Wednesday, April 3, 2013

እስልምና በኢትዮጵያ ታሪክ (ክፍል አራት)


   የጽሁፉ ባለቤቶች፤ (ለእስልምና መልስ አዘጋጅዎች ነው)

የሙሶሊኒ ግመሎች

በታዋቂው የአፍሪካ ቀንድ የታሪክ ተመራማሪ ፕሮፌሰር ኤሪሊች ሃጋይ በ2007 ከተጻፈውና Saudi Arabia & Ethiopia [ISLAM, CHRISTIANITY & POLITICS ENTWIND] ከተሰኘው መጽሐፍ ምዕራፍ አንድ ላይ የተቀናበረ ታሪካዊ ጽሑፍ፡፡
የክርስትያን ኢትዮጵያ መንግስት በቀዳማዊ ኃይለስላሴ ጊዜ ከጣሊያን ወረራ በፊት በሰኔ 1934 ከሳውዲው ኢማም ያህያ ጋር የድሮውን ነገር ግን በጣም ጥሩ ያልነበረውን ግንኙነታዊ ድልድይ ለመመስረት ጥረት አድርገው እንደነበር ታሪኩ ይገልጣል፡፡ በአፍሪካ ቀንድ ላይ ያሉትን እስላማዊ ማህበረ ሰቦችን ያገናኘው ቀይ ባህር ከክርስትያን ኢትዮጵያ መንግስት ጋር ብዙ ግንኙነትን ለማሰራት ባለማስቻሉ፡፡ በኢትዮጵያ ነገስታትና በተለያዩ የአረብ አገር መሪዎች መካከል የነበረው የታሪካዊ ግንኙነት ታሪካዊ ዘገባ የሚመስለው ጥቂት ነበረ በማለት የታሪክ ተመራማሪው ያስረዳል፡፡ የዚህ ሰንካላ ግንኙነት እና ወዳጅነት ስምምነት መጥፋትም ዋናው ምክንያት የኢትዮጵያ መንግስት ሃይማኖት ነው፡፡
ለዚህ የወዳጅነት አለመኖር ችግር በተመለከተ የሚገኘው ታዋቂ ታሪክ በአስራ ሰባተኛው መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽ ላይ በንጉስ ፋሲለደስ የተሞከረው ሙከራ እንደነበረ ጸሐፊው ታሪካዊውን ማስረጃ ያቀርባል፡፡ ንጉሱ ከየመኑ ኢማም አል-ሙታዋኪ አላ አል-አላህ ጋር (በመልእክተኞቻቸው አማካኝነት) ውይይት አድርገው ነበር፡፡ ውይይቱም ያጠናከረው ነገር በኢትዮጵያና ከቀይ ባህር ማዶ ባሉት አጎራባች አገሮች መካከል ጥልቅ የሆነ መሰረታዊ ችግር የመኖሩን እውነታ ብቻ ነበር፡፡ የየመኑ ኢማም የኢትዮጵያ መንግስት ያቀረበውን የንግድና የፖለቲካ ትብብር ጥያቄ አልቀበልም ብሎ ነበር፡፡ ምክንያቱ ምን ነበር? የየመኑ ኢማም ከኢትዮጵያ መንግስት የጠየቀው ጥያቄ ነበር፣ ጥያቄውም የሃይማኖት ለውጥ ነበር፣ ፕሮፌሰር ኤርሊች ማስረጃውን ጠቅሶ እንደሚከተለው እንደነበር አስቀምጦታል፡ ገዢውም ያለው “የኢትዮጵያው ንጉስ” ማለትም ፋሲለደስ “በቅድሚያ የነጃሺን ፈለግ መከተል አለበት” ነበር፡፡ በመሆኑም የወዳጅነት ስምምነቱ እንዲኖር ንጉሱ በቅድሚያ ሃይማኖቱን “ወደ እስልምና መለወጥ አለበት” የሚል ሰበብ ነበር፡፡ እንደዚህ ዓይነቱ መሰረታዊ ችግር ነው ጥልቅ የሆነ ዘላቂ ችግር ከውጭ ብቻ ሳይሆን ከውስጥም አገሪቱን የከበባት መሆኑን የሚያሳየው፡፡

