Friday, October 11, 2013

«የማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች የሰሞኑ የአዞ እንባ የማኅበረ ቅዱሳንን ማንነት አይለውጠውም»


አንዳንዶች ማኅበረ ቅዱሳንን ስናነሳ ለምን ተነክቶ በሚል ቁጣ ወባ እንደያዘው ሰው ይንዘፈዘፋሉ። በእርግጥ በማኅበሩ የድንዛዜ መንፈስ የተወጉ ሰዎች እንደዚያ በመሆናቸው ከያዛቸው የወባ ዛር የሚያድን ምሕረት እንዲመጣላቸው እንመኝላቸዋለን እንጂ አንፈርድባቸውም። ሌላው ቀርቶ ማኅበሩ ራሱ ከእውነት ጋር ታርቆና ራሱን በንስሐ ለውጦ ከስለላና ከከሳሽነት ማፊያዊ ሥራ ተላቆ ቤተ ክርስቲያኒቱን ለራሱ አቋም ከመጠምዘዝ ቢታቀብ ሁላችንም አብረነው በቆምን ነበር።  ከወንጌል እውነት ጋር እየተላተመ በተረት ዋሻ ሥር አናቱን ቀብሮ ከኔ ወዲያ ለቤተ ክርስቲያን ጠበቃ የለም ከሚለው ትምክህት ቢወጣ እንዴት ባማረበት ነበር። ዳሩ ግን ማኅበረ ቅዱሳን ገና ከመሠረቱ የቆመበት የህልውናው መንፈስ በደምና በማስመሰል በመሆኑ ከዚያ አቋሙ ፈቀቅ ይላል ተብሎ አይታሰብም። ጉዳዩ የታጠቀው የእልህና የበቀል መንፈስ እስኪያጠፋው ድረስ አይለቀውምና ሄዶ ሄዶ መጨረሻው እስከዚያው ድረስ መሆኑን ደጋግመን ስንለው ቆይተናል። ያ ሰዓት የደረሰበት መሆኑን ያሸተተው ይህ ማኅበር በቀንደኛ ሰዎቹ በኩል የአዞ እንባውን ማፍሰስ ጀምሯል።

 ከማኅበሩ ቀንደኛና ተላላኪ ሰዎቹ መካከል ታደሰ ወርቁ፤ ዳንኤል ክብረት፤አባ ኃይለማርያም( የጵጵስና ተስፈኛው)፤ ሐራ ዘተዋሕዶና አንድ አድርገን ብሎጎች የመሳሰሉት ሁሉ እየተቀባበሉ የቃጠሎው እሳት የደረሰባቸው ያህል የአድኑን ጩኸታቸውን ሲያሰሙ እያየን ነው። የሁሉም ጩኸት በአጭር ቃል ሲገለጽ በክርስትና አክራሪነት ቦታ የለውም ወይም ለማኅበረ ቅዱሳን ይህንን የመሳሰለ ስም ሊጣበቅበት ተገቢ አይደለም የሚል ድምጸትን የያዘ ሆኖ አግኝተናል። ይሁን እንጂ ሰዎቹ በገደል ማሚቱ ድምጻቸው እየተቀባበሉ እውነታውን ለማዳፈን ቢፈልጉም እውነቱ በማስረጃ ሊገለጥ ይገባዋልና በዚህ ዙሪያ ጥቂት የምንለው አለን። ይከተሉን።

1/ ክርስትና፤

ክርስትና ክርስቶስ የሞተለት እምነት ስለሆነ ከሚሞቱለት በስተቀር ሌሎችን ሊገድሉለት፤ ሊደበድቡበትና ሊያሳድዱበት የተገባው ስላይደለ በእርግጥም ክርስትና ወግ አጥባቂነት፤ አክራሪነትና፤ ጽንፈኝነትና አይመለከተውም።

