Thursday, February 23, 2012

«ክርስቶስን መምሰል»

  ‹‹ለእኔ ክርስትና ክርስቶስን ለመምሰል መጣር ነው››

በጋዜጣ ሻጩ ጐልማሳ ክንድ ላይ ከተደረደሩት የህትመት ውጤቶች መካከል ትኩረቴ ባረፈበት መሔት የፊት ገላይ ከቲያትር ባለሙያዋ ጀማነሽ ሰለሞን ጉልህ ምስል በታች የተፃፈውን “እኔ ክርስትና ክርስቶስን ለመምሰል የጣር ነው” የሚለው ዓ.ነገር እንዲያ ባለ ሁኔታ ደመቅ ብሎ ይሰፍር ዘንድ የቻለበትን ምክንያት ለመፈተሽ የመîሔቱን  የውስጥ ገጾች መግለጥ አስፈለገኝ፡፡ ይህንኑም ባደረኩ ጊዜ በውስጡ ከዚህ አባባል የማይተናነሱ ሃሳቦችን ማግኘቴ ሲገርመኝ ሰንብቶ ይህንን አደርግና እናገር ዘንድ ገፋፋኝ፡፡
ጀማነሽ ሰለሞንን የማውቃት ከሁለት አስርት ዓመታት በፊት እሷ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ቲያትር ጥበባት ዘርፍ ተማሪ በነበረችበትና እኔ ደግሞ ለዚያ ዘርፍ እንደ ቤተ-ሙከራ ሆኖ በሚያገለግለው በዩኒቨርስቲው ባህል ማዕከል አባል ሆኜ ሳለ ነው፡፡ በወቅቱ አብረዋት ከነበሩት እንስት ተማሪዎች በባህሪያቸው ልስልስ ሆነውልኝ ወዳጃዊ ቀረቤታን ከቸሩኝ የሻሽወርቅ በየነና ኤልሳቤጥ መላኩ በተቃራኒ ጀሜ ኮስተር ያለችና ኩሩ ቢጤ ስለነበረች ያንን ሁኔታ አልፌ ገንዘቤ አደርጋት ዘንድ የወቅቱ ስሜቴ ባይፈቅድልኝም ግና ልጅት በትምህርት ቤት ሳለችም ሆነ ወደ ሥራ ዓለም ከገባች በኋላ የተሰጥኦዋን ከፍተኝነት፣ ጉብዝናዋንና ሙያዊ ጥንካሬዋን ከሚያደንቁላት የጥበቡ አፍቃሪዎች አንዱ መሆኔን መካድ አልችልም፡፡

 ለእርሷ ወርቃማ በሚባሉት በነዚያ ዘመናት በኪነ-ጥበቡ ዓለም ላይ በተሰጥኦዋ ኃያልነት ነግሣ የነበረችው ሴት (ምንም እንኴ አሁንም ሙያዋን ብትወደው) ዛሬ ግን ከዚያ እጅግ በሚልቀው ሌላ ረቂቅ ጥበብ ላይ የማተኮሯንና የመመሰጧን ምስጢር ለማወቅ የጓጓ የሚመስለው የተወደደው ጋዜጠኛና ደራሲ ፀጋዬ ተ/ዓረጋይ ‹‹ፍልስምና›› በተሰኘው መፅሐፋም ሆነ መጋቢት ወር- 2002 .ም በወጣው ሮዝ መፅሔት ላይ ላቀረበላት እንደዚያ አይነቶቹ ጥያቄዎች ጀሜ በሰጠቻቸው ምላሾች፣ እውነቴ ለምትለው ክርስቶስ ያደረባትን ፍቅር፣ ትምክህትና ያለ ልክ መጓደድ የገለፀችበት መንገድ ለእኔ ከዚያ የተጨበጨበለት የኪነ ጥበብ ሰውነቷን በላይ ይሄኛው ምስሏ ገዝፎ እንዲታየኝ አድርጓል፡፡ መፅሐፍስ የዚህኛው ጥበብ (ክርስቶስ) ብልጫ ሲናገር ‹‹ጥበበኛ የት አለ? ጻፊስ የት አለ? የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እንዲሆን አላደረገምን? ይል የለምን? 1ቆሮ 120-21
እንግዲህም የጀሜ ቃለ ምልልስ በጌሤም የመደገሙ ሰበቡ ይኸው ብቻ ሲሆን እርሷ ስለ ህይወትና እውነት የምትመረምርበት መንገድም ሆነ የወል ግንዛቤዋን ከግላዊ መረዳቷን ጋር አጣጥማ ለመኖር የምታደገው ትግል በማህበረሰባችን ብዙም ያልተለመደ መሆኑ ይሄም ሌላኛው ምክንያት ነው፡፡ ከዚህ አንዳች ፋይዳ ሳይገኝ አይቀርምና እነሆ ከጋዜጠኛው ፀጋዬ ተ/ዐረጋይ ያደረገችው ቃለ ምልልስ እንደሚከተለው ሆኖ ቀርቧል፡፡
ጀምዬ አንቺና ስራዎችሽን በማስተዋወቅ ጊዜ ማባከን አያስፈልግም፣ ብዙዎች ሊያዩሽ ወይም ሊያደምጡሽ የሚፈልጉሽ አርቲስት እንደሆንሽ ይታወቅሻል?