በ1930ዎቹም ውስጥ በቀዳማዊ ኃይለስላሴ ለሳውዲው ንጉስ ለኢብን ሳውድ የቀረበው ጥያቄም በጣም የማይሆን እድል አጋጥሞት ነበር፡፡ በእርግጥ በዚያን ጊዜ ኢትዮጵያ ጠንካራ የሆነች የክርስትያን አገር ሆና ነበር፡፡ ስለዚህም በዋሃቢያ እምነት ላይ የተመሰረተው የሳውዲ መንግስት የኢትዮጵያን መንግስት የእነተባባር ትያቄ ሊቀበለው አልቻለም ነበር፡፡

ነገር ግን የአፍሪካን ቀንድና አረቦችን ቀይ ባህር ያገናኛል የሚለው ፅንሰ ሐሳብ ለጣሊያን ቅኝ ገዢዎች በጣም ጠቃሚ የነበረ ስልት ነበር፡፡ ከ1890 ዓም ጀምሮ የራሳቸውን አካባቢያዊ ማህበረ ሰብ በኤርትራ ውስጥ መስርተው የነበሩት ጣሊያኖች ማህበረሰባቸውን በቀይ ባርህ ስም ላይ የተመሰረተና “ማሬ ኤሪትርየም” የሚል ስያሜ ሰጥተውት ነበር፡፡ ጣሊያኖቹ በሁለቱም የባህሩ አካባቢ አገሮች ላይ ተፅዕኖአቸውን ለማምጣት አልመው ነበር፡፡ ስለዚህም በሙሶሎኒ ስር ይህ ረቂቅ ሃሳብ በጣም ንቁ የሆነ ፖሊሲ ሆኖ ነበር፡፡ በ1926 ሙሶሊኒ የጣሊያንን ማህበረ ሰብ በዲክታተሪያል ቁጥጥር ስር ካደረገ በኋላ ያወጀው የመጀመሪያው ነገር “የናፖሊዮናዊ ዓመትን” ነበር፣ በዚህም የፋሽስቱ መንግስት እራሱን የሚያረጋግጠው በሜዲትሬኒያን ባህር እና በቀይ ባህር ላይ እንደነበር ይፋ ሆኗል፡፡ በመሆኑም በጣም ሃይለኛ የኤርትሪያ ገዢ የነበረው ጃኮቦ ጋስፓሪኒ ሁለት መልክ ያለውን ተግባሩን ጀመረ፡፡ በአንድ በኩል ጣሊያን በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገባበትን ነገር ሲያጠብቅ በሌላ ጎኑ ደግሞ ከአረቢያኖች ጋር ትብብርን ለመመስረት ጥረትን አደረገ፡፡ 
በመስከረም 1926 ላይ ጋስፓሪኒ ከየመኑ ኢማም ያህያ ጋር የትብብር ስምምነትን ፈረመ ይህም ጣሊያኖች የመኖችን እንዲያስታጥቁ መንገድን ከፈተ፡፡ 

ምንም እንኳን ይህ አዲሱ የአስመራ-ሰንዓ የትብብር ስምምነት ለሳውዲው ኢብን ሳውድ (ከኢማሙ ጋር በወቅቱ በግጭት ላይ ለነበረው) ጥቃት ቢሆንም፣ በ1927 ደግሞ ጋስፓሪኒ ከሳውዲዎችም ጋር ዲፕሎማቲካዊ ግንኙነቶችን ጀምሮ ነበር፡፡

