Saturday, October 13, 2012

በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት አበምኔት የመምህር ወልደ ሰማእት አጭር የሕይወት ታሪክ

(ከገ/ዮሐንስ ገ/ማርያም ፤ (M. A. T.) አጠቃላይ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ታሪክ መጽሐፍ)    ከገጽ 56 ላይ ተሻሽሎ የተወሰደ፤

ከጥቁር ሕዝቦች መካከል በኢየሩሳሌም ቅዱሳን መካናት ውስጥ ብቸኛ ባለርስት ኢትዮጵያ ብቻ ናት። ከዚያም ባሻገር ነጮቹንም በመቅደምና እስካሁንም ሳይኖራቸው ካሉት ምእራባውያን በላይ ከመካነ ስቅለቱና ከመካነ መስቀሉ ጣሪያ ላይ የሰፈሩ ብቸኛ ሕዝቦች ኢትዮጵያውያን ናቸው። ከጥንቱ ከተማ ውጪ የነበረና አሁን አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ተብላ በምትጠራው ክፍል፤ የኢትዮጵያ ጎዳና ላይ  በ19ኛው ክ/ዘመን መጨረሻ ላይ የታነጸችው የኪዳነ ምህረት ቤተክርስቲያን በአካባቢው ብቸኛዋ የአበሾች ቤተክርስቲያን ናት።
በዚህች የ121 ዓመታት እድሜን ባስቆጠረች ቤተክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ጉልህ ስፍራ የነበራቸው፤ ነገር ግን ታሪካቸውን በአቧራና በተንኰል ድር የተሸፈነባቸው ታላቁ መምህር አባ ወልደ ሰማእት ናቸው። መምህር ወልደ ሰማእት ትውልዳቸው ሸዋ ቢሆንም ከሃይማኖት በስተቀር ዘርንና ጎጠኝነትን መሠረት አድርገው የማያምኑ ትልቅ አባት መሆናቸውን የሚያሳየው በወቅቱ የደረሰባቸው መከራና ያደረጉት ተጋድሎ ሕያው ምስክር ነው። መምህር ወልደ ሰማእት ምሁርና መጻሕፍት አዋቂ ነበሩ።  ወደኢየሩሳሌም በማቅናት ከኢትዮጵያ ገዳም በ1856 ዓ/ም ገደማ ሄደው ከማኅበሩ አንድነት እንደተቀላቀሉ ታሪካቸው ይነገራል።
ግብጻውያን መነኰሳት በኢትዮጵያ ውስጥ፤ ኢትዮጵያውያንን ለበቅሎዎቻቸው እያሰገዱ፤ በኢየሩሳሌም ያለውን ሀብትና ንብረት ደግሞ የቻሉትን ዘርፈውና ወስደው፤ በኋላ ላይ ደግሞ የፈለጉትን ለመስኮቦች ሸጠውና መነኮሳቱን ከርስታቸው ነቅለው ጸሎት ቤታቸውን በወረሷቸው  ሰዓት መምህር ወልደ ሰማእት ወደ ኢየሩሳሌም ማቅናታቸው እንደ አንድ አጋጣሚ የሚቆጠር ነው። በዚያን ወቅት ኢትዮጵያውያን መነኮሳት የጸሎት ቤታቸውን ተቀምተው እሁድ እሁድን እንኳን በየአብያተ ክርስቲያናቱ ተጠግተው ከሚያስቀድሱ በስተቀር ምንም መቀደሻ ሥፍራ አልነበራቸውም ነበር። መምህር ገ/መስቀል የኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት አበምኔት በሞት እንደተለዩ  የመምህር ወልደ ሰማእት እውቀትና ትእግስት ታይቶ አበምኔትነቱን እንዲረከቡ ተደርገዋል። ከዚያም ከ1836 ዓ/ም ጀምሮ ጠፍ ሆኖ የቆየውን ገዳም ወደነበረበት ለመመለስ መምህር ወልደ ሰማእት ወደ ኢትዮጵያው ንጉሠ ነገሥት አፄ ዮሐንስ ዘንድ በመሄድ አንድም ንጉሡ በምጽዋ  መጥቶ ድል ባደረጉት የቱርክ ሠራዊት ላይ የተቀዳጁትን ደስታ ለመግለጽ፤ በሌላ መልኩም የኢየሩሳሌም መነኮሳት ንጉሥ የሌላቸው ሕዝቦች ያህል ተቆጥረው ያለጸሎት ቤት በመንከራተት ላይ ስላሉ ንጉሡ መላ እንዲሰጧቸው  አቤቱታቸውን አሰምተው ንጉሠ ነገሥት ዮሐንስም በወቅቱ ከቱርኮች በምርኰ ያገኙትን አራት ሳጥን ገንዘብ ይሰጧቸዋል። መምህር ወልደሰማእትም የተሰጣቸውን ገንዘብ  ይዘው በመመለስ ለጸሎት ቤት ማሰሪያና ለመነኮሳቱ ማረፊያ ቦታ እንዲሆን አሁን ደብረ ገነት ኪዳነ ምህረት የተባለችው ቤተክርስቲያን ያለችበትን ርስት ገዙ። ከዚያም ከፈረንሳውያንና ቱርካውያን መሐንዲሶች ጋር በመነጋገር እራሳቸው መምህር ወልደሰማእት በነደፉት ዲዛይን መሠረት ቤተክርስቲያኒቱን በሚያዚያ ወር 1874 ዓ/ አስጀምረው ሊፈጸም ጉልላቱ ሲቀር በ1883 ዓ/ም አፄ ዮሐንስ መተማ ላይ አረፉ። የቤተክርስቲያኒና የመነኮሳቱ ማረፊያ ሥራ ፤ እንዲሁም በአሮጌው ከተማ ያለውን መንበረ ጵጵስና ባመጡት ገንዘብ ገዝተው፤ አስር ዓመታትን የፈጀባቸው ቤተክርስቲያኒቱ ግንባታ ሳይጠናቀቅ ገንዘቡ አለቀ። የተጀመረውን ያስፈጽሙላቸው ዘንድ ወደኢትዮጵያ ተመልሰው እንዳይጠይቁ ያስጀመሩት ንጉሥ አፄ ዮሐንስ አርፈው በምትካቸው አጼ ምኒልክ ንጉሠ ነገሥትነቱን ተረክበዋል።
ከዚያም መምህር ወልደ ሰማእት ሁለት መነኮሳትን ከኢየሩሳሌም ወደ አዲሱ ንጉሠ ነገሥት አፄ ምኒልክ ዘንድ ቤተክርስቲያኒቱ ያለችበትን ሁኔታ አስረድተው እሳቸው ማስፈጸሚያውን እንዲልኩላቸው ደብዳቤ አስይዘው ወደ ኢትዮጵያ ላኩ። አፄ ምኒልክም በደቡብና በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ዘመቻ ከፍተው ሀገሪቱን አንድ በማድረግ ሥራ ላይ ተጠምደው ስለነበረና በወቅቱም ወረርሽኝ በሽታ በሀገሪቱ ገብቶ ስለነበረ  የተፈለገውን ገንዘብ መላክ እንዳልቻሉ ምላሽ ይሰጣሉ። የተላኩት መነኮሳት ባዶ እጃቸውን መመለሳቸውን እንዳዩ መምህር ወልደሰማእት በአፄ ዮሐንስ ገንዘብ ከገዙት ሰፊ ይዞታ ውስጥ ከፊሉን መልሰው በመሸጥ፤ ቤተክርስቲያኒቱን በሽያጩ ገንዘብ በ1884 ዓ/ም አስጨርሰው ቅዳሴ ቤቱን ያከብራሉ።

 ከቤተክርስቲያኑ ቅጽር  መግቢያ በር ላይ እና  ከቅድስቱ ዙሪያ የውጪው ግድግዳው ላይ ቤተክርስቲያኒቱን አፄ ዮሐንስ በላኩት ገንዘብ መፈጸሙን የሚገልጽ ጽሁፍ በወርቅ ዓምድ እንዲጻፍ ያስደርጋሉ።
ከዚህ ጊዜ ጀምሮ የመምህር ወልደ ሰማእት መከራና ስደት ይጀምራል። ነገረ ሰሪና ሹመት ፈላጊ የሀገራቸው የሸዋ ሰብቀኛ ወንድሞቻቸው መነኮሳት ከአፄ ምኒልክ ዘንድ ይከሷቸዋል። እርስዎ ንጉሠ ነገሥቱ በሕይወት እያሉ በሞት የተለዩት ንጉሠ ነገሥት ስም እንዴት ይጻፋል? ብለው ስለከሰሷቸው  መምህር ወልደ ሰማእት ለጥያቄ ወደ ኢትዮጵያ ይጠራሉ። መምህር ወልደ ሰማእትም የንጉሡን ጥሪ አክብረው ከሄዱ በኋላ ለምን የዳግማዊ ምኒልክ ንጉሠ ነገሥት ስም እንዳልሰፈረ ሲጠየቁ፤ መምህር ወልደ ሰማእት ምንም ሳይፈሩና ሳያፍሩ ሀቁን ግልጥልጥ አድርገው ይናገራሉ።  መንበረ ጵጵስናውን፤ የደብረ ገነት ኪዳነ ምህረትን ቤተክርስቲያንን ሙሉ ይዞታና የመነኮሳቱን ማረፊያ የገዙት በአፄ ዮሐንስ የስጦታ ገንዘብ መሆኑንና ለማስፈጸሚያም መነኮሳት ልኬ ገንዘብ ባለመገኘቴ ከገዛሁት ርስት ላይ ቀንሼ በመሸጥ ያስፈጸምኩ ሲሆን ሙሉ በሙሉ በንጉሠ ነገሥት አፄ ዮሐንስ ገንዘብ ስለተፈጸመ፤ የጻፍኩት ያንን በመሆኑ ጥፋቴ ምንድነው? ብለው ይጠይቃሉ። መምህር ወልደ ሰማእት ምንም ዓይነት ጥፋት እንዳላጠፉ ቢታወቅም ሕያው የነበረውን ንጉሥ ትተው የሙቱን ንጉሥ ስም በማስጻፋቸው ብቻ በደብረ ሊባኖስ ገዳም እንደጥፋተኛ በግዞት እንዲቀመጡ ይወሰንባቸዋል። ከከንቲባ ገብሩ ደስታ ጋር ሌሎች ሁለት ሰዎች ተልከው የመምህር ወልደሰማእት ጽሁፍ እንዲቀየር ይደረጋል።

Thursday, October 11, 2012

ቋሚ ሲኖዶስ ጀግኗል!

በቤተ ክርስቲያን ትልቁ ችግር ከአናቱ እስከ እግሩ ጥፍሩ ያለው መዋቅር በበሰበሰ አስተዳደር መተብተቡ ነው። 2 ሺህ ዘመናትን በመከራና በወጀብ ስትናጥ፤ የደም አበላ ግብሯን ጠያይም ልጆችዋን እየሰጠች፤ ከጉዲት እስከ ግራኝ፤ ከድርቡሽ እስከጣሊያን ድረስ ከልጆቿ እስከ ንብረቷ ስትገብር የቆየችና እዚህ 21ኛው ክ/ዘመን ላይ የደረሰች ቤተክርስቲያን ሉላዊ እውቀትና አስተዳደር በዘመነበት ዘመን ላይ ምን እንደነካት ሳይታወቅ የገዛ ልጆቿ የስልጣንና የሀብት ክምሯ ላይ ሰፍረው እንደ ዳልጋ ዝንጀሮ እየፈነጩ ሲንዷት ማየቱ ውሎ ያደረ ከመሆኑም በላይ ሁሉም እየተባበሩ በአንድ ድምጽ ውድቀቷን እናፋጥን የሚሉ እስኪመስል ድረስ በጥፋት እድምተኞች መሞላትዋ ግልጽ ነው።
ሙዳየ ምጽዋት የሚገለብጡ ይሁዳዎች፤ አፍኒንና ፊንሐስ አመንዝራዎች፤ በነጻ የተሰጣቸውን የሚሸጡና በእናጸድቃለን ካባ የመበለት ቤቶችን የሚመዘብሩ ግብረ በላዎች፤ ስመ ብጽእናን ለምግባረ ብልሹ ስራቸው የደረቱ አባዎች ሞልተው የጋራ ክንዳቸውን በዐመጽና በጥፋት «አንስእ ኃይለከ» ተባብለው የተማማሉ የግብረ እከይ ሰዎችን ማንነትና አድራጎት መመልከቱም እንግዳ ነገር አይደለም። ሆዳቸው ከሞላ የበሻሻ አቦ ምእመናን ሰይፍ በአንገታቸው ቢያልፍ አፋቸው በስብ የተዘጋ ይመስል የማይናገሩ አፈ ዲዳዎች መሪ በሞላባት ዘመን ላይ ቤተክርስቲያን መድረሷ አጥፊዎቿ የውጪ ጉዲት ሳይሆን የራሷ እሬቶዎች መሆኑንም ብዙ ታዝበናል። በአዲስ አበባ ከተማችን የ2000 ብር ደመወዝ እየበላ የሁለት መቶ ሺህ ብር መኪና የሚነዳ የመሪነት ስምን የተሸከመ ሙዳየ ምጽዋት ገልባጭ ማየት የተለመደ ሆኗል። የዘረፋ መዋቅር ዘርግተው የቤተክርስቲያኒቱን ጡት ያለርኅራኄ የሚመጠምጡ አይጠ መጎጦች ተንሰራፍተው ይገኛሉ። ገንዘብ የሚገኝበትን ቤተክርስቲያን ለመምራት ከላይ እስከታች በሚደረገው መቆላለፍ ጅቦቹ አፋቸውን ከፍተው ሲያሰፈስፉ መስማትም ዛሬ ዛሬ እንደተገቢ እየተቆጠረ ይገኛል። በአንድ ወቅት የወይብላ ማርያም ቤተክርስቲያን ከነበራት የ400,000 ብር ካዝና ውስጥ በወራት ልዩነት ወደ 20 ሺህ ደርሶ ለካህናት ደመወዝ መክፈል እስኪያቅት መደረሱን አይተን እነሆ እስከዛሬ በአስገራሚነቱ መዝግበነዋል። ከማኅደረ ስብሐት ልደታ ለማርያም እስከ ዑራኤል ቤተክርስቲያን፤ ከመርካቶ ሚካኤል እስከ ግቢ ገብርኤል የጅብ መንጋ ሲግጥ ማየት እንግዳ መሆኑ ቀርቷል።  በየደረጃው የእያንዳንዱን አብያተ ክርስቲያን ካዝና ገልብጠው ባዶ ካደረጉ በኋላ ወደተረኛው ቤተክርስቲያን የሚዛወሩ ወሮ በሎች በዚህ አጭር ጽሁፍ ዘርዝሮ የሚዘለቅ አይደለም።
 የሚያስደንቀው ደግሞ ቤተክርስቲያኒቱ ምን ዓይነት ቁጣ ወረደባት እስኪያሰኝ ድረስ ከሀገር ቤት አንስቶ እስከባህር ማዶ ድረስ የአበሻ ጅቦች የሰፈሩባት መሆኑ ያስገርማል። ከቦርድ እስከ ሰበካ ጉባዔ ከተገንጣይ እስከ ገለልተኛ፤ ከግለሰብ ቤተክርስቲያን እስከ ሁለ ገብ ድረስ እየተቧደኑ መዝረፍና ማስዘረፍ፤ የየሀገራቱን ፍርድ ቤቶች ፋይል እስከማጨናነቅ ያደረሰ የዘረፋ ስልጣኔ መንገሱም ፀሐይ የሞቀው፤ አገር ያወቀው ጉዳይ ነው።
የክህነቱና የመሪነቱ መስፈርት የማንነት ሚዛንስ ምኑ ተነግሮ? እንዲያው ተከድኖ ይብሰል! ይህ ሁሉ ሲሆን ቤተክርስቲያንን በመንፈስ ቅዱስ እመራለሁ የሚል ከፍተኛው የሥልጣን እርከን ሲኖዶስ ነበራት። ለመብላትና ለመናገር ካልሆነ ለመሥራት አቅሙና ፍላጎቱ የሌለው፤ ቤተክርስቲያን ብትሞት እንጂ ለእሷ ሞት ራሳቸውን ለማስቀደም የሚደፍሩ የመሪ ቁርጠኞች በሌለበት ሁኔታ ውስጥ መገኘቷ ችግሯ እንዲባባስና ከልካይ የሌለበት እንድትመስል አድርጓታል። ወጉ ደርሶ ማስቆም ባይችሉ ራሳቸውም አብረው ወራሪና አስወራሪ መሆናቸውን ቢያቆሙ እንኳን እሰየው ባልን ነበር! ነገሩ ግን የተገላቦጦሽ ነው። ሕዝቡ በG ማይነስ ቤት ውስጥ እየኖረ እነሱ በG ፕላስ ውስጥ መኖራቸው ነገሩን ሁሉ አስከፊ ያደርገዋል።

