Thursday, May 16, 2013

የማኅበረ ቅዱሳን ተላላኪና ሙሰኛው አባ ኅሩይ ወንድይፍራው ከሥራ አስኪያጅነታቸው ታገዱ።

አባ ኅሩይ ወንድይፍራው የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊነቱን ከአባ ሠረቀ ብርሃን ወ/ሳሙኤል እጅ ተረክበው ማኅበረ ቅዱሳን በሚሰጣቸው መመሪያና ምክር መሠረት ለቤተ ክህነቱ ሸክም፤ ለማኅበሩ ግን ታማኝ አገልጋይ ሆነው መቆየታቸው ይታወሳል። በሥራው ላይ እያሉም በአንድ ወቅት አምነው የፈረሙበትን ደብዳቤ በጨለማ ተታልዬ ነው፤ አሳስተውኝ ነው፤ መዝገብ ቤቷ አሞኝታኝ ነው…………. ወዘተ፤ በሚል ማጭበርበሪያ ምክንያት የፈረሙትን ደብዳቤ መልሰው በመካድ የሰውዬው አቋመ ቢስና እምነት የማይጣልባቸው፤ እንደተልባ ስፍር የሚንሸራተቱ መሆናቸውን አይተን ከዚህ በፊት መዘገባችንም አይዘነጋም። ሰውዬው ማኅበረ ቅዱሳንን የሚያገለግሉት ስለሚወዱት ሳይሆን ስለሚፈሩት እንደሆነ በቅርብ የሚያውቋቸው ሰዎች ሲናገሩ ተሰምተዋል። ለምን እንደሚፈሩት የሚያውቁት እሳቸውና የኃጢአት መዝገብ ጸሐፊው ማኅበር ብቻ ናቸው። እንደክርስቲያን መፍራት የሚገባቸው የፈጠራቸውን እግዚአብሔርን ብቻ መሆን እንደሚገባው  ብናምንም እንደሥጋዊ ሰው ድካማቸውን አይተን ማኅበሩ እዳ በደላቸውን አደባባይ እንዳያውለው ቢፈሩ በእርግጥም ሊታዘንላቸው ይገባል እንላለን።
ይሁን እንጂ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት አራት ቦታ ተበታትኖ ልዩ ልዩ ያልጠረቁ ጅቦችን ለማዳረስ ቅርጫው በሲኖዶስ በተወሰነ ጊዜ አባ ኅሩይም አንዱ እግር ደርሷቸው በምዕራብ ክፍለ ከተማ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅነት ተመድበው ነበር። አባ ኅሩይ ብዙዎች ከሚያዝኑባቸውና ከሚያማርሩባቸው ምክንያቶች ዋናውና ግንባር ቀደሙ ጉዳይ ፈርሃ እግዚአብሔር የተለየው ጉቦኝነታቸው ሲሆን እስከዛሬም ብዙዎች እንባቸውን እንደራሔል ወደሰማይ የረጩባቸው ርኅራኄ የለሽ መሆናቸው ነው። አባ ኅሩይ እንኳን ሥራ አስኪያጅ የመሆን ብቃት ምንም የሌላቸው ይሁኑ እንጂ  ጉቦ / ዘረፋ/ በተባለው በሽታ ግን ፈጣንና ጥሩ የገፈፋ ልምድ ያካበቱ እንደሆኑ ገንዘባቸውን የገበሩ ሰዎች በምሬት ሲናገሩ ይደመጣሉ። እሰራልሃለሁ ብለው ሳይሰሩላቸው ያጉላሏቸውና አቤቱታ አቅርበው ከተባባሪ ሌባ አስተዳዳሪዎች ጋር ውስጥ ለውስጥ እየተገናኙ ባለጉዳዩን ያለሥራ ያንሳፈፈፉ፤ ማስጠንቀቂያ እንዲጻፍበት ያስደረጉ፤ የቤተ ክህነቱ ሸክምና የካህናቱ የልቅሶ ምንጭ መሆናቸው ሲነገር የቆየ ጉዳይ ነው።
ይህ ግፍና መከራው የበዛባቸውና ሸክሙ የከበዳቸው ካህናት በአንድ ድምጽ ሆ ብለው ጩኸት በማሰማታቸው፤ ጉዳዩ እስከ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ድረስ ቀርቦ ማስረጃዎች በመገኘታቸው የመጨረሻ ውሳኔ እስኪሰጥባቸው ድረስ የማኅበረ ቅዱሳኑ ተላላኪና የሙሰኞች አባት አባ ኅሩይ ወንድይፍራው በሊቀጳጳሱ ደብዳቤ ከሥራቸው ታግደዋል።
