Friday, January 24, 2014

አኩሪ አተር ወይስ አውሬ አተር?



 ከግደይ ገ/ኪዳን- ሉላዊ ሴራና የተሸሸጉ ታሪኮች (Anti Global Conspiracy) የተገኘ /

 በቅድሚያ አጠር ያለች ጉዳዩ ላይ የምታስረዳ ጽሑፍ ባቀርብ እንደ ማንቂያ ደወል ትሆንና ሌሎች የሚመለከታቸው ምሁራንና ተመራማሪዎች ይተጉበታል ብዬ ባቀርብ አጥብቀው የሚሞግቱኝ ሰዎች ገጠሙኝ፡፡ ጉዳዩን የሚቀጥልበት ሌላ ሰውም አልተገኘም፡፡ የቀጣዩ እርምጃ ሸክምም በኔው ላይ ወደቀ፡፡ ስለዚህም በጉዳዩ ላይ ጠለቅ ያለ ምርምር ያካሄዱ ሰዎች ስራዎችን ፈትሼ አጠር ያለች ቆንጆ ጽሑፍ ለማቅረብ በይነ መረብን ስሞግት ቆንጆ ያለቀለት ስራ አገኘሁ፡፡ የሳሊ ፋልኮን እና የሜሪ ጂ. ኢንግ (ፒኤች.ዲ.) የጥምር ስራ የሆነውን Newest Research On Why You Should Avoid Soy የተሰኘ ጽሑፍ፡፡ እነሆ ተርጉሜዋለሁኝ፡፡ አንብቡት፡፡
በሃገራችን ጓያ የተባለው ጥሬ በችግር ጊዜ ሰዎች ሲመገቡት እግራቸውን ሽባ እያደረጋቸው ሲመለከቱ “ጉልበት ሰባሪ” አሉት፡፡ የእግር ነርቭ የሚነካውን የጓያ አካል የሆነውን ንጥረ ነገር ጓያውን ውሃ ውስጥ በመዘፍዘፍ እና ገለባውን በማስወገድ ማጥፋት ይቻላል፡፡ ከክፍለ ሃገር የመጡ ሰዎችም መንግስትና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋሞች በዚህ ዙርያ ህዝቡን የማንቃት ስራ በዘመቻ ይሰሩና ያስተምሩ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ በጥፋት አይነቱ ከጓያ እጅግ በከፋው አኩሪ አተር ላይ ግን እንዲህ የሚያደርጉ አካላት ጠፍተዋል፡፡ መንግስታዊ ያልሆኑትስ ስለአኩሪ አተር የጤና ጠንቅ እናሳውቅ ቢሉ “በበጎ ምግባራቸው” ብዙ የሚያተርፉ አይሆኑም፡፡ ማን ሲደጉማቸው?
ችግሩ ያለው አኩሪ አተር እንደጓያ በግለሰብ ገበሬዎች ተመርቶ በትንሹ ጥቅም ላይ የሚውል ሳይሆን፣ በሰፊ ማሳ ታርሶ፣ በከፍተኛ ኢንዱስትሪ ተሳስሮ ከቅባት እስከ ስጋና ወተት እየተደረገ፣ ከከብት መኖነት እስከ ከሕጻናት ዱቄት ሆኖ ስለሚመጣ ይህን ግዙፍ ኢንዱስትሪ መጋፈጥ ከባድ እጅግ በጣም ከባድ ይሆናል፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ ከሚያደርሳቸው ጥፋቶች አንጻር ሆን ተብሎ የሚሰራጭ መሆኑን ስናውቅ የሚቃወመው ሁሉ ከባድ ስልታዊ ትግል እንደሚገጥመው ይረዳል፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ አውሬ አተሩ ከሰማይ እንደ ወረደ መና የሚቆጥሩት ቅጠል በሌ ግለሰቦች ስላሉ በፍቅሩ ተነድፈዋል፡፡ ሌሎችም ከጤና ጋር በተያያዘ ምርጫቸው ያደረጉት ይገኛሉ፡፡ ቅጠል በሎቹን ምንም ማድረግ አይቻልም ታውረዋልና ለማየት ካልፈቀዱ አይቻልም፡፡ በጤና ምክንያት የመረጡት ግን ሃኪማቸውን አማክረው ሌላ አማራጭ ቢፈልጉ ይሻላቸዋል፡፡ አተርፍ ባይ አጉዳይ እንዳይሆኑ፡፡
ከስር የተጠቀሱት ዘመን አቆጣጠሮች በግሪጎራውያኑ ነው፡፡ በመዓዝናዊ ቅንፍ ውስጥ ያሉት አስተያየቶች የኔው ናቸው፡፡ ይህ መነሻ ከነስእሉ ደግሞ እኔው የጨመርኩት መሆኑ እዳይዘነጋ፡፡ መልካም የማንቂያ ንባብ ይሁንልዎ፡፡


የሲንደሬላ መጥፎው ጎን


የአኩሪ አተር ሽያጭ በተአምራዊ መልኩ እንዲጨምር ያደረገው ፕሮፖጋንዳ እጅግ አስገራሚ የሚሆነው ከጥቂት ጊዚያት በፊት በኤስያም ሳይቀር አኩሪ አተር አይበሌ የነበረ መሆኑን ስንገነዘብ ነው፡፡ በቹ ስርወ መንግስት ዘመን (1134-246 ዓ.ዓ) አኩሪ አተር ከአራቱ ቅዱሳን እህሎች ማለትም ገብስ፣ ስንዴ፣ ዳጉሳ እና ሩዝ ጋር ተደምሮ ይቆጠር ነበር፡፡
ሆኖም ግን የወቅቱ የአኩሪ አተር ስእላዊ መግለጫ፣ ከቀደምት ዘመናት ጀምሮ የነበረው በምግብነት ይቆጠር እንዳልነበረ ያሳያል፡፡ የሌሎቹ አራቱ እህሎች ስእላዊ መግለጫ ፍሬያቸውንና ግንዳቸውን ሲያሳይ፣ የአኩቲ አተሩ ስእል የሚያሳየው ግን ስሩን ነበር፡፡ በዘመኑ የሰፈረው የእርሻ ጽሑፍ እንደሚያሳየው ከሆነ አኩሪ አተር ዘር ለማፈራረቅ ጥቅም ላይ ይውል እንደነበር ያስረዳል፡፡ እንደምንገነዘበው አኩሪ አተር የአፈሩን ናይትሮጅን ይዘት ለማስተካከል ነበር የሚተከለው፡፡ (13)
ማጠንሰስ (በውሃ መዘፍዘፍ) (ፈርመንቴሽን) ዘዴ እስኪደረስበት ድረስ አኩሪ አተር ለመብል አልዋለም ነበር፡፡ ይህ በቹ ስርወ መንግስት ዘመን የሆነ ነበር፡፡ መጀመርያ ላይ ተጠንስሶ ከአኩሪ አተር የተገኙት ምግቦች ቴምፔ፣ ናቶ፣ ሚሶ እና አኩሪ አተር ወጥ (ሶስ) ናቸው፡፡
በኋላ ላይ ምናልባት በ2ኛው ክ/ዘመን ዓ.ዓ ቶፉ (ወይም ወፍራም አተር ወጥ) በካልሺየም ሳልፌት ወይም በማግኒዠርየም ሳልፌት የነጠረ (ፕርሲፒቴትድ) የሚደረግ ምግብ አገኙ፡፡ ወድያው ወደ ጃፓንና ኢንዲነዥያ ተስፋፋ፡፡
ቻይናዎች ያልተጠነሰሰ አኩሪ አተር በሌሎች የጥራጥሬ ዝርያዎችን (ለጉምስ) ለምሳሌ እንደ ምስር ዓይነቶቹን እንደሚያደርጉት በልተው አያውቁም፡፡ ምክንያቱም አኩሪ አተር ከሌሎቹ የበለጠ ተፈጥሯዊ መርዝ ወይም “ፀረ-ንጥረ ምግብ” (“አንቲኒውትረንትስ”) አለውና፡፡ ከነዚህ የመጀመርያዎቹ ኢንዛይም አጋቾቹ ናቸው፡፡ ትራይፕሲን (trypsin) እና ሌሎች ፕሮቲንን ለመፍጨት የሚያስፈልጉ ኢንዛይሞችን ያግዳሉ፡፡
እነዚህ አጋቾች በመደበኛው የምግብ አዘገጃጀት ዘዴ ሊወገዱ የማይችሉ በጽኑ የተሳሰሩ ፕሮቲኖች ናቸው፡፡ ክፉኛ ጨጓራን የሚነኩ ሲሆኑ፣ የፕሮቲን መፈጨትን ይቀንሳሉ፣ የአሚኖ አሲድ ግብአታችንን በከፍተኛ መልኩ እንዲጠፋ ያደርጋሉ፡፡ በእንስሳት ላይ በተደረገ ሙከራ ትራይፕሲን አጋች የበዛበት ቀለብ የጣፊያ መተለቅ እና መታመም ሁኔታ ነቀርሳን ጨምሮ አስከትሏል፡፡(14)
አኩሪ አተር በተጨማሪ ሄማግሉቲኒን (haemagglutinin) አለው፣ ይህ የማርጋት ጠባይ ያለው ንጥረ ነገር ሲሆን ቀይ የደም ሴሎች እንዲጠባበቁ የሚያደርግ ነው፡፡
ትራይፕሲን አጋቾቹ እና ሄማግሉቲኒን እድገት ከልካይ ናቸው፡፡ እኚህ ፀረ-ንጥረ-ምግቦችን እንዲመገቡ የተደረጉ የአይጥ ጨቅላዎች በትክክል አላደጉም፡፡ በውሃ በሚዘፈዘፍበት ወይም በሚጠነሰስበት ወቅት እድገት የሚያውኩት ንጥረ ነገሮች ይመክናሉ፣ ቻይኖችም የመጠንሰስ ዘዴን መጠቀም ከጀመሩ በኋላ አኩሪ አተርን የመአዳቸው አካል አድርገውታል፡፡
ዝቃጭ የተደረጉ (ፐርሲፒቴትድ) ምርቶች ላይ ኢንዛይም ገዳቢዎቹ በሚነፋፋው አረፋ ላይ በመሰብሰብ እንደ እርጎ ከሚሆነው ይርቃሉ፡፡ እናም በቶፉ እና ቢን ከርድስ እድገት ከልካዮቹ በመጠን የሚቀነሱ ቢሆኑም ሙሉ ለሙሉ ግን አይወገዱም፡፡
አኩሪ አተር በተጨማሪም ጎይትሮጅንስ የተባለ ንጥረ ነገር ይገኝበታል፡፡ ጎይትሮጅን - የታይሮይድ እጢ ስራን የሚያደናቅፍ ንጥረ ነገር ነው፡፡
በተጨማሪም 99% የሚሆነው የአኩሪ አተር ምርት [ይህ በአሜሪካ መሆኑ ነው] ዘረ መሉ (ጀነቲክ) በሰው ሰራሽ መንገድ የተቀየረ ነው፡፡ ከምግቦችም ሁሉ በበለጠ በፀረ-ተባይ መድሃኒት የሚያድግ ነው፡፡
አኩሪ አተር ከፍተኛ ፋይቲክ አሲድ (phytic acid) አለበት፣ ይህ በሁሉም ጥራጥሬዎች ገለባ ወይም ቅርፊት ላይ የሚገኝ ነው፡፡ ይህ ንጥረ ነገር ወሳኝ የሆኑ ማዕድኖች በሰውነታችን እንዳይወሰዱ የሚገታ ነው፣ እንደ ካልሺየም፣ ማግኒዥየም፣ ኮፐር፣ ብረት እና በተለይም ዚንክ - በአንጀታችን እንዳይወሰዱ ያደርጋል፡፡
ፋይቲክ አሲድ በስፋት ጥናት የተደረገበት ንጥረ ነገር ነው፤ በአሁኑ በሳይንሳዊ ስነ ጽሑፍ ውስጥ ይህን የሚመለከቱ በመቶዎች የሚቆጠሩ ስራዎች ይገኛሉ፡፡ በፋይቴትስ ከፍተኛ መጠን ያላቸው ጥራጥሬ ወይም በተለይ የባቄላ ዘር ያላቸው እህሎችን ዋና ምግባቸው ያደረጉ በሶስተኛው ዓለም ያሉ ማሕበረሰቦች በስፋት ለሚፈጠርባቸው የማዕድን እጥረት ዋነኛው መንስኤ ፋይቴትስ መሆኑን ሳይንቲስቶች ይስማማሉ፡፡(15)
በነዚህ አካባቢዎች በተደረገው ጥናት በሚመገቧቸው አትክልት ምግቦች ውስጥ ካልሺየም፣ ማግኒዥየም፣ ብረት እና ዚንክ ይገኝበታል፣ ሆኖም ግን ከፍተኛ የፋይቴት ይዘት ያለው አኩሪ አተርና ጥራጥሬዎቹ እነዚህ ማዕድናት በሰውነታቸው እንዳይወሰዱ አድርጓቸዋል፡፡
አኩሪ አተር ከየትኛውም ጥራ ጥሬ ወይም የባቄላ ዘር (ለጉሜ) እጅግ በላቀ ሁኔታ የፋይቴት ይዘት አለው(16) በአኩሪ አተር ያለው ፋይቴት ደግሞ በተለመደው የፋይቴት መቀነሻ መንገድ ለምሳሌ እንደ ለረዥም ጊዜ በዝግታ ማብሰል ዓይነት ዘዴ አይቀነስም፡፡(17) በአኩሪ አተር ያለውን የፋይቴት ይዘት መቀነስ የሚቻለው ለረዥም ጊዜ በውሃ በመዘፍዘፍ (በመጠንሰስ) ብቻ ነው፡፡
እንዲዘቅጥ የተደረገ (ፕርስፕቴትድ) አኩሪ አተር ለምሳሌ እንደ ቶፉ ዓይነቱ ከስጋ ጋር ነው የሚበላው፣ በዚህም መዓድናትን የመከልከል የፋይቴት ባሕርይን መቀነስ ይቻላል፡፡(18) ጃፓኖቹም በባህላቸው እጅግ ትንሽ መጠን ያለው ቶፉ ወይም ሚሶ በማዕድናት ከበለጸገ የአሳ ሾርባ ጋር አድርገው ነው የሚመገቡት፣ ይህም ቀጥሎ የሚቀርብ ስጋ ወይም አሳ ይከተለዋል፡፡
በስጋ እና ወተት ተዋጽኦ ምትክ ቅጠል በሌ (ቨጀተርያን) የሆኑ ሰዎች ቶፉ እና የባቄላ “እርጎ” (በውሃ ተዘፍዝፎ ከታች እንደ አተላ የሚቀረው) ሲመገቡ ከፍተኛ የማዕድናት እጥረት አደጋ ይደቀንባቸዋል፡፡ የካልሺየም፣ ማግኒዥየም እና ብረት እጥረት ምን እንደሚፈጥሩ የታወቀ ነው፤ የዚንክ እጥረት ግን በብዛት አይታወቅም፡፡
ዚንክ የማስተዋል (ንቃተ ህሊና) መዓድን ይባላል፣ ምክንያቱም ለምርጥ የአእምሮ እና ነርቭ ስርዓት እድገትና ተግባር ስለሚያስፈልግ ነው፡፡ ዚንክ ለፕሮቲን መዋሃድ እና ኮላገን [አጥንት እና ጡንቻ መገጣጠምያ የሚገኝ] በመስራት ላይ ወሳኝ ሚና አለው፤ በደም-ስኳር ቁጥጥር ሂደት ሚና አለው፣ በዚህም ከስኳር በሽታ ይከላከላል፤ ለተዋልዶ ጤንነትም ያስፈልጋል፡፡
ዚንክ ብዛት ባላቸው ወሳኝ ኢንዛይሞች ውስጥ ቁልፍ አካላቸው ሲሆን በሽታ በመከላከል ስርአትም የራሱ ሚና አለው፡፡ በአኩሪ አተር የሚገኙ ፋይቴቶች ከሌሎቹ መዓድናት በይበልጥ ዚንክ መመጠጥን ይገድባሉ፡፡(19) የዚንክ እጥረት የቀንም ቅዠት ( “ምርቃና” ) ስሜት ውስጥ ይከታል፣ አንዳንድ ቅጠል በሌዎች [ቨጀተርያንስ ለማለት ነው ጫት ቃሚዎች ለማለት አይደለም፣ ወይ ምፀት/አይረኒ] ይህን ስሜት እንደ “ከፍ ከፍ” የሚያደርግ መንፈሳዊ ልምድ ወይም አብርሆት እንደገጠማቸው አድረገው እንዲያስቡ ያደርጋቸዋል፡፡ 
ወተት መጠጣታቸው አሜሪካ ያሉ የጃፓናውያን ሁለተኛ ትውልዶች ቁመት መርዘም እንደ ምክንያት ይቀመጣል፡፡ አንዳንድ ተመራማሪዎች እንደሚገምቱት ከሆነ ዝቅተኛ ፋይቴት ያለው የአሜሪካውያኑ መብል -ምንም እንኳ ሌላ ሰንኮች ቢኖሩበትም- ዋናው የቁመታቸው መጨመር ማብራርያ ነው ይላሉ፡፡ ፋይቴት የበዛበት ምግብ የሚወስዱና ተጽእኖውን ለመቀነስ በቂ ስጋ እና አሳ የማያገኙ የኤስያውያንም ሆነ የምእራባውያን ልጆች በብዛት ሪኬትስ፣ አጭር መሆን እና ሌሎች የእድገት እክሎች ይገጥሟቸዋል ሲሉ ይጠቁማሉ፡፡(20)