የሽጉጡ ጦስ ሁለት የአቡነ ገብርኤልን የቅርብ ረዳቶች ከሥራ አፈናቀለ


source: dejeselaam-dejeselaam.blogspot.com
የሲዳማ፣ ጌዴኦ፣ አማሮና ቡርጂ ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የሆኑት አቡነ ገብርኤል ወደ ሀዋሳ በሥራ ተመድበው ከሄዱበት ጊዜ ጀምሮ አንድም ቀን ሠላምና ዕረፍት አግኝተው አያውቁም፡፡ ልባቸው ከሠላምና ከዕርቅ ርቋል፡፡ ከቤተክርስቲያን የተባረሩ በሺዎች የሚቆጠሩ ምዕመናንን ጥያቄ በመመለስ ፈንታ ሕልምና ሃሣባቸው ለጥቂት ጥገኛ ነጋዴዎችና ለ"ማኅበረ ቅዱሳን" አባላት እየተሸነፈ ማንኛውም ዕርቅ እንዳይደረግ ከማገድ ውጪ ምንም ነገር አይታያቸውም፡፡
በሺዎች ከሚቆጠሩ ምስኪን ምዕመናን ይልቅ ጥቅም ሊያገኙ የሚችሉት ከጥቂት ጥገኛ ነጋዴዎችና ከ"ማኅበረ ቅዱሳን" እንደሆነ ራሳቸውን አሳምነውታል፡፡ ስለዚህ በእነዚህ ሁለት አካላት አቀነባባሪነት በድሃዎቹ የሀዋሳ ምዕመናን ላይ ጥቃት ሲፈጸም፣ አይተው እንዳላየ፣ ሰምተው እንዳልሰማ በመሆን ፍትሕን ከሀገረ ስብከቱ የሰማይ ያህል አራቁት፡፡ የእግዚአብሔር መንግሥት ወንጌል እንዳይሰበክ ሲታፈን ነገሮችን ሁሉ በፊርማና በማኅተማቸው እያፀደቁ የድኆቹ የአምልኮ ነፃነት በጠራራ ፀሐይ ሲቀማ ምንም አልተሰማቸውም፡፡
ይሁንና በዚህ ሁኔታ የተማረሩት የሀዋሳ ምዕመናን ስለመልካም አስተዳደርና ስለ ፍትሕ ጮኹ፡፡ ቁጣቸውን በተለያዩ መንገዶች ገለጹ፡፡ ግጭቱ ተጋግሞ ሀገረ ስብከቱን አልፎ በመላው ሀገሪቱ በተለይም በጠቅላይ ቤተክህነት ውስጥ መነጋገሪያ ሆነ፡፡ ቋሚና ቅዱስ ሲኖዶሶች ተከታታይ ስብሰባዎችን በማድረግ ልዩ ልዩ ውሳኔዎችን አስተላለፉ፡፡ ይሁን እንጂ አቡነ ገብርኤል ያላወረዱትን ዕርቅ፣ ዕርቅ አውርጃለሁ፣ ያልመሠረቱትን ሠላም፣ ሠላም መሥርቻለሁ፣ ያላመጡትን አንድነት፣ አንድነት አምጥቻለሁ እያሉ ጠቅላይ ቤተክህነት አካባቢ ቢዋሹም ሐቁ ግን እየገዘፈ መጥቶ ለስድስት ወራት (ጥር/2003 -ሐምሌ/2003) ያህል ለሕይወታቸው በመስጋት ሸሽተው አዲስ አበባ ላይ መቀመጥ ግዴታ ሆነባቸው፡፡
ይሁን እንጂ፣ ከእትብቱ እንደተቆረጠ ጽንስ መተንፈስ የተሳናቸው ጥቂት ጥገኛ ነጋዴዎቹና የ"ማኅበረ ቅዱሳን" አባላት እንደምንም ተሟሙተው ሐምሌ 18 ቀን 2003 ዓ.ም ምሽት በአንዲት አሮጌ ሃይላክስ ፒክ አፕ መኪና በስውር ወደ ሀዋሳ መልሰው ወሰዷቸው፡፡
ከዚያም ዙሪያውን ጥበቃ ተጠናከረላቸው፡፡ ሲወጡም ሲገቡም በግል ሴኪዩሪቲ ማሠልጠኛ የሠለጠኑ ጠባቂዎችን በመመደብ፣ ብርሃን ቀርቶ አየር እንኳን እንዳያገኙ እፍንፍን አድርገው አጀቧቸው፡፡ ዐውደ ምሕረቱ በልዩ ልዩ መሰናክል ታጥሮ ምዕመናን በቅጡ ማስቀደስ ተሳናቸው፡፡
በዚህን ጊዜ ይላሉ ውስጥ ዐዋቂዎች፣ በዚህን ጊዜ የአቡነ ገብርኤልን መንፈስ ለማረጋጋት ሲባል፣ በአግባቡ የተመዘገበ ስለመሆኑ እንኳን በቅጡ የማይታወቅ ለራስ መጠበቂያ የሚሆን አንድ ሽጉጥ ከጥገኛ ነጋዴዎቹ በአንዱ በእጅ አዙር ተበርክቶላቸዋል፡፡ በዚህ ሁኔታ የተነቃቁት ሊቀጳጳስ ምስኪኖቹን የሀዋሳ ምዕመናንን ለግል የወሲብ መጽሔት በሰጡት ቃለ መጠይቅ "ቀበሮዎች ናቸው" ብለው እስከመሳደብ ደረሱ፡፡ በሠላም የሚመጣውን በእጅ መስቀላቸው፣ በኃይል የሚመጣባቸውን ደግሞ በተሰጠቻቸው ራስ መጠበቂያ ቀልጥመው ሊያሳርፉት ንቁ ሆነው መጠበቅ ያዙ፤ በሠለጠነ ዘመን ማን ይሞታል ታዲያ?
አቡነ ገብርኤል እንዲህ እንዲህ እያሉ፣ ልባቸው ዕርቅና አንድነትን እየተፀየፈች፣ ልታረቅ ቢሉ እንኳን ጥገኛ ነጋዴዎቹና የ"ማኅበረ ቅዱሳን" አባላት እንዳይታረቁ እያከላከሏቸው የሠላም መንፈስ አንድ ቀን እንኳን በውስጣቸው ሳትገባ፣ ሀዋሳ ላይ ሥራ ከጀመሩ ሁለት ዓመት ሊሞላቸው አንድ ሁለት ወራት ብቻ ቀራቸው፡፡ ታዲያ በአንድ ዕድለ ቢስ የነሐሴ 2004 ዓ.ም የተረገመች ቀን፣ ያቺ ለራስ መጠበቂያ የተሰጠቻቸው ሽጉጥ ጠፋችባቸው፡፡ ከሁኔታው መረዳት እንደተቻለው አቡነ ገብርኤል ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ሥርዓተ ቀብር አዲስ አበባ በተገኙበት ወቅት ሽጉጣቸውን መኝታ ክፍላቸው ውስጥ ረስተውም ይሁን አስቀምጠው ያገኘ ሰው እንደወሰደባቸው ተገምቷል፡፡
በዚህ ሁኔታ የተበሳጩትና የተቆጡት አቡነ ገብርኤል ከእነርሱ በስተቀር አንስቶ ሊወስድብኝ የሚችል የለም በማለት የጠረጠሯቸውን ፍጹምን (ተላላኪያቸው) እና ሊቀመዘምራን ልሳነወርቅን (ሾፌራቸው)፣ በቅርብ እንዲከታተሉላቸውና እንዲያጠኗቸው የጥገኛ ነጋዴዎችንና የ"ማኅበረ ቅዱሳን"ን ጥምር ኮሚቴ አይሉት ስብስብ ነገር ይመድቡባቸዋል፡፡ የሽጉጧ ነገር የውሃ ሽታ ሆነ ቀረ፡፡ ፍጹም ሲጠየቅ ከልሳነወርቅ በስተቀር ሊወስድባቸው የሚችል የለም እርሱን ጠይቁት ይላቸዋል፡፡ ልሳነወርቅ ደግሞ በበኩሉ "አብሯቸው የሚያድር ማን ሆነና ነው እኔን የምትጠይቁት? ለመሆኑ ለእርሳቸው ከፍጹም የቀረበ አለ እንዴ? ፍጹምን መርምሩት" ይላቸዋል፡፡
ብፁዕ አቡነ ገብርኤል ያችን ውድ ዕቃ ሳያገኟት መስከረም ወር እንደዋዛ ሊጠናቀቅ ተቃረበ፡፡ እንደ እርሳቸው እምነት በእነዚህ ሁለት ሰዎች መጠቃታቸው ያንገበግባቸዋል፡፡ በተለይ የፍጹም እንዲህ መጨከን ሊገባቸው አልቻለም፡፡ ፍጹም እኮ ሁለ- ነገራቸው ነው፡፡ ቃል አቀባያቸው፣ ጠባቂያቸው፣ አስገቢና አስወጪ አጋፋሪያቸው፣ አንዳንዶች ደግሞ እንደሚሉት፣ የላመ የጣፈጠ ምግባቸውን ቀምሶ ለይቶ የሚያስቀርብላቸው ወጥ ቀማሽ እልፍኝ አስከልካያቸው፣ ኧረ ስንቱ . . . ? የፍትሕ ጥያቄ ለማቅረብ ወደ መንበረ ጵጵስናው የሚመጡትን የሀዋሳ ምዕመናንን "እርሳቸው የሉም"፤ "ተኝተዋል"፤ "ዕረፍት ላይ ናቸው"፤ "አሁን ሊያነጋግሯችሁ አይችሉም" እያለ የሚያባርርላቸው አለኝታቸው ነው፡፡ ሲያስፈልግም ከእርሳቸው ቀደም፣ ቀደም እያለ ምዕመናኑን ላቀረቡት ጥያቄ መልስ ሳያገኙ አፍ አፋቸውን እያለ ወደ መጡበት ይመልስላቸዋል፡፡ እርሱን እንደ እሳት መከላከያ አስቤስቶስ ነው የሚጠቀሙበት፡፡ እንደሻንጣቸው ሁልጊዜ የትም ነው ይዘውት የሚዞሩት፡፡ በተለይ ረፋድና አመሻሽ ላይ በፌስታልና በብብቱ ሥር በጋዜጣ የተጠቀለሉ የሚበሉና የሚጠጡ ፍሬሽ ፍሬሽ ነገሮችን ባሻው መንገድ በማቅረብ እርሱን የሚተካከለው አንጀት-አርስ የለም፡፡ ፍጹም እኮ በፍጹም ተተኪ የሌለው ረዳታቸው ነው፡፡
ሲያሻው ደግሞ "ተቀመጥ በወንበሬ፣ ተናገር በከንፈሬ" ብለው በሀገረ ስብከቱ ልዩ ልዩ ወረዳዎችና ከተማዎች እየወከሉት ልዩ ልዩ ካህናትን እየሰበሰበ ይገስጽላቸዋል፡፡ የተበላሹ አሠራሮችን ያስተካክልላቸዋል፡፡ እንደ እርሳቸው ሆኖ የሚገባቸውን ግብዣ ስለእርሳቸው ይጋበዝላቸዋል፡፡ ታዲያ "ፍጼን" ምን ነካው? ደግሞ እኮ እርሱን ላለማጣት ቃለ ዐዋዲን ሽረው በመዋቅር የሌለ የሥራ መደብ ፈጥረው "የጳጳሱ የመልዕክት ክፍል"     የሚል የሥራ መደብ መጠሪያ አውጥተው በወር ብር 930 ከአሮጊቶች መቀነት ከሚሰበሰብ ገቢ ወርሃዊ ደመወዝ እንዲከፈለው ቆርጠውለታል፡፡ ይህም ብቻም አይደለም፤ እርሱን ከመውደዳቸው የተነሳ ቅጥሩ ያለ ማስታወቂያና ያለ ነፃ ውድድር በመስከረም 2004 ዓ.ም ሆኖ፣ ደመወዙ ደግሞ ከቅጥሩ ቀን በፊት አንድ ወር ወደ ኋላ ተደርጎ ከነሐሴ 2003 ዓ.ም ነው የተደረገለት፡፡ እርሳቸው ይህንን ሁሉ ሕግን እየተላለፉለት፣ እየጣሱለት፣ እንዲህ ጉድ ያደርጋቸዋል? ወይኔ! ወይኔ! ወይኔ! ሰውየዉ . . . !!

Wednesday, October 10, 2012

‹‹ለእንጀራ ብዬ ›› . . . አይባልም!

በሰላማዊት አድማሱ Selam.admassu@yahoo.com

ሸዋንግዛው፣ በላይነህ፣ ጌታ ነህ፣ ግርማዊ፣ ልዑል፣ ኩራባቸው  . . . እነዚህን እና እነዚህን የመሳሰሉ ስልጣንን፣ ጌትነትን ፣ልዕልናን የሚገልፁ በርካታ ኢትዮጵያዊ ሰሞች አሉ፡፡ ስለ ስም ካነሳን ዘንድ ስያሜ ጠባይን፣ግብርንና ሁኔታን የሚገልጥ ሆኖ በእስራኤል ዘንድ ይሰየም እንደነበር የታወቀ ነው፡፡ ለምሳሌ ምናሴ፡- ‹‹ማስረሻ›› ዘፍ 41፡51 (የስም ሰጪውን ሁኔታ ሲገልጥ) ዮሴፍ ‹‹ይጨምር›› ዘፍ 30፡24 (የዮሴፍን ህይወት ያንጸባርቃል)፡፡ የእግዚአብሔር ስሞችም ባህሪውን ፤ስራውን እና አምላክነቱን ይገልጻሉ፡፡ የእኛዎቹ የኢትዮጵያውያን ስሞችስ ምን ያህሉ ይሆን እኛነታችንን የሚገልጹት? ወይንስ መግለጽ አይጠበቅባቸውም ይሆን?፡፡
    አንድ የቤተሰብ አባወራ ለልጁ የሚሰጠው ኩርማን እንጀራ፤የሚያወርሰው አንድ ክንድ መሬት ሳይኖረው ‹‹ ግዛቸው›› ብሎ ስም ያወጣለታል፡፡ ልጅዬውም ከእናቱ ጓዳ ዳቦውን እየገመጠ፤ ቆሎውን እየቆረጠመ አድጎ ለአቅመ አዳም ሲደርስ እርሱም ተራውን ለልጁ ‹‹በላይ ነህ›› ወይንም ‹‹ጌታ ነህ›› ብሎ ስም ያወጣለታል፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለ እስከ አስር ትውልድ ቢቆጠርም አንድም ጊዜ ከቤተሰቡ መሃል ‹‹እንደ ስሙ›› የሆነ ላይገኝ ይችላል፡፡ ‹‹ግዛቸው›› ተብሎ በድህነቱ ሳቢያ ላለው የተገዛ፤ ‹‹በላይነህ›› ተብሎ ‹‹ በታች›› የሆነ እጅግ ብዙ ሰው አለ፡፡ እንዲያው ለመግቢያ ያህል ምን ያህል ሥራችን እንደስማችን ወይንም ስማችን እንደስራችን ይሆን?  ስል መጠየቅ ፈለኩ እንጂ በዋንኛነት ላወራስ የፈለኩት ስለ ሥራ ነው፡፡ እንደው የስሞቻችን ነገር በሥራ ባህላችን ላይ ያመጡት አሉታዊ ተጽዕኖ ይኖር ይሆን እንዴ? እናንተስ ምን ይመስላችኋል?
የሥራ ፈጣሪው ማን ነው?
   መቼም ሁሉም ነገር መነሻና ጅማሬ አለው ፡፡ ለመሆኑ ሥራን ማን ፈጠረው? ተፈጥሮ ወይንስ ፍጥረት? ሃጢያት ወይንስስተት?  . . ሁሉ የየራሱ መላ ምት ሊኖረው ይችላል፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳችን ግን የሥራ ፈጣሪው ራሱ እግዚአብሔር እንደሆነ ይናገራል፡፡ ዘፍ 1፡28፡፡ ይህንን ሃሳብ መጋቢ ደሞዝ አበበ ሥራ-ሥራ በሚለው መጽሐፋቸው ላይ ‹‹ ሥራ የሰዎች ግኝት አይደለም፡፡ ከእግዚአብሔር የተገኘ አምላካዊ በረከት ነው፡፡ በመሆኑም በአምሳሉ ለፈጠረው ሰው ሥራን ሰጠው ፡፡ እርሱ ቦዘኔ ስላልሆነ ሰውም ቦዘኔ እንዲሆን አይፈልግም፡፡›› በማለት ገልጸውታል፡፡ ስለዚህ በቀላል እና በማያሻማ መንገድ የሥራ ፈጣሪው ራሱ እግዚአብሔር መሆኑ ተገልጾልናል፡፡
ሥራ ለምን? ለሆድ ወይንስ? . . .
    እግዚአብሔር አምላክ በዘፍጥረት መጽሐፍ ላይ ለአዳም ‹‹ሥራን›› የሰጠው ‹‹ለሆዱ›› ወይንም ለሚበላው አይደለም፡፡ ምናልባት እኛ ‹‹ለእንጀራ ብዬ ነው ስራ የምሰራው›› ብለን እንደምንለው አይነት አይደለም፡፡  ምክኒቱም ኤደን ገነት ‹‹ለእንጀራ›› የሚለፋባት አልነበረችም ዘፍ 2፡8፡፡ አንዳንድ መጽሐፍት ‹ገነት›› የሚለውን ቃል ሲተረጉሙት ሁለት ፍቺ ይሰጡታል፡፡ አንደኛው ‹‹ አትክልት ማለት ነው›› ሲሉ ሁለተኛው ‹‹ በቅጥር የተከለለ የአትክልት ስፍራ›› ማለት ነው ይላሉ፡፡ ስለሆነም የአዳም በገነት መቀመጥ እና ሥራን መስራት የተፈለገው የሚበላው ነገር ስለሌለው አልነበረም፡፡ ይልቁንም መልካሙን እና ክፉውን ከሚያሳውቀው ዛፍ በቀር በገነት ካለው ሁሉ እንዲበላ ተፈቅዶለታል፡፡ ታዲያ እግዚአብሔር አምላክ አዳም የሚበላው ነገር ሞልቶት ሳለ  ሰራተኛነቱን ለምን ፈለገ? ብለን ብንጠይቅ አዳም ከተፈጠረ በኋላ ምድርን የማበጀት እና የመጠበቅ ኃላፊነት ስለተሰጠው ነው፡፡ ‹ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ ሰውን በኤደን የአትክልት ቦታ አኖረው ሰው የአትክልቱን ቦታ እንዲያለማና እንዲንከባከበው ነው፡፡› ዘፍ 2፡15

