥ አለመኖሩ ቁልጭ ብሎ ይታየናል።  ስልጠና በተለወጠ ሰውና ለለውጥ በተዘጋጀ አእምሮ ላይ የሚዘራ ዘር እንጂ የለውጥ መንገድ እንቅፋት ሆኖ በቆየና በጨቀየ አእምሮ ላይ ሲሆን ስናይ ረዳት ሊቀጳጳሱ ወይ ስራውን አያውቁትም፤ ወይም ስራው አያውቃቸውም።
 አቡነ ቀውስጦስ የሀ/ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ሳሉ በተጠናወታቸው ዘረኝነት የጎጣቸውን ሰዎች እያመጡ ሲሰገስጉና ሲያሳድጉ ንቡረ እድ ገ/ማርያም በሩን ዘግተ አላሳልፍ ስላሏቸው ብቻ በሲኖዶስ ጉባዔ ላይ ከሳሽ ሆነው መገኘታቸውን አንዘነጋውም። ዛሬም አቡነ እስጢፋኖስ የንቡረ እድ ገ/ማርያምን ወደ አዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅነት ዳግም የመመለስ የካህናት ጥያቄ አልቀበልም ያሉት ንቡረ እዱ እጅ ከወርች አስረው ረጅም እጆችን ሁሉ ስለሚያስቆሙ ከወዲሁ የተወሰደ መላ መሆኑ ይገባናል። አቡኑ ሙስናን የሚዋጉ ከሆነ ምነዋ! የሙስናውን በር ድርግም አድርገው የዘጉትን ንቡረ እድ በሥራ አስኪያጅነት ማስቀመጥ ፈሩ? በእርግጥ አቡኑ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሳሉ ጥንቱኑ በሩን የከፈቱት እሳቸው አይደሉ እንዴ? ስለሆነም ሙስናን የመዋጋት ብቃትም፤ ሞራልም የላቸውም። ስልጠና መልካም ቢሆንም ሙስና በስልጠና አይጠፋም። ሙስናን በሚጠየፍና ለመዋጋት በተዘጋጀ አመራር እንጂ በገንዘብ አዋጡ ስልጠና ሊሆን አይችልም። የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ጽ/ቤትም ይሁን አድባራቶቹ በእነማንና በተደራጀ አዲስ አመራር ተዋቅሯል?
 ሙስናው ከዐለማውያኑ በዐይነቱ የከፋ ሆኗል። አፍኒንና ፊንሐሶች ተፈልፍለዋል። ሁሉም በዐመጻው ተካክሏል። ጠቅላላው ታማሚ በመሆኑ መድኃኒት የሚሆን ነገር ርቋል። ለዓለም ትተርፍ ዘንድ አደራ የተጣለባት ቤተ ክርስቲያን በባላንጣ ተወራለች።  አሳዛኝ ዘመን!
የሚገርመው ደግሞ ሰሞኑን ከጳጳሱ እግር ከሥር ሥራቸው ቱስ ቱስ የሚሉ የማኅበረ ቅዱሳን አሸርጋጆችን ስንመለከት  በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ውስጥ እንደፈለጉ ለመፋነን እድል ማግኘታቸው ጠቋሚ ሲሆን የሚፈሩትን ማኅበር ለማገልገል ግንባራቸውን እንደማያጥፉ  የሊቀ ጳጳሱ የቆየ ልምድ ደግሞ ያረጋግጥልናል። ከወዲያ ፓትርያርክ ማትያስ በቀጥታ መስመር በውዳሴና በተጠናው ደካማ ጎን በኩል በለስላሳ ጥበብ ተይዘዋል። ከወዲህ አቡነ እስጢፋኖስ በረዳት ሊቀ ጳጳስነት ተጠፍንገዋል። በመሀከል የሲኖዶስ ጸሐፊው የማቅ ታማኝ አባል አባ ሉቃስ ተቀምጠዋል። ጥሩ የመድረክ አዳማቂ የነበሩት አቡነ ጢሞቴዎስ ለማኅበሩ ያበረከቱት አስተዋጽኦ ለምርቃት ሳይበቃ በጎዶሎ ቀን ከኮሌጅ ተማሪዎች ጋር ተጋጭተው ከሥፍራ ተወግደዋል።  ያገለገሉትን መለስ ብሎ የማያየው ይህ ማኅበር ከአባ ጢሞቴዎስ ጋር ራሱ ተጣልቶ ከመለያየት የገላገለው የተማሪዎቹ ግርግር ሳያስበው መከሰቱ ነበር። ከጀርባም ሆኖ የተማሪዎቹን ችግር በማራገብ ነዳጅ ያርከፈክፍ የነበረው ይህ እድል ሳያልፈው ለመጠቀም ካለው ፍላጎት የመነጨ ነበር። ያሰበው በተማሪዎቹ ችግር ጀርባ ፍጻሜ አገኘ።  ከዚህ የተነሳ ማኅበሩ በትኩስ በትኩስ ምድብተኞች ለመገልገል እድል ያረግድለታል ወይም  አካሄዱን ያውቅበታል። ይኸው እንደ ሳሙና እየተሙለጨለጨ ዛሬ ላይ ደርሷል። ከዚህ በፊት ውጥረት ሲበዛበት የዐባይን ቦንድ እገዛለሁ እስከማለት መድረሱ እንደሳሙና በመሙለጭለጭ ላለመያዝ መሄድ የሚችልበት ስልት ረቂቅ መሆኑን ያሳያል።
