Showing posts with label ማብራሪያ. Show all posts
Showing posts with label ማብራሪያ. Show all posts

Monday, May 27, 2013

የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ለምን ተሐድሶ ያስፈልጋታል?


ምንጭ፡-http://www.tehadeso.com/
ቤተ ክርስቲያን በእግዚአብሔር እና በክርስቶስ ደም የታደሱና የተቀደሱ የምእመናን ጉባኤ ናት፡፡ ይህቺን አማናዊት ቤተ ክርስቲያን ከሐዋርያት ዘመን ጀምሮ ታሪኳን ስናጠና በእግዚአብሔር ሐሳብ ውስጥ የሰው ሐሳብ እየተቀላቀለ እና ጤናማውንና ርቱዕ የሆነውን አስተምህሮ የሚያደፈርሱ ሰብኣዊ፣ አጋንንታዊና ዓለማዊ ሐሳቦች በተለያየ ሁኔታና መንገድ ወደ አማናዊቷ ቤተ ክርስቲያን ዘልቀው እየገቡ እውነተኛ የሆነውን መንፈሳዊ ትምህርትም ሲያደፈርሱ እናያለን፡፡ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ ያሉ ለእውነተኛው የእግዚአብሔር ሐሳብ ቀናዕያን የሆኑ ቅዱሳን የእግዚአብሔርን ሐሳብ በሚያደፈርሱ አስተሳሰቦች እና ግለሶቦች ላይ ጠንከር ያለ ተግሣጽ ሲሰጡና አስፈላጊውን የእርምት እርምጃ ሲወስዱ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እናነባለን፡፡ ምክንያቱም ተሐድሶ አዲስን ነገር አፍልቆ ማምጣትና በነበረ እውነት ላይ መጨመር ሳይሆን ከጌታችንና ከሐዋርያት የተቀበልነውን የሚያድነውን መለኮታዊ መገለጥ (አስተርእዮ) የሚጋርድ ትምህርትና ድርጊት ሲከሠት መጽሐፍ ቅዱሳዊውን ትምህርት ለመጠበቅ የሚወሰድ የእርምት እርምጃ ስለሆነ ነው፡፡
ቤተ ክርስቲያናችንም ሐዋርያዊት በመሆኗ የተመሠረተችበት የእምነት መሠረት አማናዊ እንደሆነ እሙን ነው፡፡ ነገር ግን በየጊዜው ምንጫቸው የማይታወቅ፣ ከእግዚአብሔር ይልቅ ዲያብሎስንና ሰብእን ከእውነት ይልቅ ሐሰትን የሚያገለግሉ አስተሳሰቦች እና አስተምህሮዎች በመስኮት እውነተኛው የእግዚአብሔር ሐሳብ ወደ ጎን ተትቶ መንፈሳዊ ሕይወታችን ታውኮ በእውነተኛው ትምህርት ላይ ሐሰት ተቀላቅሎበት መንፈሳዊ ቁመናዋ ተበላሽቶ እንመለከታለን፡፡
ይህንን መንፈሳዊ ዝቅጠት የተመለከቱ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና መምህራን በየዘመናቱ እርምት እንዲወሰድበት ሲታገሉና ሲያስተምሩ ቢኖሩም ከእግዚአብሔር ያልሆነው ከቅዱሳት መጻሕፍት (ከአሥራው መጽሐፍት) የሚቃረነው አዲስ ትምህርት እንዳይታረም በነገሥታቱ ተደግፎና ታግለውለት ሲቆይና ሌላ ጊዜ ደግሞ ጨዋው ከአባቶቼ የተቀበልኩት ትምህርት ስለሆነ በማለት በእውነተኛ የክርስትና ትምህርት ላይ እንደ እራፊ የተለጠፈውን ባዕድ ትምህርት ለማስጠበቅ ሊቃውንቱንና መምህራኑን አፉን ሞልቶ “መናፍቃን ናችሁ” ብሎ መከራና ስደት እንዲነሣባቸው በማድረጉ በቤተ ክርስቲያናችን ታሪክ ብዙዎች ስለቤተ ክርስቲያንና ስለእግዚአብሔር እውነት በብዙ መከራ ሕይወታቸውን መሥዋዕት አድርገዋል፡፡ ሌሎችም ተሰድደዋል፤ ተደብድበዋል፤ ታስረዋል፤ ተራቁተዋል፡፡
ይህ በመሆኑና ዛሬም በወንጌል ትምህርት ላይ የተጨመረ አሳሳች ትምህርትን እንደ ዶግማ የሚቆጥሩ የተደራጁ የእውነት ጠላቶች በመኖራቸው ብዙ የማስፈራሪያ ድምፅ ስለሚያሰሙ መምህራኑ አፋቸው ተለጉሞ በመከራ አሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ይህ አደጋ ክፉውን መንፈስ ሊያገለግሉ በቆረጡ ደጋፊዎቹ ታጅቦ ሙሉ በሙሉ የመንፈስ ቅዱስን ሐሳብ የሚዋጋ የዲያብሎስ ጦር ሆኖ ይታያል፡፡ እንዲህ ያለውን አደጋ ገልጦ ማሳየት እና ቤተ ክርስቲያን ወደ አማናዊው የክርስቶስ ሐሳብ እንድትመለስ ማድረግ የማንኛውም ጤናማ አእምሮ ያለው ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን ግዴታ ነው፡፡ ከዚህም በመነሣት ለሰው ሳይሆን ለእግዚአብሔር ሐሳብ በመቅናት፣ ሰውን ሳይሆን እግዚአብሔርን በመስማት ቤተ ክርስቲያናችን ለምን ተሐድሶ እንደሚያስፈልጋት አስረጅ የሆኑ ምክንያቶችን እናቀርባለን፡፡
1.    በቤተ ክርስቲያኒቱ እንግዳ ትምህርቶች ስለበዙ
ክርስትናን በተመለከተ ከመሥራቹ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትና ከእርሱም ቀጥሎ ከእግሩ ሥር ቁጭ ብለው ከተማሩ ሐዋርያት ትምህርት የበለጠና የተሻለ ትምህርት አይገኝም፡፡ እነዚህ ትምህርቶች ለክርስትናችን ቋሚ መሠረት ሆነው የሚታዩና በምንም ሌላ እንግዳ ትምህርት ሊተኩ የማይችሉ ናቸው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “እኛም ብንሆን ወይም የሰማይ መልአክ ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ የተረገመ ይሁን” ብሎ በጻፈልን አምላካዊ ቃል ሙሉ በሙሉ መስማማት ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው (ገላ. 1÷8)፡፡ ወደ ፊት በስፋት እና ነጥብ በነጥብ የምንተችበት ቢሆንም በአንዳንድ ገድላት፣ ድርሳናት እና ተአምራት ላይ ተጽፈው የሚገኙ ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር በቀጥታ የሚጋጩ እንግዳ ትምህርቶችን ቤተ ክርስቲያኒቱ በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ራስዋ ተመልክታ ልታስተካክላቸው ስለሚገባ ወደ እውነተኛውና ከአምላኳ ወደተቀበችው ትምህርት እንድትመለስ ተሐድሶ ያስፈልጋታል፡፡
እንግዳ ትምህርቶቹ መወገድ የሚገባቸው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህች ምድር ወርዶ የሰው ልጆችን ለማዳን በመስቀል ላይ የሠራውን ሥራ ስለሚያቃልሉ እና እነዚህን ትምህርቶች እውነት ናቸው ብለው የተቀበሉት ሰዎች ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ባለመቻላቸው አንዳንዶች እነዚህን እንግዳ ትምህርቶች የኢትዮጵያዊነት መለያ አድርገው ቢወስዱዋቸውም፣ እንደ እውነት ቢከራከሩላቸውም፣ የሰው ልጆችን ከኀጢአት እስር ፈትቶ የዘላለም ርስታቸውን መንግሥተ ሰማያትን እንዲወርሱ ያደረገው የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው እንጂ ሌላ ምንም ነገር ስላይደለ ከሲኦል እስር ከዲያብሎስ ቁራኛነት ለመላቀቅ ከቃሉ ውጭ የሆኑ ሐሳቦችን ሽረን ለወንጌሉ እንግዳ የሆኑ ትምህርቶችን ትተን በጠራው የመስቀል መንገድ ላይ በእምነት መጓዝ በዚህ ዘመን ለቤተ ክርስቲያን ወሳኝ ጊዜ ስለሆነ ይህን ውድቀቷን በቃለ እግዚአብሔርና በመንፈስ ቅዱስ ምርመራ ከእንግዳ ትምህርቶች ልትለይ ይገባልና ተሐድሶ ያስፈልጋታል፡፡
2.    የእግዚአብሔር ቃል ተገቢውን ስፍራ ስላጣ
ሌላው ቤተ ክርስቲኒቱ ተሐድሶ እንደሚያስፈልጋት አስረጅ የሆነው እውነት ቅዱስ ወንጌል በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያናችን ተገቢውን ስፍራ ማጣቱ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሁሉን መጽሐፍ ይመረምራል፣ ይመዝናል፤ እርሱ ግን  በየትኛውም መጽሐፍ አይመረመርም፤ አይመዘንም፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱስ እውነት የተለየ ሐሳብ ያለው ማንኛውም በቤተ ክርስቲያን የምንገለገልበት  መጽሐፍ ሌላ ምንም አይነት አንድምታ ሳያስፈልገው ከስህተት ትምህርት ጎራ ሊካተት ይገባዋል፡፡ ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ የሁሉ ዳኛ በሆነው በእግዚአብሔር መንፈስ በመጻፉና የእግዚአብሔርን እውነት በመያዙ ነው፡፡ አሁን  ግን ምንጫቸው የማይታወቅ እና በቀጥታ መጽሐፍ ቅዱስን የሚቃረኑ መጻሕፍት ከመጽሐፍ ቅዱስ እኩል መሳ ለመሳ በመቀመጣቸው እና መጽሐፍ ቅዱስን በመገዳደራቸው በእውርነት ልምራችሁ የሚሉንን መጽሐፎች ተገቢውን ስፍራቸውን ማሳወቁ አግባብ ስለሆነ ተሐድሶ ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስፈላጊ ነው፡፡
ሌላው ቀርቶ በስብከተ ወንጌል መርሐ ግብር ወቅት ንጹሑን ወንጌል መስበክ እንደ መናፍቅነት እየተቆጠረ ስለመጣ አገልጋዮች የግድ የእግዚአብሔርን እውነት የሚጋፉ መጻሕፍትን እየጠቀሱ እነርሱም አገልግሎታቸውም የእግዚአብሔርን መንግሥት እውነተኛ ሐሳብ የሚቃረኑ እየሆኑ መጥተዋል፡፡ የእውነተኛ ኦርቶዶክሳዊነት መሠረቱ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እና በሐዋርያት አባቶች የተሰበከውን ቃል በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ማብራራት መሆኑ እየቀረ ድርሳነ ባልቴትን መተረክ እየሆነ ይገኛል፡፡
እንዲህ ያለው አስተሳሰብ በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ትክክለኛውን ተሐድሶ ካላገኘ እና ቤተ ክርስቲያኒቱ ሙሉ በሙሉ መመሪያዋ እንዲሆናት ወደ እግዚአብሔር ቃል ካልተመለሰች አሁንም ቢሆን በየዕለቱ እየጨመረ የመጣውን የምእመናን ፍልሰት ማስቆም ይቸግራታል፡፡ ሰውን በስፍራው ለማጽናት የተሻለው እና እግዚአብሔርም የሚደሰትበት ትክክለኛው መንገድ የእውነትን ቃል በእውነት ሳያፍሩ እና ሳይሸሽጉ እንደ ጥንት አባቶቻችን ለሕዝቡ መግለጥ ነው፡፡ ለዚህም ቤተ ክርስቲያን ጤነኛ በሆነ የተሐድሶ ኣስተሳሰብ ልትቃኝ ያስፈልጋታል፡፡
3. የመዳንን እውነት የሚገዳደሩ ትምህርቶችን ማስተናገድ ስለጀመረች
የልጅ ቡኮ ዕለቱን ነው
ቢጋግሩት ነቀፋ ነው
ቢቀምሱትም የከረፋ
ቢጨብጡት ወዮ አበሳ
እንደተባለው መንፈስ ቅዱስን ሳያማክሩ ለአሸናፊው የእግዚአብሔር ሐሳብ ብቻ መገዛትን ትተው የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተምሮ በማያውቁ እና ለስሜታቸው ባሪያ በሆኑ ሰዎች እየተፈጠሩ ያሉት አዳዲስ አስተምህሮዎች ሀይ ባይ ከልካይ አጥተው የክርስቶስን መስቀል እየወጉ ይገኛሉ፡፡ እኛም እንደ ቤሪያ ምእመናን “ነገሩ እውነት ይሆንን?” በማለት ለመመርመር ከመሞከር ይልቅ “ከኛ ወገን ያለ ሁሉ የሚለው ሁልጊዜ እውነት ነው” በሚል በጨዋ ምእመን አመክንዮ ተይዘን ለስህተት ትምህርቶች ተገዝተን እንገኛለን፡፡ እነዚህ የስህተት ትምህርቶች የመዳንን እውነት ቀስ በቀስ እየሸረሸሩ አሁን ፊት ለፊት መዋጋት ጀምረዋል፡፡ “ያለ ድንግል ማርያም አማላጅነት ዓለም አይድንም” የሚለውና እርሱን የመሰሉ ጥንተ ተፈጥሮዋቸው አጋንንታዊ የሆኑ እና “መዳን በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና” (የሐዋ.ሥራ 4÷12) የሚለውን የመንፈስ ቅዱስ አዋጅ የሚሽሩ እንግዳ ትምህርቶች በመጽሐፍ ደረጃ ታትመው እስከ መሰራጨት ደርሰዋል፡፡
በእግዚአብሔር ቃል የተገለጸውን “መዳን በሌላ በማንም የለም” ተብሎ የተዘጋውን የጽድቅ ማኅተም የሚከፍቱ በመጽሐፍ ቅዱስ ከተገለጸው እውነት ውጭ  ሌላ አማራጭ አለ ብለው የሚያስተምሩ ሁሉ ለሰው መዳን ሳይሆን መጥፋት በአጋዥነት የሚሠሩ ናቸው፡፡ ከዚህ ጋር የተያያዙ እና በዝክር፣ ወንዝ በማቋረጥ፣ ገዳማት በመሳለም፣ በቀብር ቦታ እና በሌሎችም ብዙ መንገዶች ሰው ሊድን ይችላል፡፡ ብለው የሚያስተምሩ ደፋር ብዕር የገለበጣቸው አጋንንታዊ ሐሳቦች ያሉባቸው ገድላት እና ተአምራት በመኖራቸው ሕዝቡ ያዳነውን ጌታ በእውነተኛ ማንነቱ ሳይረዳ በዋል ፈሰስ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡
መዳን የህልውና ጉዳይ ስለሆነ በቀላሉ ሊታይ የሚችል አይደለም፡፡ እናቶቻችን እንደሚሉት “እስቲ ይሁና!! ምን ይታወቃል የአንድዬ ሥራ” በማለትም በቀላሉ ሊታለፍ የሚችል ነገርም አይደለም፡፡ የአንድዬ ሥራ የሚታወቅ እና በአደባባይ በመስቀል ላይ የተከናወነ ነው፡፡ አንድዬ ለመዳናችን ከደሙ የተሻለ አማራጭ አልሰጠንም፡፡ በመስቀል ላይ የፈሰሰውን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ደም ለኔ ስለኃጢአቴ የተከፈለ ቤዛነት ነው ብሎ አምኖ መቀበል ለመዳን ዋነኛውም ብቸኛውም አማራጭ ነው፡፡
ነገር ግን ህዝቡ ይህንን እውነት አምኖ እንዳይቀበል የሚከለክሉ ሌላም አማራጭ አለህ ብለው የሚያስተምሩ በክርስቶስ የተሰጠንን መዳን ቀብረው ማሳሳቻ የሚሰብኩ ስለበዙ ቤተክርስቲያናችን ወደ ሐዋርያት ትምህርት እንድትመለስ መታደስ አለባት፡፡ መዳን በክርስቶስና በመስዋዕታዊ ሞቱ በማመን መሆኑን መቀበልና ማስተማር አዲስ ትምህርት የሚመስላቸው አሉ ግን አይደለም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ እና በተደጋጋሚ የተቀመጠ፣ ሐዋርያት የሰበኩት እስከ ዘመናችን ድረስ እውነተኛውን መንገድ የተከተሉ እንደ እነ ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ያሉ አባቶቻችን መዳን በእግዚአብሔር ጸጋ ብቻ የሆነ እና በክርስቶስ በማመን ብቻ የምንቀበለው ነው፡፡ ብለው ያስተማሩት ትምህርት ነው፡፡(ትምህርተ ሀይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት )
ስለዚህ በእነዚህ እና በሌሎች ተጨማሪ ምክንያቶች ተሐድሶ ለቤተክርስቲያኒቱ ያስፈልጋታል ብለን እናምናለን፡፡ ለእናት ቤተክርስቲያናችን መታደስም የበኩላችንን አስተዋጽኦ ለማድረግ እናገለግላለን፡፡
ይቀጥላል

