Monday, April 22, 2013

«ኩሉ ዐረየ ወኅቡረ ዐለወ፤ አልቦ ዘይገብራ ለሠናይት፤ አልቦ ወኢአሐዱ»

ሰነፍ በልቡ። አምላክ የለም ይላል። ረከሱ በበደላቸውም ጐሰቈሉ በጎ ነገርን የሚያደርጋት የለም።
የሚያስተውል እግዚአብሔርንም የሚፈልግ እንዳለ ያይ ዘንድ እግዚአብሔር ከሰማይ የሰው ልጆችን ተመለከተ።
ሁሉ በደሉ፥ አብረውም ረከሱ አንድ ስንኳ በጎን ነገር የሚያደርጋት የለም።
ሕዝቤን እንጀራ እንደሚበላ የሚበሉ ግፍ አድራጊዎች ሁሉ አያውቁምን? እግዚአብሔርንም አይጠሩትም። መዝ ፶፫፤፩-፬

ማንም በማንም ኃጢአት አይጠየቅም። ማንም ራሱን ጻድቅ አድርጎ በሌላ ሰው ድካም መፍረድ አይገባውም። ይህ የእግዚአብሔር ቃል ለእውነተኛ ክርስቲያኖች የተሰጠ መመሪያ ነው። በትክክልም እንገነዘባለን። ይህን ማለት ግን መንጋውን ለመምራት ሥልጣንና አደራ ተረክበው፤ በሌላ መልኩም ከእግዚአብሔር ጋር ቃለ መሐላ በመፈጸም በጎችህን እንጠብቃለን ብለው አዋጅ ተናግረው ሲያበቁ በማጭበርበርና ወደ ሥርየት ከማቅረብ ይልቅ በጎቹን ኃጢአት በማስተማር የተካኑ፤ ቤቱን በማፍረስ የተሠማሩ የዐመጻና የየበደል ማኅደሮችን በተቀመጡበት ቦታ ተሸክመናቸው እንዞራለን ማለት ባለመሆኑ አንድም አልታወቀብኝም ከሚሉት ዐመጻ ወጥተው በንስሐ እንዲመለሱ፤ አለያም ያንን የጣፈጣቸውን ዐመጻ ቤቴ ብለው እንዲኖሩበት ለማድረግ ሲባል እውነቱ ሊነገራቸው ይገባል ብለን እናምናለን። የክርስቶስ ቤተሰቦች በተናጠል ብዙ ኃጢአት ይኖረናል። የግላችንን ኃጢአት ግን ወስደን ለቤተክርስቲያን የኃላፊነት መድረክ ማዋል ግን የበደል በደል ነው። ከተራራ ላይ የተቀመጠችን መብራት መሸሸግ አይቻልምና ለተቀመጥንበት የከፍታ ስፍራ ጥንቃቄ ማድረግ የግድ ነው።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ጳጳስ እንደሆኑ የሚነገርላቸው አባ ኤዎስጣቴዎስን የተመለከተ መረጃ ከዚህ ቀደም ማውጣታችን ይታወሳል። የዚያ የመልካም ነገር ሁሉ እንቅፋት የሆነው ማኅበር የ/ማቅ/ ፓትርያርክ ሆነው ከሲኖዶስ በማፈንገጥና እንደአሜባ ቤተክርስቲያንን እየሰነጣጠቁ ባርኬ ሰጥቼሃለሁ በማለት ችግር ሲፈጥሩ እንደነበር ዘግበንበታል። በዳላስ ቅ/ሚካኤልን በሰባኬ ወንጌሉ በኩል ሁለት ቦታ በመሰንጠቅ በሥላሴ ስም የማቅ አዳራሽ የተባረከው በኚሁ የማቅ ፓትርያርክ ነበር። ያም ሆኖ አባ ኤዎስጣቴዎስን የነካቸው ማንም አልነበረም። ይሁን እንጂ የመሰነጣጠቅ ልምዳቸው፤ እየተከተለ እነሆ ብፁዕ ነኝ የሚሉበትን የእረኝነት ቀሚሳቸውን የሚሰነጥቅ ነውር ተከትሎ ለጥፋት ዳረጋቸው።

መሸከም ያልቻሉትን ድስት አስቀምጠው የሚችሉትንና የፈለጉትን የማድረግ መብት እንዳላቸው እናምናለን። ኃጢአቱ ያልተሰጣቸውን ጸጋ ለማግኘት መፈለግ እንጂ «ጋብቻ ክቡር ነው መኝታውም ንጹህ ነው» ያለው የእግዚአብሔርን ቃል መፈጸም አይደለም። ክፋቱ ያንን የእግዚአብሔር ቃል አልፈልግም ብሎ ሊጠብቃቸው የተሰጡትን በጎች እያጋደሙ በዝሙት ሰይፍ ማረድ አይደለም። ለዚህም እግዚአብሔር ይቅር ባይ ነውና ንስሐ ይግቡበት። ሚስት ማግባትም በደል አይደለምና የማይችሉትን ሰው ሰራሽ ድስት በመሸከም ከመንገዳገድ የሚችሉትን አግብተው የሥጋን ሸክም እያቀለሉ መኖር ይሻላልና ይህንኑ ይተግብሩ ምክራችን ይህ ነው።
ለነገሩ የኃጢአት ዋጋው ሳይታሰብ እንደዚህ ዓይነት ዋጋ የሚያስከፍል በመሆኑ እንጂ  የብፁዕነት ስያሜን ያለአቅማቸው ተሸክመው የሚንገዳገዱ ስንኩላን  ሹማምንት ብዙዎች ናቸው። የመገለጡ ዕጣ ቀድሞ ለአባ ኤዎስጣቴዎስ ከመውጣቱ በስተቀር ይህ ድርጊት የእሳቸው ብቻ አይደለም። ሌሎቹንም በዚህ አጋጣሚ የምንመክራቸው እግዚአብሔር ኃጢአትን እንጂ ኃጢአተኛን አይጠላምና በስመ ብፁዕ የሸፈናችሁትን ኃጢአት ተሸክማችሁ፤ ለራሳችሁ ሞትን፤ ለቤተ ክርስቲያን ውርደትን፤ ለእግዚአብሔር መንጋውን መጠበቅ ያለመቻል ቅጥረኝነት ለመላቀቅ ንስሐ ግቡ፤ ጋብቻችሁን መስርቱ፤ ንግድና ገንዘብ የመሰብሰብ ክፋታችሁን አራግፉ እንላለን። ኃጢአታችሁ ከራሳችሁ አልፎ ሀገር ሁሉ አውቆታል። ሰምቶታል። ኢትዮጵያዊ ይሉኝታ ስለሚያጠቃው ገመናችሁን ሸፈነው እንጂ ፈረንጅ ቢሆን ኖሮ በጋዜጣ ላይ አውጥቶ ንስሐ የመግባት እድላችሁን በማፋጠን ይተባበራችሁ ነበር። ያ ጊዜ ከመድረስ በፊት ለራሳችሁም፤ ብፁዕ አለመሆናችሁን እያወቃችሁ ብፁዕ መባላችሁ እንደማይገባችሁ አምናችሁ እንደዚያ እንደቀራጭ ራሳችሁን ዝቅ አድርጋችሁ ለንስሐ አዘጋጁ።
ለአባ ኤዎስጣቴዎስ የተጻፈው ሴት አዳኝና አደገኛ የወሲብ ቀበኛ የተባሉበትን ደብዳቤ አስፍተው/zoom/አድርገው እንዲያነቡ አቅርበነዋል።

እዚህ ላይ ይጫኑና አስፍተው ይመልከቱ