ከላይ እያልነው እንደመጣነው በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ውስጥ  ዛሬም አዲስ ለውጥ የለም። በላተኞች ስልጠና እየወሰዱ ከመሆኑ በስተቀር አዲስ የሥራ ኃይል፤ አዲስ የመዋቅር ለውጥ የለም። አሁንም የታመነባቸው፤ የሚታወቁና የተመሰከረላቸው ሰዎች በለውጥ ሂደቱ ውስጥ የሉም። በአምናውና በካቻምናው በሬ አርሶ ምርት መጠበቅ ከቶ እንዴት ይቻላል? ካልዘሩበት ማጨድ ማለት ይህ ነው።
ሁለት ወገኖች ግን ተጠቃሚዎች ይሆናሉ። ሀ/ስብከቱ በፓትርያርክ ማትያስ የተሰጣቸው ሽልማት ሲሆን ከዚህ በሚገኘው ሲሳይ የሚናኙት አዲሱ ሊቀ ጳጳስና ከአባ ጳውሎስ ሞት በኋላ ታማኞቹ ብቻ ቦታ ቦታቸውን የያዙለት ማኅበረ ቅዱሳን ተጠቃሚዎች ናቸው።
ከዚህ በተረፈ ሀ/ስብከቱ ከሕመሙ ይድናል ብለን እንድንጠብቅ የሚያደርገን የሚታይ አዲስ መንፈስ፤ አዲስ መዋቅር፤ አዲስ የአሰሪና ሰራተኛ ግንኙነት፤ አዲስ የውጤት ምዘና ስልት፤ አዲስ የልማት እቅድ የለም። ካህናቱ ከላይ የሚፈሰውን መመሪያ እንደቧንቧ ከሚጠጣ በስተቀር በሂደቱ ላይ ወሳኝ አካል ተደርጎ አልተወሰደም። ጉዞው ከየት ወደየት? ነው ብንል ከድጡ ወደማጡ ነው መልሳችን። ገንዘብ አዋጡ፤ ገንዘብ አዋጡ! ድሮም ዛሬም ከሀ/ስብከቱ ውስጥ ያልጠፋ የበላዮች ድምጽ አልቀረም። ዛሬ ላይ ይህንን እንደዘገብን አምላክ ቢፈቅድ የዛሬ ዐመትም እንዲሁ የለውጥ ያለህ ብለን እንዘግብበት ይሆናል። የዚያ ሰው ይበለን!

Wednesday, June 5, 2013

የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት እንዲሰነጣጠቅ ሲኖዶስ የወሰነው ለምንድነው?( ከዚህ በፊት የቀረበ ጽሁፍ)

            መንበረ ፓትርያርክ ቅ/ማርያም ቤ/ክ 1921 ዓ/ም (ፎቶ ምንጭ፤ ሰሎሞን ክብርዬ) 
          
ይህንን ጽሁፍ በጥቅምት/2004 ዓ/ም ሲኖዶስ ማብቂያ ላይ በዚሁ መካነ ጦማራችን አውጥተን ነበር። ዛሬ እንደገና መድገም ያስፈለገን በወቅቱ ቅዱስ ሲኖዶስ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን አራት ቦታ መከፋፈሉን በመቃወም ፤ ተገቢ እንዳልሆነና ጥናት ያልተደረገበት አሠራር ስለሆነ ውጤቱ ኪሳራ መሆኑን አመልክተን የነበረው በትክክል እንዳልነው ውጤቱ ኪሳራ ሆኖ በመገኘቱ ቅ/ሲኖዶስ በ2005 ዓ/ም ጉባዔው  ከግብታዊ ውሳኔው በመውጣት ሀገረ ስብከቱን ወደነበረበት ሲመልስ በማየታችን ነው። አሁንም ደግመን የምንለው የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ወደነበረበት የቀድሞ ተቋማዊ መልኩ መመለስ ብቻ ሳይሆን የሥልጣን ክፍፍል እንዲኖረው ማስቻል ገና የሚቀረው ሂደት ነው እንላለን። ይኸውም የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት በሠራተኛ ብዛት፤ በገቢ አቅም፤ በማዕከላዊ ተቋምነቱ ሠፊና ትልቅ ሀ/ስብከት ስለሆነ ሥልጣንን ሁሉ አንድ ቦታ ሰብስቦ እንዲይዝ የሚያደርገው ሁኔታ ስላለ ከሙስና፤ ከአድልዎ፤ ከፍትህና ውሳኔ አሰጣጥ መዛባት አንጻር ለቁጥጥር የማያመች፤ የአሰራር ዝርክርክነት የሚያስፋፋ ችግር እንደበፊቱ ተመልሶ ሊመጣ ስለሚችል ሥልጣን መከፋፈል አለበት እንላለን። ይህንንም የሥልጣን ክፍፍል በታወቀና በተወሰነ የአሠራር ደንብ ላይ ተመርኩዞ በወረዳዎች ደረጃ ወደታች መውረድ ይኖርበታል። ስለሆነም እንደእኛ እምነት ሀገረ ስብከቱን በአራት የወረዳ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በተሟላ አደረጃጀት አዋቅሮ ሥልጣን  መውረድ ካልቻለ ከችግሮች አዙሪት አለመውጣት ብቻ ሳይሆን ሀ/ስብከቱ የትናንሽ መንግሥታት ቢሮ ከመሆን አይዘልም። ሀገረ ስብከቱን ወደነበረበት ተቋማዊ አደረጃጀቱ መመለስ  ማለት የሥልጣን ጡንቻውን እንደገና አንድ ቦታ ማፈርጠም ማለት ሳይሆን ሥራን ከፋፍሎ ለመሥራት ያለመና የተሻለ ርእይ የያዘ መሆን ስለሚገባው አሁንም ይህ ይፈጸም ዘንድ ከችግሮች በፊት አበክረን እናሳስባለን።
በወቅቱ የሀ/ስብከቱን ክፍፍል በመቃወም ያወጣነውን ጽሁፍ ለማስታወስ ቀንጭበን ከታች አቅርበናል።

 ከዚህ ውስጥ ዋነኛውና አስደናቂው ውሳኔ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ሰነጣጥቆ የማጠናቀቁ ሂደት አንዱ ነበር።
የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ችግር ጠንቅቆ የሚያውቅ የሲኖዶስ አባል የለም። ጳጳሳቱ የተመደቡባቸውን ሀ/ስብከቶች ለሥራ አስኪያጆቻቸው አስረክበው ሁለትና ሦስት ወራት ከአዲስ አበባ ቤቶቻቸው መሽገው ወለተ ማርያምንና ገ/ማርያምን እያሳለሙ እንደሚቀመጡ ይታወቃል። ግድ እየሆነባቸው እንጂ ሐዋርያዊ ተልእኰ ለመፈጸም ዝግጁዎቹ ጥቂቶች ናቸው። ስለዚህ አብዛኛዎቹ ጳጳሳት በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ለመመደብ ያላቸው ፍላጎት ጫን ያለ ነው። ይህንኑ ጽኑ ምኞት ለመተግበር የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ከፓትርያርክ ጳውሎስ ልዩ ሀ/ስብከትነት  በማላቀቅ 4 ቦታ እንዲከፈልና 4 ሊቃነ ጳጳሳት ሊመደቡበት ይታገሉ እንደነበር ያለፉት ጉባዔያቶቻቸው ያስረዱናል። ተፈላጊው ነገር የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ችግሮች ምን እንደሆኑ በማወቅ መፍትሄ ለማምጣት ሳይሆን የአቡነ ጳውሎስን ስልጣን ከሀ/ስብከቱ ላይ በመቀማት 4 ጳጳሳት ተመድበውበት የሞቀ የደመቀውን በማግኘት ከክፍለ ሀገር ሀሩርና አቧራ ለመገላገል ብቻ ነበር። የሚገርመው ነገር ዛሬ አቡነ ጳውሎስ በሌሉበት ሁኔታ ውስጥ ፍላጎታቸውን ተግባራዊ ለማድረግ መቻላቸው ሳይሆን ለምን? እንዲከፈል እንደተፈለገ አለማወቃቸው ነው። ምክንያቱም ሀ/ስብከቱን እንደዓይናቸው አምሮት ከመሰነጣጠቃቸው በቀር ለምን መሰነጣጠቅ እንዳስፈለገ የተናገሩት አሳማኝና ጥናታዊ መረጃ ያለውን ዝርዝር ነገር ሲነግሩን አለመደመጡ ነው። እንደ ደጀብርሃን ብሎግ እምነት የአዲስ አበባ ሀስብከት መሰንጠቅ የተፈለገው በሁለት ምክንያት እንደሆነ ከፍላጎቶቻቸውና ከዓላማዎቻቸው አንጻር እንረዳለን።