Saturday, May 4, 2013

«ደብዳቤ ከመጻፍ መነጋገር፤ ወደሌላው ጣትን ከመጠቆም ቅድሚያ ራስን ማየት፤ ማኅበራትን ተስፋ ከማድረግም በሥራ ማሳየት ይሻል ነበር»


 
ቅዱስ ፓትርያርኩ ለአቡነ አብርሃም ሰሞኑን የንብረት አስረክብ ደብዳቤ መጻፋቸው ይታወሳል። ቅዱስ ፓትርያርኩ ከዚህ ቀደም የተጻፉትንና የተደረጉትን የጽሁፍ ልውውጦች መነሻ በማድረግ ደብዳቤውን ለመጻፍ መቻላቸውን እንጂ በእርሳቸው ደረጃ አቡነ አብርሃም ለምን እስካሁን እንዳላስረከቡ ወይም ለማስረከብም ይሁን ላለማስረከብ ያበቃቸውን ምክንያቶች ምን እንደሆኑ ለማወቅ ያደረጉት ውይይትም ይሁን ንግግር ስለመኖሩ በተጻፈው ደብዳቤ ውስጥ ምንም አልተገለጸም። ደብዳቤውን ለመጻፍ የሚያበቁ አሳማኝ ምክንያቶች መኖራቸው ቢታመንም እንኳን አቡኑን አስጠርቶ በአካል በማወያየት እሺታቸውን ይሁን እምቢታቸውን መረዳቱ የበለጠ ተቀራርቦ የመሥራት ምልክት መሆን በቻለ ነበር። የፓትርያርኩም  አዲስ የሥራ መንፈስ መሆኑን ለመረዳትም እድል እናገኝበት ነበር። ከዚህ አንጻር ፓትርያርኩ ነገሮችን በማርገብ ተወያይቶና አወያይቶ ለችግሮች የቅድሚያ መፍትሄ አምጪ መንገዶችን ለመከተል ገና ብዙ ይቀራቸዋል ብለን እንገምታለን።

Friday, April 26, 2013

ማኅበረ ቅዱሳን እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተሐድሶ ያስፈልጋታል የሚሉ ተሐድሶዎች!


ጽሁፍ፤ በተስፋ አዲስ (ይህ ጽሁፍ ከዚህ በፊት የቀረበ ነው)1
ክፍል አንድ
ተሐድሶዎች እነማን ናቸው?

ብዙ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን ስሄድ የስብከት ካሴት ሳዳምጥ፤ የተለያዩ ሥነ ጽሑፎችን ሳነብ ፡ተሃድሶዎች ተሐድሶዎች፡ የሚል ጩኸት እሰማለሁ። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሥር የተቋቋመው ማህበረ ቅዱሳን የሚባለው ድርጅት አባላቱም ሆኑ አመራሮቹ ስለተሃድሶዎች በስብከታቸው እና በጽሑፋቸው ሁሉ በቀጥታም ሆነ በተዛዋዋሪ ሳያነሱ አያልፉም።
እኔም ተሐድሶዎችን ለማወቅ ብዙ ጥረት አድርጌአለሁ። ምን ዓይነት አቋም እንዳልቸውና የት እንደሚገኙ፤ አላማቸው ምን እንደሆነ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ማሳወቅ ፈለግሁ። እነርሱ ግን ተሃድሶ የሚለውን  ስም አይቀበሉትም።  እኔ ተሃድሶዎች ስል አንባቢ በሚገባው ቋንቋ ለመጠቀም እንዳሰብሁ ይረዳልኝ። ማህበረ ቅዱሳን የሚባለው ማህበርም ከተሐድሶዎች ጋር ያለውን ቅራኔ ለማቅረብ እሞክራለሁ። አንባቢ የራሱን ተቃውሞም ሆነ ድጋፍ እንዲሠጥ አንዳችም ሳልቀንስ እና ሳልጨምር ትክክለኛውን መረጃ ለማቅረብ እሞክራለሁ። መነሻየ ግን ከማህበረ ቅዱሳን እና ከተሐድሶዎች ሥነ ጽሑፎች ነው። የሁለቱንም ቡድን እንቅሥቃሴ በተከታታይ አቀርባለሁ መልካም ንባብ።
ተሀድሶ ማለት ይላሉ ቤተ ክርስቲያን መታደስ አለባት የሚሉ ወገኖች ማደስ፣ መጠገን፣ ማጽዳት፣ ማለት ነው ይላሉ።ለምሳሌ ቤት ከተሠራ በኋላ ሳይታደስ ብዙ ከቆየ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ሊፈርስ ይችላል ስለዚህ ከመፍረሱ በፊት የሚደርግለት እንክብካቤ ቤቱን ያጸናዋል። እንደሸረሪት ድር፤ የጢስ ጠቀርሻ ያሉ ነገሮችም ከቤቱ ላይ ሊጠረጉ ይገባል። ማደስ ማለት ማፍረስ አይደለም በቤቱ ውስጥ ያለውን ቆሻሻ፤ ማስወገድ እና በፈረሰው በኩል መጠገን ነው በሌላ አነጋገር መሠረቱን ሳይነኩ እና ሳያናውጡ ጥንታዊነቱን እንደያዘ ቤቱን ማሳመር ማለት ነው።የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንም ብዙ ዘመን ከመኖሯ የተነሣ ብዙ ስሕተቶች ይገኙባታልና መጽዳት አላባት፤ ባህሉን ከሃይማኖቱ፤ ውሸቱን ከእውነቱ፤ ክፉውን ከደጉ መለየት አለባት የሚል ራእይ ያላቸውና ለዚህ ሌት ተቀን ያለ እረፍት የሚሠሩ ናቸው።
የሚገኙት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ነው ጳጳሳት፤ ቀሳውስት፤ ዲያቆናት፤ መምህራን፤ የድጓ፤ የቅኔ የቅዳሴ መምህራን የሰንበት ተማሪዎች፤ እንዲሁም ምእመናን ሁሉ ያሉበት የአስተሳሰብ ኃይል ነው። የታወቀ ማህበር ግን የላቸውም። አንዳንዶች ማህበር መሥርተዋል ። ኑራቸው እና ሥራቸው በዚያው በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ሲሆን በተለያየ ቦታ ጽ/ቤት እና በርካታ ማሰልጠኛዎች አሏቸው። በርካታ መነኮሳት እና ሰባኪዎች በነዚህ ቦታዎች ይሰለጥናሉ። ይህን ሁሉ እንቅሥቃሴ የሚያደርጉት ግን ቤተ ክህነቱ ሳይውቅ ነው። ቀሳውስቱ ስልጠናውን ከወሰዱ በኋላ በየቤተክርስቲያናቸው ሌሎች ቀሳውስት በመመልመል ያሰልጥናሉ። ከጳጳሳትም ውስጥ ለዚሁ ሥራ የሚውል በግላቸው ከፍተኛ እርዳታ ያደርጋሉ። ተሐድሶዎች ቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ቁልፍ ቦታና ስልጣን አላቸው። በተለይ በአሁኑ ሰዓት በየአብያተ ክርስቲያናቱ  ሚሊዮኖች በብዛት ይገኛሉ። በገጠር አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት እና በገዳማት ሁሉ አሉ። ደሞዛቸውን የሚያገኙት ከዚያው ከቤተ ክርስቲያኒቱ ነው። ግን ከሌሎች የእምነት ድርጅቶችም እርዳታ ያገኛሉ ተብለው ይታማሉ። ተሐድሶዎች  እንደቀደምት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ አማኞች እንጂ እራሳቸውን ተሃድሶ ብለው አይጠሩም።  ስማቸው በሥራቸው ምክንያት ከሚጠሏቸው ወገኖች የተሰጣቸው ነው። በቤተ ክርስቲያን ባሕላዊ ትምህርት ጥልቅ የሆነ ዕውቀት ያላቸው ስለሆኑ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሁለንተና ደካማ ጎንም ሆነ ጠንካራ ጎን ለይተው የሚያውቁ ሊቃውንት ናቸው። የተሃድሶዎች እንቅሥቃሴ ከባድ እንቅሥቃሴ ነው ምክንያቱም እስከሞት ድረስ የቆረጡ ሲሆኑ ታላቅ ራዕይ ያላቸው ናቸው። በማኅበር መደራጀት ሳይሆን  በግል እያንዳንዱ አውቆ መስራት አለበት ስለሚሉ እዚህ ጋ ወይም እዚያ ጋር ናቸው ያሉት አይባልም። በአጭሩ የሌሉበት ቦታ የለም።
የማኅበረ ቅዱሳን ደጋፊ ነን የሚሉ ጳጳሳት ሳይቀሩ የዚህ ተሐድሶ የሚባለውን እንቅስቃሴ በስውር ይደግፋሉ። አሁን ባለው ሁኔታ ተሐድሶ የሚባሉት ክፍሎችን ከቤተክርስቲያኒቱ ማስወገድ በፍጹም አይቻልም። ከላይ እስከታች በተያያዘ ሰንሰለት የሚሰሩ ናቸው።

Friday, April 19, 2013

«እኛ ኢትዮጵያውያን ያለነው የት ነው? ተስፋችንስ ምንድነው?»

የሰው ልጅ ሁሉ የአዳምና የሔዋን ዘር ነው። ከዚህ የወጣ የለም።  ሰው ክቡርና በእግዚአብሔር አምሣል የተፈጠረ ስለሆነ እንስሳ አይደለም። ሰው በተፈጥሮው እንስሳ ነው የሚሉ ሰዎች ቢኖሩም እንኳን ሰው ግን እንስሳ አይደለም። በእርግጥ በተፈጥሮው ሰው ቢሆንም በአስተሳሰቡ ከእንስሳ ያልተሻለ ሰው ይኖራል። እንደባለጤና አእምሮ ሰው፤ ሰውኛ ማንነቱን ገላጭ አስተሳሰብ ሊኖረው የግድ ነው። እንስሳ አስተሳሰብ ማለት በሰው አምሣል ተፈጥሮ እንስሶች የሚሰሩትን የሚሠራ ወይም እንደእንስሳ የሚያስብ ማለት ነው። ዳዊትም በመዝሙሩ ይህን ኃይለ ቃል ሲገልጸው እንዲህ አለ። «ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ አያውቅም እንደሚጠፉ እንስሶች መሰለ»               (መዝ ፵፱፤፲፪)

አዎ ሰው ክቡርነቱን ትቶ በሃሳቡና በግብሩ፤ ነፍስያቸው ምናምንቴ እንደሆኑት እንስሶች መሰለ። ሁሉም ሰው የአንድ ዘር ምንጭ ቢሆንም ቅሉ ለሰይጣን ፈቃድ አድሮ በልዩነትና በክፍፍል መኖርን መርጧል። በክፍፍሉም እርስ በእርሱ ይባላል። ምክንያቱም አእምሮው ወደእንስሳነት አስተሳሰብ በወረደ ማንነት ተመርዟልና ነው። እንስሳት እርስ በእርሳቸው ይጠላላሉ። ነገን የሚጠብቁት አድነው ስለሚበሉት እንስሳ እንጂ በተስፋ ስለሚገነቡት ሕይወት አይደክሙም። ከዚያ ባለፈ እንስሳት ተስፋ የሚያደርጉት ዘላለማዊ ነገር ምንም የላቸውም። የማይሞት ተስፋ የተሰጠው የሰው ልጅ ግን በሚሞት ምድራዊ ተስፋ ላይ ራሱን አጣብቆ ይኖራል።ዳዊትም በመዝሙሩ ላይ ቃሉን በማስረገጥ  ድኩማነ አእምሮው ሰዎችን በእንስሳ ይመስላቸዋል። «አእምሮ የሌለው ክቡር ሰው እንደሚጠፋ እንስሶች መሰለ» (መዝ ፵፱፤፳)

ጠቢቡስ «ከፀሐይ በታች አዲስ ነገር የለም» ማለቱ ምን ማለቱ ነበር?  አዎ! ያን ማለቱ በአንጻራዊ ትርጉም አዲስ ነገር ያለው ከፀሐይ በላይ ነው ማለቱ ነበር። ከፀሐይ በላይ አዲስ ነገር እንዳለ እየተናገረን እንደሆነ እንረዳለን።  ስለዚህም ነው ተስፋችን በማይጠፋና ዘላለማዊ በሆነው ከፀሐይ በላይ ባለው ነገር ላይ እንዲሆን አበክሮ በመናገር ከፀሐይ በታች አዲስ ነገር የለም የሚለን። እንዲያውም ከፀሐይ በታች ባለው ነገር ላይ ተስፋ ማድረግ ነፋስን እንደመከተል ነው ይላል። «ከፀሐይ በታች የተሠራውን ሥራ ሁሉ አየሁ እነሆም፥ ሁሉ ከንቱ ነው፥ ነፋስንም እንደ መከተል ነው» (መክ ፩፤፲፬) ነፋስን ማን ሊከተል ይችላል? ነፋስስ መሄጃው ወደየት ነው? መኖሩን እናውቃለን እንጂ ወደየት እንደሚሄድ አንረዳም፤ መቆሚያውም የት እንደሆነ አናውቅም፤ ልንከተለውም ማሰብ ከንቱ ድካም ነው። ከፀሐይ በታች ያለውን ነገር ሁሉ መከተል እንደዚሁ ይለናል። የቀደመው  ነገር አልፏል፤ ያኔ ግን እንደአዲስ ይቆጠር ነበር። ዛሬ ደግሞ ነገ ቀድሞ ይሆናል። ቀድሞም ሆነ ዛሬ የምንላቸው ነገሮች ደግሞ ነገ የሉም። ሁለቱን የሚከተል ተስፋ የለውም።  ቀድሞና፤ ዛሬ የሚባልለት ሁኔታ በሌለው ከፀሐይ በላይ ባለው አዲስ ነገር ላይ ተስፋ ማድረግ ይሻላል። ሐዋርያው እንዲህ ሲል ያስተምረናል። «እርሱም የሰጠን ተስፋ ይህ የዘላለም ሕይወት ነው» (፩ኛ ዮሐ ፪፤፳፭)