ፕሮቲንን ከአኩሪ አተር መነጠል፡ አደጋው


አኩሪ አተር ሰሪዎች እነዚህን ፀረ-ንጥረ ምግቦችን ካለቀለት የአኩሪ አተር ምርቶች ለማውጣት ብዙ ደክመዋል፣ በተለይ ከአኩሪ አተር የተነጠለው ፕሮቲን (soy protein isolate (SPI)) ውስጥ፣ ከአኩሪ አተር ከተነጠለ ፕሮቲን ስጋ እና ወተት ተዋጽኦን ለመምሰል የሚጥሩ ምርቶች ዋና አካል ነው፣ የሕጻናት የምግብ ቀመር (ፎርሙላ) እና አንዳንድ የወተት ስሪቶች፡፡
የፕሮቲን ንጣዩን እንዳሻህ በኩሽናህ መስራት የሚቻል ነገር አይደለም፡፡ ይህ የሚከወነው ኢንዱስትሪያዊ በሆኑ ፋብሪካዎች ውስጥ ሲሆን መጀመር የተለቆጠ (በውሃ የተለወሰ) አኩሪ አጠር ጥሬ ፋይበሩን ለማስወገድ ከአልካላይን ፈሳሽ ጋር ይቀላቀላል፣ ከዛ በአሲድ እጥበት እንዲዘቅጥ እና እንዲለያይ ከተደረገ በኋላ በመጨረሻ በአልካላይን ፈሳሽ ኒውትራል እንዲሆን ይደረጋል፡፡  
በአሉሚኒየም ገንዳ ውስጥ በአሲድ ማጠብ በመጨረሻ ምርቱ ላይ ከፍተኛ የአሉሚኒየም ይዘት እንዲቀላቀልበት ያደርጋል፡፡ ከዚህ የሚገኙት ዝቃጮች በከፍተኛ ሙቀት ርጭት እንዲደርቁ ይደረጋሉ፣ ይህም ከፍተኛ የፕሮቲን ምርቱን ይሰጠናል፡፡ አኩሪ አተሩን ለመጨረሻ ጊዜ ያራከሰው ቴክስቸርድ የአትክልት ፕሮቲን (ቲቪፒ) ከአኩሪ አተር ከተነጠለ ፕሮቲን ለመስራት በሚደረገው እጅግ ከፍተኛ ሙቀት፣ ከፍተኛ ግፊት (ፕሬዠር) ሂደት ነው፡፡
በከፍተኛ ሙቀት ሂደት አብዛኞቹ የትራይፕሲን አጋቾቹን ይዘቶች ማስወገድ ይቻላል፣ ሁሉም ግን አይወገዱም፡፡ በተለያዩ የአኩሪ አተር የፕሮቲን ንጥል ውስጥ የሚገኘው ትራይፕሲን አጋቾች እስከ አምስት እጥፍ ድረስ የተለያዩ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡(21) (በአይጦች በተደረገ ሙከራ እጅግ ዝቅተኛ ትራይፕሲን አጋቾች ያሉዋቸው የአኩሪ አተር ፕሮቲን ንጥል የተመገቡት ካልተመገቡት (ማነጻጸርያዎች) ጋር ሲተያዩ ክብደታቸው የቀነሰ ሁነው ተገኝተዋል፡፡(22)) 
በተጨማሪ ከፍተኛ-ሙቀት ሂደት ሌላ ተጓዳኝ ጉዳት አለው፣ በአኩሪ አተር ያሉትን ሌሎች ፕሮቲኖችን ከተፈጥሮ ውጭ ስለሚያደርጋቸው በከፍተኛ ሁናቴ ከጥቅም ውጭ ያደርጋቸዋል፡፡(23) ለዚህም ነው መኗቸው አኩሪ አተር የሆኑ እንስሳት በትክክል እንዲያድጉ ላይዚን (lysine) በተጨማሪ ከቀለባቸው እንዲጨመር የሚደረገው፡፡
ከባድ ነቀርሳ አምጪ ንጥረ ነገር (ካርሲኖጂንስ) የሆኑት ናይትራይቶች የሚፈጠሩት በሙቀት ርጭት እንዲደርቅ ሲደረግ ነው፣ በአልካላይን ሲታጠብ ደግሞ ላይሲኖአላናይን (lysinoalanine) የተባለ መርዝ እንዲፈጠር ያደርጋል፡፡(24) ብዙ አርቲፊሻል ማጣፈጫዎች፣ በተለይም ኤምኤስጂ፣ ከአኩሪ አተር የሚነጠል ፕሮቲን ላይ እና ቴክስቸርድ አትክልት ፕሮቲን ላይ ይጨመራሉ፣ ይህ እንደ ባቄላ ያለ የጣእም ቃናቸውን ለመሸፈንና እንደ ሥጋ ሥጋ እንዲሉ የሚደረግ ነው፡፡(25)
በቀለብ ሙከራዎች ወቅት ከአኩሪ አተር የተነጠለ ፕሮቲን በተፈተሸ ጊዜ የቫይታሚን ኢ፣ ኬ፣ ዲ እና ቢ12 ላይ ያለው አስፈላጊነት እንዲጨምር አድርጓል፡፡ በተጨማሪም የካልሺየም፣ ማግኒዥየም፣ ማንጋኒዝ፣ ሞሊብዲነም፣ ኮፐር፣ ብረት እና ዚንክ እጥረት ምልክቶች እንዲፈጠር አድርጓል፡፡(26) በነዚህ አኩሪ አተር ውስጥ ቀሪ ሆኖ ያለው ፋይቲክ አሲድ በከፍተኛ ሁኔታ የዚንክ እና የብረት መወሰድ እንዲቀንስ አድርጓል፤ ከአኩሪ አተር የተነጠለ ፕሮቲን እንዲመገቡ የተደረጉ እንስሳት አንዳንድ ሕዋሳቶቻቸው በተለይም ጣፍያቸው እና ታይሮይድ እጢያቸው እንዲተልቅ አድርጓል፣ በተጨማሪም በጉበት ላይ ፋቲ አሲዶች ይበልጥ እንዲከማቹ አድርጓል፡፡(27)
እንዲህም ሆኖ የአኩሪ አተር ፕሮቲን ንጥል እና ቴክስቸርድ የአትክልት ፕሮቲን [በአሜሪካ] በትምህርት ቤቶች የምሳ የምግብ ፕሮግራሞች፣ ለሽያጭ በሚሰሩ የዳቦ ምርቶች፣ ተመጣጣኝ ምግብ ይዘት ላላቸው ለስላሳ መጠጦች እና የሽያጭ ምግቦች (ፋስት ፉድስ) ላይ ጥቅም ላይ ይውላሉ፡፡ በሶስተኛው ዓለም [ድሃ ሃገሮች] ውስጥ የእርዳታ ምግብ ሆኖ በስፋት ይሰጣል፡፡
በእንስሳት ላይ ተደርጎ የተገኘው ደካማ ውጤት እንዳለ ሆኖ የአኩሪ አተር ኢንዱስትሪው የተለመደው የሰው ልጆችን መብል በአኩሪ አተር መተካት የሚመክሩ የተለያዩ ጥናቶችን ስፖንሰር አድርጎ አሰርቷል፡፡
የዚህ አብነት የሚሆነው "Nutritional Quality of Soy Bean Protein Isolates: Studies in Children of Preschool Age" የተሰኘው ነው፣ በራልስቶን ፑሪና ኩባንያ ስፖንሰር አድራጊነት የተዘጋጀ ጥናት ነው፡፡(28) የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ችግር ያለባቸው የማእከላዊ አሜሪካ ህጻናት ስብስብ ላይ የተደረገ ሙከራ ነው፡፡ መጀመርያ ላይ የተለመዱ ምግቦችን፣ ስጋንና ወተትን ጨምሮ፣ በመመገብ ወደ ጤናማ ሁኔታ ካመጧቸው በኋላ፣ ለሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት እነዚህ ልማዳዊ ምግቦች ከአኩሪ አተር በተነጠለ ፕሮቲን በተሰራ ፈሳሽ እና ስኳር እንዲተካ አድርገዋል፡፡
በኦርዌላዊ ዘዬ ወደ ሰውነታቸው የተወሰደ እና ከሰውነታቸው የተወገደ ናይትሮጅን እንዲለካ ተደርጓል፡ ልጆቹ ዘወትር ጠዋት እራቁታቸውን ክብደታቸው የሚመዘን ሲሆን፣ ዓይነ ምድራቸውና ትውከታቸው ተሰብስቦ ለምርመራ ይወሰድ ነበር፡፡ ተመራማሪዎቹ ልጆቹ ናይትሮጅ መያዝ (ማከማቸት) መቻላቸውን እና እድገታቸውም “በቂ” እንደነበር አገኙ፣ ምርምራቸውም (ሙከራቸውም) ስኬታማ ተብሎ ታውጇል፡፡   
በእርግጥ ልጆቹ በዚህ አመጋገብ ምጣኔ ጤነኛ ነበሩ ወይም በረዥም ጊዜ ልኬት በጤንነት ቆዩ ወይ የሚለው ሌላ ጉዳይ ነው፡፡ ተመራማሪዎቹ ልጆቹ “በተደጋጋሚ” ማስታወካቸውን፣ በተለይ ከማዕድ ሲነሱ፣ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ለተወሰነ ጊዜ በሚቆይ ተቅማጥ መያዛቸው፣ አንዳንዶች የላይኛው የትንፋሽ ስርአት መቁሰል (upper respiratory infections) ሲያጋጥማቸው፣ ሌሎቹ ደግሞ በሽፍታ እና በትኩሳት ይሰቃዩ እንደነበር ልብ ሊሉ እንደቻሉ ጠቅሰዋል፡፡
እዚህ ጋር ልብ ሊባል የሚገባው ነጥብ ተመራማሪዎቹ የሕጻናቱን የተመጣጣኝ ምግብ እጥረትን ለመቅረፍ የአኩሪ አተር ምርቶችን በመጠቀም ለመርዳት አለመሞከራቸውን እና የአኩሪ አተርና ስኳር ቅልቅል ከአኩሪ አተር ምርቶች የማይገኙትን በተለይ ቫይታሚን ኤ፣ ዲ እና ቢ12፣ ብረት፣ አዮዲን እና ዚንክ ንጥረ ምግቦችን ለመጨመር ተገደው ነበር፡፡  


