Sunday, February 12, 2012

መመለስ አቃተኝ!

 ጠያቂ፦ አብርሃም እባላለሁ፤ በኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል አምናለሁ፡ ቃሉንም ዘወትር አነባለሁ፡ ነገር ግን በአሳፋሪ የዝሙትና የስንፍና ሃጢአት ባሪያ ሆኝለሁ....ብዙ ጊዜ ለመመለስ ብሞክርም በተደጋጋሚ ወደቅኩ። እባካችሁ ይህንን ጥያቄ ያነበባችሁ ሁሉ ባላችሁበት ቦታ ጸልዩልኝ። ምክራችሁንም ለግሱኝ።
 መልስ፦
የዝሙት ኃጢአት ባሕርያት

ከሁሉ አስቀድሜ እየተለማመድክ ስላለኸው ኃጢአት ምንነትና ባህርይ የበለጠ መረዳት እንድትችል አንዳንድ ነገሮችን ለማለት እወዳለሁ።

እንደዚህ አይነት ኃጢአቶች ብዙ ጊዜ በትንሹ የሚጀመሩና ከጥቂት ጊዜ በኋላ የራሳቸው የሆነ ሕይወት አበጅተው በራሳቸው ጉልበትና ኃይል የሚንቀሳቀሱ ኃጢአቶች ናቸው። ብዙ ጊዜ የሚጀመሩት በፈተና ነው። የሚፈትኑና የፍትወት ፍላጎትን የሚያነሳሱ ሁኔታዎች ይገጥሙና የመጀመሪያውን ፈተና መቋቋም ባለመቻል ይጀመራል። ብዙ ጊዜ ይህንን አይነት ኃጢአት የሚለማመድ ሰው (ቀድሞውኑም ጤናማ የክርስትና ሕይወት የነበረው ሰው ከሆነ) ኃጢአቱን ለማሸነፍና ፈተናውን ለመቋቋም የተወሰኑ ትግሎችን ያደርጋል። የሚፈትን ነገር ይኖራል፤ እናም ያንን ለመቋቋም ይሞከራል፡ ነገር ግን ይወደቃል። እንደ ማንኛውም ኃጢአት ከመደረጉ በፊት የነበረው "ደስታ"ና ግፊት ኃጢአቱ ከተደረገ በኋላ ከመቅስበት ጠፍቶ ወደ ጸጸትና ሃፍረት ስለሚለወጥ፤ ፈተናውን ሳይቋቋሙ ቀርተው በዚህም ኃጢአት ሲወድቁ ሰዎች በመጀመሪያ አካባቢ ይጸጸታሉ፤ ሁለተኛም ደግመው ላለማደረግ ይወስናሉ። ነገር ግን ከጥቂት ጊዜያት በኋላ ተመሳሳይ ፈተና ይመጣል፤ ትንሽ ያንገራግራሉ ደግመውም ያንኑ ኃጢአት ሲለማመዱ ራሳቸውን ያገኙታል ወዘተ።

እንዲህ እንዲህ ይልና መጀመሪያ ፈተና ከዚያም ማንገራገር በመጨረሻም መውደቅ የሚለው አዙሪት እየተደጋገመ ይሄዳል። ይህ ድግምግሞሽ ግን ወደሚቀጥለው የኃጢአት ደረጃ ይሻገራል። ይህም ከጊዜ በኋላ ኃጢአቱ እየተወደደና እየተደጋገመ ስለሚሄድ በራሱ ሕይወት ያለው ልምድ ይሆናል። ልምድ ደግሞ የሕይወት አካል ከሆነ ኃጢአቱ የሚደረገው ፈተና ስላለ ብቻ ሳይሆን ደስ ስለሚልና ስለ ለመድነው ነው። ከፈተና አልፎ የራሱ የሆነ ሕይወት አበጀ ማለት ነው። ከፈተና አልፎ በየጊዜው የምንለማመደው የሕይወታችን አካል ሆነ ማለት ነው። በዚህ ደረጃ ከደረሰ ደግሞ ኃጢአቱን ለመለማመድ ግዴታ የሚፈትኑ ነገሮች መኖር የለባቸውም። እኛው ራሳችን፤ በራሳችን ተነሳሽነት እንደ ልማዳችን ኃጢአቱን መለማመድ እንጀምራለን። መጀመሪያ ላይ ፈተናው የሚመጣው ከውጪ ነበር፤ በኋላ ልምድ ሲሆን ግን ያለ ወጪያዊ ፈተና ኃጢአቱ መጥፎ ልማድ ስለሆነብን ተነሳሽነቱ ከእኛው ውስጥ ነው የሚመነጨው። ይህ አደገኛ አካሄድ ላይ እንዳለን የሚያሳይ ምልክት ነው። ኃጢአቱ በሕይወታችን ቤቱን እየሠራና የእኛ አንዱ አካል እየሆነ የሚያመልክት ትልቅ ማስጠንቀቂያ ነው