የማይጠፋውን የዘላለም አዲስ ተስፋ በእምነቱ የሚጠባበቅ እንደምናምንቴ ሰው ተስፋ በሌለው በዚህ ዓለም ከንቱ ነገር ላይ ራሱን አያጣብቅም። ሰማያዊ ተስፋ የሌላቸው ሰዎች በዚህ ምድር ላይ መኖራቸውን እንደመጨረሻ ምዕራፍ ቢቆጥሩት አያስገርምም። መዝሙረኛው እንደተናገረው በአሳባቸው የሚጠፉ እንስሳትን መስለዋልና።

በእምነት ተስፋ ውስጥ ያሉ ሰዎች ከፀሐይ በላይ ያለውን አዲስ ነገር ይጠባበቃሉ። ስለሆነም በዚህ ምድር ላይ እስካሉ ሁላቸውም በእምነት አንድ ናቸው። ልዩነትን አይሰብኩም። ጳውሎስም እንዲህ አለ። «በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤ ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና።አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና። እናንተም የክርስቶስ ከሆናችሁ እንኪያስ የአብርሃም ዘር እንደ ተስፋውም ቃል ወራሾች ናችሁ» (ገላ ፫፤፳፮-፳፱)

Wednesday, April 10, 2013

«የአዲሱ ፓትርያርክ ዝምታ «የመጀመሪያው መጨረሻ» ወይስ የመጨረሻው መጀመሪያ?»



ዶ/ር ስቴፈን  ኮቬይ የተባለ ምሁር  «ስምንቱ ልምዶች» በተባለ መጽሐፉ ውስጥ እንዲህ እያለ ይጽፋል።  አእምሮው ውስጥ አስቀድሞ ያልተሰራ የቤት ሥራ ደብተርህ ላይ የራይት/ /እርማት አታገኝም። ልጅ በልጅነቱ ስታድግ ምን ትሆናለህ? ብለው ቢጠይቁት የሚናገረው  የመጀመሪያውን መጨረሻ  ርቆ  በመመልከት ነው።  የመጀመሪያውን መጨረሻ ለማሳመር አስቀድሞ  የመጨረሻውን መጀመሪያ  አእምሮው ውስጥ ዛሬ ሂሳቡን ሰርቶ መጨረስ አለበት።  አለበለዚያ ገና በልጅነቱ አርጅቷል ማለት ይሆናል። አእምሮ/ mental/ ሂሳቡን ማስላት ያለበት አሁን ነው።  ከዚያም ገሃዳዊው ዓለም/ Physical world / ከአእምሮው ጋር የሚቀናጅበት ሥፍራ ነው። አእምሮው ያልሰራውን ነገር ገሃዳዊው ዓለም ሰርቶ አይሰጥህም። በእርግጥ ዶ/ር ስቴፈን ትክክል ብሏል። መጽሐፍ ቅዱስም ይህች ዓለም ጥረን ግረን እንድንበላባት ነው የተሰጠችን እንጂ የምቾት ወንበር እንድናሞቅባት እንዳይደለ አስረግጦ ነግሮናል። እንዲያውም እሾህና አሜከላ የሞላባት እንጂ የተመቻቸች አይደለችም ይለናል።
አንድ ሰው ለራሱ ኑሮ አስቦ ለዚያ ስኬት መድረስ መጣር እንዳለበት ከተማመንን አንድ ሰው ከራሱ ኑሮ ባለፈ የብዙዎችን ኃላፊነት ተሸክሞ በሥሩ ያሉ ሚሊዮኖችን በማንቀሳቀስ ስኬትን ለማግኘት ምን ያህል የርእይና የዓላማ ሰው መሆን እንዳለበት ከጥያቄ የሚገባ አይደለም።
ከዚህ አንጻር ብዙዎች የታገሉለትና በስኬት ያጠናቀቁለት  የብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ የፓትርያርክነት ሥራ ሂደት እንዴት ይታያል? ብለን ልንጠይቅ ወደድን። በእርግጥ ቅዱስነታቸው ከተሾሙ ገና ቅርብ ጊዜ ነውና ብዙም ሊባል አይችል ይሆናል። ይሁን እንጂ  ዶ/ር ስቴፈን እንዳለው  የመጀመሪያውን መጨረሻ አይተን ለመገምገም  ብዙም አንቸገርም።  በትንሹ ያልተሰራ የቤት ሥራ ሲከማች እሰራለሁ ወይም ይቆይልኝ የሚል ተማሪ ቢኖር እሱ ትምህርቱን ያቆመው በአእምሮው ውስጥ ከመነሻው እንጂ ትምህርቱ ቤቱ በሚዘጋበት የዓመቱ መጨረሻ ላይ አይደለም። ከዚህም ተነስተን «የአዲሱ ፓትርያርክ ዝምታ «የመጀመሪያው መጨረሻ ወይስ የመጨረሻው መጀመሪያ» ብለን በርዕሳችን ጠይቀናል።
ይህንን ጥያቄ እንድናነሳ ያስገደደን ልክ በተሾሙበት ሰሞን የትምህርትና የአስተዳደር ጉዳይ ጥያቄዎችን ያነሱ የቅድስት ሥላሴ ኮሌጅ ተማሪዎች ጩኸት እስካሁን አጥጋቢ ምላሽ ሳያገኝ ችግሩም በዐመጽ ወይም በሰላም ጾሙን ሊፈታ እነሆ እየተንከባለለ እኩለ ጾሙን አልፏል። ከዚህ ቀደም በዚህ ጉዳይ ላይ እንደጻፍነው የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ችግር ድንገት የፈነዳ ሳይሆን እያመረቀዘ፤ ነገር ግን ሰሚ ያጣ ሆኖ በመቆየቱ የተነሳ ነው። ችግሮቹን አንድ ላይ ጨፍልቀን ብንመለከታቸው እንኳን ለመፍታት ያንን ያህል የተወሳሰቡና መፍትሄአቸው ከባዶች አልነበሩም። ዳሩ ግን ከባድ ያደረገው ርእይና ገቢራዊ እርምት መውሰድ የሚችሉ ሰዎች ስለታጣ ብቻ ነው። ይህንን ቀላል ነገር ለማስተካከል አዲሱ ፓትርያርክ አስቸኳይ  የማጣራት እርምጃ ተወስዶ ዝርዝሩ እንዲቀርብላቸው በማድረግ በዚያ ላይ የተንተራሰ አጭር መፍትኄ ለማስገኘት ትእዛዝ መስጠት ብቻ በቂያቸው ነበር።  ሳይጀምሩ የጨረሱ ያህል ቀላሉን ነገር አንድ ጊዜ በቪኦኤ መግለጫ ብቅ በማለት፤ አንድ ጊዜ ደግሞ በኮሚቴ ይታያል እያሉ በማንከባለል እነሆ ምንም የተጨበጠ ነገር ሳይታይ ወር አለፈው፤ በዚህ መልኩ ወራትም ይከተሉት ይሆናል። አሁን ደግሞ ተማሪ ማባረር እፎይ የሚያስብል እርምጃ ተደርጎ መወሰዱን እየሰማን ነው።
ተማሪዎቹ ወጪ ጨምሩልን፤ አካዳሚያዊ ነጻነት ይሰጠን፤ ሰላማዊ ሰልፍ ይፈቀድልን፤ በዲሞክራሲያዊ መብታችን እንጩህ አላሉም። በሚሰጠን ወጪ በአግባቡ እንድንመገብ ይደረግልን፤ የአስተዳደር ኃላፊዎቹ ሙሰኞች ስለሆኑ ይነሱልን፤ ብቁ መምህራን ይመደቡልን፤ ንጽህናችን እንዲጠበቅ የተቻለው ይደረግልን የሚሉ ጥያቄዎችን ነበር ያነሱት። እነዚህን ችግሮች አጣርቶ የመፍትሄ እርምጃ ለመውሰድ አንድ ወር ይፈጃል? ግቡ አትግቡ፤ ብሉ አትብሉ፤ የሚልስ ማስታወቂያ እስከመለቅለቅ ያስደርሳል? ፓትርያርኩስ ይህንን ቀላሉን ነገር ማስተካከል ካልቻሉ በጾሙ ሱባዔ ምክንያት አቤቱታ አቅራቢ ሁሉ በያለበት ክትት ብሎ የተቀመጠው፤ ወርኀ ጾሙ ሲያበቃ ከያለበት ሲወጣ እንዴት አድርገው ሊያስተናግዱት ይሆን? ምናልባት በወርኀ ጾሙ ያላዩትን የአቤቱታ ጋጋታ ጾሙ ሲፈታ እንዳይመጣባቸው የጾሙን ጊዜ ያስረዝሙት እንደሆነ እንጃ!
የቅድስት ሥላሴ ኮሌጅ ተማሪዎች አቤቱታ ለምላሽ የዘገየው  ከሌሎች ጉዳዮች ጋር አያይዘውት እንደሆነ በባለሥልጣኖቹ ዘንድ እሳቤ አለ። በአንድ በኩል በአባ ጢሞቴዎስና አቡነ ሳሙኤል መካከል የተከሰተው የአስመራጭነትና የተመራጭነት ሽኩቻ እንደተዳፈነ ነው። መፍትሄውም ቅርብ አይመስልም። የተማሪዎቹን ጥያቄ ወደዚያ በመወርወር አባ ጢሞቴዎስ ራሳቸውን ከጥያቄው ለማውጣት የፓትርያርኩን ውለታ መላሽነት በመጠቀም ባሉበት ቦታ እንደሐቀኛ ሰው መቀጠል ይፈልጋሉ። በሌላ መልኩም ማኅበረ ቅዱሳን ከነጀሌዎቹ በተማሪዎቹ ጥያቄ ሽፋን ቅዱስ ፓትርያርኩ የጸረ ተሐድሶ ኑፋቄዎችን የሚቃወሙና ተስፋችን የሆኑ አባት ናቸው በማለት በሆዱ የሌለውን ፍቅር እየሰጠ በትር እንዲያርፍባቸው የተዘጋጁ ሰዎች ላይ ትልቅ ዱላ ይዟል። በአንድ ወገን ደግሞ እንደእናታቸው ጡት የሚጠቡትን ጥቅም እንዳያጡ የሚራወጡ ወሮበሎች የሚከላከልልላቸውን ምክንያት እየያዙ በዚያ ስር መደበቅ ይፈልጋሉ። እንግዲህ ትንሹ የተማሪዎች ጥያቄ የየራሱን ጥቅም ለማስከበር በሚፈልጉ ክፍሎች ምላሽ እንደሰማይ ርቆት ይገኛል። ወደፊትም ጠብ የሚል ነገር የለውም። ሁሉም አመራሮች ሳይጀምሩ የጨረሱ ርእይ አልባዎች ናቸውና መፍትኄው ቅርብ አይደለም። ሳሙና ይገዛልን፤ ንጽሕናው በተጠበቀ ሽንት ቤት እንጠቀም፤ የምግብ ወጪው በአግባቡ ይታይልን፤ መምህራን ይስተካከሉልን  ማለት ይህንን ያህል ዙሪያ ጥምጥም የሚያስኬድ አልነበረም። «አፍህ የት ነው ሲሉት፤ በጆሮዬ አልፎ» እንዳለው ጠማማ ሰው  የቅርቡን ትቶ ነገሩን ማወሳሰብ አግባብ አልነበረም።  ይሁን እንጂ የተወሳሰበውን ለመፍታት አሁንም አልረፈደም እንላለን። በዚህ ላይ የፓትርያርኩ እርምጃ አወሳሰድ ወሳኝነት አለው። በአጭር ጊዜ ጉዳዩን አጣርቶ መፍትኄ መስጠቱ ከባድ አይደለም። ከዚህ በፊትም «ፓትርያርኩ ከፊታቸው ብዙ ሥራ ይጠብቃቸዋል» ብለናል። ወሮበላውን፤ ሥልጣን ናፋቂውን፤ አስመሳዩን፤ አለቅላቂውንና የቀሚሱን ጭራ የሚቆላውን ሁሉ መልኩን አይተው ካዳመጡት አንድም እርምጃ ወደፊት መሄድ አይችሉም እንላለን።
የመጨረሻው መጀመሪያ እንዳይሆን መጠንቀቅ ይጠቅማል።