«ባልንጀራህን ውደድ ጠላትህንም ጥላ እንደ ተባለ ሰምታችኋል። እኔ ግን እላችኋለሁ፥ በሰማያት ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፥ የሚረግሙአችሁንም መርቁ፥ ለሚጠሉአችሁም መልካም አድርጉ፥ ስለሚያሳድዱአችሁም ጸልዩ፤ እርሱ በክፎዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን ያወጣልና፥ በጻድቃንና በኃጢአተኞችም ላይ ዝናቡን ያዘንባልና። የሚወዱአችሁን ብትወዱ ምን ዋጋ አላችሁ? ቀራጮችስ ያንኑ ያደርጉ የለምን? ወንድሞቻችሁንም ብቻ እጅ ብትነሡ ምን ብልጫ ታደርጋላችሁ? አሕዛብስ ያንኑ ያደርጉ የለምን? እንግዲህ የሰማዩ አባታችሁ ፍጹም እንደ ሆነ እናንተ ፍጹማን ሁኑ» (ማቴ 5፤43-48)

ከዚህ ተነስተን ይህንን የወንጌል እውነት ማኅበረ ቅዱሳን በተግባር ያሳያል፤ አያሳይም? የሚለውን ንጽጽር ከመመልከታችን በፊት የትኛውም እምነት ውስጥ ያለውን የሃይማኖት ወገንተኝነት ለይቶ ለመመልከት ይረዳን ዘንድ የማኅበረ ቅዱሳን አጎብጋቢዎች አክራሪነት አይመለከተንም የሚለውን ቃል ከተያያዥ ጉዳዮች ጋር ለይተን እንመልከት።

የሃይማኖት ወይም የድርጅት አባላት በየትኛውም ረድፍ ያሉ ቢሆንም መጠንና አፈጻጸማቸው ይለያያል እንጂ በሁሉም ዘንድ ጽንፈኝነት፤ አክራሪነትና ወግ አጥባቂነት አለ። እዚህ ላይ እምነትና ሃይማኖት አንድ አለመሆናቸውን ለይተን ማወቅ ይገባናል። እምነት /Faith/  ሲሆን ሃይማኖት የሚለው ደግሞ  / Religion/  የሚለውን ቃል ይወክላል። እምነት ማለት አማኙ እንደፈጣሪው፤ አዳኙ፤ ተስፋውና ፍጹም ዋስትናው አድርጎ በእምነት የተቀበለው መታመኛው ሲሆን ሃይማኖት ደግሞ እምነቱን የሚገልጽበት መንገድ፤ የሕግጋት፤ የመርህና የመለኪያ ተቋማዊ ስልት ነው። አብዛኞቹ በክርስትና ስም የሚጠሩት ሃይማኖቶች በእምነት ደረጃ ስለፈጣሪ ህልውናና ፍጹም መለኮታዊ ገዢነቱ ልዩነት የለባቸውም። ችግሩ የሚነሳው ያንን አንዱን አምላክ በሃይማኖት መርህና ሕግጋት ላይ በሚያነሱት አገላለጽ  ነው። ችግሩ ተያያዥነት የሚኖረው ደግሞ በእምነት አንድ አምላክ አለ ብለው ቢጠሩም ሃይማኖቱ፤ እምነቱን በሚገልጽበት ሕግጋትና መርህ ስለማይግባቡ እያንዳንዱ ከሌላው  ወይም ራሱ በውስጡ በሚነሳ  የአገላለጽ መርህና ሕግጋት የተነሳ በጽንፈኝነት፤ በወግ አጥባቂነት ወይም በአክራሪነት በሌላው  ወይም በውስጡ በሚነሳው ላይ ለማስከበር ይገደዳል። ስለሆነም ማኅበረ ቅዱሳን የአንድ ሃይማኖት ተለጣፊ አባል ስለሆነ ከሱ ጋር ከማይመሳሰሉ ከውጪያዊ አካላት ወይም ከውስጥ ከሚነሱ ተጠየቃዊ ሙግቶች ጋር በመጋጨት ሃይማኖታዊ መርህና ሕግጋቴ የሚለውን አቋም ለማስከበር መጋጨቱ የግድ ነው። ይህንን የጉዞ መንገዱ ከየትኛው ላይ ሊያሳርፍ ይችላል የሚለው ጥያቄ ሊነሳ ካልሆነ በስተቀር ከወግ አጥባቂነት፤ ከአክራሪነትና ከጽንፈኝነት ባንዱ ላይ መቆሙ ሳይታለም የተፈታ ነው። ስለሆነም ስለማኅበረ ቅዱሳን የሚከራከሩ የቤቱ በላተኞች ሥነ ሞገት ከንቱ ልፍለፋ ከመሆን አያልፍም።