Tuesday, October 9, 2012

የአቡነ ገብርኤል ማካሮቭ ሽጉጥ ጠፋ!

source: www.awdemihret.blogspot.com
ሰርቀሀል ተብሎ የተጠረጠረው ዲ/ን ፍጹም እንዳለ የተባለ አገልጋያቸው እንዲባረር ተደርጓል፡፡

በአቋማቸው ወላዋይነት እና ጠንካራ ነው ብሎ ያመኑበትን ክፍል በመጠጋት በሚያደርጉት እንቅስቃሴ የሚታወቁት አቡነ ገብርኤል በቤታቸው ደብቀውት የነበረው ማካሮቭ ሽጉጥ ጠፋ፡፡ አጣሪ ኮሚቴ አቋቁመው ነገሩን እንዲጣራ እያደረጉ ነው፡፡ የአጣሪ ኮሚቴው ሊቀመንበር ከሀገረ ስብከት ስራ አስኪያጅነት ከተባረረና አሁን አቡነ ጳውሎስ ካረፉ በኋላ በአባ ገብርኤል ወደ ቦታው የተመለሰው አለም እሸት ነው፡፡ አለም እሸት ከስልጣኑ የተነሳው ከ12 መኪና በላይ የሚሆን ህዝብ ከአዋሳ መጥቶ አቤቱታ ስላቀረበበት እንደሆነ አይዘነጋም፡፡ ከቅዱስነታቸው ዕረፍት በኋላ ግን አለምእሸትን አባ ገብርኤል በማን አለብኝነት መልሰውታል፡፡ 

የሽጉጡን መጥፋት በተመለከተም ምንም እንኳ አለም እሸት ማኅበረ ቅዱሳናዊ የምርመራ ዘዴውን ተጠቅሞ ለማውጣጣት ቢሞክርም ልጁ ግን ባልወሰደድኩት ንብረት እንዴት እጠየቃለሁ በማለቱ አባረውታል፡፡ እውነተኛውን ሌባ ፈልጎ እንደማውጣት ድሀን በመግፋት መፍትሔ ሰጠን የሚል አሰራር የእነ አባ ገብርኤልን እና አለምሸትን አምባገነንነት ያሳያል፡፡
ሽጉጥ በጓዳ አስቀምጠው የሀይማኖት አባት ነኝ ለማለት መሞከር በእጅግ አሳፋሪ ነገር ነው፡፡ ነገሩ አሳፋሪ ስለሆነም ለፖሊስ ለማመልከት አልደፈሩም፡፡« እስራኤልን የሚጠብቅ አያንቀላፋም» የሚለውን ቃል ያላነበበቡት አባቶቻችን ራሳቸውን ለመጠበቅ የማያንቀላፋውን ጌታ ትተው ሽጉጥን ተስፋ ማድረጋቸው ይገርማል፡፡ እውነትን ጽድቅን እየሰሩ እግዚአብሔርን ተስፋ ከማድረግ ይልቅ ሁሉን እያደፈረሱ በሽጉጥ መታመን የማይጠቅም ነገር መሆኑን መዘንጋታቸው ገርሞናል፡፡

መንግሥት ፓትርያርክ ማን ሊሆን እንደሚችል በውስጥ መሰየሙን ይነገራል።

ከታማኝ የውስጥ ምንጮች የደረሰን ዜና እንደሚያስረዳው ስድስተኛው ፓትርያርክ በመንግሥት ደረጃ ምልመላው ያለቀ ሲሆን ይህ መረጃም በማኅበረ ቅዱሳንና በቀንደኛ ጳጳሳት ዘንድም  የውስጥ ግንዛቤ እንዲያዝ ተደርጎበታል ተብሏል።
የእርቅ ሂደቱ ቢያልቅና የውጭዎቹ ጳጳሳት ከሀገር ቤቱ ሲኖዶስ ጋር በሚደረገው ስምምነት ወደአንድነት ቢጠቃለሉ ሲኖዶሱ በሚሰጣቸው ቦታ የሚመደቡ ሲሆን፤ አቡነ መርቆሬዎስ ግን ለሥራ ብቁ በማያደርጋቸው የጤናና የእድሜ ክልል ውስጥ ስላሉ በፈለጉበት ቦታ ስመ ማእረጋቸው እንደተጠበቀ በጸሎት ተወስነው እንዲቀመጡ የተፈለገ መሆኑም ተዘግቧል።
የውጪው ሲኖዶስ በሚደረገው እርቅ መሠረት በስምምነት ወደአንድነቱ የማይመጣም ከሆነ ራሱ እንዳልፈለገ ተቆጥሮ በነበረበት ሁኔታ ልዩነቱ እንደሚቀጥልም ይነገራል። ይሁን እንጂ የስድሰተኛው ፓትርያርክ ምርጫ ግን ከጥያቄ ውስጥ እንደማይገባና ወደፊት በሚመቻችለት ጊዜ ውስጥ ተመርጦ መንበረ ሥልጣኑን ተረክቦ ሥራውን እንደሚጀምር መረጃዎች ይጠቁማሉ።
በዚሁ የፓትርያርክነት የምልመላ መዝገብ ውስጥ በአንደኝነት የሰፈሩት ከዚህ በፊት በሰሜን አሜሪካ ሊቀጳጳስ የነበሩትና አሁን ወደ ኢየሩሳሌም ከተዛወሩ ጥቂት ዓመታትን ያስቆጠሩት አቡነ ማትያስ መሆናቸው ተነግሯል።

ውስጥ አዋቂ መረጃዎቻችን ያንን የሚጠቁሙ ሲሆን ለማንኛውም የሚሆነውን ጊዜው ሲደርስ እናያለን።

Thursday, October 4, 2012

«የዓላማ ሰው ከመሆን የሚከለክል ማንነትና መፍትሄው»

«ከዓላማ መር መጽሐፍ» ለንባብ እንዲመች ተደርጎ የተወሰደ

ማንኛውም ሰው ሕይወት በአንድ ነገር ግፊት ይመራል። ብዙ መዝገበ ቃላት «አንቀሳቀሰ» ለሚለው ግሥ፦ መራ፤ ተቆጣጠረ ወይም አቅጣጫን ወሰነ» የሚል ፍቺ ይሰጡታል። መኪናም ነዳህ፤ ሚስማር በመዶሻ መታህ ወይም ኳስ አንከባለልህ፤ በዚያን ወቅት ያንን ነገር እየመራህ፤ እየተቆጣጠርክና አቅጣጫውን እየወሰንክ ነው። ታዲያ ልክ እንዲሁ ሕይወትህን የሚመራው ኃይል ምንድነው?
   በአሁኑ ጊዜ በአንድ በሆነ ችግር በሆነ ጫና፤ ወይም ማለቅ ያለበትን ሥራ ለመጨረስ በጥድፊያ በመራመድና በመንቀሳቀስ ላይ ትገኝ ይሆናል። በክፉ ትዝታ፤ በአስበርጋጊ ፍርሃት ወይም በቅጡ ባልገባህ አንድ ኅሊናዊ እምነት ትመራ ይሆናል። ሕይወትህን ሊያንቀሳቅሱና ሊመሩ የሚችሉ ብዙ ሁኔታዎች፤ የሕይወት ፋይዳዎችና ስሜቶች አሉ። ቀጥሎ የተዘረዘሩት አምስቱ /5/ በጣም የተለመዱና የታወቁ ናቸው።
1/ ብዙ ሰዎች በበደለኛነት ስሜት ይመራሉ።
እንዲህ ያሉ ሰዎች ዘመናቸውን ሁሉ ጸጸትና ቁጭት ከወለደው ሃፍረታቸው ለመሸሸግ ሲሸሹ ይኖራሉ። ቁጭትና ጸጸት የሚመራቸው ሰዎች የትዝታ ተጠቂዎች ናቸው። ያለፈው ሕይወታቸው መጪውን ህይወታቸውን እንዲቆጣጠረው ይፈቅዱለታል። ብዙውን ጊዜ ሳያውቁት የሕይወት ስኬታቸውን እያበላሹ እራሳቸውን ይቀጣሉ። ቃየል ኃጢአትን በሠራ ጊዜ በደሉ ከእግዚአብሔር ህልውና ለየው፤ እግዚአብሔርም እንዲህ አለው፦ «በምድር ላይ ኮብላይና ተንከራታች ትሆናለህ» ዘፍ 412። ይህ ቃል በዘመናችን ያለ ዓላማ በሕይወት ጎዳና የሚንከራተቱ ብዙ ሰዎችን ይገልጣል።
  ምንም እንኳን የዛሬ ኑሯችን የትናንት ውጤት ቢሆንም፤ የትናንት ኑሯችን ግን የዛሬ እስረኞች ሊያደርገን አይገባም። ምክንያቱም እግዚአብሔር ዓላማ ባለፈው ሕይወትህ የሚወሰን አይደለም። እግዚአብሔር ሙሴ የተባለውን ሰው ገዳይ የነበረ ወደ ሕዝብ መሪነት፤ ጌዴዎን የተባለው ፈሪ ደግሞ ወደ ደፋር ጀግና ለውጧቸዋል። በአንተ ቀሪ ሕይወትም እንዲሁ አስደናቂ ነገሮችን ሊያደርግ ይችላል። እግዚአብሔር ለሰዎች አዲስ የሕይወት ጅማሬ በመስጠት የተካነ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል። «መተላለፉ የተከደነለት፤ ኃጢአቱም የተሸነፈችለት እንዴት ብሩክ ነው» መዝ 321
2/ ብዙ ሰዎች በቂምና በቁጣ ይመራሉ።
እንዲህ ያሉ ሰዎች ደረሰብን የሚሉትን ጉዳት ከማስወገድ ይልቅ አቅፈውት ይኖራሉ። የጉዳታቸውን ስቃይ በይቅርታ ከማስወገድ ይልቅ በመደጋገም ያብሰለስሉታል። አንዳንዶቹ ደግሞ ዝም በማለት ንዴታቸውን ውስጣቸውን  «አምቀው» ይይዙታል። የቀሩት ደግሞ የታመቀ ቁጣቸውን «በማፈንዳት» በሌሎች ላይ ያምባርቃሉ። እነዚህ ሁሉ አጸፋዎች ጤናማ ያልሆኑ የማይጠቅሙ ናቸው።
  የአንተ ቂም መያዝ፤ ቂም በያዝክበት ሰው ላይ ከሚያደርሰው ጉዳት ይበልጥ የሚጎዳው አንተን ነው። የጎዳህ ወይም ያስቀየመህ ሰው ድርጊቱን ረስቶ የራሱን ኑሮ እየመራ ይሆናል፤ አንተ ግን ያለፈውን ቂም አምቀህ በመያዝ በብስጭት ትብሰለሰላለህ።
 ልብ በል! ከዚህ በፊት የጎዱህ ሰዎች አልጥል ባልከው የገዛ ቂምህ ካልሆነ በቀር እየጎዱህ ሊኖሩ አይችሉም። ያለፈው ነገርህ አልፏል። ማንም ሊቀይረው አይችልም። በመራርነትህ ራስህን ብቻ ነው የምትጎዳው። በቃ ለራስህ ስትል ካለፈው ተማርና ተወው። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፤ «ሞኙን ሰው ብስጭት ይገድለዋል፤ ቂሉንም ቅናት ያጠፋዋል» ኢዮብ 52
3/ ብዙ ሰዎች በፍርሃት ይመራሉ።
   እንዲህ ላሉ ሰዎች የሥጋታቸው ምክንያት ሊሆኑ የሚችሉት ነገሮች በሕይወታቸው ያሳለፉት አስፈሪ ጉዳት በእውነላይ ያልተመሠረተ ምኞትና ጉጉት፤ ቁጥጥር ባለበት ቤተሰብ ውስጥ ማደግ፤ ወይም በተፈጥሮ የመጣ ፍርሃት ያለባቸው ይሆኑ ይሆናል። ምክንያቱም ምንም ሆነ ምን በፍርሃት የሚኖሩ ሰዎች ድፍረት ከማጣታቸው የተነሳ ሁኔታዎችን ስለማይጋፈጡ ብዙ እድሎች ያመልጧቸዋል። ፍርሃትን በድፍረት ከማሸነፍ ይልቅ ችግር ካለበት ሁኔታ መሸሽንና ባሉበት ሁኔታ ውስጥ መቆየትን ይመርጣሉ።
ፍርሃት እግዚአብሔር ያቀደልህን እንዳትሆን የሚያደርግህና እራስህን ያስገባህበት እስር ቤት ነው። በፍቅርና በእምነት መሣሪያነት ልትጋፈጠው ይገባል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ «በፍቅር ፍርሃት የለም፤ ፍጹም ፍቅር ግን ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል፤ ፍርሃት ከቅጣት ጋር የተያያዘ ነውና፤ የሚፈራም ሰው ፍቅሩ ፍጹም አይደለም።
4/ ብዙ ሰዎች ለመበልጸግ ባላቸው ምኞት ይመራሉ።
እንዲህ ያሉት ሰዎች የሕይወታቸው ዋና ግብ ሀብት ማግኘት ነው። እንዲህ ያለው ሁልጊዜ ሀብት የመፈለግ ግፊት የሚመነጨው ብዙ ሀብት ሲኖረኝ ይበልጥ ደስተኛ፤ ይበልጥ ታዋቂና ዋስትና ያለኝ እሆናለሁ ከሚል የተሳሳተ አመለካከት ነው። እነዚህ ሦስቱም አስተሳሰቦች ስህተት ናቸው። ሀብት ሊያስገኝ የሚችለው ጊዜያዊ ደስታን ነው። ምክንያቱም ቁሳዊ ነገሮች ስለማይለወጡ ያሰለቹናል። በመሆኑም አዳዲስ ትልልቅና የተሻሉ ነገሮችን እንደገና እንፈልጋለን።

Sunday, September 30, 2012

ክርስቲያን በፖለቲካ ውስጥ በንቃት መሳተፍ ይኖርበታልን?

                                             ከተስፋዬ ሮበሌ
                                                              ወርኀ ጥር 2004 .
                                                                                                         እንደ ኢትዮጵያውያን የዘመን አቈጣጠር
                                                                                                         ግራንድ ራፒድስ ፣ ሚሽገን