1/ ከሚመጣው ፓትርያርክ ልዩ ሀ/ስብከትነት ነጻ በማውጣት ለሚመደቡ ጳጳሳት ልዩ የደስታ ግዛት ለመፍጠር፤
2/ ለአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የአንድ ሰው ግዛት አድርጎ ከማቆየት ይልቅ ከፋፍሎ ለሌሎችም ቶሎ እንዲዳረስ ለማስቻል ነው ብለን እንገምታለን። ምክንያቱም መሰነጣጠቅ ያስፈለገው ምን ለማምጣት እንደሆነ አሳማኝ ነገር አለመቅረቡ ነው።
በኛ እምነት የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት መሰንጠቅ ትክክለኛ ያልሆነ ውሳኔና የሀ/ስብከቱን ችግር ያልተመለከተ ስሜታዊ ውሳኔ ነው እንላለን። ምክንያቶቻችንም ለሀ/ስብከቱ የተሻለ መንገድ መኖሩን በማመላከት ይሆናል።
1/ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የሀገሪቱና የአፍሪቃ ዋና ከተማ ከመሆኑም ባሻገር የቤተክርስቲያኒቱ ማእከላዊ ሀ/ስብከት  በመሆኑ ሁኔታዎችን የገመገመና ወቅቱን ያገናዘበ  ልዩ መተዳደሪያ ደንብ ሊኖረው የተገባ ነው።
2/ የሀ/ስብከቱ ጽ/ቤት አወቃቀር የመንግሥትንና ዓለምአቀፍ ተቋማትን ደረጃ ያገናዘበ ዘመናዊ፤ ሙያዊና ችሎታን የተመረኮዘ የአስተዳደር መዋቅር  የያዘ መሆን ይገባው ነበር።
3/ አሁን ያሉትን ስድስት ሥራ ፈት የወረዳ ጽ/ቤቶችን ወደ አራት በማጠቃለል በአውራጃ ጽ/ቤት ደረጃ ሥልጣንና ኃላፊነት ከሀ/ስብከቱ  ከፍሎ በመስጠት እንደአዲስ ቢደራጅ ስልጣን የተሰበሰበበትን የሀ/ስብከቱን  ማእከል ጫናና ድርሻ ከመቀነሱም በላይ ተጠያቂነት ያለው አሠራርን ማስፈን ይቻል ነበር።
4/  የሀ/ስብከቱ አድባራትና ገዳማት የአስተዳደር መዋቅር በሀ/ስብከቱ መተዳደሪያ ደንብ በትክክል የተቀመጠውን የተከተለ መሆን የሚገባው ሲሆን ሙያን፤ ችሎታን፤ ብቃትን፤ ልምድንና መልካም ሥነ ምግባር የተከተለ የአስተዳደር መዋቅር ሊፈጠርበት ይገባዋል።
5/ በየአድባራት ያሉትን ከመጠን በላይ ያለውን የሠራተኞች ቁጥር  ወደሌላ የልማት ዘርፍ በመቀነስ እንደ አዲስ ማደራጀት የግድ መሆን አለበት።ይህ የልማት ዘርፍ ከደመወዝ ጠባቂነት ይልቅ አምራች ዜጋ እንዲኖርና የሚፈልሰውን ቅጥር ፈላጊ ለመከላከል የሚያስችል ነው።
6/ የሀ/ስብከቱ  ጽ/ቤት አድባራቱ በጋራ  ያላቸውን ካፒታል በማሰባሰብ በሚያቋቁሙት የልማት ተቋም የገቢ አቅም እንዲፈጥሩና ከልመና ገንዘብ እንዲላቀቁ ማድረግ ይጠበቅበታል። ለምሳሌ በጋራ ገንዘባቸው፤ ማተሚያ ቤት ወዘተ ማቋቋም ይቻላል።
7/ ቤተክርስቲያኒቱ ብዙ ባለሙያና አዋቂ ምእመናንና ምእመናት እያሏት ከዳር ሆነው ድክመቷን እየተመለከቱ፤ እሷም ልትጠቀምባቸው ሳትችል መቅረቷ ይታወቃል። በሀ/ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የሚደራጅ የምሁራን ልጆቿ የአማካሪ ቦርድ ቢኖረው ሀ/ስብከቱ ተጠቃሚ ይሆናል።
ሌሎች ተጨማሪና አስፈላጊ ነጥቦችን ለመፍትሄው በማስቀመጥ አሁን ያለውን የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ችግር ማቃለል እየተቻለ ሲኖዶስ ሀ/ስብከቱን መሰነጣጠቅ መፈለጉ ትክክል አይደለም። የትኞቹን ችግር በየትኞቹ መንገዶች ለማቃለል ተፈልጎ ነው ሀ/ስብከቱን በብዙ ሊቃነ ጳጳሳት ስር መሰንጠቁ ያስፈለገው? ለሚለው ጥያቄ  አሳማኝ መልስ የለም።