ይሄን የሚመስል ነገር ካሁን በፊትም ጠይቀኸኛል፡፡ አዎን በህዝብ ውስጥ ጥሩ ተቀባይነት እንዳለኝ ይገባኛል፡፡ የኔ ተደራሲያን የምሰራውን የሚያደንቁ ይመስለኛል፡፡ እርሷ ካለችበት ጥሩ ሥራ ነው፡፡ የሚሉ ሰዎች እንዳሉ እሰማለሁ፡፡
ብዙ ጊዜ በሙያ ጉዳይ አማፂ ነሽ፡፡ ይታወቅሻል?
ትያትር ለኔ የረቀቀ ቁም ነገር ነው፡፡ ቁም ነገሩ ቀልድ ሲሆን ያመኛል፡፡ አንዳንዴ የምታየው እኮ ማበላሸት ነው፡፡ ከተመልካች ጋር መሳሳቅ በትያትር ፍፁም ክልክል የተባሉ ህግጋት ናቸው፡፡ አሁን ግን ነፍስ ዘርተውና መድረኩን ሞልተው የምታያቸው የድንገቴ ፈጠራዎች (Improvisation) ናቸው፡፡ ቲያትር ደራሲው አስቦ፣ ተጨንቆና ቀምሮ ላነሳው ሃሳብ ሆን ተብሎ በስሌት የሚሰራ ነው፡፡ ዛሬ ግን ጨዋታ ሆኗል፡፡ ይሄን ‹‹ተዉ›› ማለት እንደ ትልቅ ወንጀል የሚቆጠርበት ጊዜ ነው፡፡
በደራሲው ሥራ ላይ ሌላ ደራሲ የሚሆኑ ተዋንያንማ ሁሉንም መድረክ እየሞሉት ነው፡፡ ጥቂት መፍጠር ይችሉ ይሆናል ግን …
አአ … ጥቂቶቹም ቢሆኑ መፍጠር አይችሉም፡፡ ከቻሉ ራሳቸውን ችለው መፃፍ ነው ያለባቸው፡፡ አንድ መፅሔት ላይ ሳነብ በከተማው ‹‹የተወደደና የተደነቀ›› ተዋናይ ‹‹እኔ በቀቀን ነኝ እንዴ ሰው የሰጠኝን ቃል መልሼ የምደግመው?›› ብሎ በድፍረት ተናግሯል፡፡
ምን ማለት ነው ?
መድረክ ላይ እንደፈለኩ እፈጥራለሁ (Improvise አደርጋለሁ) ማለቱ ነዋ… ይሄም ቆሻሻ ምግባር ከፈጠራ እኩል ተከብሮ በአደባባይ የሚነገርበት ዘመን ላይ ተደረሰ … ተዋናዩ ደራሲ ከሆነ ‹‹ደራሲ›› የሚባል ድርሻ ለምን ኖረ? ማንም እንደሻው ሲሆን ሃይ የሚል የለም፡፡ … ‹‹እሷ ትቆጣለች፣ ኃይለኛ ናት፡፡ ማን አብሯት ይሰራል?›› ይላሉ እኔ አይደለሁም ኃይለኛ የቲያትር ህግ ነው፡፡
እውነት በድምፅ ብልጫ መዳኘት የማህበረሰቦችን ልማድ ነው፡፡ ለመለየት የሞከረ ይተኮስበታል፡፡ ከጥበቡ ውጭ በግልና በማህበራዊ ህይወትሽ ላይ ተፅእኖ አይኖርብሽም?