እንከን የለሹን ምግብ መሸጥ


“እንከን የለሽ ምግብ ማሳደግ እችላለው ብለህ አስብ፡፡ ይህ ምግብ በቀላል ወጪ የሚገኝ የተመጣጠነ ምግብ ብቻ ሳይሆን፣ ጣፋጭና በተለያየ መልኩ ለማዘጋጀት ቀላል ይሆናል፡፡ ጤናማ ምግብና የታጨቀ ስብ (saturated fat) አይኖረውም፡፡ እንዲያውም በአርባዎቹ መጨረሻ ሁነህ የወጣትነት ፀጋ ይፈስብሃል፡፡”
ይህን ጥቅስ ዲን ሁግቶን የተባለው ለ ዘ ፉሮው በሚጽፍበት ወቅት ያሰፈረው ነው፡፡(2) ይህ በ12 ቋንቋዎች የሚታተመው በጆን ዴሪ መጽሔት ነው፡፡ “ይህ እንከን የለሹ ምግብ አንዳንድ የአለማችን አሰቃቂ በሽታችን መከላከልና የታመሙት እንዲያገግሙ ማድረግ ይቻለዋል፡፡ ይህን ተአምራዊ ሰብል በተለያዩ የአፈር ዓይነቶችና የአየር ሁኔታዎች ማብቀል ትችላለህ፡፡ ይህን ሰብል ማልማት መሬቱን የሚበላ ሳይሆን የሚያለማ ነው …፡፡ ይህ ተአምራዊ ምግብ በእውን አለ ….፡፡ አኩሪ አተር ይባላል፡፡”
አስበው፡፡ ገበሬዎች ሲያስቡት ነበር - በየአመቱም ተጨማሪ አኩሪ አተር ይዘራሉ፡፡ በአንድ ወቅታ አናሳ ሰብል የነበረው፣ በ1913 በአሜሪካ እርሻ ክፍል (ሚኒስቴር) ደብተር እንደ ምግብ ሳይሆን እንደ ኢንዱስትሪያዊ ምርት ተመዝግቦ የነበረው፣ ዛሬ ላይ በአሜሪካ እርሻ መሬት 72 ሚሊዮን ኤከር [291,384,000,000 ሜ. ካሬ] ሊሸፍን ችሏል፡፡ ከዚህ አርሻ አብዛኛው ዶሮዎችን፣ ተርኪዎችን (የአሜሪካ ዶሮዎችን)፣ አሳማዎችን፣ ላሞችን እና ሳልሞንኖችን (ትልልቅ አሶችን) ለመቀለብ የሚውል ነው፡፡ ሌላው ዋና ጥቅሙ የዳቦ ቅቤ (ማርጋሪን)፣ ለሚጋገሩ የሚሆን፣ እና ሰላጣ መቀቢያ የሚሆን ዘይት መሆን ነው፡፡  
በተገኘው የቴክኖሎጂ መሻሻል እንደ ቆሻሻ ተረፈ ምርት ይቆጠር ከነበረው ከአኩሪ አተር የተነጠለ ፕሮቲን ማስገኘት ተችሏል -ስብ የሌለው ከፍተኛ ፕሮቲን ያለው የአኩሪ አተር ምርት- ለማየት የሚያስጠላ እና አስቀያሚ ሽታ ያለውን ተረፈ ምርት ሰዎች ሊበሉት ወደሚችሉት ምርት መቀየር ተችሏል፡፡ ማጣፈጫዎች፣ ከመበላሸት ጠባቂዎች፣ ኢሙልሲፋየሮች እና ሲንተቲክ ንጥረ ምግቦች ከአኩሪ አተር የተነጠለ ፕሮቲን ምርትን የምግብ ሰሪዎቹን አስቀያሚ ዳክዬ ወደ አዲስ ዘመን ሲንደሬላ ቀይረውታል፡፡
አዲሱ ተረታዊ ምግብ ለውበቷ ሳትሆን ለምግባሯ ተብላ ነው ለገበያ የቀረበችው፡፡ ከመጀመርያውኑ ጀምሮ ከአኩሪ አተር የተነጠለ ፕሮቲን ጨማሪዎች (ኤክስተንደርስ) እና የስጋ ምትክ ተብሎ ነበር መሸጥ የተጀመረው - ይህ ስልት የተፈለገውን የደንበኛ ፍላጎት ሊያስገኝ አልቻለም፡፡ ኢንዱስትሪው አቀራረቡን ቀየረ፡፡
“ብዙም ያልተረፈው ማህበረሰብ ውስጥ ምርቱ ተቀባይነት እንዲያገኝ፣” ይላል የኢንዱስትሪው ቃል አቀባይ፣ “ምርቱ ለራሱ ፋይዳ ሲባል ብቻ በተረፈው ማህበረሰብ ውስጥ እንዲዘወተር ማድረግ ነው፡፡”(3) እናም አሁን ለከፍተኛው ማህበረሰብ ክፍል አኩሪ አተር ርካሽ የችግር ምግብ ሳይሆን ተአምራዊ ንጥረ ነገር፣ የልብ ህመንንና ነቀርሳን የሚከላከል፣ ፈጣን ትኩሳት (ሆት ፍላሽ፣ ያረጡ ሴቶችን የሚያጋጥማቸው) የሚከላከል፣ አጥንት የሚገነባና ዘላለም ወጣት አድርጎ የሚያኖር ተደርጎ እየተሸጠላቸው ነው፡፡
ተፎካካሪዎቹ -ሥጋ፣ ወተት፣ አይብ፣ ቅቤ እና እንቁላል- በሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ተይጣናዊ ተደርገው ቀርበዋል፡፡ አኩሪ አተር ቅጠል በሊታ የሆኑ አዲስ መልካም ትውልዶች ሥጋ እና ወተት ሆኖ ያገለግላቸዋል፡፡


መሸጥ ገንዘብ ያስወጣል


ይህ ደግሞ በተለይ እውነት የሚሆነው ጉዳዩ በ “ምርምር” መግዘፍ የሚያስፈልግ ሲሆን ነው፣ ግን ደግሞ የገንዘብ ድጎማ ለዚህ ጉዳይ ሞልቷል፡፡ ሁሉም የአኩሪ አተር አምራቾች ከአኩሪ አተር የገበያ ዋጋ የአንድ ግማሽ እስከ አንድ መቶኛ ድረስ አስገዳጅ የመዋጮ ክፍያ ይጠበቅባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ -ወደ 80 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር የሚጠጋ (4) የአኩሪ አተር ሕብረት እንቅስቃሴን ይደጉማል፣ “አኩሪ አተር በገበያ ያለውን ቦታ ማጠናከርና የአኩሪ አተር እና የአኩሪ አተር ምርት የሃገር ውስጥና የውጭ ሃገር ገበያን ለመጠበቅና ለማስፋፋት ይውላል፡፡”
የመንግስት የአኩሪ አተር መማክርት የሜሪላድ፣ ነብራስካ፣ ዴላዌር፣ አርካንሷ፣ ቨርጂንያ፣ ሰሜን ደኮታ እና መሺጋን ሌላ ተጨማሪ 2.5 ሚሊዮን ዶላር ለ “ምርምር” ያዋጣሉ፡፡(5) እንደ አርቸር ዳኒኤልስ ሚድላንድ [ኤዲኤም]  ያሉ የግል ኩባንያዎች ደግሞ የድርሻቸውን ያዋጣሉ፡፡ ኤዲኤምን ሚት ዘፕሬስ ላይ ለማስተዋወቅ 4.7 ሚሊዮን ዶላር ያወጣ ሲሆን፣ በተጨማሪም ፌስ ዘ ኔሽን ላይ ለማስተዋወቅ 4.3 ሚሊዮን ዶላር አውጥቷል፡፡(6)
የሕዝብ ግንኙነት ድርጅቶች የምርምር ፕሮጀክቶቹን ወደ ጋዜጣ መጣጥፎች ለመቀየር እና ማስታወቅያ ለማስደረግ ተከፍሏቸው ሲሰሩ፣ የህግ ድርጅቶች ደግሞ ተስማሚ የመንግስት ደንቦች እንዲወጡ ተከፍሏቸው ይወተውታሉ (ሎቢ ያደርጋሉ፡፡) በመላው አለም ደግሞ አኩሪ አተር የሚቀምሩ ፋብሪካዎች እንዲሰሩ አይኤምኤፍ ፈንድ ይሰጣል፣ በተጨማሪም አኩሪ አተር ነገፍ በዓለም ገበያ እንዲቀርብ ነጻ የንግድ ፖሊሲ እንዲኖር ያደርጋል፡፡
ተጨማሪ አኩሪ አተር እንዲኖር የሚደረገው ግፊት የማያባራ እና በተደራሽነቱም ሉላዊ ነው፡፡ አሁን የአኩሪ አተር ዳቦ [በአሜሪካ] ገበያዎች በአብዛኛዎቹ የደረሰ ነው፡፡ “በበቆሎ የሚሰራው የሜክሲኮን ቂጣ ቶርቲላንም በፕሮቲን የታጨቀ በማድረግ ወደ 20 ሚሊዮን የሚጠጉ የሜክሲኮ ድሆችን የተመጣጣኝ ምግባቸውን ከፍ ለማድረግ”(7) እየተጠቀሙበት ይገኛሉ፡፡ በብሪታንያ አላይድ ቤከርስ የተባሉ ዳቦ ሻጮች ደግሞ ያረጡ ሴቶች ላይ በማነጣጠር ፈጣን ትኩሳትን ይቀንሳል በሚል እያስተዋወቀ ይገኛል፡፡ በሳምንት ሩብ ሚሊዮን ዳቦ ይሸጣል፡፡(8) 
“በትምህርት ቤት የምሳ ማዕድ ላይ ተጨማሪ የአኩሪ አተር ምግቦች እንዲጨመሩ” የአኩሪ አተር ኢንዱስትሪው ኖርማን ሮበርት አሶሼትስ ተባለው የሕዝብ ግንኙነት ድርጅት ቀጥረዋል፡፡(9) የአሜሪካ መንግስት ግብርና ክፍል (ሚኒስቴር) በትምህርት ቤት ምሳ ላይ ሊቀርብ የሚችለው የአኩሪ አተር ከፍተኛ መጠን ገደብ፣ 30 መቶኛ የሚለውን ለመሰረዝ ተስማማ፡፡ የኑሜኑ (NuMenu) የተባለው የምሳ መርሐ ግብር በተማሪዎች ምሳ ሊቀርብ የሚችለው የአኩሪ አተር ድርሻን ያለ ገደብ ማድረግ ይፈቅዳል፡፡ ሃምበርገር፣ ታኮ እና ላዛኛ ላይ አኩሪ አተር ተጨምሮ አጠቃላይ ስቡ ከ30 መቶኛ ካሎሪ በታች አድርገው የመንግስት ቁጥጥር ጋር ተስማሚ ሁነው ይገኛሉ፡፡ “በአኩሪ አተር የበለጸጉ ምግቦች ተማሪዎች የተሻለ ተመጣጣኝ ምግብ እና ዝቅተኛ ኮሌስትሮል እና ስብ እያገኙ ነው፡፡” 
ከሁሉም ተጠቃሚ የሆነው የአኩሪ አተር ወተት ነው፣ በ1980 ከነበረው 2 ሚሊዮን ዶላር አምና [1999] ላይ ወደ 300 ሚሊዮን ዶላር ሊያድግ ችሏል፡፡(10)
የአሰራር ሂደት ተአምራቶች፣ ጥሩ አቀራረብ፣ እና ግዙፍ የማስታወቅያ ስራ እና ምርቱ ለመልካም ጤንነት ጥቅም ሊያስገኝ ይችላል በሚል የታጀበው የሽያጭ ስልት በሁሉም የእድሜ ክልል ለሚገኙ ሰዎች ተሸማችነቱ እንዲጨምር አድርጓል፡፡ ለምሳሌ አኩሪ አተር ፕሮስቴት ካንሰር ይከላከላል የሚሉት ዘገባዎች በመካከለኛ እድሜ (ጎልማሳ) ወንዶች አኩሪ አተር ወተት እንዲጠጡ አድርጓቸዋል፡፡ “ከ 55 እስከ 60 ዓመቱ የሆነውን ወንድ የአኩሪ አተር ወተት እንዲጠጣ እጁን መጠምዘዝ የለብህም፡፡” ይላል ማርክ መዚና፡፡ ማይክል ሚልከን የእርባና ቢስ አረቦን (ጃንክ ቦንድ) በመሸጥ የከበረው የቀድሞ የፋይናንስ ነጋዴ የአኩሪ አተር ኢንዱስትሪ የነበረውን የሂፒ ምስል (የወፈፌዎች ምግብነት) በጣም በተቀነባበረ የሕዝብ ግንኙነት ዘመቻው ለሁሉም በቀን 40 ግራም የአኩሪ አተር ፕሮቲን መውሰድ አስፈላጊ ነው በሚል አተያየት እንዲቀየር አድርጓል፡፡  
ዛሬ አሜሪካ፣ ነገ ዓለሙን፡፡ የአኩሪ አተር ወተት ሽያጭ በካናዳ እየጨመረ ነው፣ ምንም እንኳ በሃገሪቱ የአኩሪ አተር ወተት ከላም ወተት ሁለት እጥፍ በዋጋ የሚበልጥ ቢሆንም፡፡ በኬንያ እንኳ የአኩሪ አተር ማቀነባበርያ ፋብሪካዎች እየተቋቋሙ ነው፡፡(11) [ዛሬ በኢትዮጵያም ተቋቁሟል፡፡] በቻይና እንኳ ሳይቀር አኩሪ አተር የችግር ጊዜ ምግብ ተደርጎ የሚወሰደው እና ህዝቡ ተጨማሪ ሥጋ እንጂ ቶፉ የማይሹት፣ እንደ ምእራባውያን ያለ የአኩሪ አተር ኢንዱስትሪ ወደ መገንባት ገብተዋል፣ እንደ ምእራባውያኑ ለከብቶች ቀለብ የሚሆን የሳር መሬት ከማልማት ይልቅ፡፡(12)