ጣሊያኖች ታላቋን የመንን ለመቆጣጠር እንዲችሉ፣ ይህም ብሪቲሽ በሳውዲ ላይ ያላትን ተፅዕኖ እንደያዘች እንዲሆን ለንደንን ማስገደድ እንዳለባቸው ጋስፓሪኒ ሙሶሊንን አሳመነው፡፡ ነገር ግን በ1920ዎቹ ላይ ኃያል የነበረችውን ቢሪቴንን በቀይ ባህር ላይ ዋና ኃይል ለመሆን ጣሊያኖች የነበራቸው ሕልም ተጋፍጠዋት ነበር፡፡ የብሪቲሽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ኦስቲን ቻምበርሊን በየካቲት 1927 ላይ ለሙሶሊኒ በግልጥ ነግሮት የነበረው ነገር ቀደም ብሎ “የንጉሱ መንግስት በአረቢያ ዙሪያ ባለው የቀይ ባህር ላይ ማናቸውም የአውሮፓ ሃይል ምንም ነገርን እንዳያደርግና ይህ ዋና ፍላጎታቸው እንደሆነ ነግሮታል”፡፡ እንዲህ ዓይነት የሆነውን የብሪቲሽን ውሳኔ በማግኘት (ብሪቲሾች በየመን ላይ እርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ መሆናቸውን ስለጠቆሙ) ሙሶሊኒ የቀይ ባህር ህልሙን (ለጊዜውም ቢሆን) መርሳት ነበረበት፡፡ ስለዚህም ጋስፓሪኒ ከኤርትራ ተነሳ የመኖች ሳውዲን ለማጥቃት ለነበራቸው ጥረትም ቀጥተኛ የሆነ የጣሊያን እገዛ አልተሰጠም፣ ከሳውዲም ጋር ይደረግ የነበረው ዲፕሎማቲካዊ እንቅስቃሴ ሙሉ ለሙሉ ቆመ፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ውስጥም ይደረግ የነበረው ሰርጎ መግባት ቀዘቀዘ፡፡ ቀጥሎም በነሐሴ 1928 ጣሊያን የሃያ ሁለት ዓመት የወዳጅነት ስምምነት ከክርስትኗ መንግስት ጋር ተፈራረመች፡፡

በ1932 ዓለም አቀፉ ታላቅ ኪሳራ ጋር እንዲሁም ከጊዘያዊ የብሪቴን ድክመት ጋር ሙሶሊኒ የቀይ ባህር ሃያልነቱን ምኞት እንደገና አነሳው፡፡ ስለዚህም በሁሉቱም ወደቦች ዙሪያ እንቅስቃሴዎች እንደገና ጀመሩ፡፡ በኤርቲሪያ ውስጥ ገዢው ኮራዶ ዞሊ  የኃይለስላሴን መንግስት እንዲያዳክምለት ጋስፓሪኒን እንደገና መልምሎት ነበር፡፡ የውስጥ ማዕከላዊ ኃይሎችን የማጠናከር ፖሊሲ በኢትዮጵያ ላይ ያተኮረው በትግሬያውያን ጎሳዎች ላይ ነበር ይህም በጥንቱ የአማራ ገዢ መደብ ጥላቻ ላይ የተመሰረተ እና ስያሜውም “ፖለቲካ ትግሪኛ” የሚል ነበር፡፡ ይህም ቀስ በቀስ አሁን የተጠናከረው እስላም እንደ ማዕከላዊ ኃይል በኢትዮጵያ ውስጥ እንደገና ሊጠናከር ይችላል በሚለውም ሐሳብ ላይ ተመስርቶ ነበር፡፡ በአረቢያ ውስጥ ኢጣሊያኖቹ ከሳውዲ ጋር በመጋቢት 29 1932 “የንግድና የወዳጅነት” ስምምነትን ተፈራረሙ፡፡ ነገር ግን እንደገና ዋናው ትኩረታቸው በየመን ላይ ነበር፡፡ ጣሊያኖች በሰንዓ የነበራቸውን እንቅስቃሴ በተግባር በጣም አጠናክረውት ነበር፤ እናም ኢማም ያህያን ሳውዲዎችና የመን የሚከራከሩበትን አካባቢ “ኢርን” ሳውዲዎችን ተቃውሞ እንዲይዝ ያበረታቱት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በየመን ላይ ጣሊያኖች ይጫወቱት የነበረው ካርድ አሳፋሪ ነበር፡፡ በግንቦት 20 1934፣ እንደተጠቀሰው ያህያ በጦርነቱ ላይ ተሸነፈ ስለዚህም “በኢር”ና በአረቢያ ባህረ ሰላጤ ላይ ሳውዲ ያላትን አገዛዝ እንዲሁም የዋቢዝምን የበላይነት ገዢነት መቀበል ነበረበት፡፡ ስለዚህም የኢጣሊያኖች በአረቢያ ላይ ያላቸው ፖሊሲ የዞረው ሳውዲዎችን በማባበልና እነርሱንም ወደፊት በአካባቢው የሚመጣውን የፋሺስትን የበላይነት አንድ ጊዜ እስኪመጣ ድረስ እንዲቀበሉ በማዘጋጀት ላይ ነበር፡፡