የአዲስ አበባ መስተዳደር እንኳን የሚተዳደረው በአንድ ከንቲባ ሥር ሆኖ ራሳቸውን ችለው በተወሰነ ሥልጣንና ኃላፊነት በተደራጁ ክ/ከተሞች እንጂ በልዩ ልዩ ከንቲባ ተሰነጣጥቆ አይታይም። የኛዎቹ በብዙ የሊቀ ጳጳስ ከንቲባ ሥር ሀ/ስብከቱን ከፋፍለው ሲያበቁ በሀ/ስብከቴ ጣልቃ አትግባ የሚል ድምጽ ለማስማትና አንድ ሠራተኛ  ከአንድ ክፍል ውስጥ ወደ ሌላኛው ክፍል እንዳይዘዋወር የሚያደርግ ስለሆነ ይህንን መፈለጋቸው አስገራሚም አሳዛኝም ነው። ውጤቱም አሳዛኝ ከመሆን አይዘልም።
ለወትሮውስ ቢሆን ርዕይና ግብ ከሌለው ጉባዔ ከዚህ የተሻለ ምን ሊጠበቅ ኖሯል? ሲኖዶሱ ራሱ ተሰነጣጥቆ አዲስ አበባንም በፈቃዱ ሰነጣጥቆ አረፈው። የ10 ቀናት ውጤት ይህ መሆን ነበረበት? ለአንባቢዎች የምናስገነዝበው ጽሁፋችን ለነቀፋ ሳይሆን በተገቢ ሂስ፤ አሳማኝ መልስ የሚሰጥ ካለ ያንን ለማግኘት ሲሆን መሠረቱም በሚታይ ገሃዳዊ እውነታ ላይ ተመስርተን ብቻ መሆኑን እንድታውቁልን ነው።

Thursday, May 30, 2013

በሰማንያ ወአሀዱ መጽሐፍ ሽፋን የተፈጸመው የጠላት ሴራ ሲገለጥ


(ክፍል ፩ )

መግቢያ፤

ሰይጣን የሰውን ልጅ ከሚያሳስትበት  አንዱ መንገድ የእግዚአብሔርን ቃል በማጣመም መተርጎም ነው። እግዚአብሔር አዳምን ከገነት ዛፎች መካከል አንዱን ሲከለክለው እንዲህ ብሎት ነበር። «ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና» ዘፍ 2፤17  ሰይጣን  ደግሞ ለዚህ ትዕዛዝ በመጀመሪያ የጥርጣሬ መንፈሱን በመርጨት «ሴቲቱንም፦ በውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን?» ዘፍ 3፣1 ብሎ ከጠየቀ በኋላ ስለማይበላው የዕጽ ፍሬ አስፈላጊነት ራሱ መልሱን ሲሰጥ እናገኘዋለን። የምንጊዜም ምላሹ ደግሞ የእግዚአብሔርን ቃል በተቃረነ መልኩ መሆኑ ነው። «እባብም ለሴቲቱ አላት። ሞትን አትሞቱም» ዘፍ 3፤4 እግዚአብሔር አምላክ ሞትን ትሞታላችሁ ሲል ሰይጣን ደግሞ ሞትን አትሞቱም ማለቱ የሀሰት አባት ያሰኘዋል። ከራሱ አመንጭቶ የሚናገር፤ ያመነጨውንም እውነት አስመስሎ የሚያቀርብ የክፋት ሁሉ ስር በመሆኑም ጭምር ነው። ሰይጣን እሱ ያመነጨውን ሀሰት አስቀድሞ ልበ ድኩም ፈልጎ  ይጭንና ሥራው ሁሉ በዚያ ሰው በኩል እየተላለፈ ለዓለሙ ሁሉ እንዲዳረስ ያደፋፍራል። ልክ የዘመኑ ትሮጃን ፈረስ የተባለው አንዱ ቫይረስ እየተራባ ኮምፒውተሮችን ሁሉ እንደሚያጠቃው ሰይጣን እውነተኛ ቃል አጣምሞ ሰዎችን ሁሉ ያጠቃል። ልዩነቱ የሰይጣን የጥቃት መሠረት የሰው ልጆችን ከእግዚአብሔር መንግሥት መለየት መቻሉ ስለሆነ ጥቃቱን የከፋ ያደርገዋል። ሰይጣን የጥርጣሬና የሞትን አትሞቱም መርዙን በቅድሚያ የረጨው በሔዋን ልቦና ውስጥ ሲሆን ስራው በትክክል ተቀባይነት ማግኘቱን ሲያረጋግጥ ትቷቸው ሄዷል። አዳምም የሞትን [ትሮጃን ሆርስ] ሃሳብ ከሚስቱ ተቀብሎ ተግባር ላይ ካዋለ በኋላ ውድቀቱን በማየቱ ረዳት የሰጠው እግዚአብሔርን በመክሰስ ለዚህ ሁሉ ውድቀቴ ምክንያቱ አንተ የሰጠኸኝ ሴት ናት በሚል ወቀሳ ሲያቀርብ እንመለከታለን።
