Monday, April 15, 2013

የካናዳዋ፤ ዊኒፔግ ቅ/ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከገለልተኝነት ወደአሜሪካው ሲኖዶስ ተቀላቀለች።





በካናዳ፤ ዊኒፔግ ከተማ፤ 353ኛው Mountain Ave መስቀለኛ መንገድ ላይ የምትገኘው የደብረ ገነት ቅ/ማርያም ቤተክርስቲያን ለብዙ ጊዜ ከየትኛውም ሲኖዶስ ነጻ ሆና በገለልተኝነት መቆየትዋ ይታወቃል።  ይሁን እንጂ  የቆይታ ጊዜዋን በማጥናትና በአዲስ አበባ ያለውን የሲኖዶስ የምርጫ ሂደት በመገምገም፤ ከእንግዲህ በአንዱ ሲኖዶስ ስር መጠቃለል እንደሚገባት በማመን ካሉት ነባራዊ ሁኔታዎች በመነሳት በአቡነ መርቆሬዎስ በሚመራው ሲኖዶስ ስር ለመጠቃለል ወስናለች።

በዚሁ መሠረት እስካሁን እውቅና ሳይሰጡት ለቆዩት የአሜሪካው ሲኖዶስ ሕጋዊ እውቅና በመስጠትና እንደትክክለኛው ሲኖዶስ በመቁጠር መንፈሳዊ ግንኙነቷን እንደምታደርግ በኦፊሴል በመግለጽ መጠቃለሏን የደረሰን መረጃ ያስረዳል።
የኢትዮጵያውን ሲኖዶስ ሽኩቻና የፓትርያርኩን ምርጫ ሂደት የመንግሥት እጅ አለበት በሚሉ ብዙ ገለልተኛ የዳያስፖራ አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ቅሬታ በማሳደሩ እውቅና ወደከለከሉት የአሜሪካው ሲኖዶስ ቀስ በቀስ እየተቀላቀሉ ይገኛሉ። ወደፊትም ይህ ሁኔታ በሌሎቹም ገለልተኛ አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ሊኖር እንደሚችል ይገመታል። የአሜሪካው ሲኖዶስም አብያተ ክርስቲያናትን በመንፈሳዊ አገልግሎት የመድረስና ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ በየአኅጉረ ስብከቱ ሐዋርያዊ ጉዞ በማድረግ የማስተማርና የማሳመን የእቅድ መርሐ ግብር ነድፎ የነበረ ሲሆን እነዚህ አብያተ ክርስቲያናት ወደአሜሪካው ሲኖዶስ ቀስ በቀስ መቀላቀል መጀመራቸው የዚህ እቅድ የሥራ ውጤት ይሁን አይሁን ለጊዜው የታወቀ ነገር የለም።
በደብረ ገነት ቅ/ማርያም ቤተክርስቲያን ውስጥ የገብርኤልም ጽላት በደባልነት እንዳለ ለማወቅ ተችሏል።
ዊኒፔግ በሀገረ ካናዳ፣ በማኒቶባ ክፍለ-ሀገር የምትገኝ ስትሆን የአየር ንብረቷ ቀዝቃዛና በርካታ ኢትዮጵያውያን የሚገኙባት ከተማ ናት።