Thursday, May 30, 2013

በሰማንያ ወአሀዱ መጽሐፍ ሽፋን የተፈጸመው የጠላት ሴራ ሲገለጥ


(ክፍል ፩ )

መግቢያ፤

ሰይጣን የሰውን ልጅ ከሚያሳስትበት  አንዱ መንገድ የእግዚአብሔርን ቃል በማጣመም መተርጎም ነው። እግዚአብሔር አዳምን ከገነት ዛፎች መካከል አንዱን ሲከለክለው እንዲህ ብሎት ነበር። «ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና» ዘፍ 2፤17  ሰይጣን  ደግሞ ለዚህ ትዕዛዝ በመጀመሪያ የጥርጣሬ መንፈሱን በመርጨት «ሴቲቱንም፦ በውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን?» ዘፍ 3፣1 ብሎ ከጠየቀ በኋላ ስለማይበላው የዕጽ ፍሬ አስፈላጊነት ራሱ መልሱን ሲሰጥ እናገኘዋለን። የምንጊዜም ምላሹ ደግሞ የእግዚአብሔርን ቃል በተቃረነ መልኩ መሆኑ ነው። «እባብም ለሴቲቱ አላት። ሞትን አትሞቱም» ዘፍ 3፤4 እግዚአብሔር አምላክ ሞትን ትሞታላችሁ ሲል ሰይጣን ደግሞ ሞትን አትሞቱም ማለቱ የሀሰት አባት ያሰኘዋል። ከራሱ አመንጭቶ የሚናገር፤ ያመነጨውንም እውነት አስመስሎ የሚያቀርብ የክፋት ሁሉ ስር በመሆኑም ጭምር ነው። ሰይጣን እሱ ያመነጨውን ሀሰት አስቀድሞ ልበ ድኩም ፈልጎ  ይጭንና ሥራው ሁሉ በዚያ ሰው በኩል እየተላለፈ ለዓለሙ ሁሉ እንዲዳረስ ያደፋፍራል። ልክ የዘመኑ ትሮጃን ፈረስ የተባለው አንዱ ቫይረስ እየተራባ ኮምፒውተሮችን ሁሉ እንደሚያጠቃው ሰይጣን እውነተኛ ቃል አጣምሞ ሰዎችን ሁሉ ያጠቃል። ልዩነቱ የሰይጣን የጥቃት መሠረት የሰው ልጆችን ከእግዚአብሔር መንግሥት መለየት መቻሉ ስለሆነ ጥቃቱን የከፋ ያደርገዋል። ሰይጣን የጥርጣሬና የሞትን አትሞቱም መርዙን በቅድሚያ የረጨው በሔዋን ልቦና ውስጥ ሲሆን ስራው በትክክል ተቀባይነት ማግኘቱን ሲያረጋግጥ ትቷቸው ሄዷል። አዳምም የሞትን [ትሮጃን ሆርስ] ሃሳብ ከሚስቱ ተቀብሎ ተግባር ላይ ካዋለ በኋላ ውድቀቱን በማየቱ ረዳት የሰጠው እግዚአብሔርን በመክሰስ ለዚህ ሁሉ ውድቀቴ ምክንያቱ አንተ የሰጠኸኝ ሴት ናት በሚል ወቀሳ ሲያቀርብ እንመለከታለን።
« አዳምም አለ፦ ከእኔ ጋር እንድትሆን የሰጠኸኝ ሴት እርስዋ ከዛፉ ሰጠችኝና በላሁ» ዘፍ 3፤12  ሔዋንም በተራዋ ጣቷን ወደእባብ ስታመለክት ማየታችን(ዘፍ 3፤13) የሰው ልጅ የራሱን ስህተት ባለመመልከት ሌላውን ስሁት አድርጎ የማቅረብ የዳበረ ልምድ እንዳለው ያረጋግጥልናል። ሰይጣን እስካለ ድረስ ድረስ ውጤታማ የሆነበትን ይህንን የማሳሳት ልምዱን ወደጥልቁ እስኪወረወር ድረስ ገቢራዊ ከማድረግ ለአፍታም እንደማያርፍ የቀደመ ሥራው ለዚህ ዘመንም አረጋጋጭ ነው። ሰይጣን ራሱ ሲጠየቅ በዓለሙ ሁሉ ለማሳሳት ያለዕረፍት እንደሚዞር መናገሩ በቂ ማስረጃ ነው።
