Friday, October 25, 2013

ኢትዮጵያውያን እንኳን በሀገራቸው በባዕድ ሀገር የነጻነትና የሃይማኖት መምህራን ነበሩ!!


በ1808 እ/ኤአ ኢትዮጵያውያን የንግድ ሰዎች ወደአሜሪካ ያቀናሉ። በቆይታቸውም ከነጮቹ ቤተ ክርስቲያን  የሰማይና የምድር ገዢ ለሆነው አምላካቸው ጸሎት ለማድረስ ይገባሉ። ይሁን እንጂ የዘር፤ የቆዳ ቀለምና የነገድ ልዩነት በሌለው አምልኮተ እግዚአብሔር ኢትዮጵያውያንን በነጮቹ ቤተ ክርስቲያን ያጋጠማቸው ነገር የተለየ ነው። ለጥቁሮቹ ተለይቶ ከተሰጠው ክልል ውጪ በጸሎት ቤት ውስጥ ከነጮቹ ጋር በእኩልነት መጸለይ ይከለከላሉ። ኢትዮጵያውያኑም የነጭና የጥቁር ተብሎ የተለየ አምላክ ሳይኖር በጸሎት ቤት ጥቁሮቹን የማግለል አሠራር ባለመቀበላቸው ጸሎት ቤቱን ለቀው ይወጣሉ። በዚህን ጊዜ በዚያ የነበሩ አሜሪካውያን ጥቁሮችም የመገለሉን እርምጃ ከተቃወሙት ኢትዮጵያውያን ጋር ተከትለው ይወጣሉ። በኢትዮጵያውያኑ መሪነት ጥቁሮቹ አሜሪካውያን በኒውዮርክ ከተማ አዲስ ቤተ ክርስቲያን በመመስረት ጸሎታቸውን በነጻነት ለመቀጠል ቻሉ።  ጥቁር አሜሪካውያን እስከዛሬ ድረስ በዚሁ ቤተ ክርስቲያን እያከናወኑ የሚገኝ ሲሆን በየጊዜው በሚያዘጋጁት መንፈሳዊ ጉዞ የእምነት ነጻነትን ስላስተማረቻቸው ቤተ ክርስቲያንና ባርነት በመዋጋት ነጻ ሀገር ሆና የመዝለቋን ታሪክ በማስታወስ እናት ምድራችን የሚሏትን ኢትዮጵያን ይጎበኛሉ። በተቃራኒው ደግሞ እናት ምድር ኢትዮጵያን ትተው ኢትዮጵያውያን ደግሞ ይሰደዳሉ። አሳዛኝ ነገር ነው። ከዚህ በፊት ይህንን በተመለከተ ያወጣነውን ዘገባ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ።
የአቢሲኒያን ባፕቲስት ቤተ ክርስቲያን መሪ የሆኑት ዶ/ር ቄስ ካልቪን በትስ በየዓመቱ በሚታሰበው የጥቁር አሜሪካውያን ታሪክና ማንነት ጥናታዊ ጉባዔ ላይ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ከነባለቤታቸው በተገኙበት ትልቅ ንግግር አድርገዋል። ፎክስ ኒውስ ደግሞ ስለኢትዮጵያ ታላቅ ሀገርነት፤ ታሪክና እምነት ሰፊ ሽፋን ሰጥቷል።  በዚህ በአፍሪካውያን ታሪክና ባህል ዓመታዊ የጥናት ጉባዔ ላይ የፕሮግራም መሪ የነበረችው በታዋቂው የቢል ኮስቢ/Bill Cosby/ ተከታታይ የቤተሰብ ፊልም ላይ መሪ ተዋናይት የነበረችው ፊሊሺያ ራሻድ ነበረች። ኢትዮጵያውያን ነጻነትን በሀገራቸው ብቻ ሳይሆን በባዕድ ሀገር ጭምር ሄደው ማስተማር የቻሉ ሕዝቦች ነበሩ። እንደዚህ እንደዛሬው በባርነት መልክ በዐረብ ሀገራቱና በየምዕራቡ ዓለም በስደት ጉልበታቸውን እንደሸቀጥ ከነነጻነታቸው ጭምር  ከመሸጣቸው በፊት ማለት ነው። ለማንኛውም ኢትዮጵያና የጳውሎስ መልዕክት ትርጉም የተወደሰበት ዝግጅት ይህንን ይመስላል።

«አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና» ገላ 3፤28