2/ ወግ አጥባቂነት/ Fundamentalism/

ወግ አጥባቂዎች ለልምድ፤ ለባህል፤ ለትውፊት፤ ለሥርዓት ከፍተኛ ትኩረት ይሰጣሉ። ልምድ፤ ባህል፤ ሥርዓትና ትውፊትን መጠበቅ በራሱ በጎ ቢሆንም ከክርስትና የመዳን ሕይወት ጋር ምንም ግኙነት የለውም። አንዳንድ ጊዜ ባህል፣ ልምድና ትውፊት ከክርስትና ትምህርት መርሆዎች ጋር ስለሚጋጭ ያንን ወስዶ እንደአንድ መመሪያ አድርጎ መጠቀም አይቻልም። በክርስትና ታሪክ መነሻ ላይ ወግ አጥባቂ ሆነው የታዩት አይሁዳውያን ነበሩ። አይሁዳውያን እጁን ሳይታጠብ የበላውን እንደርኩስ ሲቆጥሩ ኖረዋል። ይህንን አለማድረግ ደግሞ ሃይማኖት የለሽነት ነው። የተፈታ ሱሪ መታጠቅ አይፈቀድም። ይህንን የወግ ማፍረስ ተግባር ለመከላከል ቀሚስ ለመልበስ ይገደዳሉ። እንደዚሁ ሁሉ ክርስቲያን በተባሉትም ዘንድ ዛሬም ድረስ ብዙ ወጎችና ልምዶች አሉ።

   ቅዳሜ ሳይገባ የዓርብ ውሃ መቅዳት ከቆዩ ልምዶች አንዱ ነው፤ ለንጽህናው ያይደለ የፍስክ ቀን መብያ እቃዎችን በጾም ዕለት ራስን ጾም ከማፍረስ ለመከላከል በዐመድና በፈላ ውሃ በማሸት ለማጠብ መጠንቀቅ ያደግንበት ማኅበረሰብ መለያዎች ናቸው። የግዝት ቀናት ተብለው በተወሰኑት ዕለታት ሥራ መሥራት እንደሚያስቀስፍ ይነገራል። ስለዚህም ገበሬው በወርኀ ዘር በሰኔ እጁንና እግሩን አጣጥፎ ይቀመጣል። የግዝት ቀን ወይም በመብረቅ የሚያስመታ ዕለት ተለይቶ አለመቀመጡን መናገር በወግ አጥባቂዎች ዘንድ ክህደት እንደመፈጸምና ሥርዓት እንደማፍረስ ያስቆጥራል።  ረቡዕ ቀን እንደጨለማ ቀን ስለሚታሰብ ቁርሱን የሚበላ ቢገኝ እንደኮተለከ ወይም እንደካደ ሊያስቆጥረው ይችላል። በሃይማኖት ሕግ እንጂ  በእምነት ስለረቡዕ ቀን አለመብላት የተጻፈ ነገር የለም። ወግ አጥባቂዎች ጾምን በወረቀት ሕግ እንጂ በእምነት ፈቃድ የሚፈጸም አድርገው አይቀበሉም።