ለምንድነው ዝሙትን የሚያነሳሱ ነገሮች ማየት ሰዎችን ደስ የሚያሰኛቸው? ለዚህ ሰዎች የተለያዩ ምክንያቶች ቢሰጡም ዋናው ግን ሌላ ምንም ሚስጥር ሳይሆን እንደዚህ አይነት ዝሙትን የሚያነሳሱ ምስሎችን ሰዎች ሲያዩ "የደስታን" ስሜት የሚፈጥርላቸው ሰውነታቸው የሚያመነጨው ኬሚካል ሆርሞኖች ስላሉ ነው። እነዚህ ኬሚካሎች ናቸው እንግዲህ "የደስታን" ስሜት የሚሰጡአቸው። ዝሙትን የሚያነሳሱ ነገሮች ባዩ ቁጥር ሰዎች ሰውነታቸው እነዚህን ኬሚካሎች ባያመነጩ ኖሮ "የደስታ" ስሜት ብዙም ስለማይኖረው፤ ደግሞ ደጋግሞ ለማየትና ዝሙትን ለማድረግ የሚገፋፋ ነገር አይኖርም።

ዝሙትን ከሚያነሳሱ ፈተናዎች ጋር ተያይዞ የፍትወትን ፍላጎት ለማካት የሚደረጉ ድርጊቶች አብረው የተያያዙ ናቸው። የፍትወት ፍላጎት ከረካ በኋላና የሥጋዊ ኬሚካሎች ተጽኖአቸው ሲያበቃ ግን ወዲያው ልክ ማንኛውም ኃጢአት እንደሚለማመድ ክርስቲያን "የደስታ" ስሜቱ ጠፍቶ የመንፈስ ሃዘን፣ ሃፍረት፣ መቆሸሽና ማደፍ ወዘተ ስሜቶች ይወርሳሉ። ደስታው ከሥጋዊ ኬሚካል የሚመነጭ ነው። ሃዘኑ፣ ማደፉና ሃፍረቱ ግን መንፈሳዊ ነው። የመንፈስ ጉዳት በራሳችን ላይ እየደረሰ ነው። ልክ ቆሻሻና የተበከለ ሥፍራ ተጨማልቆ ልብሱ እንደቆሸሸና እንደሚሸት ሰው፤ መንፈሳዊ ሕይወታችንም በእንደዚህ አይነት ኃጢአቶች ስለሚቆሽሽና ስለሚያድፍ፤ የቆሻሻና የእድፈት ስሜት ሕይወታችንን ይወርሳል። ከእግዚአብሔር አንድ እርምጃ እየራቅን ወደ ሞትና ጥፋት ደግሞ አንድ እርምጃ እየቀረብን ነው ማለት ነው።