አፍዲኤ የሰጠው የጤና እውቅና ጥያቄ ውስጥ


በኦክቶበር 25፣ 1999 የአሜሪካ መድሃኒትና ምግብ ባለስልጣን (ኤፍዲኤ) “በታጨቀ ስብ (ሳቹሬትድ ፋት) እና ኮሌስትሮል ዝቅተኛ የሆኑ” በአንድ ጊዜ ሲቀርቡ 6.25 ግራም የአኩሪ አተር ፕሮቲን የሚይዙ ምግቦችን ለጠየና ተስማሚ የሚል እውቅና ለመስጠት ይስማማል፡፡ የቁርስ ሲርያሎች፣ የተጋገሩ ምርቶች፣ የሚመቹ የሽያጭ ምግቦች፣ የሥጋ ቅያሪዎች ለልብ እና የደም ቧንቧ (ካርድዮ ቫስኩላር) ጤና ጠቃሚ ናቸው የሚል ማስታወቅያ ሊለጠፍባቸው ይችላል ማለት ነው፣ እነዚህ ምርቶች በመቶ ግራም ማዕድ ውስጥ አንድ ማንኪያ የአኩሪ አተር ፕሮቲን ብቻ እንዲኖራቸው ይጠበቃል፡፡
ለጤና ጠንቅ የሆነን ምግብ የምትሸጥበት ምርጡ መንገድ ለጤና ተስማሚ ነው ብለህ ነው፡፡
“ከኤፍዲኤ እውቅና ለማግኘት የተሄደበት መንገድ” ይላል አንድ የአኩሪ አተር አቀንቃኝ (አስተባባይ)፣ “ረዥም እና አድካሚ ነበር፣ ላለፉት 20 ዓመታት በሰው ላይ ምርምር የተደረገበት የክሊኒክ መረጃ ተይዞ በተደረገ ጥልቅ ትንተና ነበር፡፡ የአኩሪ አተር ፕሮቲን እጅግ ጥቂት ከሆኑት ለኤፍዲኤ የጤና እውቅና ለማግኘት በቂ ሳይንሳዊ መረጃ ያለው ብቻ ሳይሆን በመጨረሻም ከባድ የሆነውን የእውቅና ሂደት ለማለፍ የበቃ ነው፡፡”(29)
እንዲያውም ወደ ኤፍዲኤ እውቅና ማግኛ የወሰደው “ረዥም እና አድካሚ” መንገድ በመሃል ያልተጠበቁ ቅያሶችን ተጠማዟል፡፡ በፕሮቲን ቴክኖሎጂ ኢንተርናሽናል ድርጅት መጀመርያ ላይ የገባው ዋናው የእውቅና ይሰጠን ጥያቄ ወረቀት፣ አይዞፍሌቮኖች ለጤና ተስማሚ ናቸው የሚል ጥያቄ ነበር፡፡ አይዞፍሎቮን እንደ ኢስትሮጅን [የሴቶች ሆርሞን] አይነት ባሕርይ ያለው በአኩሪ አተር ውስጥ በስፋት የሚገኝ ንጥረ ነገር ነው፡፡ ጥያቄውም የቀረበው “አይዞፍሎቮኖቹ እንዳይጠፉ ተደርጎ የተነጠረ የአኩሪ አተር ፕሮቲን ብቻ ነው ኮሌስትሮል እንዲቀንስ የሚያደርግ፡፡” የሚል ነበር፡፡  
በ1998 ኤፍዲኤ የጠያቂው ድርጅት ወረቀትን ተሰምቶ በማይታወቅ ሁኔታ በማረም፣ ፋይቶ-ኢስትሮጅን የሚጠቅሱ መስመሮችን በመሰረዝ እና ጥያቄው ለአኩሪ አተር ፕሮቲንን የሚመለከት አደረጉት፡፡ ይህ ተግባር የባለስልጣኑ መመርያ ውጭ የተፈጸመ ነበር፡፡ ኤፍዲኤ በቀረበለት ወረቀት ላይ ፍርዱን ይሰጣል እንጂ የማረም ስልጣን የለውም፡፡
እንዲህ ሳይታሰብ እንዲቀይሩት ያስገደዳቸው በርከት ያሉ ተመራማሪዎች፣ የአሜሪካ መንግስት የቀጠራቸው ሳይንቲስቶች ሳይቀሩ፣ አይዞፍሌቮኖች መርዝ መሆናቸውን የሚያሳዩ ወረቀቶች ስላስገቡ ነው፡፡
ኤፍዲኤ ቀደም ብሎ በ1998 የእንግሊዝ መንግስት ፋይቶኢስትሮጅን ላይ የሰራውን የመጨረሻ ዘገባ ደርሶት ነበር፣ ዘገባውም ብዙም ጥቅም ያላገኘበት ሲሆን እንዲያውም ሌላ ከባድ ጉዳት እንደሚኖረው አስጠንቅቋል፡፡(30)
እውቅናው ወደ ከአኩሪ አተር የተነጠለ ፕሮቲን ቢቀየርም እንኳ “ከባድ የሆነውን የእውቅና ሂደት” ላይ የተሳተፉት የኤፍዲኤ ቢሮክራቶች ስለ መዓድናት አጋቾቹ፣ ኢንዛይም አጋቾቹ፣ ጎይትሮጅን፣ ኢንዶክራን ማወኩ፣ ስነ ተዋልዶ መዘዙ፣ እየናረ ያለው አለርጂ አስከታይነቱ የሰጠው ምልከታ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡(31)
ከሁሉ ጠንከር ያለው የተቃውሞ ደብዳቤ የመጣው ከዶ/ር ዳን ሺሃን እና ከዶ/ር ዳንኤል ዶርጅ ነው፣ በመንግስት ስር የብሔራዊ የመርዛማነት ምርምር ማእከል (National Center for Toxicological Research) ውስጥ ተመራማሪዎች ናቸው፡፡(32) የማሳሰብያ ጽሑፎች በምርቶቹ ላይ እንዲለጠፉ መጠየቃቸው አላስፈላጊ ብለው ትተዋቸዋል፡፡
ኮሌስትሮል መጠን ይቀንሳል ለሚባለው “በቂ ሳይንሳዊ መረጃ” የመጣው በ1995 ዶ/ር ጄምስ አንደርሰን ካደረገው ሜታ-ትንታኔ ነው፡፡ ትንታኔውን የደጎመው ፕሮቲን ቴክኖሎጂስ ኢንተርናሽናል ሲሆን የታተመው ደግሞ በኒው ኢንግላንድ ጆርናል ኦፍ መዲስን ነው፡፡(33)
ሜታ-ትንተና ማለት በአንድ ርእስ ላይ የተደረጉ ብዛት ያላቸው ክሊኒካዊ ጥናቶች ዳሰሳ እና ማጠቃለያ ማቅረብ ማለት ነው፡፡ አጠቃላይ ድምዳሜ ላይ ለመድረስ ሜታ-ትንታኔን መጠቀም ከሳይንስ ማህበረሰቡ ከፍተኛ ትችት ይደርስበታል፡፡
“በጥብቅ ሙከራዎች ምትክ ሜታ-ትንተና የሚተኩ ተመራማሪዎች የተሳሳተ መላ ምት የመስጠት እና የፈጠራ ስሌት የማስቀመጥ ስህተት ውስጥ ሊገቡ ይችላሉ፡፡” ይላል የኒውዝላንድ ሮያል ሶሳይቲ ፕሬዚደንቱ ሰር ጆን ስኮት፡፡ “ተመሳሳዮች አይደሉም የሚጣበቁት፡፡ በመረጃ ስብስብ ትንሽም ትልቅም ያላቸው ምርምሮች በተለያዩ ቡድኖች አንድ ላይ እየተደባለቁ ነው፡፡”(34)
አሁን ደግሞ በአንዳንድ ተመራማሪዎች ዘንዳ በተለይ እንደ ፕሮቲን ቴክኖሊጂስ ኢንተርናሽናል ዓይነቱ ድርጅት የሚደጎሙት በትንተናቸው የሚፈለገው ድምዳሜ ላይ ከመድረስ የሚያግዱ ጥናቶችን የመተው አዝማምያ ይስተዋላል፡፡ ዶ/ር አንደርሰን ስምንት ጥናቶችን በተለያየ ምክንያት ወደ ጎን ብሏል፣ ሃያ ዘጠኝ ብቻ አካቷል፡፡
ያሳተመው ዘገባ የኮሌስትሮል መጠናቸው ከ 250 mg/dl በላይ የሆኑ ግለሰቦች “በወሳኝ ደረጃ” ከ7 እስከ 20 መቶኛ ድረስ የሴረም ኮሌስትተሮል መጠናቸው እንደሚቀንስላቸው ይናገራል፣ የእንስሳት ፕሮቲንን በአኩሪ አተር ፕሮቲን ከተኩት፡፡ የኮሌስትሮል መጠናቸው ከ 250 mg/dl በታች ለሆኑ ብዙም አልቀነሰላቸውም፡፡ 
በሌላ አነጋገር ለአብዛኞቻችን ሥጋ መተዋችን ያን ያህል የደም ኮሌስትሮላችንን አይቀንስልንም ማለት ነው፡፡ “በሰው ላይ ምርምር የተደረገበት የክሊኒክ መረጃ ተይዞ በተደረገ ጥልቅ ትንተና” በኋላ እውቅና የሰጠው የኤፍዲኤ ማረጋገጫ ሸማቾች ይህን ወሳኝ ነጥብ ማስታወሱን የዘነጋ ነው፡፡
የሞለኩዊላር ሕክምና ምርምር መርሃ ግብር እና የለውረንስ በርክለይ ብሔራዊ ላቦራቶሪ ሐላፊ የሆነው ሮናልድ ኤም. ክራውስ (ኤምዲ) አኩሪ አተርን ከኮሌስትሮል መጠን መቀነስ ጋር የሚያያይዙት ምርምሮች “እጅግ በጣም እንጭጭ” ደረጃ ያሉ ናቸው ይላል፡፡(35) በዚሁ ላይ እንደሚከተለው ማከል ይችል ነበር፡ በምግብ ወይም በመዳኒት ኮሌስትሮል መጠን ለመቀነስ በሚደረጉ ጥናቶች ለማነፃፀር ከሚቀመጡት መሞከርያዎች (ኮንትሮል ግሩፕ) ይልቅ ሙከራው የሚደረግባቸው ላይ ይበልጥ ሞት የሚደርስ መሆኑን - ሞቱም በድንገተኛ ጥቃት (ስትሮክ)፣ ነቀርሳ፣ የአንጀት መታመም፣ አደጋዎች፣ እና እራስን ማጥፋት ናቸው፡፡(36)
በሃገረ አሜሪካ ኮሌስትሮል ለመቀነስ በሚደረግ እንቅስቃሴ በአመት 60 ቢሊዮን ዶላር የሚፈስበት ኢንዱስትሪ እንዲነሳ አድርጓል፣ ሆኖም ግን ከዚህ ከሚመጣው የልብ ህመም ወረርሽኝ ህዝቡን አልታደገም፡፡


አኩሪ አተር እና ነቀርሳ (ካንሰር)