«የሚበላ የማይበላውን አይናቀው የማይበላውም በሚበላው አይፍረድ፥ እግዚአብሔር ተቀብሎታልና» ሮሜ 14፤3 በወግ አጥባቂዎች ዘንድ ይህ አይሰራም።

 ወግ አጥባቂዎች ጥቃቅኑንም ይሆኑ ትላልቁ ወግ፤ ሕግጋትና መርኅ በሙሉ ተግባር ላይ ካልዋለ በስተቀር በእምነት ጽድቅ አለ ብለው ስለማያስቡ ይህ ስለመፈጸሙ ጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል ያደርጋሉ። ወግ አጥባቂዎች ባሉበት ይህንን ወግና መርህ ማፍረስ ትልቅ ወንጀል ነው። ያስከስሳል፤ ያሰቅላል። በወግ አጥባቂዎች ዘንድ ከቆየው ወግ የሚቀነስ ወይም የሚጨመር አንዳችም ነገር የለም።

  ሐዋርያት ጣታቸውን አመሳቅለው ስለማማተባቸው የተጻፈ ባይኖርም በወግ አጥባቂ ክርስቲያኖች ዘንድ ዛሬ አለማማተብ ብቻውን ክርስቲያን እንዳልሆነ ያስቆጥራል። ሰይጣን እንኳን የሚያማትበውን ምዕመን ቀርቶ ትልቁን መስቀል ተሸክሞ የሚቀድሰውን ቄስ፤ ተራ መነኩሴና ጳጳስ ማኅደሩ ሊያደርግ ይችላል።  ወሳኙ ነገር መንፈሳዊ ሆኖ ለመገኘት ከሥጋ ሥራ በአፍአም፤ በውስጥም ተለይቶ መገኘት ነው።

«በመንፈስ ብትመሩ ግን ከሕግ በታች አይደላችሁም። የሥጋ ሥራም የተገለጠ ነው እርሱም ዝሙት፥ ርኵሰት፥ መዳራት፥ ጣዖትን ማምለክ፥ ምዋርት፥ ጥል፥ ክርክር፥ ቅንዓት፥ ቁጣ፥ አድመኛነት፥መለያየት፥ መናፍቅነት፥ ምቀኝነት፥ መግደል፥ ስካር፥ ዘፋኝነት፥ ይህንም የሚመስል ነው። አስቀድሜም እንዳልሁ፥ እንደዚህ ያሉትን የሚያደርጉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም» (ገላ 5፤18-21)

ከዚህ ዓይነቱ ለሰይጣን ማኅደር የመሆን አድራጎት ሳይለዩ በማማተብ አጋንንት እንደሚሸሹ ማስተማር የወግ ጠራቂዎች አስተምህሮ እንጂ የሐዋርያት አይደለም። «ኢየሱስ ጌታ ነው» የሚል ቃል ደጋግሞ መናገርም በራሱ ለመጰንጠጥ እንደማስረጃ ሊቆጠር ይችላል።  ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማይም፤ በምድርም የሥልጣን ባለቤት ለመሆኑ የተሰጠው ስም«ኢየሱስ» መሆኑን ለመቀበል በወግ አጥባቂዎች ዘንድ እንደማሳነስ ይቆጠራል። ኢየሱስን ብቻ ማዕከል አድርጎ ከማስተማር ይልቅ የክብር ስም በመጨመር ኢየሱስን ከማንም በተሻለ ያመለኩ መስሎ ስለሚሰማቸው ለወጋቸውና ለልምዳቸው ይጠነቀቃሉ።