በአንድ መስቀለኛ መንገድ ላይ በየቀኑ አሠቃቂ አደጋ ይከሠታል፤ ከአደጋው የተነሣም በርካታ ሰዎች ይሞታሉ፤ ከፍተኛ ንብረትም ይወድማል፡፡ ሁኔታው ያሳሰባት፣ በዚህ አካባቢ የምትገኝ አንዲት ቤተ ክርስቲያን፣ የአደጋው ሰለባ የሆኑትን ሰዎች የሚረዱ ሐኪሞችንና ነርሶችን በማሠማራት የአካባቢውን ማኅበረሰብ በንቃት ማገልገሉን ሥራዬ ብላ ተያያዘችው፡፡ የሕዝብና የመኪና ቊጥር ዕለት በዕለት እየጨመረ በመሄዱ ምክንያት ግን፣ ችግሩ በዛው መጠን ተባብሶ ቀጠለ፡፡ ይህች ቤተ ክርስቲያን እርዳታዋን በመጠንና በዐይነት ማሳደግ ብቻ ሳይሆን፣ አንድ መለስተኛ ሆስፒታል አደጋው በሚከሠትበት አካባቢ አቋቋመች፡፡ ይህ ሠናይ ምግባር የሰለባዎቹን ጤንነትና ሕይወት ከመታደግ አንጻር ብዙ ጠቀሜታ ቢኖረውም፣ ችግሩን ግን ከምንጩ ማድረቅ አልቻለም፡፡ ምክንያቱም የችግሩ ምንጭ የተሳሳተ የመንገድ ዲዛይን ነውና፡፡ በመስኩ የሠለጠኑ መሐንዲሶች መንገዱ በአዲስ መልክ ዲዛይን ቢደረግ ችግሩ ሊፈታ እንደሚችል የትራፊክ ፖሊስ ጽሕፈት ቤቱን በቃልም ሆነ በጽሑፍ ቢያሳስቡም፣ ባልታወቀ ምክንያት ጽሕፈት ቤቱ ጆሮ ዳባ ልበስ አለ፡፡ በየዘመናቱ ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስ ሰጠኝ የምትለውን ዐደራ ከዳር ለማድረስ፣ በሚያስፈልገው ሁሉ በመውተርተር ላይ ትገኛለች፡፡ ቤተ ክርስቲያን ነዳያንን በማብላት፣ የታመሙትን በማስታመም፣ ለመበለቶች ዳኛ በመሆን ጥልቅ ስም አላት፡፡ በርግጥም ቤተ ክርስቲያን የምስካየ ኅዙናን መንበር ናት፡፡ ወደ ፊትም ይህንኑ ግብረ ሠናይ ምግባሯን አጠናክራ መቀጠል እንዳለባት አያጠያይቅም፡፡ ነገር ግን ችግሩን በዘላቂነት መፍታት የምትችለው የተሳሳተ ፖሊሲ ያስከተለውን ፍሬ በመልቀም ብቻ ሳይሆን፣ መንግሥት ትክክለኛ ፖሊሲ እንዲነድፍ ስታስተምር፣ መንግሥት ሲሳሳትም ስሕተቱን ስሕተት ነው ማለት ድፍረትና ክህሎት ሲኖራት ብቻ ነው፡፡
ፖለቲካ፣ የሕዝብ አስተዳደር መዘውር ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የመዘውሩ ነገር ምን ተዳዬ የምትል ከሆነ ግን፣ በመዘውሩ እክል ምክንያት በሚከሠቱ ችግሮች ላይ ብቻ መጠመዷ አይቀሬ ነው፡፡ ይህ አስተሳሰብ በክርስቲያኑ ማኅበረሰብ ውስጥ ሠርጾ በመዝለቁ ምክንያት፣ ወደ ፖለቲካው ዓለም የሚገቡ ወይም የፖለቲካ ሳይንስ የሚያጠኑ የቤተ ክርስቲያን ልጆች፣ ከመንፈሳዊነት እንደ ጐደሉ ምናልባትም ክርስቶስን ከመከተል እንዳፈገፈጉ ይታሰባል፡፡ ክርስቲያን የዓለም ብርሃንነው፣ የዓለም ጨውነው የሚለው የቃለ እግዚአብሔር ትምህርት፣ በፖለቲካ ሕይወት ውስጥ ጨለማና አልጫ ነው ያለው ማነው? እንዲያውም ክርስቲያኖች በንቃት ሊሳተፉበት የሚገባ፣ ጨውነታቸውንና ብርሃንነታቸውን ሊገልጡበት የሚገባው የሕይወት ክፍል ፖለቲካ ነው፡፡ እንደ ንጉሥ ዳዊት፣ እንደ ንጉሥ ሰሎሞን ያሉ የእምነት አበው ፖለቲከኞች ነበሩ፡፡ እንደ ነቢዩ ናታን፣ ነቢዩ ኢሳይያስ፣ ነቢዩ ዳንኤል፣ ነቢዩ አሞጽ ወዘተ ያሉ ነቢያት ደግሞ መንግሥትን በማማከር አገልግለው እንዳለፉ ገድላቸው የናገራል፡፡ መንግሥት ሲስት ይገሥጹና ከስሕተቱ እንዲመለስ መንገድ የመላክቱ እንደ ነበር ቅዱስ ቃሉ ያስተምረናል፡፡ እንዲያውም ባልንጀራህን/ጐረቤትህን እንደ ራስህ ውደድ የሚለው የክርስቶስ ቃል ከየትኛውም የትምህርት ዘርፍ ይልቅ ፖለቲካን የሚያመላክት ነው (ማቴዎስ 22÷39)፡፡ ለተጠቃው ከመጮኽ፣ የታረዘውን ከማልበስ፣ ፍትሕ ያጣውን ለፍትሑ ከመሟገት በላይ ምን ጐረቤትን መውደድ አለ? እግዚአብሔር አምላክ ለንጉሥ ሰሎሞን የሰጠው ስጦታ የፖለቲካ ስጦታ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ፖለቲካ የጸጋ ስጦታ መሆኑን የሚያጸና ነው፡፡
ወገኖቼ ክርስትና የማይዳስሰው የሕይወት ክፍል የለም፡፡ ክርስቲያኖች በፖለቲካው ውስጥ በመግባት ብርሃንና ጨው መሆን ካልቻሉ፣ ክርስቲያን ያልሆኑና እኵይ ሥነ ምግባር ያለቸው ሰዎች የፖለቲካውን መድረክ መቈጣጠራቸው አይቀሬ ነው፡፡ እየሆነም ያለ ይመስላል፡፡ ወገኖቼ፣ ኀጥኣን ከፍ ከፍ ሲሉ ሕዝብ ይጨነቃልየሚለው የጠቢቡ ሰሎሞን አነጋገር ፖለቲካን ታሳቢ ያደረገ ነው፡፡ ወዲህም ወዲያም ብታገላብጡት ሐቁ ይኸው ነው፡፡ ክርስትናና ፖለቲካ ዐይንና ናጫ ናቸው ወዘተረፈ የሚለው ወልጋዳ አስተሳሰብ የብዙዎችን ጐዳና አሰናክሏል፡፡ ከዚህም የተነሣ ብዙ የቤተ ክርስቲያን ልጆች፣ ስለ ፖለቲካ ያለን ዕውቀት በየጋዜጣው ላይ ከሚጻፉ መጣጥፎች አንዲሁም በየዜና አውታሮች ከሚተላለፉ ፕሮግራሞች የዘለለ አይደለም፡፡ ይህ ዐይነቱ ዕውቀት ደግሞ፣ ለፕሮፖጋንዳ ውዥንብር በቀላሉ ይዳረጋል፡፡ ቃላትን ቀምሮና እውነትን አስታኮ የመጣ ብልጣብልጥ ፖለቲካኛ ሁሉ ወዳሻው ቦታ ይዞት ይሄዳል፡፡ ወደድንም ጠላንም የአገሬ ጕዳይ ግድ ይለኛልየምንል ሰዎች ሁሉ፣ ቢያንስ መሠረታውያን የሚባሉትን የፖለቲካ መርሖች በቅጡ ልናውቃቸው ግድ ነው፡፡ ለምሳሌ ፖለቲካ በአገር ግንባታ ውስጥ ያለው ቦታ እስከምን ድረስ ነው? ሰብአዊ መብት ማለት ምን ማለት ነው? ኢሕአዴግ፣ አብዮታዊ ዴሞክራሲብሎ የሚጠራው የፖለቲካ አካሄድ፣ ከምዕራባውያኑ ለዘብተኛ (ሊብራል) ዴሞክራሲ በምን ይለያል?
ይህ የፖለቲካ ፍልስፍና በአገሪቱ ፖለቲካና ምጣኔ ሀብት የሚያስከትለው አሉታዊ መዘዝም ሆነ አዎንታዊ እንድምታ እንዴት ይተነተናል? ክርስቲያኖች በፖለቲካ ውስጥ ተሳትፎ ማድረግ አለባቸው ወይስ የዳር ታዛቢ መሆናቸው ብቻ ጥሩ ዜጋ ያሰኛቸዋል? ሕዝባዊና ማኅበራዊ ተቋማት ማለትም የመገናኛ ብዙኃን፣ ፖሊስ፣ ፍርድ ቤቶችና የምርጫ ቦርድ ከመንግሥት ጣልቃ ገብነት ፍጹም ነጻ መሆን አለባቸውየሚባለው ለምንድን ነው? ነጻናቸው የሚባል ከሆነስ ደግሞ ነጻነታቸው በምን መስፈርት ይለካል? ፖለቲካ ለምጣኔ ሀብት ሕግጋት ይገዛል ወይስ ምጣኔ ሀብት ለፖለቲካ ሎሌ ያድራል? ወይስ ሁለቱም ለየቅል ናቸው? አንድ አገር ፖለቲካ ሰብአዊ መብትን እንዳሻው እየጨፈለቀ የምጣኔ ሀብት በረከት ሊያመጣ ይችላል? የማይቻል ከሆነ የቻይና ጕዳይ እንዴት ይታያል? የመናገር መብት፣ የመጻፍ መብት፣ የመደራጀት መብት ወዘተ የሚባሉት ጕዳዮች፣ በሰብአውያን ሕይወትና ዕድገት ውስጥ ያለቸው ስፍራ ምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ፖለቲካ የሚያስተምረው ትምህርት ምንድን ነው

Saturday, September 29, 2012

በሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ የሃይማኖት ብሔርተኝነት አደገኛ ነው!

«መጪውን ጊዜ በሃይማኖት ብሔርተኝነት መዋጀት» ይገባል። (ማኅበረ ቅዱሳን )

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 1 2005 ዓ.ም.
ሃይማኖታዊ ብሔርተኝነት ማለት ምን ማለት ነው?
በሳንዲያጎ ግሮስሞንት ኰሌጅ ፕሮፌሰር የሆኑት ዶ/ር ጆን ኦክስ የሃይማኖት ብሔርተኝነትን በተነተኑበት ጽሁፋቸው እንዲህ ሲሉ ያስቀምጣሉ። የሃይማኖት ብሔርተኝነት /Religious Nationalism/ የሚከተሉትን አራት ባህርያት ያሟላ ወይም ለማሟላት የሚሰራ ሲሆን በአንድ ሀገር ውስጥ ህልውናው ይረጋግጣል ይላሉ።
1/ የሀገሪቱ መንግሥት ለአንድ የተለየ  የሃይማኖት ተቋም ብቻ የእለት ከእለት እንቅስቃሴ የገንዘብ ድጋፍ የሚሰጥ ከሆነ፣
2/ የሃይማኖቱ ተቋም፦ ሞራልን፤ ግብረ ገብንና ሥነ ምግባርን በተመለከቱ በመንግሥታዊው ጉዳዮች ላይ ጫና ማሳረፍ ከቻለ፤
3/  በሀገሪቱ ውስጥ ያሉ ሌሎች ሃይማኖቶች በመንግሥት የሚደገፈውን ሃይማኖት መብት መጠበቅ ከተገደዱ፤
4/ መንግሥታዊ ድጋፍ ያለው ይህ ልዩ ሃይማኖት በፖለቲካው መስክ የመንግሥቱ ደጋፊ ሲሆን  በአንድ ሀገር ውስጥ የሃይማኖት ብሔርተኝነት አለ ማለት ይቻላል በማለት ያብራራሉ።
ለምሳሌ ኢራን፤
በኢራን ውስጥ ክርስቲያኖች፤ ቡድሂስቶችና አይሁዳውያን ያሉ ቢሆንም መንግሥታዊው ሃይማኖት ግን እስልምና ነው። እስልምናው በመንግስት በጀት ይደገፋል፤ ሃይማኖታዊውን ተቋም የሚጻረር አንድም ሕግ አይወጣም፤ ሌሎች ሃይማኖቶች የእስልምናን ብሔራዊነት የበላይነት የመጠበቅ ግዴታ አለባቸው ( ከእስልምና ሰው ሰብከው ቢወስዱ ይቀጣሉ፤ እስልምና ግን ከእነሱ ሰብኮ ቢወስድ አይጠየቅም)፤ መንግሥታዊው ሥልጣን  ከእስላም ሰዎች እጅ እንዳይወጣ ሃይማኖቱ ድጋፍ ይሰጣል።
ግሪክና፤ ራሺያም በተወሰነ መልኩ ተመሳሳይ ሃይማኖታዊ ብሔርተኝነት ይታይባቸዋል። በሀገሪቱ ውስጥ ብዙ ሃይማኖታዊ ሰዎች ቢኖሩም የመንግሥቱን ስልጣን የሚረከበው ሰው ቃለ መሃላ የሚፈጽመው በመንግሥቱ ተቀባይነት ባለውና በሚደገፈው የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ውስጥ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እጁን ጭኖ እንጂ በፌዴራሉ ዳኛና በዱማው ፊት ብቻ አይደለም።
የሃይማኖት ብሔርተኝነት /Religious Nationalism/ በራሱ ሃይማኖታዊ ተቋም ውስጥ የተለየ ሃሳብና ጥያቄን ለማስተናገድ በፍጹም ቦታ አይሰጥም ብቻ ሳይሆን ባለው የኃይል ተደማጭነት የተነሳ ልዩ ሃሳብና ጥያቄ ወይም ተቃውሞ አቅራቢዎችን የመጨፍለቅና የማስጨፍለቅ አቅም አለው።
ለምሳሌ ኢትዮጵያ ውስጥ ወደ ሃይማኖት ብሔርተኝነት ጎዳና እያዘገመ ያለው ማኅበረ ቅዱሳን የተለየ ሃሳብና አቋምን የማይቀበልና እንደነዚህ ዓይነት ልዩነቶች ለማስተናገድ ስለማይችል የሚወስደው እርምጃ  ማስደብደብ፤ ማሳሰር ብሎም ከተመቸው ማስገደል ነው። በመምህር ጽጌ ስጦታውና በዲ/ን ሙሉጌታ ወ/ገብርኤል ላይ የደረሰውን ድብደባ ማስታወስ ይሏል።
ብሔር ማለት በቁሙ ወሰን፤ ክልል፤ድንበር፤ ጠረፍ ያለው  ሀገር ማለት ነው። የሃይማኖት ብሔርተኝነት ማለትም የራሱ ድንበር፤ አጥር፤ክልል ወሰን ያለው የሃይማኖት ተቋም  ማለት ነው። የኮርኔል ዩኒቨርሲቲ የስነ ሃይማኖት ሌክቸረር ማይክል ኤሪክ ዳይሰን ስለሃይማኖት ብሔርተኝነት እንደዚህ ይላሉ። "No religion has a particular right on the nation»  በሀገሪቱ ውስጥ የተለየ መብት ያለው ሃይማኖት የለም»
ታዲያ የሃይማኖት ብሔርተኝነትን ማኅበረ ቅዱሳን የሚያቀነቅነው ለምንድነው? ምናልባት ከአባ ጳውሎስ በኋላ የፓትርያርክነቱ  ተራ የወሎዬዎች ነው እየተባለ የሚዘፈነውን በመስማቱ ሃይማኖታዊ ብሔር እንጂ ጎጣዊ ብሔር በቤተክርስቲያን የለም ለማለት ፈልጎ ይሆን?  የብሔር ድጋፍና ጥላቻ እንግዳ ነገር አልነበረምና ሹመቶቹን ሁሉ በእግዚአብሔር ፈቃድ ላይ ማላከክ ተገቢ አይደለም። የእግዚአብሔርን ፈቃድና እውቅና ማቀላቀል አይገባም። ሰዎች የእግዚአብሔርን ፈቃድ ሲከተሉ፤ ፈቃዱ ይፈጸምላቸዋል። የልባቸውን አሳብ ሲከተሉ ደግሞ  የልባቸውን መንገድ እንዲሄዱ እግዚአብሔር እውቅና ይሰጣቸዋል እንጂ በሁሉም ሹመቶች ላይ የእግዚአብሔር ፈቃድ የለም።
እንደ ልባቸው ሥራ ተውኋቸው፥ በልባቸውም አሳብ ሄዱ» መዝ 81፤12
እስራኤላውያን ሳኦል ይነግስ ዘንድ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ባይሆንም የልባቸውን አሳብ አይቶ ሳሙኤል ቀብቶ እንዲያነግስላቸው እግዚአብሔር እውቅናውን ሰጥቷል።
« እግዚአብሔርም ሳሙኤልን አለው። በእነርሱ ላይ እንዳልነግሥ እኔን እንጂ አንተን አልናቁምና በሚሉህ ነገር ሁሉ የሕዝቡን ቃል ስማ» 1ኛ ሳሙ 8፤7
ስለዚህ ሰዎች በቡድንና በጎጥ እየተደራጁ የሚያደርጓቸውን ሹመቶች ሁሉ በእግዚአብሔር ፈቃድ እንደተፈጸመ ለማድረግ ቢሞክሩ ከእግዚአብሔር ቃል አንጻር ሚዛን አይደፋም።  እንደማኅበረ ቅዱሳን ዜና ዘገባ ከዚህ በፊት በቡድንና በፖለቲካ ድጋፍ የተደረገ የፓትርያርክ ሹመት እንዳልነበረ  በመቁጠርና ዛሬ እንደዚህ ዓይነት አስተሳሰብ መከሰቱን በሚያሳብቅ መልኩ የሃይማኖት ብሔርተኝነትን ወደማራገብ መሸጋገሩ ጉንጭ አልፋ ስነ ሞገት ከመሆን አያልፍም። ምክንያቱም በሁላችንም ዘንድ ያለው እውቀት ያንን አያሳይምና ነው። ያለን መረዳት ከዚህ በፊት የቡድን ወይም የፖለቲካ ድጋፍ እንደነበረ ሲሆን የከዚህ በፊቱ የቡድንና የፖለቲካ ድጋፍ ምርጫ መቀጠል የለበትም ነው ሊባል የሚችለው። ይህ እውን ሊሆን የሚችለው ደግሞ በእግዚአብሔር ላይ በመታመን እንደ ሐዋርያው ማትያስ ምርጫ በመንፈስ ቅዱስ እጣ ሰጪነት  ላይ በመጽናት ብቻ ነው። (ሐዋርያም ማትያስ አልኩኝ እንጁ አባ ማትያስ ዘካናዳ ወይም አባ ማትያስ ዘአሜሪካው አላልኩም)። ምርጫ ምንም ዓይነት «የሃይማኖት ብሔርተኝነት» ሳይጨመርበት መሆን ይገባዋል። ሃይማኖታዊ ብሄርተኝነት የሚታመነው በሃይማኖታዊ ወግና ባህል ላይ እንጂ በእግዚአብሔር አሠራር ላይ ስላይደለ የከዚህ በፊቶቹ  ስህተቶች እንዳይደገሙ ለማድረግ ዋስትና አይሰጥም።
ከዚህ አንጻር ማኅበረ ቅዱሳን በሃይማኖት ብሔርተኝነት እንቁም በማለት ጥሪ ሲያቀርብ ምን ማለቱ ነው?
ሁሉም ሃይማኖት የየራሱን እምነት አጥብቆ መያዝና መከተል ባህርያዊ ነው። ነገር ግን ችግሩ የሚመጣው «የኔ ብቻ» የሚል ጽንፍ ሲከተለው ነው። እግዚአብሔር አሜሪካና ሕዝቧን ይባርክ ማለት ለራስ የማሰብ አንድ አካል ነው። ነገር ግን እግዚአብሔር አሜሪካና ሕዝቧን ባርኳል ማለት ሌላ ነገር ሲሆን ይህም «እኔ ብቻ» የሚለው ጽንፍ «ኢራንን አልባረከም» እንደማለት በመሆኑ ራስን በሁሉን ዓቀፍነት ዓይነት ማየት አደገኛ ነው በማለት የኮርኔሉ ሌክቸረር ዳይሰን ያሰምሩበታል።
« Religious nationalism can also give a sense of exclusivity»

Wednesday, September 26, 2012


ውድ የደጀ ብርሃን ብሎግ ተከታታዮች፤

በፅሑፍ፤በሃሳብ፤ በገንቢ አስተያየት፤ ትችትና ነቀፋ አብራችሁን ለዘለቃችሁ ሁሉ በእግዚአብሔር ስም እጅግ በጣም እናመሰግናለን።

"....ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያውያንስ ምን ተናግረው ይሆን?