ጣሊያኖች የአረቢያን - የመን ካርዳቸውን ካጡ ከሰባት ቀናት በኋላ የኢትዮጵያው አማራጭ መስመር መያዝን ጀመረ፡፡ ግንቦት 27 1934 የምስራቅ ትግሬ ገዢ የነበረው ኃይለ ስላሴ ጉግሳ ለጣሊያኖች በምስጢር የገባላቸው ቃል ኪዳን ሰራዊታቸው ወደ ኢትዮጵያ መካከል ወይንም እምብርት የሚገባበትን መንገድ እርሱ እንደሚከፍትላቸው ነበር፡፡ ከአራት ቀናትም በኋላ ሙሶሊኒ ሚኒስተሮቹ ኢትዮጵያን ለመውጋት እንዲዘጋጁ አዘዘ፣ ከዚያም በሐምሌ ወር እርሱ እራሱ ሙሶሊኒ ዕቅዱን መቆጣጠር ጀመረ፡፡ ታህሳስ 5 1934 በኢትዮጵያና በሶማሊያ ድንበር ላይ ግጭት ተፈጠረ (በወልወል) ያም የአቢሲኒያን መፍረክረክ የበለጠ ለማቀጣጠል (የታቀደ) ነበር፡፡ የሙሶሊኒ ዛቻና ኢትዮጵያን ለመውጋት የሚያደርገው ዝግጅት የመንግስታቱን ህብረት የአንድነት ጥበቃ ፅንሰ ሐሳብ በ1935 ዓመት ሙሉ ሲያናጋው ቆይቷል፡፡ በዚህም ጊዜ ውስጥ የሙሶሊኒን ኃይለኛ ውሳኔና እንዲሁም የጀርመኑን ሂትለርን ለመደባለቅ የሚያደርገውን ዛቻ በማየት ብሪቲሽ ሁኔታውን ዝቅ አድርጋ ልትመለከተው አልደፈረችም፡፡ ስለዚህም ቢሪቲሾች በ1935 በጋው ላይ ምንም እንኳን የዲፕሎማቲክ ጥረት ቢያደርጉም ኢትዮጵያን አሳልፎ ለመስጠት መወሰን ነበረባቸው፡፡ በዓለም ዙሪያ እየገዘፈ ካለው ሁኔታ ጋር ለመጋፈጥ እየጣሩ የብሪቲሽ ፖሊሲ አውጭዎች በቀይ ባህር ዙሪያ ላይ በጣም ጥንቃቄ ያለው እንቅስቃሴ ይወስዱ ጀመር፡፡ ፋሽስት በመጨረሻ በጥር 3 1935 ላይ ኢትዮጵያን በወረረበት ጊዜ ሙሶሊኒ አምኖ የነበረው ነገር በትክክል ከብሪቲሾች ጋር የግጭት አደጋ ውስጥ እንደማይገባ ነበር፡፡