« አዳምም አለ፦ ከእኔ ጋር እንድትሆን የሰጠኸኝ ሴት እርስዋ ከዛፉ ሰጠችኝና በላሁ» ዘፍ 3፤12  ሔዋንም በተራዋ ጣቷን ወደእባብ ስታመለክት ማየታችን(ዘፍ 3፤13) የሰው ልጅ የራሱን ስህተት ባለመመልከት ሌላውን ስሁት አድርጎ የማቅረብ የዳበረ ልምድ እንዳለው ያረጋግጥልናል። ሰይጣን እስካለ ድረስ ድረስ ውጤታማ የሆነበትን ይህንን የማሳሳት ልምዱን ወደጥልቁ እስኪወረወር ድረስ ገቢራዊ ከማድረግ ለአፍታም እንደማያርፍ የቀደመ ሥራው ለዚህ ዘመንም አረጋጋጭ ነው። ሰይጣን ራሱ ሲጠየቅ በዓለሙ ሁሉ ለማሳሳት ያለዕረፍት እንደሚዞር መናገሩ በቂ ማስረጃ ነው።
«እግዚአብሔርም ሰይጣንን፦ ከወዴት መጣህ? አለው። ሰይጣንም። ምድርን ሁሉ ዞርሁአት፥ በእርስዋም ተመላለስሁ ብሎ ለእግዚአብሔር መለሰ» ኢዮብ 1፤7
ሰይጣን ምድርን ሁሉ የሚዞረው ስለአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ ጥናት ለማካሄድ አለያም የተፈጥሮ ሀብት ክብካቤ ወይም የሰላምና ጸጥታ ሁኔታን መርምሮ ለማረጋጋት እንዳልሆነ እርግጥ ነው። መልካምነት ባህርይው ስላልሆነ ሰይጣን ዙረቱ ሁሉ ማጥፋት፤ ማሳሳት፤ መፈተንና መግደል ብቻ ነውና አሁን ድረስ እንደዞረ ነው። በዚህም ዘመን የሰው ልጆችን ዋና የሚያጠቃበት መሣሪያው ሰዎች እግዚአብሔርን ወደማወቅ እንዳይደርሱ፤ እውነቱን አውቀው ንስሐ እንዳይገቡ፤ የእግዚአብሔርን ቃል በመጋረድና በመከለል የስህተት መንገድ እንዲፈጠር በማድረግ ነው። ምክንያቱም ይህ ትውልድ የያዕቆብን አምላክ የሚፈልግ ነውና። «ይህች ትውልድ እርሱን የምትፈልግ ናት፥ የያዕቆብን አምላክ ፊት የምትፈልግ» መዝ 24፤6  በመጨረሻው ዘመን የመንግሥትም ወንጌል በዓለሙ ሁሉ እንደሚሰበክ አስቀድሞ ተነግሮ ነበርና። (ማቴ 24፤14) የቀረለት  ጊዜ  ጥቂት እንደሆነ ስለሚያውቅ እየዞረ ቃሉን በማጣመም እግዚአብሔር እንዳይመለክ ይጋርዳል፤ እውነት የሚመስል የስህተት ቃል እየፈጠረ ይከራከራል።
«ስለዚህ፥ ሰማይና በውስጡ የምታድሩ ሆይ፥ ደስ ይበላችሁ፤ ለምድርና ለባሕር ወዮላቸው፥ ዲያብሎስ ጥቂት ዘመን እንዳለው አውቆ በታላቅ ቍጣ ወደ እናንተ ወርዶአልና» ራእይ 12፣12
ልክ እንደተወርዋሪ ኮከብ በዘመናት ውስጥ ብቅ ብለው (በቀደሙት ዘመናት፤ እንደአባ እስጢፋኖስ ፤በኋላም እንደአለቃ ታዬና አቡነ ፊልጶስ ጳጳስ ዘኢየሩሳሌም ወዘተ) ዓይነቶቹ ብርሃናቸውን አብርተው ሳይጨርሱ እልም ብለው የጠፉት ቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ጠላት ባስቀመጠው እንቅፋት እንደነበር ታሪክ ይነግረናል። ለዚህም ዋናው ነጥብ ጠላት ቤተክርስቲያኒቱ ጥንት ከምትቀበለውና በሐዋርያት መሰረት ላይ ከታነጸችበት አለት ላይ እያንሸራተተ በመከራ ወጀብ እንድትናጥ የሚያደርጋት የክፉ መንፈስ አሰራር በመንገሱ ነው። ወደዋናው የሰማንያ አሀዱ ገመና ከመግባታችን በፊት እስኪ አንዱንና  ፈጣሪን  ከፍጡራን ጋር አዳብሎ  በአምሳለ አምላክ የማስመለክ የጠላትን አሰራር አስቀድመን እንመልከት። ይህንን ቃል የማቅ አገልጋይ ዲ/ን ኅብረት የሺጥላ ከዚህ ቀደም እርሱ ከሚፈልገው መንገድ በመተርጎም የበለሱን ውበት እንዲያስጎመጅ አድርጎ አቅርቦት ነበር። ብዙዎችም ይህንን በለስ እየተቀባበሉ በማማሩ ተስበው ሲመገቡት ቆይተዋል። እስኪ ከዚያ እንጀምር።
1/ ፍጡርና ፈጣሪ አንድ ምስጋና ይገባቸዋልን?