«እግዚአብሔርም ሰይጣንን፦ ከወዴት መጣህ? አለው። ሰይጣንም። ምድርን ሁሉ ዞርሁአት፥ በእርስዋም ተመላለስሁ ብሎ ለእግዚአብሔር መለሰ» ኢዮብ 1፤7
ሰይጣን ምድርን ሁሉ የሚዞረው ስለአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ ጥናት ለማካሄድ አለያም የተፈጥሮ ሀብት ክብካቤ ወይም የሰላምና ጸጥታ ሁኔታን መርምሮ ለማረጋጋት እንዳልሆነ እርግጥ ነው። መልካምነት ባህርይው ስላልሆነ ሰይጣን ዙረቱ ሁሉ ማጥፋት፤ ማሳሳት፤ መፈተንና መግደል ብቻ ነውና አሁን ድረስ እንደዞረ ነው። በዚህም ዘመን የሰው ልጆችን ዋና የሚያጠቃበት መሣሪያው ሰዎች እግዚአብሔርን ወደማወቅ እንዳይደርሱ፤ እውነቱን አውቀው ንስሐ እንዳይገቡ፤ የእግዚአብሔርን ቃል በመጋረድና በመከለል የስህተት መንገድ እንዲፈጠር በማድረግ ነው። ምክንያቱም ይህ ትውልድ የያዕቆብን አምላክ የሚፈልግ ነውና። «ይህች ትውልድ እርሱን የምትፈልግ ናት፥ የያዕቆብን አምላክ ፊት የምትፈልግ» መዝ 24፤6  በመጨረሻው ዘመን የመንግሥትም ወንጌል በዓለሙ ሁሉ እንደሚሰበክ አስቀድሞ ተነግሮ ነበርና። (ማቴ 24፤14) የቀረለት  ጊዜ  ጥቂት እንደሆነ ስለሚያውቅ እየዞረ ቃሉን በማጣመም እግዚአብሔር እንዳይመለክ ይጋርዳል፤ እውነት የሚመስል የስህተት ቃል እየፈጠረ ይከራከራል።
«ስለዚህ፥ ሰማይና በውስጡ የምታድሩ ሆይ፥ ደስ ይበላችሁ፤ ለምድርና ለባሕር ወዮላቸው፥ ዲያብሎስ ጥቂት ዘመን እንዳለው አውቆ በታላቅ ቍጣ ወደ እናንተ ወርዶአልና» ራእይ 12፣12
ልክ እንደተወርዋሪ ኮከብ በዘመናት ውስጥ ብቅ ብለው (በቀደሙት ዘመናት፤ እንደአባ እስጢፋኖስ ፤በኋላም እንደአለቃ ታዬና አቡነ ፊልጶስ ጳጳስ ዘኢየሩሳሌም ወዘተ) ዓይነቶቹ ብርሃናቸውን አብርተው ሳይጨርሱ እልም ብለው የጠፉት ቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ጠላት ባስቀመጠው እንቅፋት እንደነበር ታሪክ ይነግረናል። ለዚህም ዋናው ነጥብ ጠላት ቤተክርስቲያኒቱ ጥንት ከምትቀበለውና በሐዋርያት መሰረት ላይ ከታነጸችበት አለት ላይ እያንሸራተተ በመከራ ወጀብ እንድትናጥ የሚያደርጋት የክፉ መንፈስ አሰራር በመንገሱ ነው። ወደዋናው የሰማንያ አሀዱ ገመና ከመግባታችን በፊት እስኪ አንዱንና  ፈጣሪን  ከፍጡራን ጋር አዳብሎ  በአምሳለ አምላክ የማስመለክ የጠላትን አሰራር አስቀድመን እንመልከት። ይህንን ቃል የማቅ አገልጋይ ዲ/ን ኅብረት የሺጥላ ከዚህ ቀደም እርሱ ከሚፈልገው መንገድ በመተርጎም የበለሱን ውበት እንዲያስጎመጅ አድርጎ አቅርቦት ነበር። ብዙዎችም ይህንን በለስ እየተቀባበሉ በማማሩ ተስበው ሲመገቡት ቆይተዋል። እስኪ ከዚያ እንጀምር።
1/ ፍጡርና ፈጣሪ አንድ ምስጋና ይገባቸዋልን?