በአዲሱ የኤፍዲኤ መመርያ መሰረት በማንኛውም ምግብ ላይ ነቀርሳ ይከላከላል ብሎ መለጠፍ ይከለክላል፣ ሆኖም ግን ይህ መመርያ በአኩሪ አተር ኢንዱስትሪ ያሉት ሻጮች በማስተዋወቅያ ጽሑፎቻቸው ላይ እንዲሁ ከማለት አላገዳቸውም፡፡ 
“ልብን ከመጠበቁም በላይ፣” ይላል የቫይታሚን ኩባንያ በራሪ ወረቀት፣ “አኩሪ አተር ከፍተኛ የፀረ-ነቀርሳ ጥቅሞች አሉት …፡፡ ጃፓኖቹ ከሰሜን አሜሪካውያን 30 እጥፍ በላይ አኩሪ አተር የሚበሉት፣ ዝቅተኛ የጡት፣ የማሕፀን እና የፕሮስቴት ነቀርሳዎች ክስተት ይታይባቸዋል፡፡”(37)  
እርግጥ ነው ዝቅተኛ ነው፡፡ ሆኖም ግን ጃፓኖቹ እና ኤስያውያኑ ባጠቃላይ በሌላ የነቀርሳ ዓይነት በተለይ የኢሶፈገስ፣ የሆድ፣ የጣፊያ እና የጉበት ነቀርሳ በከፍተኛ መጠን ይጠቃሉ፡፡(38) ኤስያውያ በመላው ዓለም ደግሞ ከፍተኛ የታይሮይድ ነቀርሳ አለባቸው፡፡(39) በብልት አካባቢ (ፕሮስቴት) የሚነሳ ነቀርሳ ዝቅተኛ ደረጃ መሆኑ አኩሪ አተር በመብላት ነው ከተባለ ከፍተኛ የታይሮይድ እና የምግብ መፍጫ አካላት ይበልጥ በነቀርሳ መጠቃታቸው ተጠያቂነቱን ለአኩሪ አተር ማድረግ ውጤቱ ይሆናል፡፡ በተለይም ደግሞ ምርምር በተደረገባቸው የላቦራቶሪ አይጦች ላይ አኩሪ አተር እኚሁኑ ነቀርሳዎች አስከትሎባቸዋል፡፡
ኤስያውያኑ ግን ምን ያህል አኩሪ አተር ነው የሚመገቡት? በ1998 በተደረገ ጥናት በመሃከለኛው በጃፓን ውስጥ የሚወሰደው የአኩሪ አተር ፕሮቲን መጠን 8 ግራም ለወንዶች 7 ግራም ለሴቶች ከሁለት ማንኪያ በታች ሆኖ አግኝቶታል፡፡(40) ዝነኛው የኮርኔል የቻይና ጥናት የባቄላ ዘር (ለጉሜ) አወሳሰድ በቀን ከ 0 እስከ 58 ግራም እንደሆነና መሃከለኛው 12 መሆኑን አሳይቷል፡፡(41)
ከሚመገቡት የባቄላ ዝርያ ውስጥ ሁለት ሶስተኛው አኩሪ አተር ነው ብንል፣ በከፍተኛ መጠን ሊወስዱት የሚችሉት 40 ግራምና ከዛ በታች ነው፣ ወይም በቀን ከሥስት ማንኪያ በታች ማለት ነው፣ በመሃከለኛው ስሌት ደግሞ ስንቆጥር ወደ ዘጠኝ ግራም ይሆናል ወይም ከሁለት ማንኪያ በታች፡፡ በ1930ዎቹ በተደረገ ጥናት በቻይኖች ማዕድ አኩሪ አተር 1.5 መቶኛ የካሎሪ ምንጭ ድርሻ ነበረው፣ ከአሳማ የሚያገኙት ካሎሪ 65 መቶኛ ነበር፡፡(42) (ኤስያውያን በባሕላቸው ምግብ የሚያበስሉት በአትክልት ዘይት ሳይሆን በአሳማ ቅባት ነው!)
በባሕላዊ ልማድ በኤስያውያን ማዕድ የተዘፈዘፈ (የተጠነሰሰ / ፈርመንትድ የሆነ) የአኩሪ አተር ውጤት ጣፋጭ እና ለኤስያውያን ማዕድ የሚያስፈልጉ ንጥረ ምግቦችን ሊያስገኝላቸው ይችላል፡፡ ሆኖም ግን በድርቅ ጊዜ ካልሆነ በስተቀር ኤስያውያን እጅግ በጣም ትንሽ አኩሪ አተር ነው የሚመገቡት፣ እርሱም እንደማባያ ነው እንጂ እንደ እንስሳት ተዋጽኦ ምትክ አድርገው አይወስዱትም፣ ከአንድ ሁኔታ በስተቀር፡፡ ቅጠል በል ሁነው በገዳማት የሚኖሩት የመነኑ ባሕታውያን የአኩሪ አተር ምግብ ምርጫቸው ነው፣ ምክንያቱም የወሲብ ጉልበታቸውን (ሊቢዶአቸውን) ያደነዝዝላቸዋል፡፡  
በኑትሪሽንና ካንሰር ላይ የታተመው የ1994 የማርክ መሲና ሜታ-ትንታኔ ነበር አኩሪ አተር ፀረ-ካንሰር አነሳሽ (አንቲካርሲኖጂን) ጠባይ አለው የሚለውን ውዝግብ ያስነሳው፡፡(43) መሲና በ26 እንስሳት ላይ በተደረገው ጥናት እንደተመዘገበው 65 መቶኛዎቹ የመከላከል ውጤት አሳይተዋል፡፡ በዚህ ትንታኔው ላይ ከማካተት የዘነጋቸው ጥናቶች ነበሩ ቢያንስ በአንድ በ1985 በራኪስ በተደረገ ጥናት አኩሪ አተር መቀለብ የጣፍያ ነቀርሳ ምክንያት ሆኖ ተገኝቷል፡፡(44) ባሰፈራቸው በሰው ላይ በተደረጉ ጥናቶች ውጤቶቹ የተዘባረቁ ናቸው ብሏል፡፡ [በዚህ ሁኔታ ነው አኩሪ አተር መመገብ የሚመከረው?]
ጥቂቶቹ የመከላከል ውጤት ቢያሳዩም አብዛኞቹ በአኩሪ አተር መመገብና በነቀርሳ መካከል ትስስር የሌለው መሆኑን የሚሳዩ ነበሩ፡፡ በመደምደሚያው ላይ “በዚህ ክለሳ መረጃ መሰረት አድርጎ አኩሪ አተር የነቀርሳ ስጋትን ይቀንሳል ብሎ መናገር አያስችልም፡፡” ሆኖም ግን በቀጣይ “The Simple Soybean and Your Health” በሚለው መጽሐፉ ላይ እንዲሁኑ የከለከለውን ድምዳሜ ይሰብካል፣ አንድ ኩባያ ወይም 230 ግራም የአኩሪ አተር ተዋጽኦ በቀን መመገብ ነቀርሳ ይከላከላል ይላል፡፡
በአሁኑ ጊዜ በሺዎች የሚቆጠሩ ሴቶች አኩሪ አተር ከጡት ነቀርሳ ይከላከለናል በማለት እየተመገቡት ይገኛሉ፡፡ ሆኖም በ1996 ዓ.ም በተደረገ ጥናት ከአኩሪ አተር የተነጠለ ፕሮቲን የሚመገቡ ሴቶች የሰውነት ውስጥ አካላት ሽፋን ህመም በሆነው ኤፒተልያል ሃይፐርፕላዝያ (epithelial hyperplasia) ፣ ለማዳን የማይቻል ሁኔታ ከመድረሱ በፊት በሚታይ ህመም የመያዝ እድላቸው ጨምሮ ተገኝቷል፡፡(45) ገንስታይን [የፋይቶኢስትሮጅን አይነት] ለማዕድ ሲውል የጡት ሴሎችን ወደ ሴል ኡደት እንዲገቡ እንደሚያነሳሳቸው ተደርሶነታል - ይህም ግኝታቸው የጥናቱ አዘጋጆች ሴቶች ከጡት ካንሰር እራሳቸውን ለመታደግ አኩሪ አተር መመገብ የለባቸውም ከሚል ድምዳሜ እንዲደርሱ አድርጓቸዋል፡፡(46)   

 
ፋይቶኢስትሮጅንስ፡ ዕጸ ሕይወት ወይስ ዕጸ ሞት?


በሃሩሩ ቀጠና ያሉት አእዋፋት የወንድ ዝርያዎቹ ሲወለዱ ብዙ የማይስበው የእናታቸው ቀለም ያለውን ላባ ይይዙና ካደጉ በኋላ በተራቸው ወላጅ ሊሆኑ ሲሉ በዘጠኝ እና 24 ወር መሃከል ገደማ ቀለም ማውጣት ይጀምራሉ፡፡
በ1991 ሪቻርዳ ቫለሪ ጄምስ ዋንገራይ፣ ኒውዚላንድ የሚገኙ ወፍ አርቢዎች፣ ለአእዋፋቶቻቸው አዲስ የቀለብ ዓይነት ገዙላቸው - በአኩሪ አተር ፕሮቲን የተገነባ፡፡ (47) አኩሪ አተር መሰረት ያደረገ ቀለብ ሲሰጣቸው በጥቂት ወራት ውስጥ ቀለም አወጡ፡፡ እንዲያውም አንድ የቀለቡ ዓይነቱ አዘጋጅ እንዲህ ፈጥኖ መድረስ የቀለቡ ውጤት መሆኑን የሚገልፅ ፅሑፍ ምርቱ ላይ ለጥፏል፡፡ 
የ1992 የሩዲቡሽ (Roudybush) ቀለብ ማስታወቅያ የአውስትራሊያው በቀቀን የላባው ቀለም ከ 18 እስከ 24 ወር ጊዜ ውስጥ የሚያወጣው በ 11 ሳምንት እድሜው እንዲያወጣ ያደርገዋል ብሎ ቃሉን ይሰጣል፡፡
የሚያሳዝነው ግን ቀጥሎ ባሉት አመታት የአእዋፋቱ የመራባት አቅም ቀንሶ ተገኝቷል፣ ቀድሞ ለወላጅነት አቅም መድረስ፣ የአካል ቅርጽ መበላሸት፣ ደቃቅና ደንዛዛ ጫጩቶች መውለድ፣ ያለእድሜያቸው መሞት፣ በተለይ በሴቶቹ ላይ ታይቷ፣ ይህም አጠቃላይ የሚያረቧቸው የእእዋፋት ቁጥር እንዲቀንስ አድርጓል፡፡
ወፎቹ የመንቁርና የአጥንት መበላሸት፣ እንቅርት፣ በሽታ የመከላከያ ስርአታቸው መዛባት እና ከሕመም የደረሰ የአስቸጋሪነት ጠባይ ተከስቶባቸዋል፡፡ የእህል መፍጫ የሰውነታቸው ክፍሎች ክፉኛ እንደተጎዱ በአካላታቸው ላይ የተደረገው ምርመራ አሳይቷል፡፡ በአእዋፋቱ የታዩት ችግሮች የነጄምስ ቤተሰብ በሁለቱ ልጆቻቸው ላይ በተመሳሳይ መልኩ ተከስተዋል፣ ልጆች በጨቅላነታቸው በአኩሪ አተር የተሰራ የሕጻናት ምግብ በልተው ነው ያደጉት፡፡
የተደናገጡትና የተናደዱት እነ ጄምስ መርዛማነት አጥኚውን (ቶክሲኮሎጂስቱን) ማይክ ፊትዝፓትሪክን (ፒኤች.ዲ) በጉዳዩ እንዲመራመር ቀጠሩት፡፡ ዶ/ር ፊትዝፓትሪክ በመስኩ ያሉትን ጽሑፎች አገላብጦ አኩሪ አተር ብዛት ካላቸው ሕመሞች እንደ መሃንነት፣ የነቀርሳ መጨመር፣ የሕፃናት ሊኩሚያ፣ ጋር ትስስር እንዳለው ደርሶበታል፣ በተጨማሪም ቀደም ብሎ በ1950ዎቹ(48) በተደረጉ ጥናቶች በአኩሪ አተር ያለው ገንስታይን በእንስሳት የኢንዶክራይን መታወክ እንደሚያመጣ ያሳያል፡፡ 
ዶ/ር ፊትዝፓትክ ለአእዋፋቱ የቀረበውን ቀለብ በመመርመር ከፍተኛ የፍይቶኢስትሮጅን በተለይ ገንስታይን ይዘት እንዳለው ለማወቅ ችሏል፡፡ የጄምስ ቤተሰብ በአኩሪ አተር ላይ የተመሰረተ ቀለብ መጠቀም ካቋረጡ በኋላ፣ ከጊዜ በኋላ አእዋፋቱ ወደ ጤናማ የእርባታ ልማድና ጠባይ ተመልሰዋል፡፡
የጄምስ ቤተሰቦች በአኩሪ አተር ስላለው መርዝ ሕዝቡንና የመንግስት ባለስልጣናትን ለማስጠንቀቅ የራሳቸው ዘመቻ ጀመሩ፣ በተለይም ደግሞ ኢንዶክራይን በሚያውኩት አይዞፍሌቮኖች ገንስታይንና ዲያሰዜን ላይ፡፡ ፕሮቲን ቴክኖሎጂ ኢንተርናሽናል የነጄምስን ወረቀት በ1994 እንዲደርሰው ተደርጓል፡፡
በ1991 የጃፓን ተመራማሪዎች ባደረጉት ጥናት በቀን 30 ግራም ወይም ሁለት መመገቢያ ማንኪያ የሚያክል አኩሪ አተር ለአንድ ወር መመገብ ታይሮይድ የሚያነቃቃ ሆርሞንን እንዲጨምር እንደሚያረግ አሳይተዋል፡፡(49) የእንቅርት መነፋትና ሃይፖታይሮዲዝም በአንዳንድ ሙከራው በተደረገባቸው ላይ የታየ ሲሆን አብዛኞቹ የሆድ ድርቀት (constipation) ድካም፣ መልፈስፈስ (lethargy) ታይቶባቸዋል የሚወስዱት አዮዲን መጠን በቂ ሆኖ ሳለ፡፡
በ1997 ከኤፍዲኤ የመርዛማነት ምርምር ብሔራዊ ማእከል የመጡ ተመራማሪዎች ለተቋሙ በሚያሳፍር መልኩ የአኩሪ አተር ጎይትሮጅኖች አይዞፍሎቮኖች መሆናቸውን ደረሱበት፡፡(50)
ሃያ አምስት ግራም የሚሆን ከአኩሪ አተር የተነጠለ ፕሮቲን፣ ፕሮቲን ቴክኖሎጂ ኢንተርናሽናል ኮሌስትሮል ይቀንሳል ያለው መጠን መሆኑ ነው፣ 50 እስከ 70 ሚሊ ግራም አይዞፍሌቮን ይይዛል፡፡ ባላረጡ ሴቶች ላይ በተደረገው ጥናት 45 ሚሊ ግራም አይዞፍሌቮን ብቻ በሰውነታቸው ታይሮይድ ትክክለኛ ሥራ የሚያስፈልገው ሆርሞን እንዲቀንስባቸው አድርጓል፡፡ እኚህ ተፅእኖዎቹ አኩሪ አተር መውሰድ እንዲቆም ከተደረገ በኋላ ለሦስት ወራት ያክል ጊዜ ተጽእኖው ሰውነት ውስጥ ነበር፡፡(51)
መቶ ግራም የአኩሪ አተር ፕሮቲን - ኮሌስትሮልን ለመቀነስ ጥሩ ነው ተብሎ ከተነገረው ከፍተኛው መጠን፣ በፕሮቲን ቴክኖሊጂስ ኢንተርናሽናል የሚመከረው መጠን - 600 ሚሊ ግራም አይዞፍሌቮን ሊይዝ ይችላል፣ (52) ይህ ሊካድ በማይችል መልኩ መርዛማ ይዘት ነው፡፡ በ1992 የስዊዝ ጤና አገልግሎት 100 ግራም የአኩሪ አተር ፕሮቲን በኢስትሮጂን ከወሊድ መከላከያ ኪኒን ጋር ተነፃፃሪ መሆኑን ተናግሯል፡፡(53)
በቫይትሮ (ከሕይወታውያን ሰውነት ውጪ በሚደረግ) ጥናት አይዞፍሌቮኖች የኢስትራዶይል መዋሃድን ከልክሏል፣ የስቴሮይድ መዋሀድንም እንዲ ከልክሏል፡፡(54) [ኢስትራዶል የኢስትሮጅን እጥረትና የጡት ነቀርሳን ለመዋጋት የሚጠቅም ተፈጥሯዊ የሴት ሆርሞን ሲሆን ስቴሮይድ ደግሞ የወሲብ አካላት እድገት ላይ ተጽእኖ ያለው ሆርሞን ነው፡፡] የስርአተ እርባታ ችግር፣ መሃንነት፣ የታይሮይድ ህመም እና የጉበት ሕመም በአይዞፍሌቮን መውሰድ (መመገብ) ምክንያት እንደሚከተል በተለያዩ የእንስሳት ዝርያዎች፣ በአቦ ሸማኔ፣ በጅግራ፣ በአሳማ፣ በአይጥ፣ በትልቅ አሳ (sturgeon)፣ እና በበግ ላይ ታይተዋል፡፡(55)
አኩሪ አተር ባረጡ ሴቶች ላይ ጥሩ ጥቅም አለው ይባላል፣  ፈጣን ትኩሳት (ሆት ፍላሽ) እና የአጥንት መሳሳት (ኦስትዮፖሮሲስ) ይከላከልላቸዋል ይባላል፡፡ ከፈጣን ትኩሳት የሚመጣውን ምቾት መጓደል በቁጥር ለማስቀመጥ እጅግ ከባድ ነው፣ በግለሰቡ ስሜት ላይ ስለሚመረኮዝ፡፡ አብዛኞቹ ጥናቶችም በተሰጠው አኩሪ አተር ልክ የፈጣን ትኩሳት መቀነስ ተመዝግቧል ይላሉ፡፡(56) አኩሪ አተር ኦስትዮፕሮሲስ ይከላከላል የሚለው ጥቆማ እጅግ የሚያስገርም ነው፣ የአኩሪ አተር ምግቦች ካልሺየም የሚያግዱና የቫይታሚን ዲ እጥሬት የሚፈጥሩ መሆናቸው የሚታወቅ ነውና፡፡
ኤስያውያን ከምእራባውያን በላቀ መልኩ ዝቅተኛ የኦስትዮፖሮሲስ ችግር ካለባቸው፣ ምግቦቻቸው በቂ ቫይታሚን ዲ ከሽሪምፕ (አሳ)፣ ከአሳማ እና የባሕር ምግቦች ስለሚያገኙና፣ በቂ ካልሺየም ደግሞ ከአጥንት ቅቅል (bone broths) ስለሚያገኙት ነው፡፡ በምእራባውያኑ ከፍተኛ የኦስትዮፖሮሲስ ክስተት ያለው በቅቤ ምትክ የአኩሪ አተር ቅባት ስለተጠቀሙ ነው፣ ቅቤ ደግሞ የቫይታሚን ዲ እና ካልሺየምን በሰውነታችን ለመምጥ የሚያስፈልጉ በስብ ውስጥ የሚሟሙ ማነቃቅያዎች አሉት፡፡