Tuesday, April 2, 2013

ድኅነት በሂደት ወይስ በቅጽበት? ለሚለው የዳንኤል ክብረት ስብከት የተሰጠ ምላሽ



ደግመን ደጋግመን እንደምንለው አሁንም እንላለን። ማቅና አገልጋይ ወኪሎቹ ጊዜና እድል ስላረገደላቸው ብቻ በጠለቀ እውቀት ውስጥ  ሆነው የሚያስተምሩና የሚሰብኩ ይመስላቸዋል። ከእነዚህ መንጋና ጎጋ ሰባኪዎቹ መካከል አንዱ የተረት አባት የሆነው ዳንኤል ክብረት የተባለው ሰው ነው። ለስሙ፤ ለክብሩና ለዝናው ዘወትር የሚተጋ፤ ነገር ግን የአስተውሎት ደኃው ዳንኤል ክብረት በአንድ ስብከቱ ላይ እንዲህ በሚል ርእስ ስህተቱን ለተከታዮቹ ሲረጭ ተመልክተነዋል።

«መዳን በሂደት ወይም በቅጽበት?

በዚህ ርእስ ላይ ዳንኤል «መዳን» ባመኑበት ሰዓት በቅጽበት የሚሰጥ ሕይወት ሳይሆን በሂደት የሚገኝ ሀብት ነው ይለናል። ስለዚህም ክርስቲያኖች ለመዳን  ከፈለግን ለድኅነት የሚያበቃ ተጋድሎ እየፈጸምን መቆየት የግድ አለብን በማለት ድነት/መዳን/ በቅጽበት የመሰጠቱን ነገር ክዶ ሊያስክድ ያባብላል። እውነት፤ ዳንኤል እንደሚለው መዳን በቅጽበት የሚሰጥ ጸጋ ሳይሆን ክርስቲያኖች ለመዳን ሂደትን መጠበቅ አለባቸው?  የእግዚአብሔርስ ቃል እንደዚያ ያስተምረናል? ሰው ለድኅነት ስንት ዘመን መቆየት አለበት? በስንት እድሜው ላይ ሊያረጋግጥ ይችላል? ድነኻል ብሎስ ማን ይነግረዋል? ዳንኤል ለእነዚህ ጥያቄዎች የሚሆን ማብራሪያ መስጠት አልፈለገም፤ እንዲያው ሾላ በድፍኑ ብሎ ፤ ድኅነት በጥረትና በትግል ሂደት የሚገኝ እንጂ በቅጽበታዊ እምነት የሚሰጥ አይደለም ለማለት አጋዥ ምክንያቶቹን በመፈለግ ሊያሳምነን ይሞክራል። ይህንን የሚሉ ካሉ ተሳስተዋል ወይም መናፍቃን ናቸው ሲልም የራሱን ትክክለኛነት ለራሱ ነገሮ ስሙኝ ይላል።  ከየትኛውም ትምህርት ቤትና መምህር እንደዚህ የሚል ቃል እንዳገኘ አይነገረንም።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  በ«ቅዳሴ እግዚእ»  ቅዳሴ ወቅት በእርገተ እጣን ሰዓት በኅብስቱና ጽዋዕ ላይ ካህኑ እንዲህ እያለ በማጠን ይጸልያል።
«ሰፍሐ እደዊሁ ለሕማም፤ ሐመ ከመ ሕሙማነ፤ ያድኅን እለ ተወከሉ በላዕሌሁ»  ትርጉም፤  «እጆቹን ለሕማም ዘረጋ፤ በእርሱ የታመኑትን ያድን ዘንድ እንደ ሕሙማን ታመመ» ይለናል።  እንግዲህ ክርስቶስ ሕማምና ስቃይን ተቀብሎ እንዳዳነን ይህ ቃል ያረጋግጣል። ሰባኪው ዳንኤል በክርስቶስ ስቃይ እኛ መዳናችን በጊዜ ሂደት የሚረጋገጥ እንጂ በሞተልን ሰዓት የተቀበልነው አይደለም የሚለው ከየት አምጥቶ ነው?
ይህንን የዳንኤልን አሳሳች ስብከትና የጥፋት መርዝ ትምህርቱን  በወንጌል ቃል ገላልጠን  ለማሳየት እንፈልጋለን። አንባቢም የዳንኤልን ስብከት ፈልጎ እንዲያዳምጥ እንጋብዛለን ወይም በስተግርጌ ያስቀመጥነውን ሊንክ በመጫን ይህንን ጽሁፍ አንብቦ እንደጨረሰ አዳምጦ እንዲያገናዝብ ለሚዛናዊ ፍርድ አስቀምጥነዋል። ለወደፊቱም እሱንና እሱን መሰል ስሁታን አረፋ እየደፈቁና እየተንዘፈዘፉ በየመድረኩ የሚወራጩ  የሐሳውያንን  የጥፋት መንገዶች ለማሳየት እንመረምራለን። ሕዝቡን ወደጥፋት የሚነዱ የጠላት መልእክተኞች የሆኑበትን ስብከት እንደዚሁ እየመዘዝን ለማሳየት እንሞክራለን።

Wednesday, March 13, 2013

ማኅበረ ቅዱሳንን የምንወቅሰው በግብሩ እንጂ ማኅበር ሆኖ ስለቆመ አይደለም!




ብዙዎች ስለማኅበረ ቅዱሳን በምንጽፋቸው ጠጣር መልዕክቶች  በጣም ሲያዝኑ እንመለከታለን።  በኢሜል ወቀሳና ከዚያም ሲያልፍ ስድብ የሚልኩልን አሉ። በጽሁፎቻችን ውስጥ ማኅበሩን ነካ ባደረግን ቁጥር የሚያማቸውና ጸያፍ አስተያየቶችን የሚሰጡንም አጋጥሞናል። አንዳንዶች ስለማኅበረ ቅዱሳን የምንጽፋቸውን  እውነትነት አላቸው  ብለው እንደሚቀበሉን ሁሉ ተቃራኒውን አመለካከት እንደተለየ ሃሳብ ቆጥረን በአክብሮት እኛም ስንቀበላቸው ቆይተናል። ወደፊትም እንደዚሁ! የሃሳብ ልዩነት በዱላ ማስገደድ እስካልተቀላቀለበት ድረስ ለበጎ ነው እንላለን።  እኛ የሚታየንና እውነት ነው ብለን የተቀበልነው ነገር ለእነርሱ እንደስህተት ቢቆጠር አያስገርምም። እኛም ያላየንላቸው የእነርሱ እውነት ሊኖር እንደሚችል አስበንላቸው ተቃራኒ ሃሳባቸውን እናከብራለን። በዚሁ መንገድ የሁለት ወገን እሳቤን ተቀብለን ወደተነሳንበት ርዕሰ ጉዳይ እናምራ።
ማኅበረ ቅዱሳን እንዴት ተመሠረተ? ብለን የዓመታቱን መታሰቢያ የልደት ሻማዎችን ለመለኮስ ወይም አስልቺ የሆነውን የልደት ትረካ በመዘብዘብ ጊዜ ለማባከን አንፈልግም። ግብሩን ለመናገር ጥያቄዎችን እንጠይቅና እንመርምር።

፩/ ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያኒቱ  የእውቀት ገበታ ነው ወይ?