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ እና ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ በእስትንፋሳቸው መጨረሻ ስለ ራሳቸው፣ ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያውያንስ ምን ተናግረው ይሆን…?

ይህ መጣጥፍ በሪፖርተር ጋዜጣ የእሁድ እትም በፍቅር ለይኩን የተባሉ ጸሐፊ ካስነበቡት ጹሑፍ ለጦማራችን በሚመስማማ መልኩ መጠነኛ ማሰተካከያ ተደርጎበት የተወሰደ ነው፡፡

 ‹‹እግዚአብሔር ሆይ ሁሉንም ነገር ለአንተ እተዋለሁ. . . አሜን!›› (በቅርቡ የሞቱት የጋናው ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ሚልስ ከመሞታቸው በፊት ከተናገሩት የተወሰደ፡፡)
ሞት የሰው ልጆች ሁሉ አይቀሬ የሆነ የሕይወት ዕጣ ፈንታ ነው፡፡ ትልቁ ቁም ነገር በምድር ላይ በኖርንበት ወይም እንድንኖርበት በተሰጠን ዘመን የሠራነው ደግ/መልካምም ሆነ ክፉ ሥራችን ግን ሁሌም ከመቃብር በላይ ቋሚ ሀውልታችን ወይም ቅርሳችን ሆኖ እንድንታወስ ሊያደርገን እንደሚችል በቅጡ ማሰብ ይመስለኛል፡፡
ሰዎች ስለ ሞት የተለያየ አመለካከት አላቸው፡፡ ለአንዶንዶች ሞት ትርጉም የለሽ ጸጥታ ነው፡፡ ለሌሎች ደግሞ ሞት ዘላለማዊ እረፍት ነው፡፡ ለአንዳንዶች ሞት ምስጢራዊ እና ረቂቅ ነገር ነው፡፡ በክርስትናው ዓለም ውስጥ ላለን በርካቶች ደግሞ ሞት ወደ ዘላለማዊው፣ ፍፁም ሰላም እና እረፍትን ወደ ተሞላው ሰማያዊ ዓለም እንደ መሸጋገሪያ ድልድይ የሚቆጠር ነው፡፡
ስለ ሞት ያለን ግንዛቤ፣ ትንታኔ እና ፍልስፍና እንዳለንበት እና እዳደግንበት ማኅበረሰብ የኑሮ ልማድ፣ ባሕል እና እምነት/ሃይማኖት የተለያየ ፍቺ ይሰጠዋል፡፡ ሞት የቅርባችን እና የዕለት ተዕለት ክስተት የመሆኑን ያህል በአንፃሩ ደግሞ መቼም የማይለመድ እንግዳ ክስተት ሆኖ መቀጠሉ ለብዙዎቻችን እንቆቅልሽ ነው፡፡ ምነው በአዲሱ ዘመን፣ በወርኻ አደይ፣ ምድር፣ ተራሮች እና ሜዳዎች፣ ጋራ እና ሸንተረሩ በአበቦች አምረውና ተውበው በሚያጌጡበት፣ ሰዎች ሁሉ በአዲስ ራእይ ሕይወትን ውብ እና ፍቅርን የተሞላች ለማድረግ ብሩህ ተስፋን ሰንቀው ‹‹ጉልበቴ በርታ በርታ!›› በሚሉበት ውብ እና ተወዳጅ በሆነችው በወርኻ መስከረም ምን ነክቶህ ነው እንዲህ ሞት ሞት የሚሸት ጹሑፍ ምነው!? እረ…! ደግም አይደል የሚሉኝ ሰዎች አይጠፉም ብዬ እገምታለሁ፡፡
ግና ወደድንም ጠላንም መራሩ እውነታ ሞት ለሁላችንም የማይቀር ዕዳ መሆኑ ነው፡፡ ሞት የሁላችንም ዕጣ ፈንታ መሆኑ ማንኛችንም ብንሆን ለአፍታም ያህል ቢሆን እንዘነገዋለን ብዬ ለመናገር አልደፍርም፡፡ ስለዚህም ሞት ሲመጣ አማክሮ፣ ጊዜ እና ወቅትን ተከትሎ አይደለምና ስለ ሞት ለማውራት ምቹ ጊዜ፣ የተመረጠ ሰዓት ሊኖር ይችላል ብዬ አላስብም፡፡ ሞት አዲስ ዘመን፣ ወርኻ ክረምት፣ በጋ ወይም ጸደይ፣ ትንሽ፣ ትልቅ፣ መሪ ተመሪ፣ ንጉሥ፣ አገልጋይ፣ ሕጻን፣ አዛውንት… ወዘተ አይልምና፤ ለዚህም ነው በለመለመ ብሩህ ተስፋ እና ራእይ ሕይወትን ውብ እና ጣፋጭ ለማድረግ መልካም ምኞታችንን በምንገልጽበት በአዲሱ ዘመን መባቻ ስለ ሞት ለማውራት መጨከኔ፡፡
    የዕብራውያን ጸሐፊ የሆነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱም በኋላ ፍርድ ተመደቦባቸዋል፡፡›› (ዕብ ፱፣፳፯) በማለት የሞትን አይቀሬነት ያስገነዝበናል፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ እንደገናም በሮሜ መልእክቱ፡- ‹‹በአዳም ኃጢአት ምክንያት ሞት በሰው ልጆች ሁሉ ላይ መንገሱን እና የዚህ የሞት ኃይል በክርስቶስ ኢየሱስ ሞት ድል መነሳቱን እና በክርስቶስ ሞት ምእመናን የዘላለም ሕይወትን እንደታደሉ›› እንዲህ ይተርካል፡- ‹‹በአንዱም (በአዳም) በደል ሞት በአንዱ በኩል ከነገሠ፣ ይልቁን የጸጋን ብዛት እና የጽድቅን ስጦታ ብዛት የሚቀበሉ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሣሉ፡፡›› (ሮሜ ፭፣፲፯) ይለናል፡፡

   ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በወንድሟ በአልዓዛር ሞት እጅጉን ልቧ ተሰብሮ እና ሁለንተናዋ በሀዘን ደቆ በእግሩ ሥር ተደፍታ እያነባች፡- ‹‹ጌታ ሆይ አንተ በዚህ ኖረህ ቢሆን ኖሮ ወንድሜ ባለሞተ ነበር!›› ላለችው ለማርታ፡- ኢየሱስም፡- ‹‹ትንሣኤ እና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳን ሕያው ይሆናል፡፡›› በማለት በእርሱ (በሕያው እግዚአብሔር ልጅ) የሚያምኑ ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዳላቸው በቃሉ አረጋገጦላታል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በቅዳሴው ‹‹ሞትን ይሽረው ዘንድ ሞተ!›› በማለት የሞት ኃይል በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ሞት ለዘላለም መሻሩን ይመሰክራል፡፡
ሞት በክርስቶስ ላመኑ በፍፁም የሚያስፈራ እና የሚያስጨንቅ ነገር አይደለም፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹ለእኔስ ወደ ጌታዬ መሄድ ይሻለኛል ይህንንም እናፍቃለሁ፡፡›› ሲል ሞቱን ወደ ጌታው እና አምላኩ የሚሻገርበት ድልድይ እንደሆነ ለፊሊጵስዩስ ክርስቶሳውያን የወንጌል ልጆቹ በላከላቸው መልእክቱ በግልፅ ነግሯቸዋል፡፡ እናም ሞት በክርስቲያኖች ዘንድ አስፈሪ እና አሳፋሪ አይደለም፣ ሊሆንም አይችልም፣ ሆኖም አያውቅም፡፡ የቀደሙት አባቶቻችን የወንጌል አርበኞች፣ ጻድቃን እና ሰማዕታት ሞታቸውን እግዚአብሔር አምላካቸውን በዝማሬ እያመሰገኑ፣ እያመለኩ፣ በታላቅ ደስታ እና በጸጋ ነው የተቀበሉት፡፡
ወደ ተነሳሁበት ወደ ርዕሰ ጉዳይ ስመለስ 2004 ዓ.ም በሀገራችን በሃይማኖት፣ በሥነ ጥበብ እና በፖለቲካው መስክ አንቱ የተባሉ ሰዎችን ያጣንበት ዘመን ነው፡፡ በተለይም ደግሞ ወርኻ ነሀሴ ከሕይወት ጋር ግብ ግብ የገጠመ በሚመስል አስገራሚ ጥድፊያ፣ ዓመቱ ከማለቁ በፊት ሳልቀደም ልቅደም ያለ ይመስል በዓመቱ መጨረሻ በወርኻ ነሀሴ ሁለት ታላላቅ መሪዎችን በሳምንት ልዩነት ውስጥ ያጣንበት እንደ አየሩ ጠባይ ሁሉ ጨፍጋጋ እና አስደንጋጭ ወር ሆኖ አልፏል፡፡    
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ን አባት እና መሪ የሆኑት ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እና የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚ/ር አቶ መለስ ዜናዊ የተከታተሉበት የሞት መርዶ ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያውያንን ከዳር እስከ ዳር ያነጋገረ እና የሀዘን ከል ያለበሰ ክስተት ሆኖ አልፏል፡፡
በዚህ የሞት ክፉ ዜና የተነሳ በሀገራችን ያረበበው የሀዘኑ ድባብ እንደ ሰማዩ ደመና ገና ሙሉ በሙሉ የተገፈፈ አይመስልም፡፡ አሁንም ድረስ የእነዚህ የቤተ መንግሥቱ እና የቤተ ክህነቱ መራኅያን ያልተጠበቀ የሞት ጥሪ ለብዙዎቻችን ባሰብነው ቁጥር እንቆቅልሽ እንደሆነብን ዘልቋል፡፡ ለአንዳንዶች በተመሳሳይ ወቅት በቤተ መንግሥቱ እና በቤተ ክህነቱ የተከሰተው ይህ ያልተጠበቅ የሞት ጥሪ ‹‹የእግዚአብሔር ቁጣ ነው›› እኛም ንስሀ እንግባ ዘንድ ያስፈልገናል በማለት የእግዚአብሔርን ታላቅነት እና ኃያልነት ዳግም እንዲያስቡ እና እንዲያስተውሉ እንዳደረጋቸው ሲናገሩ በአደባባይ ተደምጠዋል፡፡
ለሌሎች ወገኖቻችን ደግሞ የቤተ መንግሥቱ እና የቤተ ክህነቱ የሞት መርዶ ያው እንደተለመደው ተራ የፖለቲካ ጉንጭ አልፋ ወሬ ከመሆን አላለፈም፡፡ እናም አንዳንዶች ለሰሞኑ የቤተ መንግሥቱ እና የቤተ ክህነቱ ያልተጠበቀ የሞት ጥሪ ያልተገባ የስንፍ እና የፍርድ አስተያየት ከመሰጠት ባለፈ ሌላ አንድምታ እንዳልሰጡት በሰሞኑ ከሚነገሩ ወሬዎች፣ በማኅበረሰብ ድረ ገጾች እና በየብሎጉ ከሚጻፉ በርካታ ፍርድ አዘል ጹሑፎች እና አስተያየቶች ታዝበናል፡፡ እንዲያም ሲል ደግሞ እሰይ ስለቴ ሰመረ በሚል የሚያዜሙ እና ፍፁም ኢትዮጵያዊ ጨዋነት እና ባሕል በጎደለው ሁኔታ በእነዚህ መሪዎች ሞት ጮቤ እየረገጡ ያሉ ወገኖችንም እረ ምን ጉድ ነው እያልን ለመታዘብም በቅተናል፡፡ 
እንዲሁ እንደ ዋዛ ለህክምና በሚል ሰበብ እንደ ወጡ እስከ ወዲያኛው የተለዩንና ከአሁን ከአሁን ጤንነታቸው ተመልሶ ይመጣሉ በሚል ተስፋ የጠበቅናቸው ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ በስተመጨረሻ ለብዙዎቻችን ጆሮ የማይታመን የሆነውን የሞታቸውን መርዶ ዜና ለማመን እየቸገረንም ቢሆን ለመስማት ነበር የተገደድነው፡፡ ደህና ናቸው፣ ከህመማቸው እያገገሙ ነው፣ በአዲሱ ዓመት ሥራቸውን ይጀምራሉ የተባለላቸው ጠቅላይ ሚ/ር በድንገት በተከሰተ ኢንፌክሽን ምክንያት በድንገት ሞቱ መባላቸው አሁንም ድረስ ለብዙዎቻችን ኢትዮጵያውያን የጠቅላይ ሚ/ሩ ህመማቸው እና አሟሟታቸው ምስጢር ነው፡፡
በዚህ ጽሑፌ ለመዳሰስ የፈለግኩት የቤተ ክህነቱ እና የቤ መንግሥቱ መሪዎች በሕይወታቸው እስትንፋስ መጨረሻ ምን እንደተናገሩ በመጠየቅ የተነሳው የመጣጥፌ ርዕሰ ጉዳይ እንደ አለመታደል ሆኖ አትኩሮቱን ያደረገው በውጩ ዓለም ባሉ መሪዎች እና ታላላቅ ሰዎች ላይ ነው፡፡ የዚህ ዐቢይ ምክንያት ደግሞ በቅርብ በሞት የተለዩን ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስም ሆነ ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ በመጨረሻ የሕይወታቸው እስትንፋስ ምን እንዳሉ፣ ምን እንደተናገሩ እና ለሕዝባቸው ምን ዓይነት የመጨረሻ መልእክት እንዳስተላለፉ የነገረን ሰው ወይም እኔ ምስክር አለሁ የሚለን ሰው እሰካሁን አለመገኘቱ ነው፡፡
ፍቅርን፣ ይቅር ባይነትን/እርቅን፣ ግልፅነትን፣ ታማኝነትን… ወዘተ በቃላቸውም ሆነ በተግባራቸው የሚሰብኩ መሪዎች ድርቅ ክፉኛ የመታት እናት ኢትዮጵያ መሪዎቿ እና ሕዝቦቿ በቅጡ ሳይተዋወቁ እና በፍቅር ሳይቀራረቡ ማዶ ለማዶ እንደተያዩ በሞት እስከ ወዲያኛው የሚሸኙባት ምድር የመሆኗ ምስጢር ማብቂያው መቼ እንደሆነ ግራ የሚያጋባ ነው፡፡
በምስኪኗ ኢትዮጵያ መሪዎቻችን ብዙ ነገራቸው ለሕዝባቸው ምስጢር ነውና እነዚህ ለሁለት አሥርት ዓመታት በቤተ መንግሥቱ እና በቤተ ክህነቱ መሪዎች ሆነው ያስተዳደሩ ፓትርያርክ አባ ጳውሎስ እና ጠቅላይ ሚ/ር መለስ በእስትንፋሳቸው መጨረሻ ምን እንዳሉ ምን መልእክት እንዳስተላለፉ ለማወቅ አልታደልንምና ሳንወድ በግድ ቁጭት እና እልህ እየተፈታተነንም ቢሆን በጀመርኩት ርዕስ ስለ ባሕር ማዶዎቹ መሪዎችና ታላላቅ ሰዎች የመጨረሻ የሕይወታቸው እስትንፋስ መልእታቸው ላምራ፡፡
ከጠቅላይ ሚ/ር መለስ ከጥቂት ሣምንታት በፊት በሞት የተለዩት የጋናው ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ሚልስ በጉሮሮ ካንሰር በሽታ ምክንያት በአሜሪካ አገር ህክምና ያደረጉ ቢሆንም በቅርቡ ህመማቸው አገርሽቶ ወደ ሀገራቸው የጦር ኃይሎች ሆስፒታል ገብተው ሕክምና በመከታተል ላይ እያሉ ነበር ያረፉት፡፡ Web Ghana የተባለው ድረ-ገጽ ‹‹Mills’ Last Words Before He Died/የፕሬዝዳንት ሚልስ እልፈት እና ከመሞታቸው በፊት የተናገሩት የመጨረሻ ቃላቸው›› በሚል ርዕስ ባስነበበው ጹሑፍ ፕ/ር ሚልስ ከሞታቸው በፊት ካጠገባቸው የነበሩትን ወንድማቸውን ዶ/ር ካድማን ሚልስን በመጥቀስ የሚከተለውን ዘገባ አስነብቦ ነበር፡-
"Before my brother (Mills) died, the last words that he said that I clearly remember is that, he raised his hands in the air and he said ‘God, I leave it all to you, Amen’. I’ve no doubt that God heard his call. I’ve no doubt that he is now in the bosom of the Lord. I’ve no doubt that he’ll find eternal peace. Pray for him, and May God be with you, Fiifi," Dr Cadman Mills said.