የወሊድ መቆጣጠርያ ኪኒን ለሕጻናት


ሆኖም ግን እነ ጄምስን እጅግ ያወካቸው በሕጻናት ምግብ የሚገኙት አይዞፍሌቮኖች ነበሩ፡፡ በ1998 ተመራማሪዎች ይፋ ባደረጉት መሰረት አካል-ክብደት መጠን መሰረት በማድረግ ሲሰላ አዋቂዎች አኩሪ አተር ሲበሉ የሆርሞን ተጽእኖ ይፈጥርባቸዋል ከሚባለው ሕጻናት ከሚመገቡት ምግብ ላይ ያለው አይዞፍሎቮን ከ 6 እስከ 11 እጥፍ ይዘት እንዳለው አሳውቀዋል፡፡ ለሕጻናት በሚሰጡ በአኩሪ አተር የተሰሩ ምግቦች በላም ወተት ለሕጻናት ከሚዘጋጀው ምግብ በፕላዝማ ኢስትራዶይል ይዘት በ 13,000 እስከ 22,000 እጥፍ ድረስ ይበልጣል፡፡(57)
በጡጦ ከሚመገቡ ሕጻናት በአሜሪካ 25 መቶኛ የሚሆኑት በአኩሪ አተር የተሰራ ይመገባሉ - ከምእራቡ አለም እጅግ ከፍተኛው ነው፡፡ ፊትዝፓትሪክ ባስቀመጠው ግምት መሰረት በአኩሪ አተር የተሰራ ምግብ ብቻ የሚመገብ ሕጻን (አካል-ክብደት መሰረት በማድረግ) ሲሰላ አምስት የወሊድ መከላከያ ውስጥ የሚገኝ ያህል ኢስትሮጅን ይወስዳል ማለት ነው፡፡(58) በአንጻሩ ግን ከላም ወተት ወይም ከሰው ወተት እናትየዋ አኩሪ አተር ብትመገብ እንኳ ምንም ዓይነት ፋይቶኢስትሮጅን አልተገኘባቸው፡፡ 
ለረዥም ዘመናት ሳይንቲስቶች በአኩሪ አተር የተሰሩ የህጻናት ምግቦች የታይሮይድ ችግር እንደሚፈጥር የሚያውቁት ጉዳይ ነው፡፡ የአኩሪ አተር ምርቶች ግን በሁለቱም ወንድና ሴት ሕጻናት የሆርሞን እድገት ላይ ምን ዓይነት ተጽእኖ ነው ያላቸው?
ወንዶች ሕጻናት “የቴስተስተሮን መጨመር” በሕይወታቸው መጀመርያ ወራት ይገጥማቸዋል፣ የቴስተስተሮን መጠናቸው የአዋቂ ወንዶችን መጠን ሊያክል ይችላል፡፡ በዚህ ወቅት ለጉርምስና (ፑበሪቲ) በሚደርስበት ወቅት የወንዴ ባሕርያት እንዲያሳይ ይሞላል በወሲባዊ አካላቱና ሌላ ተክለ ሰውነቱ ብቻ ሳይሆን በአእምሮውም የወንዴ ባሕርያት ቅርጽ እንዲፈጠር ይሞላል፡፡
በጦጣዎች የወንዴ ሆርሞን እጥረት የቦታ ግንዛቤ (spatial perception) እድገት እንዲጎዳ ያደርጋል፡፡ (በሰዎች ላይ ይህ ከሴቶች ይልቅ በወንዶች ላይ ጉዳቱ ይልቃል) ፣ የመማር ችሎታን ይጎዳል፣ እና የእይታ መለየት የሚደረጉ ሥራዎች (ለምሳሌ ለማንበብ እንደሚያስፈልገን አይነት) ይቀንሳል፡፡(59) በዚህ አይነት ሆርሞናዊ ድባብ አድጎ የመጪው እድሜ ዘመን የወሲብ ዝንባሌ (ምርጫ) ቅጥ ላይም ተጽእኖ ሊያሳድር እንደሚችል መናገር አያስፈልገውም፡፡
በማሕፀን እያሉ ለዳይታይልስቲልብስትሮለ (ዲኢኤስ) የተጋለጡ ወንድ ፅንሶች፣ ለጉርምስና በሚደርሱበት ወቅት ከጤናማው ያነሰ ፍሬ ነብስ ይኖራቸዋል፣ ዲኢኤስ ማለት በእንስሳት ላይ በተደረገ ሙከራ ከፋይቶኢስትሮጅን ጋር ተመሳሳይ ባሕርይ ያለው ንጥረ ነገር ነው፡፡(60)
[በአሜሪካ] ወንዶች ልጆች ትምህርት መቀበል አለመቻል (መደደብ) መስፋፋት ከወረርሽኝ ደረጃ ደርሷል፡፡ በስፋት አኩሪ አተር ለሕጻናት ምግብ ሆኖ መሰጠት የጀመረው በ1970 መጀመርያዎቹ ነው - ይህም ክስተት ለወረርሽኙ ሁኔታ ማብራርያ አይሆንም ተብሎ ማለፍ አይቻልም፡፡
ሴቶቹ ደግሞ በአስደንጋጭ ቁጥር የሚሆኑት ወደ አቅመ ሔዋን ከጤናማው እድሜ ክልል በጣም ቀድመው እየደረሱ ነው፣ ፔድያትሪክስ የሚባለው ጥናታዊ ሕትመት እንደዘገበው፡፡(61) ተመራማሪዎች ከአጠቃላይ ሴት ልጆች አንድ መቶኛ ሚሆኑት ጡት ማውጣት እና የኮረዳ ፀጉር ማውጣት የመሳሰሉትን የኮረዳነት ምልክቶች ሦስት ዓመታቸው ሳይሞሉ ማሳየት እየጀመሩ ነው፤ በስምንት አመታቸው ከነጭ ሴቶች 14.7 መቶኛ የሚሆኑት እና ደግሞ ከጥቁር ሴቶች ወደ 50 መቶኛ የሚጠጉት ከተጠቀሱት ሁለት ምለክክቶች አንዱን ወይም ሁለቱን ያሳያሉ፡፡
በስነ ምህዳሩ የሚለቀቁ ከባብያዊ ኢስትሮጂንስ እንደ ፒሲቢ እና ዲዲኢ (ከዲዲቲ የሚገኝ) ዓይነቶቹ በሴቶች ላይ ቀድመው ኮረዳ እንዲሆኑ ያደርጓቸዋል፡፡(62) በ1986 በተደረገ የፖርተ ሪኮ ያለ እድሜ ጡት መውጣት (Premature Thelarche) ጥናት እንደተገኘው ከሆነ ያለእድሜ ቀድሞ ወሲባዊ እድገት ማሳየት የሚመጣው በብዛት በመገናኛ ብዙሃን እንደሚነገረው ዶሮ ሳይሆን የህጻናት ከአኩሪ አተር የተሰራ ምግብ እንደሆነ ደርሶበታል፡፡(63)
ሕጻንነትን እንዲሁ ያለጊዜው በመቀጨቱ የሚመጣው መዘዝ እጅግ አሳዛኝ ነው፡፡ ሕጻናት ሴቶች ለአቅመ ሔዋን ሲደርሱ አዋቂዎች እንኳ መጋፈጥ የሚከብዳቸው ስሜቶች ጋር ዝግጁ ሊሆኑ በማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ ሁነው ለመጋፈጥ ይገደዳሉ፡፡ በሴቶች ልጆች ቀድሞ ለአቅመ ሔዋን መድረስ ኋላ ላይ በሕይወታቸው ከተዋልዶ ስርአታቸው ጋር በተያያዘ ለሚገጥማቸው ችግር አመላካች ነው፣ የወር አበባ መቋረጥ፣ መሃንነት እና የጡት ነቀርሳ ከችግሮቹ ይገኙበታል፡፡
እነ ጄምስ ቤተሰቦች ጋር የተገናኙ ሌሎች ልጆቻቸውን የአኩሪ አተር እያበሉ ያሳደጉ ወላጆች በልጆቻቸው የደረሰ የተለያዩ ችግሮችን አካፍለዋቸዋል፡፡ ፅንፍ የሚወጣ ስሜታዊ ባሕርያት፣ አስም፣ በሽታ የመከላከል አቅም መዳከም፣ የፒቱታሪ እጢ መዳከም (pituitary insufficiency) ፣ የታይሮይድ መታወክ፣ የሆድ እቃ መታወክ (irritable bowel syndrome) - ከነገሯቸው ችግሮች ይጠቀሳሉ፡፡ እኚህ ችግሮች እነ ጄምስ በሚያረቧቸው በቀቀኖች ላይም የታዘቧቸው ናቸው፡፡