ይኖራል ይህ ግን የእኔ አቋም ነው፡፡ … ይህ የእኔ ዓለም ነው፡፡ ማረጋገጥ የምፈልገው አቋሜ ልክ መሆኑን እንጂ በዚያ የሚመጣውን መከራ መሸከም አያሳስበኝም፡፡
ህመሙ አይሰማሽም?
ይሰማኛል እንጂ እኔ መጀመሪያ ወደዚህም ዓለም ስመጣ የራሴን መንገድ ለመሄድ ነው፡፡ ትያትር ከመንገዶቼ አንዱ ነው ብዬ አስባለሁ እንጂ ‹‹እኔ ቲያትር ነኝ ወይም ትያትር ካልሰራሁ ሟምቼ አልቃለሁ›› ብዬ አላስብም፡፡  እኔ የራሴ እምነት አለኝ፡፡ በዚያ እምነት ልደርስ የምፈልግበት ግብ አለኝ፡፡ ዋናው ሕይወቴ እዚያው ላይ የተጠመደ ነው፡፡ ጥሩ ሆኖ ካገኘውት ሙያውን እወደዋለሁ፡፡ ሰራዋለሁ፡፡
‹‹እኔነቴ ልክ ነው?›› ብለሽ ትጠይቂያለሽ?
እኔንም በጣም እመረምረዋለሁ፡፡ ለእውነቱ መስፈርቱ ማንነው? የሚለውን እመረምራለሁ፡፡ እኔና አንተ ብንወዳደር ‹‹አንቺ ቀይ ነሽ›› ትለኛለህ፡፡ ፈረንጆቹ ሀገር ብንሄድ እኔ ጥቁር ነኝ፡፡ ፈራጅ ማን ነው? ማህበረሰቡ? የመንግስት ህግ? ጓደኞች? … ለእኔ የእውነት መልሱ መንፈሳዊ ህይወት ውስጥ የሚገኝ ይመስለኛል፡፡ በተቻለ መጠን ከክርስቶስ ትምህርት አለመውጣት ነው፡፡ የእኔ መስፈርቱ እሱ ነው፡፡ ከእሱ መራቄ ነው የሚያሳስበኝ፡፡ እውነት ለእኔ ክርስቶስ ነው፡፡
ወደ ሌላ የሀሳብ ጥግ እንሂድና ብዙ ጊዜ ወደ ገዳማት ትመላለሻለሽ ወደ ገዳማቱ ስትሄጂና ጉዳይሽን ጨርሰሽ ስትመለሺ በውስጥሽ የሚፈጠረው ለውጥ ምንድነው?