ማኅበረ ቅዱሳንን እንደምናየው በጠለቀ ደረጃ ባይሆንም በተወሰነ መልኩ በቤተ ክህነቱ የአብነት ትምህርት ቤት ውስጥ ያለፉ ሰዎችን ለመያዝ ሞክሯል። አብዛኛው ግን የቤተ ክርስቲያን ፍቅር ያቃጠላቸው እንደሆኑ የሚናገሩ የሰንበት ት/ቤት አባላትን ያቀፈና ዘግየት ብሎም ከሰንበት ት/ቤትም ሆነ ከፈለገ ሕይወት ት/ቤት ቅርበት ያልነበራቸውን ለመያዝ የሞከረ እንደሆነ ይታወቃል።  ይህንና ይህንን የመሳሰሉ ሰዎችን ይዞ እየተጓዘ እዚህ የደረሰው ማኅበር በነማን ምን ሰራ? ምንስ አበረከተ? የሚለውን  ልክ ስንመለከት ማኅበሩ እንዳዋቀሩት ሰዎች የማንነት ደረጃ አለኝ የሚለውን  የእውቀት ልክ ከነድርጊቶቹ እንመዝናለን እንጂ ዝም ብለን በጥላቻ አንፈርጅም። 

  ከዚህ አንጻር ማኅበሩ ሌላውን የሚመለከትበት ዓይን ራሱን ባዋቀረበት አቅምና ባለው የእውቀት ልክ ሳይሆን ነገሮች እየገጠሙ ስለተጓዙለት ብቻ ራሱን የቤተ ክርስቲያኒቱ የእውቀት ገበታ አድርጎ ማስቀመጡ አስገራሚ ይሆንብናል። በማኅበረ ቅዱሳን ሠፈር ራስን በማሳበጥ የእውቀትና የቤተ ክርስቲያኒቱን ትምህርት አብጠርጥሮ የማወቅ ችግር እንደሌለ ትልቅ ሥዕል አለ። መድረክ ላይ ቆሞ የማስተማር  እድልና  የእውቀት ጥማት ባላቸው ብዙ ምእመናን ጉባዔ ላይ ተገኝቶ የመናገር እድል በመግጠሙ ብቻ ማኅበሩ የእውቀት ርካታ የማካፈል ብቃት እንዳለው አድርጎ ራሱን አግዝፎ  ማየቱን ስናይ ይገርመናል። ብዙዎቹን የማኅበሩ አንጋፋ ተናጋሪዎቹን ትምህርት በአካልና በድምጽ ወምስል መልዕክት ማስተላለፊያ መንገዶች የማየት እድሉ ነበረን። አንዳንዶቹ የእውቀት ሳይሆን የንግግር ችሎታ ያላቸው ናቸው። አንዳንዶቹ የእውቀትም፤ የንግግር ችሎታ የሌላቸው ነገር ግን እድል የከነፈችላቸውና የሰው ወፍ የሚረግፍላቸው  ስለሆኑ ብቻ መምህራን መሆናቸውን ለራሳቸው የነገሩ ናቸው። አንዳንዶቹ እውቀት ያላቸው ቢሆኑም  ነገር ግን እውነቱን በማጣመም ልክፍት የተያዙ ጠማማዎች ሲሆኑ  አረፋ እየደፈቁ ለጉባዔ ሲናገሩ ከማንም በላይ የደረሱበትን እውቀት የሚያስተምሩ ይመስላቸዋል። ሌሎቹም እውቀቱ እያላቸው ለማስተማር የማይፈልጉ  ጥገኞች/Parasitic/ ሆነው ተጎልተዋል። ከምንም ከምኑም  ውስጥ የሌሉ ነገር ግን ክፋትና ሴራ በመጎንጎን የተካኑ የጥፋት መንፈስ ያሰገራቸው ሰዎችንም ተሸክሟል።

 እንግዲህ እነዚህ ሁሉ ባሉበት ማኅበር ውስጥ በተለየ መደብ በቅንነት፤ በየዋህነትና በእምነት የተሰለፉ አያሌዎች ደግሞ የማኅበሩ ቀኝ እጅ ሆነው እያገለገሉ መገኘታቸው እውነት ነው።  አለማወቅ በራሱ ችግር ቢሆንም ቅኖችና የዋሃን ከማኅበሩ ጋር በመቆማቸው የማኅበሩ ድክመት እንደጥንካሬ  በመቆጠሩ ብቻ ቅን ማኅበር ነው ሊሰኝ አይችልም።

Sunday, March 3, 2013

ጥቁር ይሁን እንጂ ማንኛውንም ቀለም መቀባት ትችላላችሁ”

 (Addis Admas)
የዱር አራዊት ተሰብስበው ግብረ - ገብነታችንንና ሥነ-ምግባራችንን የሚያርቅ፣ መሠረታችንን የሚያበጅ፣ ደህና ጠባይ ያለው እንስሳ እንምረጥ ይባባላሉ፡፡
አንበሳ፤ የአራዊቱ ሁሉ ንጉሥ ነውና “ምርጫው ይሳካ ዘንድ ጦጣን፣ አህያንና ነብርን ስጡኝና የአመራረጡን ሥነ ስርዓት አስቀድመን እናበጃጀው!” ይላል፡፡ አራዊቱ፤ “መልካም ሀሳብ ነው፡፡ እነዚህን ሶስቱን ወስደህ ምከሩበት፡፡ አስቀድመህ ግን፤ ለምን እነሱን እንደመረጥክ ምክንያቱን አስረዳ” አሉት፡፡
አንበሳም፤
“መልካም፡፡ በአዘጋጅ ኮሚቴነት ሶስቱን ስመርጥ ሶስት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉኝ፡፡ እጅግ አስፈላጊ የሆነው የሥራ ሀላፊነት፡-
አንደኛ - ብልሃተኛ መሆን ነው፡፡ ለዚህ ጦጣን መረጥኩ፡፡
ሁለተኛ - ሸክም የሚችል ትከሻ ያስፈልጋል፡፡ እንደምታውቁት ለዚህ ከአህያ የተሻለ መሸከም የሚችል አይገኝም፡፡
ሦስተኛ - ፈጣን መሆን ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ እንደነብር ጥይት የለም፡፡
ምክንያቴ ይሄ ነው፤ አለ፡፡ ጭብጨባው ቀለጠ፡፡
“ጥሩ፡፡ በሉ ምርጫውን አሳኩት” ተባሉ፡፡
አንበሳ አስመራጮችን ሰብስቦ “እህስ? እንዴት እናድርግ ትላላችሁ?” አለ፡፡
አህያ፤ “ማናቸውንም በሸክም ዙሪያ ያለ ሥራ ለእኔ ይሰጠኝ” አለች፡፡
ነብር፤ “በፈጣንነቴ የትኛውም የጫካው ድንበር ድረስ ሮጬ የተሰጠኝን መልዕክት አደርሳለሁ” አለ፡፡
አያ አንበሶም፤ “እሺ እመት ጦጣስ? ምን እናድርግ ትያለሽ? መቼም መላ የሚጠበቀው ካንቺ ነው?!” አላት፡፡ ጦጣም፤
“መቼም አያ አንበሶ! የአህያም ሥራ ሸክም መሆኑ በሙያዋ ነው፡፡ የነብርም ሩጫ የተፈጥሮ ክህሎቱ ነው፡፡ እጅግ ከባዱ ጥያቄ ግን በእኔና በእርሶ በጌታዬ በአያ አንበሶ ጫንቃ ላይ ነው የወደቀው፡፡”


Friday, March 1, 2013

አዲሱ ፓትርያርክ ብዙ ሥራ ይጠብቃቸዋል!


በዚህም ተባለ፤ በዚያ አቡነ ማትያስ ፮ኛው ፓትርያርክ ሆነው ተሹመዋል። ባለፈው ግድፈትና እውነት ላይ  እያነሳንና እየጣልን ጊዜ አናጠፋም። ይልቅስ ብዙዎች የታገሉለት የምርጫው ስኬት እንዳሰቡት ጥሩ የሥራ ጊዜ ይዞ ይመጣላቸው  እንደሆነ የምናይበት፤  ገሚሶቻችንም የምናያቸው የቤተ ክህነት ተግዳሮቶች የሚቀረፉበት፤ ሰናይ የአስተዳደርና መንፈሳዊ ዘመን ናፍቆታችንን ተስፋ በማድረግ እንደዚህ በፊቱ አስቀድመን አንዳንድ ነገሮችን ለማመልከት ወደድን።
የአዲሱ ፓትርያርክ አዲስ የሥራ ዘመን ቀላል እንደማይሆን ይገመታል። የተጠራቀሙ የቤተ ክህነቱ ችግሮችና ብዙ እንከኖች  ከፊታቸው ይጠብቋቸዋል። የችግሮቹ ዓይነቶች፤ ደረጃና ጥልቀት የተለያዩ እንደመሆናቸው መጠን የተለያየ ውሳኔና እርምጃንም የሚጠይቁ ናቸው። ለዚህ የተዘጋጀ የአእምሮ ዝግጁነት፤ የእውቀት በሊህነት፤ ድፍረትና ማስተዋል እንደሚጠይቁም አይጠረጠርም።  ያንን ዓይነት ሰው ከየት እናገኛለን ብለን አናሳብም። ምክንያቱም ምርጫው /ከተባለ/ ትልቅ አባት ሰጥቶናልና። ስለዚህ ወደችግሮቹ እንንደርደር።

1/ የቤተ ክህነቱ ላዕላይና ታህታይ መዋቅር ማሻሻል

የቤተ ክህነቱ ቀዳሚው ችግር ሥራና ሠራተኛ የተገናኘበት ተቋም አለመሆኑ ነው። ሥራና ሠራተኛ ካልተገናኘ ደግሞ  በየትኛውም መልኩ የቤተ ክህነቱ የሥራ አፈጻጸም «ከርሞ ጥጃ» መሆኑ አይቀርም። ሥራና ሠራተኛ ማለት ለተገቢው ሥራ ተገቢ ባለሙያ ወይም ተቀራራቢ ችሎታ ያለው ሰው ማለት ነው። እንደዚህ ባለው ሰው ላይ የተቋሙን ዓላማና ግብ በደንብ ካስጨበጡት ከችግሮቹ ብዛት አንጻር ባንድ ጊዜ ፈጽሞ ባይወገድም፤ ከየትኛውም ጊዜ የተሻለ ለውጥ ሊመጣ ይችላል። በዘመድ አዝማድ የተለጣጠፉና የተደረቱ ክፍሎችን ይዞ መቀጠል ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ ይሆናልና አሁን ያለን የሥራና ሠራተኛ አቋም የችግሩ ዋና ምንጭ ነው ባይባልም የችግሩ አካል ነውና ከጥገናዊ ለውጥ ወይም ከማስመሰል /pseudo/ የራቀ ለውጥ ያስፈልገዋል። ከአቅም በታች ለመሥራት የእድሜ ጣሪያ የገደባቸውም  በየመልኩ ቦታቸውን መያዝ  ካልቻሉ ቤተ ክህነት የዘመዳ ዘመዶች የጡረታ ተቋም ሆኖ ይቀጥላል እንጂ የሥራ ብቃት መለኪያ ስፍራ ሊሆን አይችልም። 