የአውራዎቹ መከፋፈል


ሶስተኛው ዓለም አቀፍ የአኩሪ አተር አውደ ጥናት አዘጋጆች ጉባኤውን ሙሉ ለሙሉ ስኬታማ ነበር ለማለት አስቸጋሪ ይሆንባቸዋል፡፡ በአውደ ጥናቱ ሁለተኛ ቀን ተቀማጭነቱን ለንደን ያደረገው ፉድ ኮሚሽን እና የዋሽንግተን ዲሲው ዌስቶን ኤ. ፕራይስ ፋውንዴሽን ዓውደ ጥናቱ በሚካሄድበት ሆቴል የሕጻናት የአኩሪ አተር ምግብ ላይ ያላቸውን ስጋት ለማሳወቅ የራሳቸውን የጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ስብሰባ እያካሄዱ ነበር፡፡
የኢንዱስትሪው ተዋካዮች የተጨነቁ ሳይንቲስቶች እና ወላጆች በአኩሪ አተር የሚሰሩ የሕጻናት ምግቦችን ከገበያው እንዲወገዱ ሊያደርስ የሚችሉትን አደጋዎች ዝርዝር ሲቀርብ ደንዝዘው ሲከታተሉ ነበር፡፡ በእነ ጄምስ ቤተሰቦች ተጽእኖ ምክንያት የኒው ዚላንድ መንግስት በ1998 በአኩሪ አተር የሚሰራ የሕጻናት ምግብ ያለውን የጤና ጠንቅነት ማስጠንቀቅያ አውጥቷል፤ አሁን ደግሞ የአሜሪካ መንግስት እንዲሁ የሚያደርግበት ጊዜ ነው፡፡ [በሃገራችን የአኩሪ አተር ስጋት የሚነገርበት ጊዜው አሁን መሆን አለበት ኢንዱስትሪው ሳይፈረጥም፣ ሳይቃል በቅጠል፣ ማን ይሆን ህዝቡን ለማንቃት የሚንቀሳቀሰው፣ ሕዝቡ ከነቃ ባለስልጠናቱ ሊያወግዙት ይገደዱ ነበር፡፡]
በአውደ ጥናቱ የመጨረሻ ቀን ላይ የቀረበው ከመርዛማነት ጋር የተያያዘ መረጃ በምርቃና ውስጥ ለነበረው ጉባኤ መስበሪያ ነበር ሆነበት፡፡ ዶ/ር ሎን ዋይት በሃዋይ በሚኖሩ ጃፓን-አሜሪካውያን ላይ በተደረገ ጥናት በመጥቀስ ሁለት እና ከዛ በላይ በሳምንት የቶፉ ማዕድ መብላትና “የተፋጠነ የጭንቅላት ማርጀት” መሃከል ስታቲስቲካዊ ትስስር መኖሩ እንደተረጋገጠ ተናግሯል፡፡(64) 
በመሃከለኛ የእድሜ ዘመን ላይ ያሉ የምርምሩ ተሳታፊ ቶፉ ተመጋቢዎች በኋላ ሕይወታቸው ጊዜ የአእምሯቸው የመረዳት ችሎታ ዝቅተኛ መሆንና ከሌላው በላቀ መልኩ በአልዛይመር እና በአእምሮ መሳት (ዲመንሺያ) ሕመም ተይዘዋል፡፡ “በተጨማሪም” አለ ዶ/ር ዋይት “ቶፉ አብዝተው የተመገቡት በ75 ወይም 80 ዓመታቸው አምስት አመት ይበልጥ እድሜ ያላቸው መስለው ይታሉ፡፡”(65) [ይህ እየተባለ ያለው የአኩሪ አተር ኢንዱስትው ባዘጋጀው አውደ ጥናት መሃከል ነው፡፡] ዋይት እና አጋሮቹ ለአሉታዊ ጎኖቹ አይዞፍሌቮን ተጠያቂው እንደሆነ ተናግረዋል - ይህ አዲሱ ቃላቸውም ቀድሞ የተደረገው ያረጡ ሴቶች ከፍተኛ የኢስትሮጅን መዘዋወር በውስጣቸው ካለ የመረዳት ችሎታቸው ይቀንሳል የሚለውን የሚደግፍ ነው፡፡(66)
ዳንኤል ሺሃን እና ዳንኤል ዶርጅ የተባሉት ከብሔራዊ የመርዛማነት ምርምር ማእከል የመጡት ሳይንቲስቶች በአይጦች ላይ በተደረገ ጥናት መሰረት፣ በአኩሪ አተር ምግቦች የሚገኘው ገንስታይን ማዳን በማይቻል መልኩ የታሮይድ ሆርሞንን እንዲዋሃድ የሚያደርጉ ኢንዛይሞችን እንደሚጎዳ በመናገር የፕሮቲን ቴክኖሎጂስ ኢንተርናሽናልን ቀን አበላሹበት፡፡(67)
“በአኩሪ አተር መመገብና በእንቅርት መሃከል፣ በእንስሳትም በሰዎችም ዘንድ ረዥም ታሪክ አለው፣”  ይላሉ ዶ/ር ዶርጅ “በአሁኑ ጊዜ አኩሪ አተር ይሰጣቸዋል ለሚባሉ ጥቅሞች ማስረጃ ሲቀርብ ሊያደርስ ስለሚችለው አደጋ ሙሉ መረዳትም ያስፈልጋል፡፡”
ዶ/ር ክላውድ ሁገስ እንደዘገቡት ደግሞ ገንስታይን ከተቀለቡ አይጦች የተወለዱት ለንጽጽር ከተቀመጡት (ኮንትሮልስ) ያነሰ ክብደት አሳይተዋል፣ በወንዶቹ ደግሞ ለጉርምስና ቀድመው መድረስ ታይቷል፡፡(68) ምርምሩ እንዳሳወቀው ከሆነ በአይጦች ላይ የታየው “በትንሹ በሰው ልጆች ላይ ሊከሰት የሚችለውን አመላካች ነው፡፡” 
በጽንሱ ላይ አስደንጋጭ የቅርጽ መበላሸት ይደርሳል ማለት ላይሆን ይችላል ሆኖም ግን የነርቭ-ወ-ባሕርይ ቅጥ (neurobehavioral attributes) ፣ በሽታ የመከላከል ተግባራት፣ እና የፆታ ሆርሞኖች መጠን የመሳሰሉትን ሊያዛባ ይችላል፡፡ “ውጤቶቹ” ይላል ተመራማሪው “ምንም አለማለት ሊሆን ይችላል ወይም ደግሞ ትልቅ የስጋት ምንጭ ሊሆን ይችላል፣ እንደ ፆታ ሆርሞን የሚያደርግ ጠባይ ያለው ነገር እናት የምትበላ ከሆነ፣ የጨቅላው እድገት ላይ ለውጥ ያመጣ ይሆን ብሎ መጠየቁ መሠረተ እውነት የተከተለ ነው፡፡”(69)
እኚህ በጨቅላዎቹ ላይ ሊከሰቱ የሚችሉ ለውጦች ምን እንደሆኑ በጥር 2000 ዓ.ም የታተመው ቅጠል በል የሆኑ እናቶች የወለዷቸው ልጆች ላይ የተደረገው ምርምር አሳይቷል፡፡ ቅጠል በል የሆኑ እናቶች የሚወልዷቸው ልጆች በሃይፖስፓዲያስ፣ በውልደት ጊዜ የሚገኝ የወንድ ብልት እንከን፣ የመጠቃት እድላቸው አምስት እጥፍ ሆኖ ተገኝቷል፡፡(70) የጥናቱ ጸሐፊዎች በቅጠል በሌዎች ዘንድ ተወዳጅ የሆነው አኩሪ አተር ምግቦች ውስጥ የሚገኙት ፋይቶኢስትሮጅኖች በስፋት መጋለጥ እንደሆነ ገምተዋል፡፡
የቅጠል በል እናቶች ሴት ጨቅላዎች የሚገጥማቸው ችግር ወድያው ሳይሆን ይበልጡኑ ቆይቶ የመታየት እድል ያላቸው ናቸው፡፡ የአኩሪ አተር ኢስትሮጅናዊ ተጽእኖ ከዲያታይልስቲልቤስትሮል (ዲኢኤስ) ያነሰ ቢሆንም፣ በአጠቃላይ የሚወሰደው ይዘት ግን ሳይበልጥ አይቀርም ምክንያቱም በምግብነት ነውና የሚወሰደው፣ እንደ መድሃኒት አይደለም፡፡ በእርግዝና ወቅት ዲኢኤስ የወሰዱ እናቶች ልጆች በእድሜያቸው ሃያዎቹ ውስጥ ሲደርሱ ከመሃንነት እና ነቀርሳ ስቃይ ገጥሟቸዋል፡፡


ጥያቄ ምልክት በደህንነት መዓርጉ ላይ


ኢንዱስትው ለአኩሪ አተር ከፈጠረው ግዙፍ ምስል በስተጀርባ በምግብ ላይ ከአኩሪ አተር የተነጠለ ፕርቲን የመጨመር ተግባር በራሱ ህጋዊ ነው ወይ የሚል ወጥሮ የሚይዝ ጥቄ አለ፡፡ ከ1958 በፊት ጥቅም ላይ ያልዋሉ በምግብ ላይ የሚጨመሩ ኝጥረ ነገሮች ሁሉ የእውቅና መዓረግ ያስፈልጋቸዋል፣ ግራስ - GRAS (Generally Recognized As Safe) ይባላል፡፡ በ1972 የኒክሰን አስተዳደር የግራስ ማእረግ አላቸው ተብለው የሚታሰብ ንጥረ ነገሮችን ዳግም መረመረ፣ በወቅቱ ከነበረው ሳይንሳዊ መረጃ አንጻር፡፡
ይህን ዳግም ፍተሻ ካዚን (casein) ፕሮቲንን [ከወተት የሚገኝ ፕሮቲን] ያካተተ ነበር፣ በ1978 የግራስ ማእረግን አገኘ፡፡ በ1974 ኤፍዲኤ ስለ አኩሪ አተር ፕሮቲን ጽሑፍ ተሰጠው፣ ምክንያቱም እስከ 1959 ድረስ በምግብነት አልዋለም ነበርና፣ እስከ 1970ዎቹ ድረስ እንኳ በስፋት አይታወቅም ነበር፣ በምግብ፣ መድሃኒት እና መዋብያ አዋጅ የግራስ እውቅና ቀድሞውኑ እውቅና ለማግኘት እንኳ ብቁ አልነበረም፡፡(71)
እስከ 1974 ድረስ የነበረው በፋብሪካ በተሰራ አኩሪ አተር ፕሮቲን ላይ ብዙ ፀረ-ንጥ ምግቦችን መዝግቦ የያዘ ነበር፣ ትራይፕሲን አጋቾቹን፣ ፋይቲክ አሲድ እና ገንስታይን ጨምሮ፡፡ ሆኖም ግን ኤፍዲኤ ሰፊ አጥፊ ጎኑን የሚያነሳውን የጽሑፍ ክለሳ ላይ የሚደረግ ውይይትን “በቂ በሆነ ሁኔታ ከተሰናዳ” ያስወግዳቸዋል በማለት ችላ ብሏል፡፡ 
ገንስታይን በአልኮል ሲታጠብ ሊወገድ ይችላል፣ ሆኖም ግን ይህ ወጪ የሚያስወጣ ሂደት ስለሆነ ሰሪዎቹ አይተገብሩትም፡፡ በኋላ ላይ በተደረጉ ጥናቶች ትራይፕሲን አጋቾች ሊወገዱ የሚችሉት ረዘም ላለ ጊዜ ሙቀት እና ግፊት በመጠቀም ብቻ መሆኑን አስረዱ፣ ሆኖም ግን ኤፍዲኤ አምራቾች ይህን እንዲያደርጉ ምንም አይነት አስገዳጅ ደንብ አላወጣላቸውም፡፡
ኤፍዲኤ ይበልጥ የጨነቀው በሚቀነባበርበት ወቅት የሚፈጠሩት መርዞች ናቸው፣ በተለይም ናይትራይቶች እና ላይሲኖአላናይን፡፡(72) በጥም ዝቅተኛ በሚባል መልኩ እስከ አንድ ሶስተኛ ግራም በቀን መውሰድ፣ እዚህ ውስጥ የሚገኙት እነዚህ ነቀርሳ አነሳሽ ንጥረ ነገሮች (ካርሲኖጅንስ) ምክንያት ለሕብረተሰቡ ጤነማ ጠንቅ ናቸው ተብሎ የግራስ እውቅና ማግኘት ተከልክሎ ኑሯል፡፡
የአኩሪ አተር ፕሮቲን በካርቶን ለሚሰሩ ሳጥኖች መስሪያ እንዲሆን እውቅና ነበረው፣ ይህም ፈቃድ እንዲቀጥል ተደርጓል፣ ምክንያቱም ተመራማሪዎች ከሳጥኑ ወደ ምግቦች ሊሸጋገር የሚችለው ናይትሬት ነቀርሳ ያሲዛል የሚለው ስጋት ትንሽ ነው በሚል ነው፡፡ የኤፍዲኤ ባለስልጣናት ለምግን የግራስ ማእረግ ከመስጠታቸው በፊት የደህንነት ማረጋገጫ ትእዛዞችና የቁጥጥር አካሄዶች ያስቀምጡ ነበር፡፡
እኒህ ቅድመ ሁኔታዎች እንዲሟሉ አልተደረገም፡፡ እስከዛሬዋ እለት ድረስ የአኩሪ አተር ፕሮቲን የግራስ እውቅና ያለው ለዚህ ውሱን ኢንዱስትሪያዊ የሆነ የምግብ እቃዎች ማሸጊያ ካርቱን ለመስራት ብቻ ነው፡፡ ይህም ማለት አምራቾች እንደ ምግብ ሊጠቀሙበት ወይም ምግብ ላይ ሊጨምሩት ሲፈልጉ ለገበያ ከማውጣታቸው በፊት የፈቃድ ሂደቶችን የማለፍ ግዴታዎች ይኖርባቸዋል፡፡
የአኩሪ አተር ፕሮቲን የሕጻናት ምግብ ሁኖ የመጣው በ1960ዎቹ መጀመርያ ላይ ነበር፡፡ ይህም አዲስና በፊት ለምንም አይነት ጥቅም ሲውል ምንም ዓይነት ታሪክ ያልነበረው ምርት ያደርገዋል፡፡ የአኩሪ አተር ፕሮቲን የግራስ ማእረግ ያልነበረው ቅድመ ገበያ የምርት ምርመራ / እውቅና ፈቃድ ያስፈልገዋል፡፡ ይህ አልሆነም አሁንም አልተደረገም፡፡ ለሕጻናት የሚቀመረው ከአኩሪ አተር የሚሰራው ምግብ ግብአት ደህንነቱ አስጊ አይደለም የሚል እውቅና የለውም፡፡  


ቀጣዩ አስቤስቶስ?