የራሴ የሕይወት ሙከራ አለኝ፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ምንድነው እውነት? የቱ ነው እውነት? ለየትኛው እውነት ነው መኖር ያለብን?…. ህይወት ምርጫ ነው፡፡ የሚስማማህን የምትመርጠው አንተ ነህ፡፡ ራስህን እየፈለክ፣ እውነቱን እየፈተሽክ ትሄዳለህ፡፡ እኔ የዚያ አካል ነኝ፡፡ በትያትርም፣ በእምነትም፣ በፍልስፍና ውስጥም ያንን እውነት ነው የምፈልገው… እዚያ ስሄድ ብቻ ሳይሆን መፅሐፍ ሳነብም ሆነ መድረክ ላይ ስወጣ ይህን ነው የምመረምረው … ለዓላማቸው ሲሉ ፍላጐታቸው መሰዋት የሚችሉ ሰዎችን አደንቃለሁ፡፡ ገዳምን የብርቱዎችና የጠንካሮች መኖሪያ ሥፍራ አድርጌ ነው የምቆጥረው፡፡ ገዳም ባትሄድም እነዚህን ነገሮች ችለህ በዓለም አትኖርም ማለት ግን አይደለም፡፡ ቃለ መጠይቁ ስብከቱ እንዳይሆንብህ እንጂ፡፡
የአንቺን እውነቶች እንድትገልጪልኝ ነው የተገናኘነው፡፡
መፅሐፍ ቅዱስ ሁለት ሲስተም እንዳለ ይናገራል፡፡አንዱ በዚህ ዓለም እኛ የምንገዛበት ሲሆን ሌላው ደግሞ የእግዚያብሔር የአገዛዝ ሲስተም ነው፡፡ ‹‹አባታችን ሆይ›› ስንል፣ ‹‹መንግስትህ ትምጣ›› እያልንም የምንፀልየው ለዚህ ነው፡፡ ጠባቡን ስትመርጥ ፈተና ይበዛዋል፡፡ መጨረሻው ግን ጥሩ ነው፡፡ ሌላው ደግሞ ሰፊ ነው፣ ብዙ ፈተና የለበትም፣ መጨረሻው ግን መጥፎ ነው፡፡ አንድ እግርን እዚህ ሌላውን እዚያ አድርገህ መኖር አይቻልም፡፡ ምርጫው አንድ ነው፡፡
አንቺ የቱን መረጥሽ?
ከዚህ በፊት ‹‹ፍልስምና›› መፅሐፍህ ላይ እንዳነሳነው እኔ ብዙውን ጊዜ የዚህ ዓለም ሲስተም አይስማማኝም፡፡ ዋጋዎቹ ውሸት፣ ቅጥፈት፣ ማስመሰል፣ተንኮል ናቸው፡፡ የጠባቡ መንገድ ህግጋት ደግሞ እውነት፣ ፍቅር፣ ሀቅ፣ ግልፅነት፣ ፊት ለፊት መኖር ናቸው፡፡ … እኔ የዚህኛው ሀገር ነዋሪ መሆን እፈልጋለው ካልክ ህጉን ማክበር ግዴታህ ነው፡፡ ሌላኛውም መብትህ ነው፡፡
በርግጥ ጠባቡን መንገድ መርጫለው ብለሽ ታምኛለሽ?
አዎን መርጫለው፡፡ ፍፁም ሆኛለው ስላላልኩ እርሱን ከእኔ አትጠብቅ፡፡ ቢያንስ ግን ጠባቡ መንገድ ላይ ነኝ፡፡ ልቤን የምከፍተው ለእርሱ ነው፡፡ እውነት እከተላለው፡፡ እስከማውቀው ድረስ እውነት ማለት ክርስቶስ ነው፡፡ ተቃውሞና ውዥንብር የሚያነሳብኝ ለዚህ ነው ብዬ አምናለው፡፡
ሰፊውን (ብዙዎች የመረጡትን) ዓለም አንቺ እንዴት ነው የምታይው
እንደነገርኩህ ነው፡፡ ዓለም ማለት ለእኔ በእሾህ ላይ እንደመረማመድ ነው፡፡ አለም መኖር የተመቻቸና የተደላደለ ነው የሚል ህልም የለኝም፡፡ ከዓለም ውስጥ የምፈልገው ደስታ የለኝም፡፡ ደካማ ነኝ፣ አቅመ ቢስ ነኝ፡፡ ግን በተቻለኝ መጠን ለማምንበት ነገር ለመኖር ሙጥን ብዬ ልይዘው የምፈልገው ክርስቶስን ነው፡፡ እርሱን ተይ ያሉኝ እለት እሞታለው፡፡ ሌላውን ግን እተወዋለው፡፡ እንጀራ ነው? ይውሰዱት፡፡ ልብስ ነው? ይውሰዱ፡፡ ንፁህ ይሁን እንጂ ሁለት ልብስ ለብሼ መኖር እችላለሁ፡፡ ኑሮዬም ከሆነ ይነስ፡፡