Saturday, September 22, 2012

መንፈሳዊ ሃሳብ ላለው ሰው ሁሉ ከፓትርያርክ ምርጫ በፊት እርቅ ይቀድማል!

ስለእርቅ ብዙ ብዙ ተብሏል።  ሰዎች እርቅን ከሁኔታዎችና ከአዋጭነቱ አንጻር መዝነው ይፈጽማሉ። በእርቁ የሚያገኙትን ሂሳብ ቅድሚያ ያሰላሉ። አንድ የተጨበጠ ነገር ካላገኙ እርቅን ሰማያዊ ዋጋ ከማግኘት ጋር አያይዘው  ለመወሰን ይቸገራሉ። ብዙ እርቆች በዚህ መንገድ የሚከናወኑ ናቸው። ፖለቲከኞቹ እንኳን /Give & Take/ ሰጥቶ መቀበል ይሉታል። ይህ የሥጋዊ እሳቤ ውጤት በመሆኑ በዚህ እርቅ ምድራዊ ስምምነት ካልሆነ በስተቀር ከላይ ከአምላክ ዋጋ ያስገኛል በሚል ስላልሆነ ውጤቱ ጊዜያዊና ምድራዊ ነው። ሰማያዊ አስተሳሰብ ምን ጊዜም የእርቁን ጥቅም ከአዋጭነቱ ወይም ከሚያስገኘው የሚታይ ዋጋ በላይ በመሆኑ ለዚህ እርቅ ራስን የመስጠት ዋጋ እስኪከፈልበት ድረስ ግዴታን ያስከትላልና ከባድ ነው። እንኳን የበደሉትን፤ የበደለንን ይቅር እስከማለት የሚያደርስ ህግጋት ስለሆነ ሚዛናዊነቱ በመንፈስ ዓይን ብቻ የሚታይ ነው። በዘወትር ጸሎት «ከመ ንሕነኒ ንሕድግ ለዘአበሰ ለነ» እኛም የበደሉንን ይቅር እንደምንል…» እያልን በደላችንን ሁሉ በደሙ እንዳጠበው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛም የበደሉንን ይቅር እንላለን እያልን የምናውጀው የጸሎት አዋጅ ዋጋ የሚኖረው በእውነትም ለእርቅ የተዘጋጀ ልቡና ሲኖረን ነው። ያለበለዚያ እየዋሸንና ጌታችንንም ለዚህ ዋሾ አንደበታችን ተባባሪ እንዲሆነን እየጠራነው ካልሆነ በስተቀር  በተግባር ይቅርታ በሌለበት ልባችን ውስጥ መንፈስ ቅዱስ በምንም መልኩ ሊያድር አይችልም። ይቅርታ የሌለው ልቦና መንፈሳዊ አይደለም።


«እናንተ ግን ይቅር ባትሉ በሰማያት ያለው አባታችሁም ኃጢአታችሁን ይቅር አይላችሁም» ማር 11፤26

ይቅርታን የማያውቅ ሲኖዶስ ወይም ማኅበር እንዴት ለሀገርና ለህዝብ ይጸልይ ዘንድ ይችላል? ከማን ዘንድ ይቅርታን ለማግኘት? አንዳንዶች በስም ብጹእና ቅዱስ ተብለው በተግባር ግን ከቅድስና ማንነት የሚመነጨው መንፈሳዊ ብቃት ሲታይ፤ ፍሬ አልባዎች ናቸው። የክብርና ዝና፤ የገንዘብና ሥልጣን ምኞቶች ይቅር ማለት በሚገባው ልባቸው ላይ ተቀምጠው ይገኛሉ። ከዚህም የተነሳ ለሌሎች ይቅርታን ለማድረግ ጊዜን ይፈጃሉ፤ እነርሱ ግን ለኃጢአታቸው ወዲያውኑ ከእግዚአብሔር ዘንድ ይቅርታ እንዲወርድላቸው ሲጸልዩ ይታያሉ።  በእርግጥም ለጸሎታቸው ምላሽ ያልመጣላቸው ከዚህ እልከኛ ልባቸው የተነሳ ይሆናል። «አድን ሕዝበከ ወባርክ ርስተከ» ብለው ይጸልያሉ። ህዝቡም አልዳነም፤ በበረከትም ተሞልቶ በስደት ከመሞት አልዳነም። በእልከኝነት መንፈስና ይቅር ባለማለት  የእግዚአብሔርን የይቅርታ ፈቃድ በእጃቸው ያሰሩ ሰዎች እንዴት፤ የይቅርታ እጅ ለእነሱ ከሰማይ እንዲወርድ ይለምናሉ? እግዚአብሔር ልብና ኩላሊት ያመላለሰውን እልከኛ ልብ አይመረምርም ማለት ነው? ለይቅርታ ባልተዘጋጀ ማንነት ያሉ ጨካኞችና ክፉዎች ይቅርታን አያውቁም፤ ልበ ርኅሩኆችና ቸሮች እንጂ!!

«እርስ በርሳችሁም ቸሮችና ርኅሩኆች ሁኑ፥ እግዚአብሔርም ደግሞ በክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ ይቅር ተባባሉ» ኤፌ 4፤32

እንግዲህ እውነት እውነቱን እንነጋገር ከተባባልን ይቅርታን ገንዘብ ማድረግ የማይችሉት ክፉዎችና ጨካኝ መሪዎች ሁሉ ናቸው። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የተባራሪና አባራሪ፤ የውስጥና የውጪ፤ የሕገ ወጥና ሕጋዊ፤ ሲኖዶስ ስያሜ ሕልውና ኖሮት በየራሱ ክፍል ተለያይቶ መኖር ከጀመረ እነሆ ሃያ አንድ ዓመት አስቆጠረ። እንዴትና ምክንያቱን ለመዘርዘር የዚህ ጽሁፍ ዓላማ ባለመሆኑ ወደዚያ የቆሸሸ ታሪክ መግባት አያስፈልግም።   በተወጋገዘ የጳጳሳት ቡድንና ደጋፊ የቤተክርስቲያኒቱ አንድ ማኅበር ልዩነቱ ዛሬም መኖሩን በማመን መፍትሄ በመፈለግ ላይ ለማተኮር ይሻል። 21 ዓመት በልዩነትና በክፍፍል የቆየነው ለምንድነው? አሁን ያህ ክፍፍል እንዳይቀጥል ምን የሚታይ ነገር አለ? ወደፊትስ ምን ማድረጉ ይበጃል? በሚሉት ላይ ጥቂት ለማለት እንወዳለን።

1/ ለይቅርታ የተዘጋጀ ወገን የለም!

በሁለቱም ሲኖዶሶች በኩል በክርስቲያን ይቅርባይ የእምነት ማንነት ላይ ሆኖ ይቅር ለመባባል የፈለገ ማንም  ወገን የለም። የክርስቶስ አማኝ ይቅርታን በሁኔታ፤ በአዋጭነቱና በሚያስገኘው የሚታይ ዋጋ ላይ ተመስርቶ ለይቅርታ ድርድር አይቀመጥም። ይሁን እንጂ ሁለቱም ሲኖዶሶች ለይቅርታ የሚነጋገሩት የሚያዋጣቸውን ስልት ነድፈው ጥቅሞቻቸውን በማስጠበቅ ውጤታማ ለመሆን የሚታገሉለት ምድራዊ አስተሳሰብ የነገሰበት ሆኖ በመቆየቱ አንዳችም ውጤት ማምጣት አልተቻለውም። የቤተክርስቲያን አንድነት ሰዎች ስለፈለጉት  ወይም ስላልፈለጉት ሳይሆን የተመሰረተው በክርስቶስ ደም ስለሆነ አንዳችም ቅድመ ሁኔታ የሌለበት ነገር ነው።
«ቤትም እርስ በርሱ ከተለያየ ያ ቤት ሊቆም አይችልም » ማር 3፤25
«በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ» የሐዋ 20፤28
የክርስቶስን መንጋ ለሁለቱ የከፈሉ ሲኖዶሶች የክርስቶስን ቤት በአንድነት ለማቆም ያለመቻላቸው ዋናው ምክንያት ቤተክርስቲያንን ለመጠበቅ መንፈስ ቅዱስ የሰጣቸውን ሹመት ወደ ሥጋዊ አስተሳሰብና የድርድር ሂሳብ ስላወረዱት ብቻ ነው። እንዲያ ካልሆነማ 21 ዓመት ለእርቅ ያንሳል? ከእንግዲህስ ስንት 21 ዓመት ያስፈልጋል? በሁለቱም ወገን ለቤተክርስቲያን አንድነት የተዘጋጀ ማንነት ባለመኖሩ ውጤቱ ከህልም ዓለም አልፎ እውን መሆን አልቻለም። አሁንም ይህን አስተሳሰብ አስቀምጠው የክርስቶስን ማኅበር መሰብሰብና የቤተክርስቲያንን አንድነት ማስቀደም እስካልቻሉ ድረስ ከመንፈሳዊ ውጤት ላይ መድረስ አይቻላቸውም።

2/ የሀገር ውስጡ ሲኖዶስ የበለጠ ችግር አለበት።

አንዳንዶች ማለትም ማኅበረ ቅዱሳንን ጨምሮ የፓትርያርክ መርቆሬዎስን ሀገር ለቆ መሄድ ሲኮንኑ ይታያሉ።  የመንፈሳዊ አባቶችን የጥንት የስደት ሁኔታ ከታሪክ አምጥተን እዚህ ላይ ብዙ መከራከሪያ ጭብጥ በማቅረብ መሞገት ይቻላል። ይሁን እንጂ ጉልጭ አልፋ እንዳይሆን እንለፈውና የፓትርያርክ መርቆሬዎስን ስደት ተገቢ እንዳልነበረ ብንቆጥረው እንኳን ስህተታቸውን አጉልቶ የማያሳይ ነገር አለ። ይኼውም  ፓትርያርክ መርቆሬዎስ መንፈሳዊ ሥልጣናቸውን የሚጠሉት ኢህአዴግ ሲገባ ሊሆን አይችልም። ታመዋልም ቢባልም እንኳን  በሞት ከዚህ ዓለም ተለይተዋል ማለት አይደለም። በሞት እስካልተለዩ ድረስ በህመም ይሁን በሌላ ምክንያት ከመንበሩ ላይ ካልተገኙ በምትካቸው ሌላ ፓትርያርክ ይመረጣል የሚል ሕግ አለ ወይ?    ምንም እንኳን ፓትርያርክ መርቆሬዎስ እስከመጨረሻው ድረስ ባሉበት መቆየት እንደነበረባቸው ባያጠያይቅም እውነታው ግን የፓትርያርክ መርቆሬዎስን መባረርና ከስልጣን በህመም ይሁን በሞት መሰናበት የሚፈልጉ የሲኖዶስ አባላት መኖራቸውን ልንክድ አይገባም። ምክንያቱም ፓትርያርኩ በሕይወት እያሉ ሌላ ፓትርያርክ አንሾምም ያለ አንድም የሲኖዶስ አባል አልነበረም። ይልቁንም ከባለጊዜው ንፋስ ጋር ሲነፍሱ ታይተዋል። አንዳንዶቹም ለመሾም ሲሯሯጡ ነበር።  በህመም ወይም በሌላ ምክንያት መሥራት ባይችሉ እንደራሴ የማይመራበት ምክንያቱ ምን ይሆን? ሕጉን በሕግ ባለማሻሻል ለመጣስ ያደረሰው ምን ይሆን?  ተወደደም ተጠላ፤ ፓትርያርኩን በመጥላትና በማስወገድ ሥልጣኑን ለመጨበጥ የፈለጉ ቡድኖች ለቤተክርስቲያን መከፋፈል ትልቁን ሚና ተጫውተዋል። ብዙዎቹን ባለድርሻዎች እናውቃቸዋለን። ገሚሶቹም ሞተዋል፤ በህይወት ያሉትም አሉ። ይህ ከሆነ እነሆ 20 ዓመታት አለፉ።  ስህተቶችን በማመን ለማስተካከል መሞከር ግን አሁንም ቁርጠኝነቱ ካለ አልረፈደም። በመሬት ላይ ያለው እውነታ ግን ለመተራረም ያለውን ነገር ብዙም አያሳይም።
 የሀገር ቤቱ ሲኖዶስ ከውጪው ሲኖዶስ ጋር ለሚደረገው እርቅ እንቅፋት ናቸው ብሎ የክስ መዝገቡን በአቡነ ጳውሎስ ላይ ሲለጥፍ የነበረ ቢሆንም  ከሞታቸውም በኋላ ይህ እርቅ በየምክንያቱ እንዲጨናገፍ የሚፈልግ አካል እንጂ ከአቡነ ጳውሎስ በተሻለ መልኩ ለእርቁ ቀናዒ  ስለመሆኑ የምንሰማውና የምናየው ነገር የለም። ይልቁንም ከወዲያ ወዲህ የሚናፈሰው ስለ 6ኛው ፓትርያርክ ምርጫ ነው። ምናልባትም አቡነ ጳውሎስን ከመጥላት የተነሳ  ውንጀላን የሚቆልሉባቸው ከሳሾቻቸው እሳቸው በሞት ዘወር ሲሉ  የከሳሾች የሀሰት ክስ ጊዜውን ጠብቆ እየተገለጸ እያየን ነው። ስለ6ኛው ፓትርያርክ በተዘዋዋሪና በቀጥታ መነገሩ እርቁ አልተፈለገም ማለት ነው። ድሮውንም ፓትርያርክ ጳውሎስን የሚወነጅሉት ለስም ማጥፋት እንጂ እርቁን ፈልገውት አልነበረም። ምክንያቱም እርቁ እውን ሆኖ የውጪዎቹ ጳጳሳት ወደ ሀገር ውስጥ ለመግባት ቢችሉ፤ አሁን ባለው የሀገር ውስጡ ሲኖዶስን ጉባዔ በሚፈልጉት መንገድ የሚጠመዝዙ ቡድኖች ከልዩ ልዩ አስተሳሰብና ከእውቀት ብልጫ አሰላለፍ አንጻር የመዋጥና የያዙትን የወሳኝነት  ወንበር በመልቀቅ ወደጥጉ እንገፋለን የሚል የስነ ልቦና ፍርሃት አላቸው። ያን ጊዜ የማኅበረ ቅዱሳን ነደ እሳት የሚባል ጳጳስ አይኖርም፤ እገሌ ጧፍ ነው፤ እገሌ ደግሞ ሻማ እያሰኘ የሚያሞካሸውን ጀግና ደጋፊ አያገኝም።  ስለዚህ ሁሉም ቡድኖች እርቁ በፍጥነትና በሁኔታዎች አጋጣሚ እንዲፈጸም አይፈልጉም። ከእነዚህም አንዱ የሀገር ውስጡ ሲኖዶስ አጫፋሪ የሆነው ማኅበረ ቅዱሳን ከነተባባሪ አባቶቹ እርቁን አይፈልጉትም።

3/ የውጪውም ሲኖዶስ ችግር አለበት።

 ፓትርያርክ መርቆሬዎስ እድሜአቸው መግፋቱ እውነት ነው። በዚህ እድሜያቸው አሁን ያለውን የቤተክርስቲያን ተግዳሮቶች ፈጥነው በመረዳትና በመንቀሳቀስ ተፈላጊውን መፍትሄ በመስጠት ላይ ተገቢውን አመራር መጠበቅ እንደሚቸግር መረዳት አይከብድም። በዚህ ላይም ሕመም እንዳለባቸውም እንሰማለን።  ብዙ ጊዜም የሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ ድምጽ በውክልና ከሚሰማ በቀር የፓትርያርኩ ድምጽ ርቋል። ይህም እንደ አንድ ችግር ቢነሳ አግባብነት ይኖረዋል። ከዚህ በተጨማሪም እርቅን የሚያክል ትልቅ ኃላፊነትና ተልእኮ የሚጠብቀው የውጪው ሲኖዶስ አባላት ለእርቅ እንቅፋት የሚሆኑ ፖለቲካዊና ሃይማኖታዊ መሰል መግለጫዎችና አሰላለፎችን ሲያሳዩ ይታያሉ። ከሀገር ውስጥ ሲኖዶስ ጋር በመስማማት ብቻ ያለ ኢትዮጵያ መንግሥት ድጋፍ እርቁ ከግብ ሊደርስ እንደማይችል ይታወቃል።  የውጪው ሲኖዶስ አባላት የፖለቲካ ሰልፎችን በማስተባበር የኢትዮጵያን መንግሥት ማስኮረፍ በራሱ ችግር አለው። መቃወም መብት ቢሆንም የፖለቲካ «ሀሁ» ብዙም በሀገሩ ውስጥ ባላስፋፋ መንግሥት ጉዳይ እየገቡ ወደእርቅ እንደርሳለን ለማለት እንዴት ይቻላል? እርቁ ቢቀርም፤ ይቅር ካልተባለ በስተቀር  እስከ ኤርትራ የደረሰ የሲኖዶስ አባል ያለው የውጪው ሲኖዶስ አቋሙ ጥርት ያለና ለእርቅ ዝግጁነት ያለው ነው ለማለት ይቸግራል።  እስካሁንም እነዚህ ጉዳዮች ለእርቅ ያላቸውን ጉዳት ገምግሞ ዝግጁነቱ እስከየት ድረስ እንደሆነ በግልጽ የሚታወቅለት ነገር የለም። ፖለቲካዊ ጥያቄዎችንም እንደሚያነሳ ይሰማል። ቤተክርስቲያንን አንድ ለማድረግ ካልሆነ በስተቀር ሲኖዶስ ለፖለቲካዊ ጥያቄ መፍትሄ የቅድሚያ ስራው እንዴት ሊሆን ይችላል? የሚቀድመውን ማስቀደምና በሂደት ደግሞ የሚከተለውን ከመስራት ይልቅ አቀላቅሎ ሁሉንም ፍላጎቶች በአንዴ ለማሳካት መፈለግ ሁሉም እንዳይሆን ለማድረግ ከመጣር የተለየ አይደለምና ሊታሰብበት ይገባል።