በአንገቱ ላይ በባለሦስት ቀለም ክር የከረረ ገመድ አለማሰር ወግ አጥባቂዎች ዘንድ ከማኅበራቸው አባልነት እንዳፈነገጠ ያስቆጥራል። ወግ አጥባቂዎች ክርስቲያን መሆናቸውን ለማሳመን የግድ ክር ማሰር ይጠበቅባቸዋል። ባለማሰራቸው አጋንንት እንደሚጨፍሩባቸው አእምሮአቸውን ስላሳመኑ እንዳይበጠስ እጅግ ይጠነቀቃሉ። ሌላው ሰው ስለሚያምነው ነገር ከመጠየቅ ይልቅ በአንገቱ ላይ ክር መታሰሩን አስቀድሞ በመመልከት ብቻ የማኅበራቸው አባል መሆኑን ለማወቅ ይጣደፋሉ። ክር በማሰር ክርስቲያን ለመሆን የሚጨምርለት ወይም ባለማሰሩ የሚያጎድል የእምነት ሕግጋት ባይኖረውም በወግ አጥባቂዎች ዘንድ ይህንን ማጓደል እንደክህደት ይቆጠራል። በልምድም ክሩን በጥሷል ከተባለ ክዷል ተብሎ ስለሚታሰብ አማኝ የመሆን ግዴታ ተደርጎ ይወሰዳል። በወግ አጥባቂዎች ዘንድ ካልሆነ በስተቀር ክር በአንገቱ ላይ ያላሰረ አይጸድቅም የሚል ክርስትና በክርስቶስም ሆነ በሐዋርያት አልተሰበከም። ይህ ደግሞ ያለወግ አጥባቂዎች በስተቀር ዓለም በመላው ይኮነናል የሚል አስተምህሮ የግብዝነት አንድ ማሳያ ከመሆን አይዘልም።

ወግ አጥባቂ ክርስቲያኖች ተረፈ አይሁዶች ናቸው። ከላይ ስንጠቅስ እንደቆየነው ወግ፣ ልምድና ባህላቸውን ለማስከበር በራሱ ክፋት ባይኖረውም ከክርስትና አስተምህሮ ጋር የሚጻረረውን ወይም እንደክርስትና መርህ ሊቆጠር የማይገባውን እንደሆነ አድርጎ ማስተማርን መቃወም በወግ አጥባቂዎች ዘንድ ሃይማኖቱን እንደመጻረር ስለሚቆጥሩ ያንን ለማስከበርና ለማስጠበቅ ኃይል እስከመጠቀም ይደርሳሉ። ማሳደድና መክሰስማ ዋነኛ መለያ ባህርያቸው ነው። አይሁዳውያን ክርስቶስን ከከሰሱስበት ክስ አንዱ የአባቶች ወግ ያፈርሳል የሚለው ክስ ይገኝበት ነበር። በተመሳሳይ መልኩ ይህንን ክስ በማቅረብና በመወንጀል የዘመኑ ተረፈ አይሁድ ማኅበረ ቅዱሳን ስለመሆኑ አድራጎቱን ተመልክቶ መናገር ይቻላል። የማኅበረ ቅዱሳኑ አዝማሪ ዳንኤል ክብረት በአንድ ወቅት ማኅበረ ቅዱሳን የስለላ ማዕከል እንዳለው የገለጸው ለክስና ለውንጀላ ብሎም ለማሳደድና ለግድያ የሚጠቀምበት ስልት እንደሆነ ያስረዳናል። ስለላ የክርስትና ባህርይ መገለጫ አይደለም። የወግ አጥባቂዎችና የአክራሪዎች ጠባይ እንጂ። ወግ አጥባቂዎች ሃይማኖት እንጂ እምነት የላቸውም።