«"ለእሉ ክሌቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ»  «ለእነዚህ ሁለት ፍጡራን/ለማርያምና ለመስቀል/ የፈጣሪ ምስጋና ይገባቸዋል፤ በክብራቸው ተካክለውታልና» የሚለውን ትርጉም ዲ/ን ኅብረት የሺጥላ እንዲህ ሲል በመተርጎም ዓይናችሁን  ግለጡና የበለሱን ውበት ተመልክቱ በማለት ያባብለናል።
«ይህ መጽሐፍ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጸሎት መጽሐፍ ነው፡፡ ለበርካታ መቶ አመታት አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ በተሐድሶ መናፍቃን ጠንካራ ትችትና ነቀፋ ቢደርስበትም አሁንም አገልግሎቱን እየሰጠ ይገኛል፡፡ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ስለቅዱስ መስቀል በተጓዳኝ አንሥቶ ይናገራል፡፡ ካለ በኋላ ዲ/ኑ በመቀጠል ፤በመስተብቁዕ ዘመስቀል ላይ የሚገኘው ‹‹እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ›› የሚለው የግዕዝ ዐረፍተ ነገር ወደ አማርኛ ‹‹በክብር ተመሳስለዋልና›› ተብሎ መተርጎም ሲኖርበት ወደ አማርኛ የመለሰው ክፍል ‹‹በክብር ተካክለዋልና›› ብሎ ስለተረጎመው አንባቢን የሚያሳስት ሊሆን ችሏል፡፡ ስለዚህ ዋናው ችግር የመጽሐፉ ሳይሆን ከግዕዝ ወደ አማርኛ የመለሰው ሰው ነው፡፡በዚህ ዐረፍተ ነገር ውስጥ ወሳኝ ሚና የሚጫወተው ቃል ‹‹ዐረየ›› የሚለው ግሥ ነው፡፡ ‹‹ዐረየ›› ሁለት ፍቺ አለው፡፡ አንደኛው ‹‹ተካከለ›› ማለት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ‹‹ተመሳሰለ›› የሚል ነው፡፡ «ዐረየ» በመለኮት «ተካከለ» እንደሚባል ነግሮን «ዐረየ« የሚለው «ተመሳሰለ» ተብሎ የሚተረጎምበትን ምክንያታዊ ጭብጥ ሳይነግረን ዝም ብሎ አልፎታል። «ማርያምና መስቀል፤ ከፈጣሪ ጋር ተመሳስለዋል » ተብሎ ቢፈታ ትንሽ የላላ መስሎት ከሆነ ፍጡርና ፈጣሪ በምን ሊመሳሰሉ እንደሚችሉ ሊነግረን የግድ ይሆናል። ያለበለዚያ «ለእሉ ክልዔቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ» ለእነዚህ ሁለቱ ፍጡራን የፈጣሪ ምስጋና ይገባቸዋል» በማለት የስህተት ቃል በቀደመችው ቤተክርስቲያን ውስጥ ጠላት የተከለውን ስህተት ዲያቆኑ ደግሞ  የዘርዓ ያዕቆብን  ሌጋሲ ለማስቀጠል ካለው ፍላጎት የመነጨ ከመሆን አይዘልም።
እንግዲህ ይህ ሰው መስተብቁዕን አይቶ አያውቅም ወይም ግሱን ከመጻሕፍት አላገላበጠም። ካልሆነም ደግሞ እባብ ያሳየውን የበለሱን መልክና ውበት ተቀብሎ እያገለገለ ነው ማለት ነው። «ተዐረዩ በክብሮሙ» በክብር ተካክለዋልና የሚለውን ቃል «በክብር ተመሳስለዋል እንጂ ተካክለዋል ማለት አይደለም በማለት ሊያዘነጋን ይሞክራል። ስሁት መንገዱን ከፍቶ ኑ በዚህ ሂዱ እያለ የሞትን በለስ ጎዳና ያመላክተናል። ትርጉሙን ስንመለከት «ዐርይ» ማለት በገቢር መምሰል፤ መተካከል፤ ትክክል መሆን ሲሆን በተገብሮ ደግሞ ተካከለ፤ ተመሳሰለ ማለት ነው።  በፈጣሪነት ባህርይ፤ በሥራው ካልተስተካከለው ወይም ካልመሰለው፤ አከለው፤ መሰለው ማለት አንችልም። አለበለዚያም መመሳሰልን ወደምድራዊ የሰዎች ሚዛን በማውረድ «መስቀልን፤ማርያምንና ክርስቶስን» ወደመለካት ክህደት ውስጥ የባሰ መውረድ ይሆናል። ዲያቆኑ በዚያ መንገድ ተመልከቱ እያለ መገኘቱ ከማይወጣው ድቅድቅ ውስጥ እየገባ ነውና የምታውቁት እባካችሁ ምከሩት። ንስሐም ይግባ!