Thursday, September 20, 2012

የማኅበረ ቅዱሳን ሰዎች በአቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ሹመት ደስተኛ አለመሆናቸውን ቤተክህነት አካባቢ በሚያናፍሱት ወሬ እየገለጹ ነው

ዐቃቤ መንበሩ «መናፍቃኑ ኃይለ ማርያምን ጠቅላይ ሚኒስትር ሊያደርጉት እየጸለዩ ነው አሉ፤ እርሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነ ማለት ለእኛ እጅግ ክፉ ነገር ነውና የምንችለውን ሁሉ ማድረግ አለብን» ብለዋል

ምንጭ፦ አባ ሰላማ ድረ ገጽ


 ዐቃቤ መንበሩ «መናፍቃኑ ኃይለ ማርያምን ጠቅላይ ሚኒስትር ሊያደርጉት እየጸለዩ ነው አሉ፤ እርሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነ ማለት ለእኛ እጅግ ክፉ ነገር ነውና የምንችለውን ሁሉ ማድረግ አለብን» ብለዋል.
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የኢህአዴግ ሊቀመንብር ሆነው መመረጣቸውንና በቀጣይም ለጠቅላይ ሚኒስትርነት ቃለ መሐላ የሚፈጽሙ መሆናቸው ከተገለጸ ጊዜ ጀምሮ፣ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ በመሆናቸው ምክንያት በማኅበረ ቅዱሳን መንደርና በቤተክህነቱ አካባቢ ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ግንኙነት ባላቸው አካላት ዘንድ «ጴንጤ አይገዛንም» የሚል ቅስቀሳ ውስጥ ውስጡን እየተደረገ መሆኑ እየተነገረ ነው፡፡
በዘመን መለወጫ በዓል ላይ በጠቅላይ ቤተክህነት አዳራሽ በተዘጋጀው መርሀግብር ላይ የተገኙትና ንግግር ያደረጉት አቃቤ መንበር አባ ናትናኤል ትዝብት ላይ የጣላቸውን ንግግር ማድረጋቸውን በስፍራው የነበሩ ምስክሮች እየገለጹ ነው። አቡነ ናትናኤል በአቃቤ መንበርነት ከተሾሙ ጀምሮ ጊዜውን እየተሻሙና ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስን ለመምሰል ጥረት እያደረጉ መሆናቸውን እያደረጉ ካለው እንቅስቃሴ መታዘብ ተችሏል፡፡ «እርሳቸው ወንበር ላይ አስቀምጡኝ» ከማለት «እርሳቸው የሚበሉትን ስጡኝ» እስከማለት መድረሳቸውን ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡
ከዚሁ ጋር ተያይዞ በየዓመቱ በዘመን መለወጫ በዓል ለሚደረገውና ቅዱስ ፓትርያርኩን እንኳን አደረስዎ ለሚባልበት መርሐግብር ከአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት ለተገኙ የደብር አለቆች፣ ካህናትና ዲያቆናት ባደረጉት ንግግር ውስጥ «መናፍቃኑ ኃይለ ማርያምን ጠቅላይ ሚኒስትር ሊያደርጉት እየጸለዩ ነው አሉ፤ እርሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነ ማለት ለእኛ እጅግ ክፉ ነገር ነውና የምንችለውን ሁሉ ማድረግ አለብን» ያሉ ሲሆን፣ ከበዓሉ ጋር የተገናኙ ሐሳቦችን ካቀረቡ በኋላም መጨረሻ ላይ «ቅድም ያነሣሁላችሁ የመናፍቃኑ ጉዳይ ምሥጢር ነውና በምሥጢር ያዙት» ብለዋል፡፡ ይህም የተናገሩት ተገቢ ያልሆነ ቃል እንደወቀሳቸውና ሀሳቡ መጀመሪያም ቢሆን ከራሳቸው ያመነጩት እንዳልሆነ ግምት እንዲወሰድ አድርጓል፡፡ አባ ናትናኤል ከእርጅናም ዲፕሎማሲያዊ አቀራረቡንም በሚገባ ባለማወቃቸው የተነሳ በብዙዎች ፊት የሰነዘሩትን ይህን ሀሳብ እነማንያዘዋል ሹክ እንዳሏቸው ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ሰዎች ገልጸዋል፡፡
አቶ ማንያዘዋል የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ቀብር እለት ወደቤተመንግስት እገባለሁ አትገባም በሚል ቤተመንግስት በር ላይ ከአስተናጋጆች ጋር ሲወዛገብ በቴሌቪዥን መስኮት ያዩትና የሚያውቁት ሁሉ መነጋገሪያ አድርገውት የሰነበቱ ሲሆን፣ «አባ ናትናኤልን ደግፌ የምይዝ ነኝ» በሚል በትግል መግባቱ ታውቋል፡፡ ይህም ማኅበሩ ቀድሞም ያደርግ እንደነበረ የሚፈልገውን በእርሱ በኩል ወደአባ ናትናኤል እያቀረበ ለመሆኑ በቂ ምስክር ነው ይላሉ ታዛቢዎች፡፡ የአቶ ኃይለማርያም ደሳለኝን ሹመት በመቃወም በዋናነት እያቀነቀነ የሚገኘው ማኅበረ ቅዱሳን መሆኑን ምንጮቻችን እየተናገሩ ነው፡፡ ቤተክህነት አካባቢ «ጴንጤ ሊገዛን አይገባም» የሚል ወሬ እያናፈሰ ሲሆን፣ አንዳንድ ወዳጆቹ ጳጳሳት ግን «ከዚህ በኋላ አንዳች ስሕተት ከተገኘባችሁ የምትከፍሉት ዋጋ ቀላል አይሆንምና ሁሉን ነገር በጥንቃቄ ነው ማድረግ ያለባችሁ» የሚል ምክር እንደለገሷቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡


Wednesday, September 19, 2012

‹‹ባለራእዮች ይሞታሉ ራእያቸው ግን አይሞትም›

ዲያቆን ፈታሂ በጽድቅ ከተባለ የብሎጋችን ተከታታይ የተላከ ጽሁፍ

የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስቴር የመለስ ዜናዊን ዜና ዕረፍት ከሰማን በኋላ ብዙዎቻችን አዝነናል፡፡ በሰውኛ አቅሙ ሁሉም ምንም ማድረግ ስላልቻለ ነው እንጂ አንዳንዶች እሳቸው ከሞት ተርፈው እኔ በተተካሁ ሲሉ ሌሎች ደግሞ ምንም እንኳ ራሳቸውን አሳልፈው ለመስጠት ባያስቡም በሆነ መንገድ ከሞት አስነስተው የማቱሳላን እድሜ ቢቸሯቸው ደስተኛ እንደሚሆኑ በየመጓጓዣው፣ በየስራ ስፍራውና በየመዝናኛ አካባቢዎች የነበሩት ጭውውቶች ይናገሩ ነበር፡፡

ከሞት ማስነሳት ባንችልም ግን ሁላችንም ሐዘናችንን በተለያየ መንገድ ስንገልጽ ቆይተናል፡፡ ምንም እንኳ ሐዘኑ አሁን እየቀነሰ ያለ ቢሆንም የሐዘኑ ስሜትና የሐዘን መግለጫ መልእክቱ አሁንም በቴያ መልኩ እንዳለ ነው፡፡ ከብዙዎቹ የሐዘን መግለጫዎቻችን መካከል ከላይ በርዕስነት ያነሳነው አንዱ ነው፡፡ ይህን መልእክት ጎላ ጎላ ባለ ፊደል ከአቶ መለስ ፎቶግራፍ ጋር በተደጋጋሚ በተለያየ ይዘትና ስፍራ ላይ ተስቅሎ አይተነዋል፡፡

ይህን መልእክት የሰቀሉ ሰዎች ሊሉ የፈለጉት ምንም እንኳን አቶ መለስ ዜናዊ የዚህ ዓለም ቆይታቸውን ጨርሰው በሞት ቢለዩንም ራእያቸውን ግን ቀደም ሲል ጀምረውት ወይም አካፍለውን ስለሆነ የሄዱት ራእያቸው አይሞትም፡፡ ይልቁንስ እኛ እንጨርሰዋለን የሚል ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ቃል እየገቡ እንዳሉት ለማድረግ ከቻሉ የአቶ መለስ ራእይ አይሞትም ማለት ነው፡፡ አለበለዚያ ግን. . .

በዚህ መልእክቴ ለማሳየት የፈለኩት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስቴር የአቶ መለስ ዜናዊን ራእይ እንዴት እንፈጽም? እንዴትስ እንዳይሞት ለማድረግ እንችላለን? የሚለውን ማሳየት አይደለም፡፡ እርሱን ለማድረግ ያለሁበት ስፈራ፣ ዕውቀትና ሁኔታ አይፈቅድልኝምና ወደዚያ አልገባም፡፡ ነገር ግን ብዙዎች ሊገድሉት ተማምለው ስለወጡበት አንድ ራእይ ነው ለማሳየት የምፈለገው፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ወደቀደመ ትምህርቷና ወደሐዋርያት እምነት እንድትመለስ እስጢፋኖሳውያን ሕይወታቸውን ሰውተዋል፡፡ በወቅቱ የነበረው ጨካኝና ከሃዲ መሪ ሰዎቹ እንዲደበደቡ፣ እንዲታሰሩ፣ እንዲሰደዱ እንዲሁም እንዲሞቱ ሲያደርግና ሲያስደርግ በእሱ እምነት ራእያቸውም አብሮ ይሞታል ብሎ ተስፋ አድርጎ ነበር፡፡ ነገር ግን ታሪካቸው እንደሚለው መሰደዱም፣ መገደሉም፣ መታሰሩም ሰዎቹ እንዲጠፉ ከማደረግ ይልቅ ‹‹እግዚአብሔር የተጋዙበትን ሀገር እየከፈተላቸው ብዙዎችን በስብከታቸው እያሳመኑ ክርስቲያኖች እንዲያውም መነኮሳት አድርገዋቸዋል›› (ደቂቀ እስጢፋኖስ በህግ አምላክ ገጽ 35)፡፡ ጨካኙ መሪ እንደጠበቀው ሳይሆን ካሰበው ውጪ ሲሆንበት ጭካኝና ፀረ ወንጌል በመሆኑ የሚከተሉትን የማሳቀያና የመግደያ መንገዶች ወደመጠቀም ዞረ፡-

1.         በድንጋይ ደበደቧቸው፡፡
2.         ቆመውም ሆነ ተንበርክከው መጓዝ እንዳይችሉ የእግሮቻቸውን ጅማቶች አወጡባቸው በዚህ ምክንያት ደብረ ብርሃን ከተማ ወድቀው ቀሩ፡፡
3.         በጅራፍ ገረፏቸው፡፡
4.         በመሬት ላይ አስተኝተው እንደሚለፋ ቆዳ በመርገጥ ጤማይ የተባለ የንጉሡ ወንጀለኞች መግረፊያ ሁሉም የሠራዊቱ አባል እጃቸው እስኪደክማቸው ገረፏቸው፡፡
5.         አንዲትን ሴት ሁለት እግሮችዋን ግራና ቀኝ ወጥረው በማሰር ራቁትዋን አስተኝተው እሳት ካነደዱ በኋላ በፍሙ ቀኑን ሙሉ ጭኗን እና ብልቷን በእሳቱ እየጠበሷት ሲያቃጥሏት በስቃይ ሞተች፡፡
6.         እጃቸውንና እግራቸውን በመቁረጥ በድንጋይ በመደብደብ የተገደሉም ነበሩ፡፡
7.         አንገታቸውን የተቆረጡም ነበሩ፡፡
8.         በጣም በሚያሰቅቅ ብርድና ቅዝቃዜ ውስጥ ራቁታቸውን እንዲሆኑ በማድረግ በቅዝቃዜውና በእርጥበቱ ምክንያት ከመጣው ተላላፊ በሽታ የተነሳ 98 ሰዎች ሞቱ፡፡
9.         ጆሮአቸው ውስጥ ጉንዳን የተጨመረባቸው ነበሩ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የጥናት እና ምርምር ማእከል ባዘጋጀው በ፬ኛው የኢትዮጵያ ቤተ- ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ ላይ የተደረገ አጭር ደሰሳ፡፡