ከዚህ በፊት «ደጀሰላም» ብሎግ እኒህን ሙሰኛ መነኩሴ ሲያንቆለጳጵሳቸውና ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ተስማምተው ለመስራት ተነሳሽነቱ ያላቸው እያለ ለመካብ የሞከረ ቢሆንም በወቅቱ እንደዘገብነው ጊዜውን ጠብቆ ማንነታቸው ገሃድ ወጥቶ እነሆ በሙስና ተግባራቸው ከስራቸው እስከመታገድ ደርሰው የተሸፈነው ሲገለጥ ለማየት ችለናል። ጊዜው ቢረዝምም «ጉድና ጅራት ከወደኋላ ነው» እንዲሉ ከብዙ ጥፋት በኋላ ስራቸው  ማንነታቸውን ገልጦ ሰዓቱ ሲደርስ በመናገሩ፤ ማኅበረ ቅዱሳንን ሲሸማቀቅባቸው፤ እውነታውን ሲለፈልፉ ያልተሰሙት ደግሞ ተግባሩ ራሱ ምስክርነቱን ሰጥቶላቸዋል።  እነማን የማኅበሩ አባላት እንደሆኑ እንደአንድ ማሳያ  ሆኖም ይቆጠራል።
በሌላ መልኩ በእነአሉላ ጥላሁን፤  በእነ መረዋ ዱከሌ በዘመናዊ ስሙ/ ጳውሎስ መልክአ ሥላሴ/ እና በመሰሎቹ የሚዘወረው ከደጀ ሰላም ብሎግ ሞት በኋላ አዲስ የመጣው የማኅበሩ አገልጋይና የደብረ ብርሃን ወታደር የሆነው/ ሐራ ዘተዋሕዶ/ ብሎግ በአዲሱ ፓትርያርክ ምርጫ ወቅት የምርጫው ሂደት ፍትሃዊ አይደለም ሲል እንዳልቆየ ሁሉ የፈለገው አለመሳካቱን ሲያረጋግጥ ፓትርያርኩ ከሰማይ የወረዱ መልአክ ናቸው ወደሚል ውዳሴ መሸጋገሩ ፍቅር ስለጸናበት ሳይሆን »ጅብን ሲወጉ……» እንዲሉ ሆኖ በፓትርያርኩ ሙገሳ ተተግኖ «የማኅበሩ መንገድ ይጠረግ፤ ስርጓጉጡም ይቅና» ለማለት ካልሆነ በስተቀር የንግድ ማኅበሩን ነጋዴነትና የሙሰኞች ወዳጅነቱን ሊሸፍነው አይችልም። ለቤተ ክርስቲያን ከማሰብ የመነጨ እንዳይደለም አሳምረን እናውቃለን። ሌላው ጉዳይ ደግሞ የሙስና አለቃና የቤተክህነቱ ሸክም እንደሆነ የሚነገርለት ንቡረ እድ ኤልያስ አብርሃና  በዙሪያው ያሉ ሙሰኞች የስራ መሰናክል መሆናቸው ባይካድም ማኅበሩ ደግሞ ይህንን ግልጥ ጉድለት በሐራ ተዋሕዶ በኩል ፓትርያርኩን ተጠግቶ እየጮኸ፤  መንገዱን በመዝጋት ማኅበሩ ሰርጎ እንዳይገባ እንቅፋት የሆነባቸውን ሰው በስመ ሙስና አስወግደው  የራሳቸውን የቀን ጅቦች በቦታው ለመተካት ብሎጉ ሲዳክር ይታያል። ነገሩ «ከዝንጀሮ ቆንጆ ማን ይመራርጡ» ስለሆነ የእነ ንቡረ እድ ኤልያስ ቡድንም ይሁን የደብረ ብርሃኑ ወታደር ቡድን ሁላቸውም በቤተክህነቱ ውስጥ የራሳቸውን ጥቅም ለማስጠበቅ የሚደክሙና የፍትህና ርትዕ ዜማ እየጮሁ ቀበሮነታቸውን ለመሸፈን የሚጥሩ አስመሳይ በላተኞች እንጂ ቤተክህነት የምትሄድበትን የቁልቁሊት መንገድ ለማቃናት ተፈጥሮም ዓላማም የላቸውም። ምክንያቱም  እነንቡረ እድ የሚታሙበትን ሙሰኝነት በተቃራኒው በማኅበሩ አባልና ደጋፊ በአባ ኅሩይም በኩልም እየተገለጸ ይገኛልና። ሁሉም ሙሰኞችና ነጋዴዎች ስለሆኑ ከቤተክህነት ዐውድ መገኘታቸው አንዱ አንዱን ለመጣል በሚደረገው የባለሥልጣናት ጥገኛ የመሆን አባዜ ውስጥ ቤተ ክህነቱን የመንፈሳዊነት ሳይሆን የጥቅም ጦር ዐውድማ አድርገዋታል።
ለፓትርያርኩ የምናሳስበውና የምንጠይቀው ዐብይ ነጥብ ማንም የቤተ ክህነቱ አዛኝ መስሎ የሚጮኸውን ሁሉ በግ ብለው እንዳይቆጥሩና እንዳይታለሉ ሲሆን የመዋቅር ለውጥ፤ የአስተዳደር ሪፎርም፤ የሥራና ሠራተኛ ግንኙነትን ማሻሻል፤ ሕግና ደንብ ገዢ ማዕከል እንዲሆን በማስቻል አዲስ የሥራ መንፈስን በመፍጠር እንጂ በጥገናዊ ለውጥ አንዱን በማቅረብ ሌላውን በማራቅ ላይ አይጠመዱ ድምጻችን ነው። የአባ ኅሩይን የእግድ ደብዳቤ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