የሙሶሎኒ ጦርነትና ትርጉሙ

በኢትዮጵያ ላይ ሙሶሊኒ የሚያሂደው ጦርነት በእርሱ እይታ የመረማመጃ ድንጋይ ብቻ ነበር፡፡ የጣሊያኑ ዲክታተር የጥንቱን የሮማን ግዛት በምስራቅ ለማምጣት ሕልም እንደነበረው በፍፁም አልሰወረም፡፡ ስለዚህም የኢትዮጵያ ጦርነት ማለት የአፍሪካ ጦርነትና ወደ መካከለኛው ምስራቅ የመግቢያ መስፈንጠሪያ ነበር፡፡ ስለዚህም ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ በኩል ወደ ሜድትራኒያን የጓሮ መግቢያ በር እንድትሆን ታስቦ ነበር፡፡ የሆነው ሆኖ ከእንግሊዝና ከፈረንሳይ ጋር ቆይቶ ጦርነት እንደማይቀር ሙሶሊኒ አውቋል፤ ይህንንም ከአካባቢው የጦር ትብብርና እርዳታ ካላገኘ እንደማይወጣውም ተገንዝቦ ነበር፡፡ ስለዚህም እርሱ የእስልምናንና የአረባዊነትን ኃይል በመጠቀም ከፈረንሳይና ከእንግሊዝ ጋር ሊመጣ ለሚችለው ጦርነት ያዘጋቻቸው ጀመር፡፡ የጣሊያን ከእስልምና ጋር መዳራት በ1920 በሊቢያ ውስጥ ከተከሰተው ችግር ጀምሮ፤ ችግር አጋጥሞታል፣ ይህም የሳኑሲ ተቃውሞ ስላጋጠመው ነበር፡፡ እነርሱንም በጭካኔ ከመጨፍጨፍ ሌላ ምንም አማራጭ ስላልነበረው አጠፋቸው እና መሪያቸውን ኡማር አል-ሙክታርን በ1931 መስከረም ወር ላይ በአደባባይ ሰቀለው፡፡ ይህ ጭካኔ የሙሶሊኒን ስም በአጠቃላይ ሙስሞሊሞች ዘንድ መጥፎ አድርጎትና አዋርዶት ነበር፡፡ ይህንን ስሙን እንደገና ለማንሳት በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገው ጦርነት ወሳኝ ነበር፡፡ ስለዚህም በ1932፣ ስሙን “የእስልምና አዳኝ” ለማድረግ የሚቻለው ኢትዮጵያን በመውረርና በ1896 በአድዋ ጣሊያንን ድል ያደረገችውን ኢትዮጵያን ከመበቀል ውጭ፣ እና ስልታዊ መካከለኛ ምስራቅን ለመቆጣጠር መግቢያ ከማድረግ ውጭ ኢትዮጵያን መውጋት መስሎ የቀረበው ስለ እስልምና መዋጋት ተደርጎ ነበር፡፡
በ1934 ውስጥ ጣሊያን የእስልምና ደጋፊ፣ የአረብ ደጋፊ ናት የሚለው የቅስቀሳ ጥረት በጣሊያን መር ምስራቃውያን ዘንድ በትልቅ ቅናት ተቀጣጥሎ ነበር፡፡ የዚህም እንቅስቃሴ ዋና መልእክት ኢትዮጵያ የምትባለው አገር፡ ከፊል አረመኔያዊ የክርስትያን መንግስት ስትሆን በታሪኳ ሁሉ ውስጥ ሙስሊሞችን የጨቆነች አገር ናት የሚለው ነበር፡፡ ይህ የጥላቻ አነጋገር በዚያን ጊዜ በነበረው የመካከለኛው ምስራቅ አገሮች እስላማዊ ደጋፊ አገሮች ሁሉ ውስጥ ተሰራጭቶ ነበር፡፡ በመሆኑም በአረቡ አገር ሁሉ ውስጥ ታላቅ ክርክርንና ልዩነቶችን ፈጥሮ ነበር፡፡ አሁንም በአገሪቱ ውስጥ ባሉት የዋሃቢያ ተከታዮች ዘንድ የሚሰራጨው ቅስቀሳ ተመሳሳይ ነው ማለትም ኢትዮጵያ እስልምናን የጨቆነች አገር ናት እንዲያውም የእስልምና ጠላት ናት የሚለው ነው፡፡ በሚቀጥለው የፕሮፌሰር ኤሊሪች ጽሑፍ በኢትዮጵያ ውስጥ የዋሃቢያን እንቅስቃሴ በጥልቅ የምንመለከተው ይሆናል፡፡   