   ፍቅር ለይኩን ለደጀ ብርሃን የላከው ጽሁፍ
[fikirbefikir@gmail.com/befikir12@yahoo.com

‹‹ሁሉን መርምሩ የተሻለውን ያዙ!›› የሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ሕያው ቃል ባለ አእምሮ የሆነ ሰው ሁሉ በማስተዋልና በጥበብ መንፈስ ሆኖ መልካሙን ከክፉ ለመለየት ጥናት እና ምርምር በእጅጉ አሰፈላጊ መሆኑን የሚያሳስበን ኃይለ ቃል/ምክር ይመስለኛል፡፡ የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በአይሁድ ምኩራብ ተገኝቶ በተደጋጋሚ ስለ ጌታችን፣ አምላካችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት፣ ጌትነት እና አዳኝነት የሰበከላቸው ልበ ሰፊዎቹ የቤሪያ ሰዎች፡- ‹‹ነገሩ እንዲህ ይሆንን በማለት መጻሕፍትን በመመርመር ቃሉን በሙሉ ልብ ተቀበሉ ይለናል፡፡›› (ሐዋ  ፲፯፣፲፩)   
የሥልጣኔ ምንጭ፣ የሺህ ዘመናት ባለ ታሪክ እና የበርካታ ቅርሶች ባለቤት ለሆነችው ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የጥናት እና ምርምር ሥራ ታላቅ ፋይዳ ያለው መኾኑ አያጠራጥርም፡፡ በኢትዮጵያ ባሕልና ቱሪዝም ሚ/ር በቅርስ ጥናት እና ጥበቃ ባለሥልጣን አዳራሽ ጳጉሜን ፫ እና ፬ ለሁለት ቀናት በተካሄደው ‹‹ኛው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ›› አንገብጋቢ እና ወቅታዊ በሆኑ ሀገራዊና ሃይማኖታዊ ጉዳዮች ላይ በቤተ ክርስቲያኒቱ ምሁራን፣ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በመጡ፣ ከተለያዩ መንግሥታዊ እና መንግሥታዊ ካልሆኑ መሥሪያ ቤቶች በተጋበዙ እንግዶች በአማርኛ እና በእንግሊዝኛ ቋንቋ ሰባት የጥናት ወረቀቶች የቀረቡበት ጉባኤ ነበር፡፡
ጥናት እና ምርምር በሳይንሳዊ ዘዴ ለችግር መፍትሔ ለማፈላለግ፣ አዳዲስ ግኝቶችን ለመፍጠር፣ ተጨማሪ እውቀትን ለማግኘት፣ አስፈላጊውን መረጃ ተገቢውንሳኔ ለመስጠት የሚያስችል ዐቢይ ተግባር ነው፡፡ ዛሬ አንቱ የተባሉ፣ ዓለምን ያስደመሙ ጥበባት ኹሉ የጥናትና ምርምር ውጤቶች ናቸው፡፡ በዘመናችን በዓለም ላይ የተጋረጡ በርካታ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ አካባቢያዊ፣ ፖለቲካዊ እና መሰል ችግሮችን ለመፍታት ዋነኛው መንገድ ጥናት እና ምርምር መሆኑ ግልፅ ነው፡፡
ስለሆነም በሀገራችን ይህን የሚያስፈጽሙ አያሌ የጥናት እና ምርምር ተቋማት ተመሥርተዋል፡፡ ይሁን እንጂ በሀገራችን የረጅም ዘመን የሥነ መንግሥት/ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ ማኅበራዊ ኑሮ፣ ታሪክ፣ ባሕል እና ሥልጣኔ እንዲሁም ፍልስፍና፣ ሕግ፣ ሥነ ጹሑፍ፣ ኪነ ጥበብ እና ሥነ ሕንጻ/አርክቴክቸር ሰፊ እና ጉልህ አሻራ ያላት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ዙሪያ ሰፊ የሆነ ምርምር እና ጥናት በማድረግ ረገድ ቤተ ክርስቲያኒቱ በሀገራችን ለትምህርት መጀመር ከተጫወተችው ግንባር ቀደም ሚና እንዲሁም ጥንታዊት፣ ሐዋርያዊት እና ወንጌላዊት እና በበርካታ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ምእመናን ያሏት ተቋም የመሆኗን ያህል በበቂ ሁኔታ የተደራጀ የጥናት እና የምርምር ማእከል የላትም፡፡
ለቤተ ክርስቲያኒቱ አንድ ለእናቱ ሊባል የሚችለው በዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ደረጃ አለ የሚባለው የቅድስት ሥላሴ ኮሌጅም በብዙ አካዳሚያዊ እና አስተዳደራዊ ችግሮች የተተበተበ በመሆኑ እንደ አንድ አካዳሚያዊ ተቋም በበቂ ሁናቴ የተደራጀ እንኳን ቤተ መጻሕፍት የለውም፡፡ በየጊዜው በአኀተ አብያተ ክርስቲያናትም ሆነ በክርሰቲያኑ ዓለም የሚወጡ አዳዲስ መጻሕፍቶች፣ የጥናት እና የምርምር ጆርናሎች እና ፐሮሲዲንጎች በዚህ ተቋም ውስጥ እጅጉን ብርቅ ናቸው፡፡ እናም ይህ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ብቸኛ እና አንድ የሆነ የሥነ መለኮት ተቋም የሚጠበቅበትን ያህል ለቤተ ክርስቲያኒቱም ሆነ ለሀገር መፍትሔ አመላካች የሚሆኑ ብቁ እና ወዳዳሪ የሆኑ ምሁራንን በብዛት እና በጥራት ለማፍራት ቀርቶ ተቋም እራሱ በበርካታ ችግሮች ተተብትቦ የሌሎችን ብርቱ እገዛ ወደሚፈልግበት ደረጃ የደረሰ ይመስላል፡፡
እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ማለት ይቻላል የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን በማጥናት በኩል ከእኛ ይልቅ ምዕራባውያኑ እና አሜሪካውያን ምሁራን ሰፊውን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡ ይህ ደግሞ በቤተ ክርስቲያናችን ብቻ ሳይሆን በሀገራችን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ስለ ችግሮቻችን አጥንተው መፍትሔ አሳብ የሚያቀርቡልን ፈረንጆቹ መሆናቸው ነገሩን እንቆቅልሽ ያደርገዋል፡፡ ለዚህም ደግሞ በተለይም በቤተ ክርስቲያናችን ጥናት እና ምርምርን የሚያበረታቱ አመቺ ሁኔታዎች እና ተቋማት አለመኖራቸውና ለረጅም ዘመናት የቆየው የቤተ ክርስቲያኒቱ ባሕላዊ የሆነ የትምህርት ሥርዓትም ያለውን ከማስጠበቅ አልፎ አዲስ እውቀት ለማምረት (Knowledge Production) የሚያስችል የጥናት እና ምርምር በር ለመክፈት አለመቻሉ እንደ አንድ ምክንያት ሊወሰድ የሚችል ይመስለኛል፡፡
ፊደል ቀርፃ፣ ቀለም በጥብጣ፣ ብራና ዳምጣ የድንቁርና እና የአለማወቅን ጨለማ ለመግፈፍ ገና ከጥንት ከጠዋቱ ታጥቃ የተነሳች ቤተ ክርስቲያናችን በጀመረችው ፍጥነት መጓዝ ተስኗት እና ይባስም ሲል በምርምር እና በጥናት እጅጉን የተራቀቁ እና የመጠቁ የሥነ መለኮት እና የፍልስፍና ሊቃውንቶችን ያፈራች ቤተ-ክርስቲያን በዘመናችን በብዙ ችግሮች ተተብትባ መንገዷ ሁሉ ባለህበት እርገጥ መሆኑ ሁላችንንም ሊያስቆጨን የሚገባ ጉዳይ መሆኑን መዘንጋት አይኖርብንም፡፡
ይህን ቤተ ክርስቲያኒቱ እና የትምህርት ተቋማቶቿ ኅብረተሰቡ ከእነዚህ ተቋማት የሚጠብቀውን ያህል አለመንቀሳቀሳቸው፣ ያሉባቸውን እና የተጋረጡባቸውን ሁለተናዊ እንቅፋቶች እና ቤተ-ክርስቲያኒቱ በዚህ ረገድ እጅግ ወደ ኋላ መንደርደሯን የታዘቡ አንድ ምሁር እና ፖለቲከኛ በአንድ ወቅት ‹‹ነፃነትን የማያውቅ ነፃ አውጭ›› በሚል በመጽሐፋቸው ላይ፡-
በአንድ ወቅት በምድረ አውሮፓ እና በአረቢያ ከነበሩ ተመሳሳይ የመንፈሳዊ እውቀት ተቋማት ጋር መወዳደር የሚችል የትምህርት ዓይነቶች ያስተምር የነበረ ቤተ ክህነት፣ አውሮፓውያኑ እነዚህን ተቋማት ወደ ትላልቅ እና ዝነኛ የጥናት እና የምርምር ማእከላት እና ዩኒቨርስቲዎች መቀየር ሲችሉ የእኛው ቤተ ክህነት ተቋማት እንዴት ከነ ከፍተኛ ሕዝባዊ ተቀባይነታቸው እና ክብራቸው ጋር የእርግማን ሰባኪ ተቋም ብቻ ሆኖ እንደቀረ እኔም ሆነ ትውልዴ ለማወቅ አልጣርንም፣ አልፈለግንም በማለት ቁጭታቸውን ገልጸው ነበር፡፡
ዛሬ በዓለማችን ያሉ ትላልቅ የሃይማኖትም ሆኑ ዓለማዊ ተቋማት ከፍተኛ የሆነ ወጪ የሚመድቡት ሰፊ እና ጥልቅ በሆነ ጥናት ለታገዙ የምርምር ስራዎች እና አማካሪዎች/መማክርት ነው፡፡ በሀገራችንም ሆነ በቤተ ክርስቲያናችን ለተጋረጡብን ሁልቆ መሣፍርት ለሌላቸው ችግሮቻችን በዚህ ዘመን ጥልቅ የሆኑ በእግዚአብሔር ጥበብ እና ማስተዋል መንፈስ የተቃኙ ጥልቅ የሆኑ አሳቢዎች/ተመራማሪዎች (Great Thinkers) በእጅጉ ያሰፍልጉናል፡፡
በቀደመው ታሪካችን ዘመን በሀገራዊ እና በቤተ ክርስቲያን አጀንዳዎች ላይ ሰፊ ጊዜ በመውሰድ የሚያሰላስሉ፣ የሚጸልዩ፣ በጽሞና መንፈስ ሆነው በእግዚአብሔር ፊት በጽናት እና በትዕግስት የሚቆዩ አባቶች እንደነበሩን የታሪክ ድርሳናቶቻችን ይመሰክራሉ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ተጋድሎ እና መንፈሳዊነት ዛሬ በታሪክ ብቻ በነበር የምናወሳው የሩቅ ዘመን ትዝታችን ሆኖ መቅረቱ ሁላችንንም ሊያንገበግበን ይገባል፡፡ አውሮፓውያን እና አሜሪካውያን ዛሬ ለደረሱበት እጅግ ለመጠቀ ሥልጣኔ፣ የአስተሳሰብ ምጥቀት፣ ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ እድገቶች እና ለውጦች ትልቅ መሠረት የጣሉ በሃይማኖት ተቋማቶቻቸው የነበሩ ጥልቅ አሳቢዎች እና ተመራማሪዎች እንደ ነበሩ የታሪክ ድርሳናት ይመሰክራሉ፡፡
በአውሮፓውያኑ ዘንድ ስለ ኢትዮጵያ ጥንታዊ ሥልጣኔ፣ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ቅርስ፣ ፍልስፍና፣ ኪነ ህንፃ እና ኪነ ጥበብ በሰፊው እንዲጠና በመካከለኛው ዘመን የነበሩ ኢትዮጵያውን መነኮሳት እና ሊቃውንት በተለይ በአውሮፓ ለኢትዮጵያ ጥናት እና ምርምር መከፈት ምክንያት መሆናቸውን ታሪካችን ያወሳል፡፡ በተለይ አባ ጎርጎሪዎስ ዘመካነ ሥላሴ የተባሉት መነኩሴ ጀርመናዊውን ሉዶልፍን የግዕዝን ቋንቋ፣ የሀገራችን እና የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን ታሪክ በማስተማር በመካከለኛው ዘመን በአውሮፓ ምድር የኢትዮጵያ ጥናት እንዲጀመር በቀደምትነት መሠረትን የጣሉ  ኢትዮጵያዊ ሊቅ እንደሆኑ የሀገር ውስጥም ሆኑ የውጭ ሀገር ምሁራን ይመሰክራሉ፡፡
በእነዚህ ኢትዮጵያውያን መነኮሳትና ሊቃውንት በአውሮፓ የተጀመረው ጥናት እስከ አሁን ዘመን ድረስ ቀጥሎ በአውሮፓና በሰሜን አሜሪካ ትላልቅ ዩኒቨርስቲዎች፣ የጥናት እና ምርምር ማእከሎች በኢትዮጵያ ጥንታዊ ቋንቋ በሆነው በግዕዝ፣ በሀገሪቱ የረጅም ዘመን ታሪክ እና ሥልጣኔ ዙሪያ ሰፋ ያለ ጥናት በማካሄድ ላይ ናቸው፡፡ ለአብነትም ያህል በፈረንሳይ፣ በኢጣሊያን ፍሎረንስ እና ኔፕልስ ዩኒቨርስቲዎች፣ በጀርመን ሀምቡርግ ዩኒቨርስቲ፣ በለንደን School of Oriental and African Studies እና በአሜሪካ በሚገኙ ታላላቅ ዩኒቨርስቲዎች በጥንታዊው የኢትዮጵያ ቋንቋ በግዕዝ እና በሀገራችን ጥንታዊ ሥልጣኔ እና ታሪክ፣ ባሕል እና ቅርስ ዙሪያ ጥናቶች ይደረጋሉ፡፡
እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በአብዛኛው በኢትዮጵያ ዙሪያ ጥናት እና ምርምር የሚያካሂዱ የውጭ ሀገር ምሁራን መሆናቸው ቀስ በቀስ እየተለወጠ ቢገኝም እኛ ኢትዮጵያውያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ስለ እራሳችን በጥናት እና በምርምር በተደገፈ ሁኔታ በልበ ሙሉነት ለመናገርም ሆነ በተለያዩ ቋንቋዎች የዳጎሱ የጥናት መጻሕፍቶችን በማቅረብ ረገድ ገና ብዙ የሚቀረን ይመስለኛል፡፡ ምናልባትም የዚህ የማኅበረ ቅዱሳን የምርምር እና የጥናት ማእከል በየዓመቱ የሚያዘጋጀው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ዓመታዊ ጉባኤም በከፊል የዚህ ቁጭት እና ቅናት ውጤት የወለደው ነው ለማለት የሚቻል ይመስለኛል፡፡
የጥናት እና ምርምር ፋይዳውን የተረዱ የቤተ ክርስቲያኒቱ ፍሬዎች የሆኑ እና በተለያዩ የትምህርት መስክ እስከ ፒ ኤች ዲ የተማሩ ልጆቿ ጥረት ለአራተኛ ጊዜ በማኅበረ ቅዱሳን የምርምር እና ጥናት ማእከል የተዘጋጀው አራተኛው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ፣ በጥናት እና በምርምር በመታገዝ በቤተ ክርስቲያናችን ያሉትን ችግሮች በሚገባ አጥንቶ በቤተ ክርስቲያንም ሆነ ተያያዥ በሆኑ፣ በወቅታዊ የሀገራችን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ መፍትሔ ለማፈላለግ የበኩሉን ድርሻ ለማበርከት በሚል ከአራት ዓመታት በፊት የተጀመረ ጉባኤ መሆኑን የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ የሆኑት ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም በመክፈቻ ንግግራቸው ገልጸዋል፡፡
ለአራተኛ ጊዜ በሀገር አቀፍ ደረጃ ለሁለት ቀናት በተደረገው የኢትዮጵያ ቤተ-ክርስቲያን የጥናት ጉባኤ ላይ በቀረቡት የጥናት ወረቀቶች እና ከተሳታፊያን በተነሱ ጥያቄዎች፣ አስተያየቶች እና ውይይቶች ዙሪያ መጠነኛ የሆነ አጭር ደሰሳ በማድረግ ይህችን አጠር ያለች ጹሑፍ ለአንባቢያን ለማቅረብ ወደድሁ፡፡
ይህ ጹሑፍ እግረ መንገዱንም በተለይ በማኅበረ ቅዱሳን እና ከማኅበረ ቅዱሳን በተቃራኒ በቆሙ ማኅበራት እና ግለሰቦች ደጋግመው ማኅበረ ቅዱሳንን ስለሚከሱበት፡- ‹‹ማኅበሩ የወንጌል ጠላት ነው፣ ማኅበረ ቅዱሳን የፖለቲካ ድ/ት ነው፣ ማኅበሩ በመንፈሳዊነት መጋረጃ ጀርባ የለየለት ዘራፊ እና ነጋዴ ሆኗል፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ ላለፉት ሃያ ዓመታት ለገባችበት ቀውስ በከፊልም ቢሆን የማኅበሩ ተጠያቂ ነው…ወዘተ፡፡›› በማለት ማኅበሩን የሚከሱትን ቡድኖችንም ሆነ ግለሰቦች በሩቅ ቆመው ከመካሰስ እና እርስ በርስ ከመፈራረድ ይልቅ በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በማኅበረ ቅዱሳን በኩል አሉ የሚሏቸውን ችግሮች እና ትዝብታቸውን በተጨባጭ መረጃ፣ በጥናት እና በምርምር በማስደገፍ ማቅረብ ቢችሉ እንዴት መልካም በሆነ ነበር፡፡ እንዲሁም በእንዲህ ዓይነቶቹ እና በተመሳሳይ የጥናት ጉባኤ መድረኮች ላይ በመገናኘት፣ በመቀራረብ እና በግልጽ በመነጋገር ልዩነቶችን አሰውግዶ በአንድነት መሥራት የሚቻልበት መንገድ እንዲኖር በሚል በቅንነት መንፈስ ያቀርብኩት ደሰሳ እንደሆነ ከወዲሁ ለአንባቢዎቼ በአክብሮት ለመግለጽ እወዳለሁ፡፡
በዚህ አራተኛው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ ላይ ከቀረቡት እና በጨርፍታ ዳሰሳ ላደርግባቸው ከመርጥኳቸው የጥናት ወረቀቶች መካከል በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፕሬስ ባልደረባ፣ የታሪክ ምሁር እና ተመራማሪ እንዲሁም በሀገራችን በሚታተሙ ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና የታሪክ ነክ መጽሐፎች ላይ ሰፊ እና ጥልቅ የሆኑ ዳሰሳዎችን (Book Reviews and Critics) በማድረግ የሚታወቀው አቶ ብርሃኑ ደቦጭ፡-

‹‹የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመት ውጤቶች በቤተ ክርስቲያን እና በሀገራዊ አጀንዳዎች ላይ ያላቸውን የአዘጋገብ ሂደት›› በተመለከተ ባቀረቡት የጥናት ወረቀት ላይ በተለይ በስምዓ ጽድቅ ጋዜጣ ርዕሰ አንቀጾች፣ ዜናዎች እና ሐተታዎች ላይ አጥኚው ሰፋ ያለ ትንታኔ ለመስጠት ሞክረዋል፡፡ ጋዜጣዋ በቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባዎች፣ ሂደቶች እና ውሳኔዎች ላይ፣ በሃይማኖታዊ ግጭቶች መንስኤዎች ዙሪያ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ በሆኑ ወቅታዊ እና ሀገራዊ አጀንዳዎች ላይ የሚወጡ ዘገባዎች በአብዛኛው ፍርሃት የሚንጸባረቅባቸው ቢሆኑም ስምዓ ጽድቅ ጋዜጣ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያሉትን ችግሮች በማሳየት ረገድ አዎንታዊ ሚና እንዳላት ጠቁመዋል፡፡ ነገር ግን ተግባራዊ የሚሆን መፍትሔን በማቅረብ ረገድ ግን ጋዜጣዋ ድካም እንደሚታይባት ገልጸዋል፡፡
አቶ ብርሃኑ ባቀረቡት የጥናት ወረቀት ላይ አንድ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት እና በቅርስ ጥናት እና ጥበቃ የሥራ ባልደረባ የሆኑ ሰው በሰጡት አስተያየት፡- ‹‹ስምዓ ጽድቅ ጋዜጣ እንደ ስሟ እውነትን በመናገር ረገድ ብዙም የተዋጣላት አይደለችም፡፡›› የማኅበረ ቅዱሳን ኅትመት ውጤቶች፡- ‹‹የቤተ ክርስቲያን ዋና ተልእኮ የሆነው ወንጌልን ገሸሽ ያደረጉና የወንጌሉ ዐቢይ መልእክት እውነት፣ መንገድ እና ሕይወት የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን በሚገባ የማይገልጽ ነው በሚል አስተያየታቸውን አጠናክረዋል፡፡›› በሌላ በኩል ደግሞ ሌሎች አስተያየት ሰጪዎች፡- ‹‹የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመት ውጤቶች በቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባዎች እና ውሳኔዎች ላይ እንዲሁም ሀገራዊ በሆኑ ወቅታዊ እና አንገብጋቢ ፖለቲካዊ አጀንዳዎች ላይ ግልፅነት እና ተጠያቂነት የሚያንሰው ነው ሲሉ…›› ሌሎች በግል ያነጋገርኳቸው ተሳታፊዎች ደግሞ በዋነኝነት፡-
‹‹በቤ/ን እና በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመት ውጤቶች መንፈሳዊ ወኔ እና ድፍረት የሚጎድለው አዘጋገብ እንደ ሚንጸባረቅበት…›› አስተያየታቸውን ሰጥተውኛል፡፡