Tuesday, October 9, 2012

የአቡነ ገብርኤል ማካሮቭ ሽጉጥ ጠፋ!

source: www.awdemihret.blogspot.com
ሰርቀሀል ተብሎ የተጠረጠረው ዲ/ን ፍጹም እንዳለ የተባለ አገልጋያቸው እንዲባረር ተደርጓል፡፡

በአቋማቸው ወላዋይነት እና ጠንካራ ነው ብሎ ያመኑበትን ክፍል በመጠጋት በሚያደርጉት እንቅስቃሴ የሚታወቁት አቡነ ገብርኤል በቤታቸው ደብቀውት የነበረው ማካሮቭ ሽጉጥ ጠፋ፡፡ አጣሪ ኮሚቴ አቋቁመው ነገሩን እንዲጣራ እያደረጉ ነው፡፡ የአጣሪ ኮሚቴው ሊቀመንበር ከሀገረ ስብከት ስራ አስኪያጅነት ከተባረረና አሁን አቡነ ጳውሎስ ካረፉ በኋላ በአባ ገብርኤል ወደ ቦታው የተመለሰው አለም እሸት ነው፡፡ አለም እሸት ከስልጣኑ የተነሳው ከ12 መኪና በላይ የሚሆን ህዝብ ከአዋሳ መጥቶ አቤቱታ ስላቀረበበት እንደሆነ አይዘነጋም፡፡ ከቅዱስነታቸው ዕረፍት በኋላ ግን አለምእሸትን አባ ገብርኤል በማን አለብኝነት መልሰውታል፡፡ 

የሽጉጡን መጥፋት በተመለከተም ምንም እንኳ አለም እሸት ማኅበረ ቅዱሳናዊ የምርመራ ዘዴውን ተጠቅሞ ለማውጣጣት ቢሞክርም ልጁ ግን ባልወሰደድኩት ንብረት እንዴት እጠየቃለሁ በማለቱ አባረውታል፡፡ እውነተኛውን ሌባ ፈልጎ እንደማውጣት ድሀን በመግፋት መፍትሔ ሰጠን የሚል አሰራር የእነ አባ ገብርኤልን እና አለምሸትን አምባገነንነት ያሳያል፡፡
ሽጉጥ በጓዳ አስቀምጠው የሀይማኖት አባት ነኝ ለማለት መሞከር በእጅግ አሳፋሪ ነገር ነው፡፡ ነገሩ አሳፋሪ ስለሆነም ለፖሊስ ለማመልከት አልደፈሩም፡፡« እስራኤልን የሚጠብቅ አያንቀላፋም» የሚለውን ቃል ያላነበበቡት አባቶቻችን ራሳቸውን ለመጠበቅ የማያንቀላፋውን ጌታ ትተው ሽጉጥን ተስፋ ማድረጋቸው ይገርማል፡፡ እውነትን ጽድቅን እየሰሩ እግዚአብሔርን ተስፋ ከማድረግ ይልቅ ሁሉን እያደፈረሱ በሽጉጥ መታመን የማይጠቅም ነገር መሆኑን መዘንጋታቸው ገርሞናል፡፡

ብጹዕነታቸው በደርግ ጊዜ አድርገውት በነበረው ንግግር “ሰው ራሱን በሚያስፈልጉ ነገሮች መጠበቅ አለበት፡፡ እግዚአብሔርም እኮ የሚጠብቁት ጠባቂ መላዕክት አሉት” በማለት እግዚአብሔርን በማያውቅ ባህሪያቸው ስለ እግዚአብሔር የስህተት ትምህርትን አስተምረው እንደነበረ ይታወቃል፡፡ በቅዳሴያችን “መላዕክትን የምትጠብቃቸው አንተ ነህ” የተባለውን ጌታ፤ አቡነ ገብርኤል ግን ብቻውን ምንም እንደማያደርግ አስበው መላዕክቱ ይጠብቁት ነበር ማለታቸው በወቅቱ ትዝብት ላይ ጥሎዋቸው እንደ ነበረ ይታወሳል፡፡ እኚሁ ጳጳስ ታድያ እግዚአብሔርም ይጠበቃል ብለው የሚያምኑ በመሆናቸው ለራሳቸው መጠበቂያ ሽጉጥ ቢይዙ የሚደንቅ አይሆንም፡፡ ብቻውን ሀያል እና አሸናፊ የሆነውን ጌታ በማንነቱ አለማወቅ እና ልጆቹን አክብሮ እንደሚይዝ እና እንደሚጠብቅም አለማወቅ፣ ከማካሮቭ ሽጉጥ ጋር ተቃቅፎ ለመተኛት እንደሚዳርግ እሙን ነው፡፡ የሀይማኖት አባቶች የሚጠበቁት በመንፈስ ቅዱሰ እንጂ በሽጉጥ አለመሆኑን ለአባቶቻችን እግረ መንገዳችንን ለማስታወስ እንወዳለን፡፡