የዚህን ኃጢአት አሠራሩን በጥቂቱም ከተረዳን አንድ በእርግጠኝነት ልናውቅ የሚገባው ነገር ቢኖር ከዚህ ኃጢአት በእርግጥ መላቀቅ መቻሉ ነው። ከዚህ እሥራት መላቀቅ ይቻላል። የመጀመሪያው ነገር ያለህበት መንገድ መንፈስን የሚያረክስና የሚጎዳ መንፈሳዊ ሕይወትንም ገድሎ ለሞት የሚያበቃ ኃጢአት መሆኑን መረዳት ነው። በጣም የሚገርመው ነገር ደግሞ ክቡሩን መንፈስህን የምትጎዳውና የምታቆሽሽው ትልቅና ልዩ ለሆነ ነገር ሳይሆን ለጥቂት ጊዜ ሰውነትህ ለሚያመነጨው ኬሚካል ነው። ኤሳው የከበረውን ብኩርናውን ለሚጠፋ እንጀራና ለምስር ወጥ እንደሸጠ፤ ከኤሳው በከፋ ሁኔታ አንተም ሰውነትህ ለሚያመነጨው ኬሚካሎች በተቀደሰው እግዚአብሔር ፊት ለዘላለም ይኖር ዘንድ ዳግም የተወለደውን መንፈስህን እያሳደፍክ እንደሆነ እወቅ። ይሄ ኃጢአትም የሕይወትህ አካል ሆኖ በመጨረሻ ደህንነትህን ሊያሳጣህ እንደምትችል መረዳት ይኖርብሃል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ በኃጢአት እየኖሩ የእግዚአብሔርን መንግስት መውረስ ይቻላል ብለን ራሳችንን እንዳናስት ደጋግሞ ያስጠነቅቀናልንና።
Quote:
1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 6
9 ወይስ ዓመፀኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንዳይወርሱ አታውቁምን? አትሳቱ፤ ሴሰኞች ቢሆን ወይም ጣዖትን የሚያመልኩ ወይም አመንዝሮች ወይም ቀላጮች ወይም ከወንድ ጋር ዝሙት የሚሠሩ
10 ወይም ሌቦች ወይም ገንዘብን የሚመኙ ወይም ሰካሮች ወይም ተሳዳቢዎች ወይም ነጣቂዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም

ወደ ገላትያ ሰዎች 5
19 የሥጋ ሥራም የተገለጠ ነው እርሱም ዝሙት፥ ርኵሰት፥
20 መዳራት፥ ጣዖትን ማምለክ፥ ምዋርት፥ ጥል፥ ክርክር፥ ቅንዓት፥ ቁጣ፥ አድመኛነት፥
21 መለያየት፥ መናፍቅነት፥ ምቀኝነት፥ መግደል፥ ስካር፥ ዘፋኝነት፥ ይህንም የሚመስል ነው። አስቀድሜም እንዳልሁ፥ እንደዚህ ያሉትን የሚያደርጉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም

እነዚህ ማስጠንቀቂያዎች የተላለፉት ለዓለማውያን ሳይሆን በቆሮንቶስና በገላትያ ለነበሩ አማኝ ክርስቲያኖች ነው።

ከዝሙት ለመላቀቅ የሚረዱ ምክሮች

በመንፈሳዊ ሕይወትህ ላይ ሊያደርስ የሚችለውን አደገኝነቱን በሚገባ ከተረዳህ በኋላ ከዚህ የልምድ ኃጢአት ለመላቀቅ ትችል ዘንድ የሚከተለቱን ምክሮች እሰጥሃለሁ።
  • ከሁሉ በፊት ይህ ኃጢአት ኃይሉ መሰበር የማይችል ግዙፍ ኃያል አድርገህ አትየው። በአንተ ላይ ያለው ኃይል ሊሰበር የሚችልና አንተም ከዚህ ነጻ ሆነህ ልትላቀቀው የምችለው ኃጢአት ነው።