 እምነት በክርስቶስ በማመን የሚገኝ ጸጋ ሲሆን ሃይማኖት ደግሞ ወጉን በማስከበር ለማግኘት የሚታገሉበት ተቋማዊ ደንብ ነው።  ዳሩ ግን እምነት ከድካምና ወግን ከመጠበቅ የሚታደግ እንዲያው የተሰጠ ቢሆንም ይህንን ለማግኘት በድካም መጣር ግን የእውቀት እጦት መገለጫ ነው። ሐዋርያው ጴጥሮስ በገሊላ ባህር ላይ ሌሊቱን መረቡን ሲጥል አድሮ አንዲትም ዓሳ መያዝ አልቻለም ነበር። ጌታ በታንኳይቱ በስተቀኝ ጣሉ ባላቸው ጊዜ ሌሊቱን ሁሉ ስንደክም አንዳችም ባላገኘንበት ባህር ላይ ለምን ታደክመናለህ? ሳይሉ በእምነት መረባቸውን በጣሉ ጊዜ ያገኙት እንደወትሮው  አልነበረም። ከመቼውም ጊዜ የበለጠና ሐዋርያቱን ሁሉ ለመረብ ጉተታው የጋበዘ ነበር። ሰዎች በራሳቸው መንገድ የጽድቅን ዓሳ ማጥመድ ይፈልጋሉ፤ የጽድቅ ዓሳ ደግሞ በእምነት እንካችሁ በተባልንበት ከጽድቅ ጀልባችን በክርስቶስ የተሰጠችን ናት።

«አብርሃም በሥራ ጸድቆ ቢሆን የሚመካበት አለውና፥ ነገር ግን በእግዚአብሔር ዘንድ አይደለም። መጽሐፍስ ምን አለ? አብርሃምም እግዚአብሔርን አመነ ጽድቅም ሆኖ ተቈጠረለት። ለሚሠራ ደመወዝ እንደ ዕዳ ነው እንጂ እንደ ጸጋ አይቈጠርለትም፤ ነገር ግን ለማይሠራ፥ ኃጢአተኛውንም በሚያደድቅ ለሚያምን ሰው እምነቱ ጽድቅ ሆኖ ይቆጠርለታል። ( ሮሜ 3፤2-5)

ወግ አጥባቂው ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን አይቀበልም፤ ይህንን ለማስከበር ደም ያፈሳል፤ ይከሳል፤ ይሰልላል።  ይወነጅላል። ማኅበረ ቅዱሳን ቁጥር አንድ የኦርቶዶክስ ፌንዳሜንታሊስት ነው?  መስፈርቶቹን ስለሚያሟላ መልሱ አዎ ነው፤ ነው። ወግ አጥባቂ ወጉን፤ ባህሉን፤ ልምዱን፤ ትውፊቱን ለማስከበር ሲል በሚወስዳቸው የስለላና ኃይል አማራጮቹ የተነሳ ወደአክራሪነት የማደግ ተጽዕኖ አለው።