ስለመለኮት  ዕሪና ስንናገር አንዱ ከሌላው ጋር የተካከለ/እኩል የሆነ/፤ የተስተካከለ/ከፍታና ዝቅታ የሌለው/፤ ምንም ያልተለየ ፤ፍጹም አንድ የሆነ ማለት ነው። አምላክ፤ ወልደ አምላክ ኢየሱስን ከማርያምና ከመስቀል ጋር ማመሳሰልም ሆነ ማስተካከል አይቻልም። «ለእሉ ክልዔቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ» ለእነዚህ ሁለቱ ፍጡራን የአምላክ ምስጋና ይገባቸዋል» ማለት የአምላክነት ባህርይን ይጋራሉ ማለት ሲሆን ምክንያታዊ ንጽጽሩን ሲያቀርብ ደግሞ «እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ» በክብር ተካክለውታልና በማለት ያመጣዋል። የፈጣሪነት ክብር ከፍጡርነት ክብር ጋር ሊተካከልም ሆነ ሊመሳሰል በፍጹም አይችልም። ቅድስት ማርያም ኢየሱስን በመውለዷ ወደአምላክነት አልተቀየረችም። መስቀሉም ኢየሱስ ስለሞተበት አምላክ ወደመሆን አልተለወጠም። ፍጡር በፈጣሪ ይከብራል እንጂ ከማንም የማይቀበልና ማንም ሊወስድበት የማይችል ክብር ያለውን አምላክ ከፈጣሪ ጋር ተመሳሳይ ምስጋና ይገባቸዋል ማለት ትልቅ ክህደት ነው። ጸጋ ተቀባይ ቢከብር ከሰጪው ቸርነት እንጂ  ራሱ ባለው አምላካዊ የመሆን ብቃት አይደለም።
«ጸጋን የተመላሽ ክብርት ሆይ ደስ ይበልሽ» ብለን ማርያምን ስናመሰግናት ጸጋውን የመላት አንድያ ልጇ መሆኑን እንረዳለን። ብጽእት ማርያም እያለ ትውልድ ማመስገኑ ከአምላክ ጋር ስለተካከለች ወይም ስለተመሳሰለች ሳይሆን ከሴቶች ሁሉ ተመርጣ የአብ አንድያ ልጅ ኢየሱስን በሥጋ ስለወለደችው ነው።  ማርያም መውደድና ማክበር ወደአምላክነት እስክንቀይራት ድረስ እንድንሄድ  ሊያደርገን አይገባም። « ነፍስየሰ ትትሐሰይ፤ በአምላኪየ ወበመድኃኒትየ» ነፍሴ በአምላኬና በመድኃኒቴ ሀሴት ታደርጋለች ማለቷን ስንመለከት ድንግል ማርያም የትህትናና የእውነት እናት መሆኗን ነው። እኛ እውነቱን ስንናገር ማርያምን አትወዷትም በማሰኘት ሰይጣን በሌሎች አፍ ሊከሰን ይፈልጋል። ዝም ስንል ደግሞ በሌሎች አፍ አድሮ  እሷ እኮ ለአምላክ የሚሰጠው ምስጋናና አምልኮ ይገባታል እያለ ያታልላል። «ይህንን ዕፅ ብትበሉ ዓይናችሁ ይከፈታል» በማለት ለሔዋን ሹክ እንዳለው ዛሬም  ቅን በምትመስል ቃለ እግዚአብሔር ስር ተከልሎ አምላክ ብቻውን እንዳይመሰገን ለማስቀናት ሥራውን ይሰራል። እግዚአብሔር ራሱ ሁሉን የሰራ፤ ሁሉን የተሸከመና ከማንም ጋር እንደማይመሳሰል በቃሉ እንዲህ ሲል ይነግረናል።
«እስከ ሽምግልና ድረስ እኔ ነኝ፥ እስከ ሽበትም ድረስ እሸከማችኋለሁ እኔ ሠርቻለሁ እኔም አነሣለሁ እኔ እሸከማለሁ እኔም አድናለሁ።በማን ትመስሉኛላችሁ? ከማንስ ጋር ታስተካክሉኛላችሁ? እንመሳሰል ዘንድ ከማን ጋር ታስተያዩኛላችሁ?» ኢሳ 46፤5
ይቀጥላል…………….