  • ጉዳዩ እጅግ አሳሳቢ መሆኑን አውቀህ፤ በፍጹም ፍላጎት ከልብህ እግዚአብሔር ይሄንን ሃይል ሰብሮ እንዲያወጣህ ከልብህ ለምን። ስለ ጸሎት ብዛት ወይም መደጋገም አይደለም እዚህ ላይ የማሳስብህ ነገር ግን እንደ ሃና አይነት አንድ ጊዜም ቢሆን ከውስጥ ከልብ የመነጨ እግዚአብሔር ዘንድ የሚደርስ አንድ ልመና ማለቴ ነው።

  • ሌላው የልምድ ኃጢአት መሆኑን መረዳት ነው። ከላይ እንደገለጽኩት ሳትፈተን እንኳን ስለለመድከው የምትለማመደው ኃጢአት ስለሆነ፤ ከዚህ ለመላቀቅ ልምድን መስበርም ያስፈልጋል። ይህ እንዲሆን ታዲያ እግዚአብሔር ብቻ ሳይሆን አንተም ትልቅ ሃላፊነትና ድርሻ እንዳለህ መገንዘብ ይኖርብሃል። ስለዚህ ይህ ልምድ ከሕይወትህ እንዲሰበር፤ ማለትም የለመድከውን ልምድ እንድትተው፤ ኃጢአቱን ልትለማመድ የምትችልባቸውን ጊዜዎች፣ ቦታዎችና ሁኔታዎች ጨክነህ መሸሽ ይኖርብሃል። ይሄ የአንተ ድርሻ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ "ከዝሙት ሽሹ" 1ቆሮ 6፡18 ሲል እኛ መሸሽ እንደምንችልና እኛም ለዚህ ሃላፊነት እንዳለብን ሲገልጽልን ነው። ስለዚህ ወደ ዝሙት ከሚገፋፉ ሁኔታዎችና ቦታዎች ጨክኖ መሸሽ አማራጭ የሌለው ግዴታ ነው። በዚያ ፋንታ ወደ ዝሙት ሃሳብ ፈጽሞ ሊያስገቡህ ከማይችሉ ዘመዶች፣ ጓደኞች ወይም ክርስቲያን ወገኖች ጋር በሕብረት ለማሳለፍ ሞክር።

  • ከዚሁ ጋር በተያያዘ፤ ጊዜ ባገኘህ ቁጥር አዕምሮህንና መንፈስህን በቆሻሻ ነገሮች ከመበከል ፈንታ፤ መጽሐፍ ቅዱስንንና መንፈሳዊ ጽሑፎችን በማንበብና መንፈሳዊ ቪዲዎዎችን በማየት ወዘተ እንድታድስና ሰውነትህ ከሚያመነጨው ኬሚካል በላይ የዘለላለም ደስታና ሃሴት የምናገኝባትን ሰማያዊ ማደሪያችንን እያሰብክና እየናፈቅህ፤ ልብህ ከርካሽና ልክስክስ ከሆነ ነገር ወደ ሰማይ አሻግሮ የዘላለሙን ውበት እንዲያይ ሕይወትህ በመንፈሳዊ ነገሮች እንዲጠመድ አድርግ። ከመጥፎ ልምድ መሸሽ ብቻውን ሙሉ ድል አይሰጥም፤ መጥፎውው ልምድ በመልካምና መንፈስን በሚያንጽ ልምድ መተካት አለበት። አዕምሮንና መንፈስን በሚያድስ የእግዚአብሔር ቃልና መንፈስ ቅዱስ መሞላት አለበት። በሰማያዊ ሃሳብና በጌታ ሥራ መጠመድ አለበት። በመንፈስ ቅድስ ተሞልተህ ካልሆነ ስለ መንፈስ ቅዱስ ጥምቀት የሚያስተምሩ መጽሐፍትን በማንበብ የመንፈስ ቅዱስን ጥምቀት አጥብቀህ ፈልግ! የመንፈስ ቅዱስን ጥምቀት አግኝተህና በልሳንም የምትናገር ከሆነ መፈስህን ለማነጽ ጊዜ ባገኘህ ቁጥር አብዝተህ በልሳን ጸልይ "በልሳን የሚናገር ራሱን ያንጻል" 1ኛ ቆሮንቶስ 14፡4