ቀጥሎ ላነሳው ወደ ነበረው ጥያቄ ነው የመጣሽልኝ በዚህ ዓለም ቋሚ ነገር ትቶ በማለፍ ታምኛለሽ? ዓላምንም፡፡አይገርምም?… ዓለም ለኔ ግልፅ አይደለም፡፡ ለምን እዚህ እንዳለሁ ገና በእርግጠኝነት አላወኩትም፡፡ ልጅ ሆኜ እናቴን አስጨንቃት ነበርኩ፡፡
የሰው ልጅ ታሪክ ከውልደት እስከ ሞት የተዘረጋ ነው ብለሽ ታመኛለሽ? አላምንም፡፡ የሰው ልጅ ኑሮ እዚህ ስለማያበቃ፣ የሞት እለትም ስለማይቋጭ እዚህ የተተከለው መልካም ዘር ፍሬው እዚያ ነው የሚበላው ብዬ አምናለሁ፡፡ (ጥያቄው) አንተ የትኛው ዛፍ ላይ ነው የተተከልከው? ነው፡፡ እኔ ከዚህኛው አገዛዝ ላይ ተተክያለሁ ካልክ ‹‹እንደ አባትህ መሆን ግዴታህ ነው፡፡›› ይልሃል መፅሐፍ ቅዱስ፡፡ ሁልጊዜ አባትህን ለመምሰል ነው ጥረትህ፡፡ መልካም ሰርቶ ማለፍ ክልክል ነው፡፡ ለምን? አባቴ መልካም ስለሆነ እኔም አባቴን መምሰል ነው ጥረቴ፡፡
አባቴ ስትይ … የሥጋ ወይስ የመንፈስ መንፈሳዊ ማለትሽ ነው?
መንፈሳዊ አባቴን እንጂ እግዚያብሔርን፡፡ እግዚያብሔር መልካም ስለሆነ ፍፁም ክፋ ነገር በውስጡ ስለሌለው በዚህ በምልህ ኑሮ ውስጥ እየታገልኩ፣ቢያመኝም እንኳ ክፋቴን ከላዬ እየጣልኩ እሱን ለመምሰል መጣር ነው፡፡ ለእኔ ክርስትና ክርስቶስን ለመምሰል መጣር ነው፡፡ ጋሼ ጥላሁን ገሠሠ በህይወት እያለ ሁላችንም አጨብጭበንለታል፡፡ ሲሞት በአጀብ ቀብረነዋል፡፡ ባለውለታነቱን መስክረናል፡፡ ሀውልት እንዲሰራለት፣ መንገድና ት/ቤት እንዲሰየምለት ጮኸናል፡፡ ትንሽ ሲቆይ ግን እሱን ትተን ወደ ግል ጉዳያችን ገብተናል፡፡ እስቲ የሆነ ነገር በይኝ፡፡
ስለምኑ? ስለ ሀውልትና መንገዱ? እነዚህን ሁሉ ብትሠራለትም ለጥላሁን ጥቅም የለውም፡፡ ጥላሁን አሁን ላለበት ሁኔት ትርጉም የለውም፡፡ ምንም ዘላቂ ባልሆነ ኑሯችን ግጭቱ ከዚህ ይጀምራል፡፡ በዚህ ዓለም ቋሚ አይደለንም፡፡ በኋላፊው አለምና በሚያልፈው ሕይወታችን ቋሚ ሆነን መኖር የምንፈልግ ፍጥረቶች ነን፡፡ትግሉ ይታይሀል? ለእኔ ግን ያስቀኛል፡፡… ይሄን ያህልስ መታሠቢያ ጥለህ ለማለፍ የምትጓጓላት ዓለም ናት ወይ ያለችው? እርግጠኛ አይደለሁም፡፡
ጣፋጩን ፍሬ በመጨረሻም ባታገኘው እንኳ አገኛለው ብለሽ ማሰብ ያረካሻል?
አየህ እኔ እግዚያብሔር መኖሩን ዳስሼና ነክቼ አይደለም ያወቅኩት፡፡ የእግዚአብሔር መኖር አረጋግጬ አይደለም የማምነው፡፡ አምኜ ነው የማረጋግጠው፡፡ እምነት አካሄዱ እንዲህ ነው፡፡ እንደ ዓለም አይደለም፡፡ ክርስቶስን ስታምነውና ልብህን ስትሰጠው ታየዋለህ፡፡
 http://gesame.net