3/ አክራሪነት /Extremism/

አክራሪነት በውስጡም፤ በውጪውም «እኔ ብቻ» የሚል ጠባይ ይከተለዋል። ሌላውን አልይ፤ ብትወዱኝ ተቀበሉኝ፤ ባትወዱኝ ጥፉ የሚል መርህ ይቀድመዋል። አክራሪ አብዛኛውን ጊዜ በጉድጓድ ውስጥ ሆኖ ቀና ሲል በሚታየው ሰማይ ልክ ዓለሙን የሚመለከት ሰውን ይመስላል። ከእርሱ በስተቀር ማንም እንዲኖር አይፈልግም። ከእርሱ ውጪ ያለው የትኛውም ሃይማኖት አቻ ሆኖ የመኖር መብት የለውም። በውስጡም ሃይማኖታዊ ህግጋቱን የማይጠብቁ ወይም በተቀመጠው ላይ መጠይቅ የሚያቀርቡ ሁሉ በማስተማር ወይም በመነጋገር መፍትሄ ይመጣል ብሎ ስለማያምን ለመግደል፤ ለመበቀል ወይም ሀገር አስለቅቆ ለማባረር ምን ጊዜም ዝግጁ ነው። በአብዛኛውም የተለየውን ወይም ሊለየው የፈለገውን ወይም የተለየና በእሱ ላይ ጣቱን የሚቀስረውን ጣት ከመቁረጥ በዘለለ በመሞት ዋጋውን ማግኘት አለበት ብሎ ያምናል። በ17ኛው ክ/ዘመን በካቶሊኮችና በተሐድሶ አንቃኞች መካከል ዋና ግጭት ያስነሳው ጉዳይ የካቶሊኮች የሁሉ የበላይነት አባዜ ነበር። እንደ ካቶሊክ ኢንሳይክሎፒዲያ አባባል «apostolic succession is only “found in the Catholic Church” and no “separate Churches have any valid claim to it» ሐዋርያዊ ወራሽነት የሚገኘው በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ብቻ በመሆኑ ሌላው የትኛውም ከዚህ የተለየ ቤተ ክርስቲያን  ይህንን ቢል ዋጋ የሌለው ነው» የሚለው ለአክራሪነት መቀስቀስና ያንን ያልተቀበለውን ለመደምሰስ የተደረገው ፍጅት ተጠቃሽ ነው። በኢትዮጵያችንም ውስጥ መጽሐፍ ቅዱስ ይዘናል የሚሉ ክርስቲያኖች ሁሉ በአንዲት እምነት፤ ጥምቀትና ጌታ ቢያምኑም እኔ ብቻ እወከልበታለሁ ሊል የሚችል ብቸኛ አካል ማንም የለም።  እያየን ያለው ነገር ግን በእምነት ሌላውን የሚቀይር ምግባር ከማሳየት ይልቅ በመፈክር ሌላውን ለአጸፋ የሚያነሳሳ ሰልፍ በማኅበረ ቅዱሳንና በጥምቀት ተመላሾች በአደባባይ መታየቱ ለማን? ምን ዓይነት መልዕክት ለማስተላለፍ ተፈልጎ ነበር? እንድንል ያደርገናል። የማኅበረ ቅዱሳን ስልትና አፈጻጸም ግን ጥበባዊና ስልታዊ መንገድን የተከተለ ስለሆነ ሽፋኑ በሃይማኖታዊ ስርዓት ከለላ ስለሚፈጸም በሰይፍ ወይም በፈንጂ ሲገድል አይታይም። እኔ ብቻ ለዚያ የበቃሁ ነኝ የሚል ሃይማኖታዊ መፈክር በማጥለቅ አደባባይ መታየት የጠብ ያለሽ በዳቦ ጥሪ ከመሆን አይዘልም።
ከዚሁ ጋር በዋናነት የሚጠቀሰው የዘመናችን አክራሪ ቡድን የእስልምና ወሃቢያ ቡድን ነው። ሃማኖታዊ ስልጣንን ከነመንግሥታዊ ሥርዓት የመቆጣጠር ኢስላማዊ ዶክትሪን ከዐረብ ሀገር የሚጫንለት አንዱ ክፍል ሲሆን ወሀቢያ ባለበት የዓለም ቦታ ሁሉ ሁከትና ፍጅት አለ። ኢትዮጵያም በዚህ አክራሪ ጥቁር መዝገብ ውስጥ ከሰፈሩ ሀገራት አንዷ መሆኗ ይታወቃል።ወግ አጥባቂዎችም ሆኑ አክራሪዎች ተመሳሳይ ጠባያቸው ሁሉንም ነገር የሚፈቱበት መንገድ በኃይል መሆኑ ነው። እኔነትን ማዕከል በማድረግ ይንቀሳቀሳሉ። ለሌላ ሃሳብ በፍጹም እድል አይሰጡም። አክራሪነት ግን በደረጃው ከወግ አጥባቂነት ይበልጣል።