«"ለእሉ ክሌቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ»  «ለእነዚህ ሁለት ፍጡራን/ለማርያምና ለመስቀል/ የፈጣሪ ምስጋና ይገባቸዋል፤ በክብራቸው ተካክለውታልና» የሚለውን ትርጉም ዲ/ን ኅብረት የሺጥላ እንዲህ ሲል በመተርጎም ዓይናችሁን  ግለጡና የበለሱን ውበት ተመልክቱ በማለት ያባብለናል።
«ይህ መጽሐፍ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጸሎት መጽሐፍ ነው፡፡ ለበርካታ መቶ አመታት አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ በተሐድሶ መናፍቃን ጠንካራ ትችትና ነቀፋ ቢደርስበትም አሁንም አገልግሎቱን እየሰጠ ይገኛል፡፡ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ስለቅዱስ መስቀል በተጓዳኝ አንሥቶ ይናገራል፡፡ ካለ በኋላ ዲ/ኑ በመቀጠል ፤በመስተብቁዕ ዘመስቀል ላይ የሚገኘው ‹‹እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ›› የሚለው የግዕዝ ዐረፍተ ነገር ወደ አማርኛ ‹‹በክብር ተመሳስለዋልና›› ተብሎ መተርጎም ሲኖርበት ወደ አማርኛ የመለሰው ክፍል ‹‹በክብር ተካክለዋልና›› ብሎ ስለተረጎመው አንባቢን የሚያሳስት ሊሆን ችሏል፡፡ ስለዚህ ዋናው ችግር የመጽሐፉ ሳይሆን ከግዕዝ ወደ አማርኛ የመለሰው ሰው ነው፡፡በዚህ ዐረፍተ ነገር ውስጥ ወሳኝ ሚና የሚጫወተው ቃል ‹‹ዐረየ›› የሚለው ግሥ ነው፡፡ ‹‹ዐረየ›› ሁለት ፍቺ አለው፡፡ አንደኛው ‹‹ተካከለ›› ማለት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ‹‹ተመሳሰለ›› የሚል ነው፡፡ «ዐረየ» በመለኮት «ተካከለ» እንደሚባል ነግሮን «ዐረየ« የሚለው «ተመሳሰለ» ተብሎ የሚተረጎምበትን ምክንያታዊ ጭብጥ ሳይነግረን ዝም ብሎ አልፎታል። «ማርያምና መስቀል፤ ከፈጣሪ ጋር ተመሳስለዋል » ተብሎ ቢፈታ ትንሽ የላላ መስሎት ከሆነ ፍጡርና ፈጣሪ በምን ሊመሳሰሉ እንደሚችሉ ሊነግረን የግድ ይሆናል። ያለበለዚያ «ለእሉ ክልዔቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ» ለእነዚህ ሁለቱ ፍጡራን የፈጣሪ ምስጋና ይገባቸዋል» በማለት የስህተት ቃል በቀደመችው ቤተክርስቲያን ውስጥ ጠላት የተከለውን ስህተት ዲያቆኑ ደግሞ  የዘርዓ ያዕቆብን  ሌጋሲ ለማስቀጠል ካለው ፍላጎት የመነጨ ከመሆን አይዘልም።
እንግዲህ ይህ ሰው መስተብቁዕን አይቶ አያውቅም ወይም ግሱን ከመጻሕፍት አላገላበጠም። ካልሆነም ደግሞ እባብ ያሳየውን የበለሱን መልክና ውበት ተቀብሎ እያገለገለ ነው ማለት ነው። «ተዐረዩ በክብሮሙ» በክብር ተካክለዋልና የሚለውን ቃል «በክብር ተመሳስለዋል እንጂ ተካክለዋል ማለት አይደለም በማለት ሊያዘነጋን ይሞክራል። ስሁት መንገዱን ከፍቶ ኑ በዚህ ሂዱ እያለ የሞትን በለስ ጎዳና ያመላክተናል። ትርጉሙን ስንመለከት «ዐርይ» ማለት በገቢር መምሰል፤ መተካከል፤ ትክክል መሆን ሲሆን በተገብሮ ደግሞ ተካከለ፤ ተመሳሰለ ማለት ነው።  በፈጣሪነት ባህርይ፤ በሥራው ካልተስተካከለው ወይም ካልመሰለው፤ አከለው፤ መሰለው ማለት አንችልም። አለበለዚያም መመሳሰልን ወደምድራዊ የሰዎች ሚዛን በማውረድ «መስቀልን፤ማርያምንና ክርስቶስን» ወደመለካት ክህደት ውስጥ የባሰ መውረድ ይሆናል። ዲያቆኑ በዚያ መንገድ ተመልከቱ እያለ መገኘቱ ከማይወጣው ድቅድቅ ውስጥ እየገባ ነውና የምታውቁት እባካችሁ ምከሩት። ንስሐም ይግባ!