ኃይለሥላሴ እና እስልምና፡

ሙሶሊኒ የእስልምና ጠባቂና ነፃ አውጪ ነው የሚለውና ልጅ ኢያሱ ደግሞ ሕጋዊ የኢትዮጵያ ንጉስ ነው የሚሉት መልእክቶች ለኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች በስፋት ተነገሩ፡፡ በአጣሊያን የመረጃ ምንጮች መሰረት ሙሶሊኒ ኃይለስላሴን አስወግዶ እስልምናን የአገሪቱ የፖለቲካ መሳሪያ የማድረጉ ጉዳይ በጥሩ ሁኔታ በሐረር፣ በኦጋዴን፣ በደቡብ ኢትዮጵያ ኦሮሞዎች ዘንድና እንዲሁም በአዲስ አበባ ባሉት አረብ-እስላም ነጋዴዎች ዙሪያ  በስፋትና በብቃት ተሰራጨ፡፡ ፋሺስቶች ለሁሉም ዓላማና ፍላጎቶቻቸው ወኪሎቻቸው ሁሉ የኢትዮጵያን መከላከያ ለማዳከም የሚያስችልን ስራ ለመስራት በሙስሊሞች ማህበረ ሰቦች ሁሉ ውስጥ በስፋት ተንቀሳቀሱ፡፡ ስለዚህም ወረራውን ለማድረግ ሲዘጋጁ ጣሊያኖች ሰባ ሺ የሙስሊም ወታደሮችን (ተዋጊዎችን) “አስካሪስ” የሚሏቸውን መልምለውና ቀጥረው ነበር፡፡ እነርሱንም የመለመሉት ከኤርትሪያ፣ ከሶማሊያ የነበረ ሲሆን ከአረቢያም እንደዚሁም ከሌሎች የአረብ አገሮችም ጭምር ነበር፡፡ በራሱ በጦርነቱ ወቅትም እጅግ ብዙ የኦሮሞ ሙስሊም ተዋጊዎች የጣሊያንን ወራሪ ጦር ሰራዊት ተደባልቀውት ነበር፡፡

የኃይለስላሴ ጥረት፡

በጊዜው በውጥረት ላይ የነበረው የኃይለስላሴ መንግስት በተለያዩ መንገዶች ልዩ ልዩ ጥረቶችን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ለወታደራዊው ዝግጅት በአውሮፓውያን መንግስታት በኩል እርዳታ ለማግኘት ጥረት ቢደረግም የሙስሊሞች ነገር ግን ችላ ሊባል የሚገባ ነገር አልነበረም፡፡ ግራኝ መሐመድ ያስቀመጠው ታሪካዊ ጠባሳ እንዳለ ነበርና ስለዚህም በአፍሪካ ቀንድ ላይ ያሉትን ሙስሊሞች የውጭ ኃይላት አንቀሳቅሰዋቸውና ድጋፍም አድርገውላቸው በአገሪቱ ውስጥ የሙስሊም መንግስት ለመመስረት ትግል ያደርጋሉ የሚለው ፍርሃት አሁንም እንዳለ ነው፡፡ የሆነው ሆኖ ፕሮፌሰር ታሪክን አጣቅሶ ያስቀመጠው የኃይለስላሴ መንግስት ለዚህ ሶስት ዘርፍ ያለው ምላሽን እንዳደረገ ነበር እነዚህም፡
To be continued…..