ሀገር አቀፍ ተቋም የሆነው ቤተ ክህነት ሀገር አቀፍ አደረጃጀት ሊኖረው የግድ ነው። ከላይ እስከታች አደረጃጀቱ መሻሻል አስፈላጊ ከሚባልበት ጊዜ ላይ ተደርሷል ብለን እናምናለን። በአንድ ወቅት በአሁኑ ሰዓት የአንበሳ አውቶቡስ ድርጅት ሥራ አስኪያጅ የሆኑት አቶ በድሉ አሰፋ የቤተ ክህነቱን የአቅም ግንባታ ክፍል ሆነው ጥናት አቅርበው እንደነበር አስታውሳለሁ። ቤተ ክህነትና የዘመኑ ጥናት ሊግባቡ ባለመቻላቸው ቤተ ክህነትም በአሮጌ ልምዷ ስትቀጥል፤ አቶ በድሉም አሮጌው ጎዳና አላሰራ ስላላቸው ትተውት የተሻለ ቦታ ሄደዋል። ስለዚህ ቤተ ክህነትን ከአሮጌ መዋቅር ወደዘመነ ሥርዓት ለማስገባት አዲሱ ፓትርያርክ ትልቁ ሥራቸው መሆን አለበት  እንላለን። የተደረተውን በመጠገን  ላይ ካተኮሩ ግን ልባቸው ወልቆ እርጅናቸውን ከማፋጠን በስተቀር ለእርሳቸውም ይሁን ለቤተ ክህነቱ ቀጣይ አስተዳደር አንዳችም  ነገር ጠብ ሳይል ይቀጥላል ማለት ነው። ይህን ማስተካከል የአዲሱ ፓትርያርክ ፈታኝ ሥራ ነው ብለን እናስባለን።


2/  እርምጃ አወሳሰድ፤ የሥራ ብቃት መለኪያና አፈጻጸሙን የመቆጣጠሪያ ስልት፤

 ቤተክህነትን በብቃት የሚመራ ሕግ፤ መመሪያና ደንብ የለውም። ያለውንም በሥራ የሚያውል አካል አልነበረም። ነገሮች ሁሉ በልምድና በስምምነት የሚሰራበት ሆኖ ቆይቷል። ሥልጣንና ተግባር ለክቶ የሚሰጥ መመሪያ ባለመኖሩ ሥራና ኃላፊነት ተደበላልቀው በባለሥልጣን ይጣሳል፤ ወይም በመሞማዳሞድ ይሸፈናል።  መመሪያው ሕግ ሳይሆን ሹመኛው ራሱ ሕግ ሆኖ ያገለግላል። የአድርግና አታድርግ፤ የጌታና የሎሌ አስተዳደር እንጂ የ21ኛው ክ/ዘመን የተጠያቂነት አሠራር በቤተ ክህነት  የለም። ባለሥልጣናቱ ከፈለጉ ከአፈር ይቀላቅሉሃል፤ ከወደዱም ጣሪያ ላይ ይሰቅሉሃል። ሰው  የሚያድገውም  ይሁን  ድባቅ የሚመታው ተጠያቂነት በሌለው ሁኔታ ውስጥ ሆኖ ቆይቷል።  ለሠራው ሥራ ብቃትና ጉድለት መለኪያ  ሚዛን የለም። ሌላው ይቅርና የፓትርያርክ የምርጫ ሕግ እንኳን ከእንከን የጸዳ ባለመሆኑ በነቶሎ ቶሎ ቤት ጥበብ  ተለክቶ የተሰፋው በቅርቡ መሆኑን ልብ ይሏል።  እንግዳነቱ ብዙ ጭቅጭቅና ክርክር ማስነሳቱም  አንዱ የቅርብ ጊዜ ትዝታ መሆኑ አይዘነጋም።  ነገም ይህ ችግር ላለመደገሙ ዋስትና የለም። ስለዚህ ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አጥቢያ  ወጥነት ያለው ሕግ፤ መመሪያና ደንብ ሊኖር ይገባል።  ይህንን ችግር አጥንቶ የተሻለ መፍትሄ በማምጣት ላይ አዲሱ ፓትርያርክ ትልቅ ሥራ ይጠብቃቸዋል።

3/ መንፈሳዊ ሲመት/ሹመት/ በተገቢው መለኪያ ማከናወን

ከጵጵስናው ጀምሮ እስከ እልቅና ድረስ ያለው የሲመት አሰጣጥ ሲባል እንደቆየውና እንደምናውቀው ወይ ገንዘብ ያለው፤ ወይ ዘመድ ያለው እንጂ በችሎታና በብቃት ልኬት የሚገኝ አልነበረም።  ጉልበት ስር መንበርከክን ዝቅ ሲልም ትቢያ መላስን እንደመስፈርት ሲሰራበት ቆይቷል። መከባበር ተገቢ መሆኑ እንዳለ ሆኖ ትሕትናን ገንዘብ በማድረግ ያይደለ ሥጋዊ ክብርን ከመፈለግና ለሹመት ሲባል ወደአምልኮ የተቀየረ ስግደት የመስጠት ትእቢታዊ  ግብር ማላቀቅ ተገቢ ነው። ጵጵስናውንም እንደሲሞን መሰርይ ሽጡልኝ ወደሚባልበት ደረጃ ማውረድ ወይም በአማላጅና በሽማግሌ የሚረከቡት ንብረት መሆኑ መቆም አለበት።   መሪው በተመሪው የተመሠከረለት ቢሆን እንዴት ባማረ ነበር? ጳውሎስም የመከረን ይህንኑ እንድናደርግ ነበር።  ብዙ ጊዜ እንደሚታየው መሪውን ገንዘብ ይመርጥና ወደተመሪው ሕዝብ ይላካል። እዚያም እንደደረሰ መሪው ለሚመራው ሕዝብ ሳይሆን አገልጋይነቱ ለመደቡት ክፍሎች ይሆናል። ሕዝቡም በሚወርድበት የዐመጻ ሥራ የተነሳ እምነቱን እንዲጠላ፤ እንዲያፍርና እንዲሸማቀቅ ብሎም እንዲኮበልል ይገደዳል። ሕገ ወጥነት የሰለጠነበት የቤተ ክህነት ሥልጣን እንደገና መበጠር ይገባዋል።  ሕዝቡ መጣብን ሳይሆን መጣልን የሚል መንፈሳዊ መሪ ይፈልጋል። በመጡበት ተላላኪዎች እስከዛሬ መሮታል። እናም አዲሱ ፓትርያርክ ይህንን ሁሉ ችግር ተረክበው የጣፈጠ ሥራን ሊያሳዩት ይጠበቃል።  ያለፈውን ችግር ተሸክመው በምን ቸገረኝነት ይቀጥላሉ ወይስ ይህንን የሚሸከም ጀርባ የለኝም ይሉ ይሆን? እሳቸውንና ደጋፊዎቻቸውን የምንጠይቃቸው  መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ትልቁ ፈታኝ ሥራቸው እንደሆነ ግን በበኩላችን አስምረንበት እናልፋለን።

Wednesday, February 27, 2013

ቀልድ እንደ እውነት!

 ከጥበበ ሲራክ ዘጉንዳጉንዶ


ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ  ማ…………ቴዎስ        
                           
                            ………….ትያስ


ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም፤ ወእጨጌ ዘመንበረ ተ/ሃይማኖት መልካም የሥራ ጊዜ  እንዲሆንልዎ እንመኛለን።

ቀልደኞች እንደእውነት ሲያደርጉት ለእኛስ መልካም ምኞት አይከለከልም አይደል?

Tuesday, February 26, 2013

ለነ አባ እንቶኔ!!


እመሰ አማን ጽድቀ ትነቡ...


ይድረስ ለነ አባ እንቶኔ፦(geezonline.org)


ሰላም ለክሙእንዳልላችኍ፤ እንደ እኔ ያለ አንድ ምስኪን እንደ እናንተ ላሉ ታላላቆች ከታች ወደላይ ሰላምታ ማቅረብ የማይገባው መስሎ ስለሚታያችኍ፤ ላስቀይማችኍ አልሻምና ይቅርብኝ።ሰላምክሙ ይብጽሐኒብየ እንዳልማጠናችኍም፤ ስንኳን ለሌላ የሚተርፍ ለራሳችኍ የሚበቃ ሰላም እንደሌላችኍ እያየኍ የሌላችኍን ነገር በመለመን እንዳሳቅቃችኍ ኅሊናየ አይፈቅድልኝም። ስለዚህ የሰላምታን ነገር በዚሁ እንለፈው።   

ሰላምታውን በዚሁ ካለፍነው ዘንድ ነገሬን በቀጥታ ልጀምር። ከቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜ ባገኘኹት ላይ ተመርጉዤ። በሊቃውንት ቋንቋ እንድገልጠው ከፈቀዳችኹልኝ፦ ጳጳሳት አይደላችኍ? ከብሉይ ታሪክ ምሳሌ አምጥቼ ግሥ ልገሥሥላችኍ ነው።