[አስቤስቶስ ለግንባታ የሚውል ከሲሚንቶ ጋር የሚቀላቀል ምርጥ ግብአት ሲሆን ሥራው ካለቀ በኋላ ግን ለተገልጋዮቹ የሳምባ ነቀርሳ ያተርፍላቸዋል፣ እንደ አውሮፓ ሕብረት ያሉት ጥቅም ላይ እንዳይውል አግደውታል]
“ከወረደለት ሰፊ ውደሳ ጀርባ … -ምንም እንኳ የማያጠራጥር ጥቅም ያለው ቢሆንም- አኩሪ አተር አንዳንድ የጤና ጠንቆችን ሊያስከትል ይችላል፣” ስትል ትጽፋለች ማሪያን ቡሮስ፣ ለኒው ዮርክ ታይምስ የምግብ አምድ ጸሐፊ የሆነችው፡፡ ከማንኛውም ጸሐፊ በላይ ቡሮስ ስለ ዝቅተኛ ስብ፣ ቅጠል በሌ ማእዶችን የምትጽፋቸው በርካታ አሜሪካውያንን በአኩሪ አተር ላይ ተመሰረቱ ምግቦችን ከሱፐር ማርኬት መደርደርያዎች እንዲለቅሙ አድርጓቸዋል፡፡ 
በጥር 26፣ 2000 ዓ.ም የጻፈችው "Doubts Cloud Rosy News on Soy" የሚለው አምዷ ግን እንደሚከተለው የማስጠንቀቅያ መልእክት የያዘ ነበር፡ “እዚህ ከቀረቡት 18 ሳይንቲስቶች አይዞፍሌቮኖች ከስጋት ነጻ ናቸው ለማለት ፍቃደኛ የሆነ አልነበረም፡፡” ሙሮስ ስጋቶቹ ምን እንደሆኑ አልዘረዘረችም፣ እንዲወሰድ የተመከረው በቀን 25 ግራም አኩሪ አተርም ስስ ለሆኑ ግለሰቦች ስጋት ለመሆን በቂ አይዞፍሌቮኖች ይይዛል ወይ ስለሚለውም ያለችው ነገር አልነበረም፣ ሆኖም ግን ይህ የሚያመላክተን ኢንዱስትሪው ቀድሞ እራሱን መከላከል መጀመር እንዳለበት እንዳሰበ ያስረዳል፡፡
ኢንዱስትሪው በጣም ስለተጋለጠ … የወደፊት ሥጋት (የተጠንቀቅ) ጠበቆች ከሳሽ ሊሆኑ የሚችሉ ተጎጂዎች ቁጥር በሚሊዮኖች እንደሚቆጠርና ከፍተኛ ወጪ እንደሚያስወጣ የሚደርሱበት ጉዳይ ነው፡፡ ጥፋተኝነት ወሳኞች (ጁሪስ) እንደሚከተለው ያለ ነገር ይሰማሉ፡
“ኢንዱስትሪው አኩሪ አተር ብዙ መርዞችን እንደሚይዝ ለዓመታት ያውቅ ነበር፡፡
“መጀመርያ መርዞቹ በማጥራት ሂደት ተወግደዋል ብለው ለህዝብ ነገሩ፡፡ የማጥራት ሂደቱ የማያስወግዳቸው መሆኑ ሲታወቅ ጊዜ እኚህ ንጥረ ነገሮች ጥቅም አላቸው በሚል መከራከር ጀመሩ፡፡ መንግስታችሁ [የአሜሪካ] መርዛማ ለሆኑ ንጥረ ነገሮች ለጤና ተስማሚ የሚል ማረጋገጫ ሰጠ፣ ኢንዱስትሪው ደግሞ ተጨማሪ አኩሪ አተር ለመሸጥ ሕዝቡን ዋሸ፡፡”
“ኢንዱስትሪ” ሲባል ነጋዴው፣ አምራቾቹ፣ ሳይንቲስቶቹ፣ ሕዝብ ግንኙነት ሰራተኞቹ፣ ቢሮክራቶቹ፣ የቀድሞ የአረቡን ነጋዴዎች፣ ስነ ምግብ ጸሐፍት፣ የቫይታሚን ድርጅቶች እና ቸርቻሪዎቹን ሁሉ ያካተተ ነው፡፡ ገበሬዎች የማምለጥ እድል ይኖራቸው ይሆናል ምክንያቱም እነርሱም እንደኛው ተታለው ይሆን ይሆናል፡፡ ሆኖም ግን ነገሩ ከመገንፈሉ በፊት ሌላ የሚተክሉት ነገር በፍጥነት መፈለግ ይኖርባቸዋል፡ ሳር የሚበሉ ከብቶች፣ ጤናማ አትክልቶች … ወይም በእልፍ አእላፍ የሚቆጠር የክስ መዝገብ መጻፍያ የሚሆን ወረቀት መሥሪያ እንዲሆን ቃጫ ቢተክሉ ጥሩ ነው፡፡
ከኔክሰስ መጽሔት ተወሰደ፡
Nexus Magazine, Volume 7, Number 3 (April-May 2000)

ስለ ጸሐፊዎቹ፡


ሳሊ ፋሎን (Sally Fallon) Nourishing Traditions: The Cookbook that Challenges Politically Correct Nutrition and the Diet Dictocrats (1999, 2nd edition, New Trends Publishing, tel +1 877 707 1776 or +1 219 268 2601) የተባለው መጽሐፍ ደራሲና የዌስቶን ኤ. ፕራይስ ፋውንዴሽን (Weston A. Price Foundation, Washington, DC (www.WestonAPrice.org) ፕሬዚደንት ነች፡፡
ሜሪ ጂ. ኢንግ ፒኤች.ዲ. (Mary G. Enig, Ph.D.) በተለይ በስብ እና ቅባት ላይ በምታደርገው ምርምር የምትታወቅ የኑትሪሽኒስት ነች፣ አማካሪ፣ ክሊኒሺያን እና Nutritional Sciences Division of Enig Associates, Inc., Silver Spring, Maryland ዳይሬክተር ነች፡፡
የዶክትሬት ዲግሪዋን ያገኘችው በስነ ምግብ ሳይንሶች (Nutritional Sciences) ከሜሪላንድ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ፓር በ1984 ዓ.ም ነው፡፡ ለዩኒቨርሲቲው የስነ ምግብ ሳይንሶች ለመጀመርያ ተመራቂ ተማሪዎች ንጥረ ምግቦችና መድሃኒት ትስስር ያስተማረች ሲሆን፣ ከ1984 እስከ 1991 ድረስ የፋኩልቲ (ትምህርት ዘርፍ) ምርምር አጋርነት ቦታን ይዛለች፣ በኬሚስትሪና ባዮኬሚስትሪ ዲፓርትመንት (ትምህርት ክፍል) ውስጥ ከሊፒድስ ምርምር ቡድን ጋር፡፡  
የአሜሪካ የስነ ንጥረ ምግብ ኮሌጅ አጋር (ፌለው) ነች፣ የአሜሪካ የሥነ ምግብ ኢንስቲትዩት አባል ነች፡፡ በረዥም ዓመታት የምግብ ስብ እና ቅባት ምርመራ ዘመኗ እንደ “ተቀያሪ ኬሚስትነቷ” በፉደራልና ክልል መንግስታት የምግብ ደረጃና ይዘት ውሳኔ ላይ ሚና እንዲኖራት መሰረት ሁኗታል፡፡ 
ዶ/ር ኢንግ "Journal of the American College of Nutrition" የተባለው የምርምር ሕትመት አማካሪ አዘጋጅ (ኤዲተር) ስትሆን "Clinical Nutrition" ደግሞ ጽሑፏን የምታበረክት ኤዲተር ነች፡፡ የምግብ ስቦችና ቅባቶች በተመለከተ 14 ሳይንሳዊ ወረቀቶች ያሳተመች ሲሆን ለተለያዩ መጻሕፍት የሥነ ምግብ ምእራፎችን ጽፋለች፣ በተጨማሪም ስለ ምግብና ንረ ምግብና በተመለከተ ከ 35 በላይ ሳይንሳዊ ወረቀቶችን አበርክታለች፡፡
Maryland Nutritionists Association ፕሬዚደንት ስትሆን፣ Coalition of Nutritionists of Maryland የቀድሞ ፕሬዚደንት ነበረች፣ በተጨማሪም በ1986 በሜሪ ላን ገዢ የሜሪላንድ መንግስት የስነ ምግብ መማክርት አባል የተደረገች ሲሆን የጤና ንኡስ ኮሚቴም ሊቀ መንበር ሁና አገልግላለች፣ መማክርቱ በ1988 እስኪበተን ድረስ፡፡

ምስጋና ይድረስ ለእንስቱ ሊቃውንት፡
እጅግ አስፈላጊ የሆነውን ይን የአኩሪ አተር መረጃ ስላቀረባችሁ እናመሰግናለን፡፡ አንድ ሰው አኩሪ አተርን ከቤቱ ማእድ ማራቅ እንደሚገባው የሚስረዳ በቂ መረጃዎችን አሳይተውናል፡፡ ይህ በጣም ትልቅ ሥራ ነው የሚመለከተው ሁሉ አርአያቸውን በመከተል የሚገባውን ትኩረት እንዲያገኝ ይህን መረጃ ያሰራጭ፡፡ በግሌ የድርሻዬን አበርክቼ ጨርሻለው፡፡
[ተጨማሪ መረጃ]
http://www.westonaprice.org/soy-alert/studies-showing-adverse-effects-of-soy
http://www.westonaprice.org/soy-alert/studies-showing-adverse-effects-of-isoflavones
ማጣቀሻዎቹ፡
1. Program for the Third International Symposium on the Role of Soy in Preventing and Treating Chronic Disease, Sunday, October 31, through Wednesday, November 3, 1999, Omni Shoreham Hotel, Washington, DC.
2. Houghton, Dean, "Healthful Harvest", The Furrow, January 2000, pp. 10-13.
3. Coleman, Richard J., "Vegetable Protein - A Delayed Birth?" Journal of the American Oil Chemists' Society 52:238A, April 1975.
4. See www/unitedsoybean.org.
5. These are listed in www.soyonlineservice.co.nz.
6. Wall Street Journal, October 27, 1995.
7. Smith, James F., "Healthier tortillas could lead to healthier Mexico", Denver Post, August 22, 1999, p. 26A.
8. "Bakery says new loaf can help reduce hot flushes", Reuters, September 15, 1997.
9. "Beefing Up Burgers with Soy Products at School", Nutrition Week, Community Nutrition Institute, Washington, DC, June 5, 1998, p. 2.
10. Urquhart, John, "A Health Food Hits Big Time", Wall Street Journal, August 3, 1999, p. B1
11. "Soyabean Milk Plant in Kenya", Africa News Service, September 1998.
12. Simoons, Frederick J., Food in China: A Cultural and Historical Inquiry, CRC Press, Boca Raton, 1991, p. 64.
13. Katz, Solomon H., "Food and Biocultural Evolution: A Model for the Investigation of Modern Nutritional Problems", Nutritional Anthropology, Alan R. Liss Inc., 1987, p. 50.
14. Rackis, Joseph J. et al., "The USDA trypsin inhibitor study. I. Background, objectives and procedural details", Qualification of Plant Foods in Human Nutrition, vol. 35, 1985.
15. Van Rensburg et al., "Nutritional status of African populations predisposed to esophageal cancer", Nutrition and Cancer, vol. 4, 1983, pp. 206-216; Moser, P.B. et al., "Copper, iron, zinc and selenium dietary intake and status of Nepalese lactating women and their breastfed infants", American Journal of Clinical Nutrition 47:729-734, April 1988; Harland, B.F. et al., "Nutritional status and phytate: zinc and phytate X calcium: zinc dietary molar ratios of lacto-ovovegetarian Trappist monks: 10 years later", Journal of the American Dietetic Association 88:1562-1566, December 1988.
16. El Tiney, A.H., "Proximate Composition and Mineral and Phytate Contents of Legumes Grown in Sudan", Journal of Food Composition and Analysis (1989) 2:6778.
17. Ologhobo, A.D. et al., "Distribution of phosphorus and phytate in some Nigerian varieties of legumes and some effects of processing", Journal of Food Science 49(1):199-201, January/February 1984.
18. Sandstrom, B. et al., "Effect of protein level and protein source on zinc absorption in humans", Journal of Nutrition 119(1):48-53, January 1989; Tait, Susan et al., "The availability of minerals in food, with particular reference to iron", Journal of Research in Society and Health 103(2):74-77, April 1983.
19. Phytate reduction of zinc absorption has been demonstrated in numerous studies. These results are summarised in Leviton, Richard, Tofu, Tempeh, Miso and Other Soyfoods: The 'Food of the Future' - How to Enjoy Its Spectacular Health Benefits, Keats Publishing, Inc., New Canaan, CT, USA, 1982, p. 1415.
20. Mellanby, Edward, "Experimental rickets: The effect of cereals and their interaction with other factors of diet and environment in producing rickets", Journal of the Medical Research Council 93:265, March 1925; Wills, M.R. et al., "Phytic Acid and Nutritional Rickets in Immigrants", The Lancet, April 8,1972, pp. 771-773.