ስለመለኮት  ዕሪና ስንናገር አንዱ ከሌላው ጋር የተካከለ/እኩል የሆነ/፤ የተስተካከለ/ከፍታና ዝቅታ የሌለው/፤ ምንም ያልተለየ ፤ፍጹም አንድ የሆነ ማለት ነው። አምላክ፤ ወልደ አምላክ ኢየሱስን ከማርያምና ከመስቀል ጋር ማመሳሰልም ሆነ ማስተካከል አይቻልም። «ለእሉ ክልዔቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ» ለእነዚህ ሁለቱ ፍጡራን የአምላክ ምስጋና ይገባቸዋል» ማለት የአምላክነት ባህርይን ይጋራሉ ማለት ሲሆን ምክንያታዊ ንጽጽሩን ሲያቀርብ ደግሞ «እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ» በክብር ተካክለውታልና በማለት ያመጣዋል። የፈጣሪነት ክብር ከፍጡርነት ክብር ጋር ሊተካከልም ሆነ ሊመሳሰል በፍጹም አይችልም። ቅድስት ማርያም ኢየሱስን በመውለዷ ወደአምላክነት አልተቀየረችም። መስቀሉም ኢየሱስ ስለሞተበት አምላክ ወደመሆን አልተለወጠም። ፍጡር በፈጣሪ ይከብራል እንጂ ከማንም የማይቀበልና ማንም ሊወስድበት የማይችል ክብር ያለውን አምላክ ከፈጣሪ ጋር ተመሳሳይ ምስጋና ይገባቸዋል ማለት ትልቅ ክህደት ነው። ጸጋ ተቀባይ ቢከብር ከሰጪው ቸርነት እንጂ  ራሱ ባለው አምላካዊ የመሆን ብቃት አይደለም።
«ጸጋን የተመላሽ ክብርት ሆይ ደስ ይበልሽ» ብለን ማርያምን ስናመሰግናት ጸጋውን የመላት አንድያ ልጇ መሆኑን እንረዳለን። ብጽእት ማርያም እያለ ትውልድ ማመስገኑ ከአምላክ ጋር ስለተካከለች ወይም ስለተመሳሰለች ሳይሆን ከሴቶች ሁሉ ተመርጣ የአብ አንድያ ልጅ ኢየሱስን በሥጋ ስለወለደችው ነው።  ማርያም መውደድና ማክበር ወደአምላክነት እስክንቀይራት ድረስ እንድንሄድ  ሊያደርገን አይገባም። « ነፍስየሰ ትትሐሰይ፤ በአምላኪየ ወበመድኃኒትየ» ነፍሴ በአምላኬና በመድኃኒቴ ሀሴት ታደርጋለች ማለቷን ስንመለከት ድንግል ማርያም የትህትናና የእውነት እናት መሆኗን ነው። እኛ እውነቱን ስንናገር ማርያምን አትወዷትም በማሰኘት ሰይጣን በሌሎች አፍ ሊከሰን ይፈልጋል። ዝም ስንል ደግሞ በሌሎች አፍ አድሮ  እሷ እኮ ለአምላክ የሚሰጠው ምስጋናና አምልኮ ይገባታል እያለ ያታልላል። «ይህንን ዕፅ ብትበሉ ዓይናችሁ ይከፈታል» በማለት ለሔዋን ሹክ እንዳለው ዛሬም  ቅን በምትመስል ቃለ እግዚአብሔር ስር ተከልሎ አምላክ ብቻውን እንዳይመሰገን ለማስቀናት ሥራውን ይሰራል። እግዚአብሔር ራሱ ሁሉን የሰራ፤ ሁሉን የተሸከመና ከማንም ጋር እንደማይመሳሰል በቃሉ እንዲህ ሲል ይነግረናል።
«እስከ ሽምግልና ድረስ እኔ ነኝ፥ እስከ ሽበትም ድረስ እሸከማችኋለሁ እኔ ሠርቻለሁ እኔም አነሣለሁ እኔ እሸከማለሁ እኔም አድናለሁ።በማን ትመስሉኛላችሁ? ከማንስ ጋር ታስተካክሉኛላችሁ? እንመሳሰል ዘንድ ከማን ጋር ታስተያዩኛላችሁ?» ኢሳ 46፤5
ይቀጥላል…………….