ርግጥ ነው ብዙዎቻችኍ ትርጓሜ መጻሕፍትን በወንበር ተምራችኋል ብየ አላስብም። እውነት ለመናገር ከመካከላችኍ አንዳንዶቹ ተነሹን ከወዳቂ፥ እሚጠብቀውን ከሚላላው፥ በፍቅደት የሚነበበውን በውኅጠት ከሚነበበው በሚገባ ለይታችኍ ማወቃችኍን ስንኳ እጠራጠራለኍ። አዛኜን። ይኹን እንጂ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ እንዲሁም የዐጤ ኀይለ ሥላሴ ስም አጠራራቸው የተመሰገነ ይኹንና አቡኑ አእምሮ፥ ንጉሡ ገንዘብ ኾነው በረድኤተ እግዚአብሔር ያሳተሙትን የዳዊት አንድምታ ከመጽሐፍ መደርደሪያችኍ ፈላልጉና (ድንገት ለነ አቦይ መልእክት ስትፋጠኑ ጊዜ አላደርስ ብሏችኍ እስከዛሬ ያልገዛችኹት ከኾነም፤ ስንኳን አንድ መጽሐፍ አገር ምድሩን የሚገዛ ገንዘብ በየባንክ ቤቱ ስለሞላችኍ ዛሬውኑ ልካችኍ አስገዙና) የምገሥሥላችኍ ግሥ ተስማሚ መኾን አለመኾኑን አረጋግጡ።

የምተኩረው በዳዊት መዝሙር ላይ ነው። 57ኛው። ትርጓሜው የመቃብያንን ታሪክ ያስተርካል። ከታሪኩ አኹን የያዝነውን መዝሙር ለመረዳት የሚያሻው ክፍል፦ ስምዖን፥ እልፍሞስ፥ መባልስ የተባሉ ሦስት ንኡሳን ካህናት ለሹመት ሲሉ እስራኤልን የአሕዛብ ንጉሥ አንጥያኮስ እጅ እንዲያደርጋት መምከራቸውን፤ እሱ ስንኳአኹን የተናገራችኹትን ነገር ሳላስበው ውየ ዐድሬ አላውቅም። ነገር ግን እስራኤል ሰዎቹ ጽኑዓን ናቸው፤ አምባቸውም ጽኑ ነው ሲሉ እሰማለኍ። ፈጣሪኣቸውም ይረዳቸዋልና መቅረቴ ስለዚህ ነው እንጂ።ቢላቸው፤እኛ ባወቅነ እናስገባኻለን። አንተም አመንኍ ብለኽ ዐዋጅ ነግረኽ ምስዋዕተ እሪያውን በዃላ በዃላ እያስጎተትኽ ላሙን በጉን በፊት በፊት እያስነዳኽ ብለው መክረውት ኺደው የከተማዋን ቅጥርክፈቱልንያሏቸውን ይመለከታል። በዚህም ምክንያት "ፈጣሪየ የሃይማኖት አብነት ቢያደርገኝ የክህደት፥ የጥብዓት አብነት ቢያደርገኝ የፍርሃት፥ የበጎ አብነት ቢያደርገኝ የክፋት አብነት እኾናለኹን? አይኾንም" ያለው እውነተኛ ካህን አልዓዛር ሰባት ልጆቹ በሰይፍ ሲመቱ ሚስቱም በጡትና በጡቷ መኻል በኩላብ ተሰቅላ በሰይፍ ተቀልታለች። እሱም ይኽን ኹሉ እያየ ስንኳ ከጽናቱ የማይመለስ በመኾኑ በሰም የተጠማ የጋለ ብረት ምጣድ በራሱ ላይ ተደፍቶበት ተንጠቅጥቆ ሙቷል። በዚያኑ ጊዜ ከእስራኤል አራት ዕልፍ ዐብረው ዐልቀዋል፤ አራት ዕልፍ ተማርከዋል፤ አራቱን ዕልፍ ይሁዳ መቅብዩ እየተዋጋ ይዟቸው ወጥቷል። ስለዚህ በዚያን ጊዜ በሃይማኖታቸው የጸኑት ባባታቸው በመቃቢስ መቃብያን ተብለዋል። ዕጉሣን በስደት ጽኑዓን በምግባር ወበሃይማኖት ማለት ነው።

Monday, February 25, 2013

ያሳዝናል! ያሳዝናል! ያሳዝናል!...... (የሐራ ዘተዋሕዶ ዘገባ)

 (To read in PDF please Click here )

አንድ ጥያቄ እናስቀድም፤ ለመሆኑ ኢትዮጵያ ካለው የአሜሪካ ኤምባሲ ይልቅ የኢትዮጵያ መንግሥት አሜሪካዊ ዜጋ ስለመሆንና አለመሆን ጉዳይ ይመለከተው ይሆን? ለማንኛውም «ሐራ ዘተዋሕዶ» መሳጩን የሲኖዶስ ውይይት በቦታው የነበረ ያህል በአስደማሚ ዘገባ አቅርቧልና እንዲያነቡት እነሆ!

‹‹ቤተ ክርስቲያን ስትጠራኝ እምቢ እላለኹ ወይ ! ! !›› /ብፁዕ አቡነ ማትያስ/

    ‹‹አጃቢ ነን!›› /ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል/

    ‹‹እንኳን አይደለም ፕትርክናው ጵጵስናውም ከብዶኛል፤ እኔ እጠፋለኹ›› /ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ/

    ‹‹እኛ መናጆ ተብለን ነው የገባነው፤ የሚመረጠው አባ ማትያስ ነው›› /ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ/

    ‹‹ነገ በታሪክ የሚጠየቅና የሚወገዝ ሲኖዶስና አባት መኖር የለበትም›› /ብፁዕ አቡነ ገብርኤል/

ከላይ በዋናው ርእስ የተመለከተው÷ ቁጭት እንጂ አቅም ያነሳቸው ንግግሮች የተሰሙት ትላንት፣ የካቲት 16 ቀን 2005 . በፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴው በቀረቡት ዕጩዎች ላይ ለመወያየት የተሰበሰበው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ውል ያለው ግልጽ ውሳኔ ላይ ሳይደርስ ከቀትር በኋላ በተጠናቀቀበት ወቅት ነው፡፡

በስብሰባው ሂደት÷ ለፕትርክናው የተሠየሙትን ብፁዕ አቡነ ማትያስን ጨምሮ ተሳትፎ በነበራቸው ብፁዓን አባቶች መካከል የነበረው የከረረ የቃላት ልውውጥ፣ ተሳትፎ ባልነበራቸው ብፁዓን አባቶች ላይ የታየው ስጋትና ድብታ፣ በኮሚቴው ዋና ጸሐፊ ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጩ ምትክ የኮሚቴውን ሪፖርት ያቀረበው የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊው ለቅ/ሲኖዶሱ ጠረጴዛና ለአጀንዳው ታላቅነት የማይመጥን፣ ውክልናውና ያጸደቀለትን ማኅበር የሚያስንቅና የሚያስወቅስ ደርዝ የሌለው ንግግር፣ በዋናነትም ስብሰባው የተጠናቀቀበት ውል አልባ ኹኔታ ነው ይህን የሐዘን ንግግር ያናገረው፡፡ በዚህ ቃል ሲናገሩ ከተሰሙት አረጋውያኑ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጥቂቱን ለመጥቀስ÷ አቡነ አትናቴዎስ፣ አቡነ ኤርሚያስ፣ አቡነ አረጋዊ፣ አቡነ ኤፍሬም እና ከዕጩዎች አንዱ አቡነ ማቴዎስ ናቸው፡፡

ስብሰባው ጠዋት 300 ላይ በውዳሴ ማርያም፣ መልክአ ኢየሱስ እና መልክአ ማርያም ጸሎት ከተከፈተ በኋላ ዐቃቤ መንበሩ የዕለቱን የስብሰባ አጀንዳ ሲያስተዋውቁ፣ ‹‹የአስመራጭ ኮሚቴውን ሪፖርት ሰምተን ለማጽደቅ ነው፤›› በሚል ነበር ያስጀመሩት፡፡ የአስመራጭ ኮሚቴው አባላት ተጠርተው ገብተው በሕዝብ ግንኙነት ሓላፊው በኩል የዕጩዎች አመራረጥ፣ ዝርዝርና ማንነት በንባብ ከተሰማ በኋላ የነበረው የስብሰባው ድባብ ግን፣ ሰምቶ ማጽደቁ ቀርቶ የተጋጋሉ ውይይቶችንና ትችቶችን ያስተናገደ፣ ከሕዝብ ግንኙነት ሓላፊው በቀር ብዙኀኑ የኮሚቴው አባላት አንዳች የውስጥ ክፍፍልን በሚያሳብቅ አኳኋን (በተለይም ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ) በእጅጉ አዝነውና ተክዘው የታዩበት፣ ኮሚቴው ከብፁዓን አባቶች ለቀረቡለት ጥያቄዎች የተረጋገጠ መልስ ሊሰጥ ያልቻለበት አሳዛኝ ኹኔታ ነበር፡፡

ኮሚቴው የተረጋገጠ ወይም በቂ ያልኾነ ምላሽ ሊሰጥባቸው ያልቻለባቸውና ለተካረረ መንሥኤ የኾኑ ዋነኛ ነጥቦች፣ የመጀመሪያው÷ ዕጩ ፓትርያሪኮች የቀረበቡበት መንገድ የምርጫ ሕገ ደንቡ ተሟልቶ ያልተፈጸመበት መኾኑ ነው፤ ሁለተኛው÷ የምርጫው ሂደትና ጠቅላላ ኹኔታ ለውጭ ኀይሎች ተጽዕኖ እና ለውስጥ ቡድኖች ፍላጎት የተጋለጠ መኾኑ ነው፡፡ እኒህን አከራካሪ ነጥቦች በየጊዜው ባወጣናቸው ዘገባዎች እያጋለጠናቸው ቆይተናል፤ እስኵ አሁን ደግሞ በስብሰባው ሂደት ከተንሸራሸሩት ሐሳቦች አንጻር በመጠኑ እንመልከታቸው፡፡

በምልአተ ጉባኤው ስብሰባ ከዋነኛ አነጋጋሪ ነጥቦች አንዱ÷ የምርጫው ሂደትና ጠቅላላ ኹኔታ ለውጭ ኀይል ተጽዕኖ እና ለውስጥ ኀይሎች ጥቅማዊ ፍላጎት የተጋለጠ መኾኑ ነው፡፡ የውጭ ኀይል ሲባል ሌላ ማንም ሳይኾን የመንግሥት ተጽዕኖ ማለታችን ነው፡፡