4/ ጽንፈኝነትና ዐመጸኝነት  /Radicalism, fanaticism/

ጽንፈኝነትና ዐመጸኝነት እኔነትንና  ለእኔነት ከሚመጣው ቀናተኝነት የሚመነጩ የኃይል ተግባራት መገለጫዎች ናቸው። በዚህ አድራጎት ላይ ወግ አጥባቂዎችም ሆኑ አክራሪዎች እንደአሰላለፋቸውና አቅማቸው በየደረጃው ጥቅም ላይ ያውላሉ። ተግባራቱ በስውርም፤ በግልጽም ሊካሄዱ ይችላሉ። ሃይማኖትን ሽፋን በማድረግ ወይም ፖለቲካን እንደከለላ በመጠቀም የሚፈልጉትን ስውርና ግልጽ ዓላማ በእጅ ለማድረግ የሚጓዙበት የኃይል መንገድ ነው። በዚህ ጥበብ ደግሞ ማኅበረ ቅዱሳን በደንብ ተክኖበታል። መንገዱ ደግሞ ስውር ነው። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ለመቆጣጠር የራሱን ምልምል የጳጳሳት ኃይል ማደራጀት፤ በምርጫ ሂደት እንዲሾሙ መረባረብ፤ ደጋፊ ያልሆኑትን ወደዚያ ስልጣን እንዳይደርሱ የስም ማጥፋት ዘመቻ ማካሄድ፤ በስራ ላይ ያሉትን ደግሞ ለራሱ ዓላማና አደረጃጀት ከጀርባ ሆኖ መጠቀም፤ ማኅበረ ቅዱሳን ተቀባይነት ባጣባቸው ቦታዎች በራሱ ስውር ኃይል ሁከትና ብጥብጥ መቀስቀስ ለምሳሌ /በሃዋሳ በሐረርና በድሬዳዋ/ እንደተፈጸመው፤ ጠብ ቀስቃሽና ዐመጽን አነሳሽ መፈክር፤ ባጅ/ምልክት/ ሪቫን/ ጥለትና ክር በማሰር በሃይማኖት ሰበብ ወጣቶችን ማሰማራት የመሳሰሉትን ያካትታል። በፖለቲካ ምርጫ ሽፋን የራስን ደጋፊ ወይም መውደቅ የሚገባውን ክፍል ለመጣል ኃይልን በበቂ የአእምሮ ትጥቅ ማሰለፍን ሊያካትት ይችላል። በዚህ ዙሪያ ወሃቢያ ከመጣላቱ በፊት የኢትዮጵያ መንግስት ደጋፊ መስሎ አባላቱን ለመሰግሰግ ሞክሯል። ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ በተቃራኒው ይበጀኛል በሚለው ጎራ በስውር ተሰልፎ እንደነበር ይነገራል። አመራሮቹ እንደሚናገሩት ለስልታዊ አካሄድ ይሁን አምነውበት እንደሆነ ለጊዜው ባናውቅም በአንድ መግለጫቸው አብዛኞቻችን የኢህአዴግ አባላት እኮ ነን ሲሉ አድምጠናቸዋል። ምን ለማለት ተፈልጎ ነው? የኢህአዴግ አባል ሆኖ አለመገኘት ዋጋ እንደሚያስከፍል ለመግለጽ የተፈለገና የታመነበት ይመስላል። አዎ ለስውር ዓላማ ግብ መሳካት አባል ነን ብሎ ማወጅ ጠቃሚ ነው።

ጽንፈኝነትና ዐመጸኝነት ሁኔታዎችን ጠብቆ፤ አጋጣሚዎችን ተጠቅሞ ስውርና ግልጽ ዓላማን የማስፈሚያ የኃይል መንገዶች ናቸው። ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ ለዚህ ድርጊት ፈዛዛ አይደለም። ስለዚህ የማኅበረ ቅዱሳንን ፍርፋሪ የበላችሁ ዳንኤል፤ ታደሰ ወርቁና ሐራ ዘተዋሕዶ፤ እንዲሁም ፍርፋሪውን የምትጠብቁ እጩ ጳጳስ እንደሆነ ቃል የተገባለት አባ ኃይለ ማርያም  ስለማኅበሩ ያለቀሳችሁት የአዞ እንባ እውነታውን አይሰውረውም። ማኅበረ ቅዱሳን ወግ አጥባቂና ጽንፈኛ ማኅበር ነው። አራት ነጥብ።