Monday, March 4, 2013

ጥንቆላ - በሀገራችን ፣ በቤተ ክርስቲያናቸን እንዲሁም በእያንዳንዳችን ላይ ሊኖረው የሚችለው ተጽዕኖ


ክፍል ሁለት         (www.abaselama.org)


ባለፈው ጽሑፌ ጥንቆላ ምን እንደሆነ ጥቂት ለማሳየት ሞክሬያለሁ፤ በሰፊው ግን አልገለጥሁትም። የሰይጣንን ክፋት በሰፊው ከመግለጥ የእግዚአብሔርን ደግነት አጉልቶ መግለጥ ይሻላል የሚል እምነት ስላለኝ ነው። ነገር ግን ወገኖቼ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ጥንቆላን እንደቀላል ልማድ በማየት በጨለማው ገዢ ሥር ሲወድቁ እያየሁ ስለማዝን እውነታውን ለማሳየት ምክሬያለሁ። ዛሬ ደግሞ አንዳድ መናፍስት ጠሪዎችና ደጋሚዎች የሚያጠምቁበትን ዘዴ ከአንድ ደብተራ ጓደኛዬ ያገኘሁትን ምስጢር በጥቂቱ መግለጥ እሞክራለሁ።


አስማቱ በመስቀል፤ በጣት ቀለበት እና በመቁጠሪያ ሊሠራ ይችላል። በመስቀል ቅርጽ እንዲሁም በመቁጠሪያነት ለድግምቱ የሚያገለግሉ እጸዋት ሁለት ናቸው። አንደኛው አርግፍ የሚባል ሲሆን ሁለተኛው ጠንበለል ይባላል። እጸዋቱ በደጋማ ሥፍራዎች ይገኛሉ። በትክል ድንጋይና በሰከላ በብዛት ይገኛሉ። የአስማቱ ባለሙያዎችም ከላይ በጠቅስሁአቸው ቦታዎች አሉ። በተለይ አርግፍ የሚባለውን እንጨት በአካባቢው ያሉ ገበሬዎች እየጠረቡ ለሕጻናት ከሰይጣን እና ከቡዳ ይጠብቃል እያሉ ባንገታቸው ያደርጉላቸዋል።

 ይህ እንጨት የማይሰራበት አስማት የለም ይባላል፤ ሰዎችን ለክፉዎች አሳልፌ እንዳልሰጥ ሁሉን ከመግለጥ እቆጠባለሁ። ለማጥመቅ ሲጠቀሙበት ግን የሚያደርጉትን መናገር ግድ ሆኖብኛል። እንጨቱን ሲቆርጡት የሚደግሙት አላቸው። ሰባት ቀን ሲደግሙ ቆይተው የዶሮ ወይም የሰው ደም ቀብተው ይቆርጡታል። ቅጠሉን በአዲስ ሸክላ[ውሃ ወይም እህል ያልነካው] ዘፍዝፈው አርባ ቀን ከደገሙበት በኋላ ዋናው ለማጥመቅ የተዋረሰው ግለሰብ ይጠመቅበታል። አጥማቂው አርባ ቀን በተደገመበት ውሃ ሲጠመቅ መናፍስት ያለ ከልካይ በብዛት እንደሚያድሩበት ይነገራል።


 ግንዱን ወይም ሥሩን መቁጠሪያ አድርጎ ወይም በመስቀል ቅርጽ ሊይዘው ይችላል፤ ወይም በሰውነቱ ትከሻውና ግንባሩ አካባቢ ሊያስቀብረው ይችላል። በአንድ ገመድ ውስጥ የሚገኙ መቁጠሪያዎች ሁሉ አንድ ዓይነት ወይም የተደገመባቸው እንጨቶች ላይሆኑ ይችላሉ። ከነዚያ መቁጠሪያዎች መካከል አንዷ ወይም ሁለቱ ጠጠሮች የተደገመባቸው ናቸው። መቁጠሪያ ከሄትም ተገዝቶ አንድ ወይም ሁለት የተደገመባቸው ጠጠሮችን በገመዱ ውስጥ መጨመር ይቻላል።

 ሌላው በብር ቀለበት ተደግሞ እጣት ላይ ወይም ክንድ ላይ ሊታሰር ይችላል። በእግዚአብሔር ጥበቃ ሥር ያልተገኘ ማንኛውም ሰው ሁሉ የዚህ አስማት ሰለባ ሊሆን ይችላል። መናፍስቱ ከሰውየው ላይ እየወረዱ እርሱ በሚያጠምቀው ሰው ላይ እያደሩ ይቀልዳሉ። ቡዳ ነኝ ብሎ ጮኾ ከወጣ በኋላ በሌላ ጊዜ አይነ ጥላ ነኝ ይላል። በሌላ ጊዜ የደብተራ ድግምት ነኝ ሊል ይችላል። እራሱን እየቀያየረ ድራማ ይሰራል። ዛሬ ጩኾ ወጥቶ ከሆነ ነገም ተመልሶ ይጮሓል። ይህን ለማረጋገጥ ትንናንትና ጮኾ ወጣለት የተባለውን ሰው በማግስቱ ተከታትሎ ማየት ነው። ተመልሶ ሲጮህ ታገኙታላችሁ። ሰይጣን ሰይጣንን አያወጣውም በገዢ ጋኔንና በተገዢው ጭፍራ የሚከናወን ስምምነት ነው እንጂ። አንዳዴ የስጋ ሕመም ያለበት ሰው በጋኔኑ ሥር ከወደቀ የርሱ ማደሪያ ከሆነ በኋላ ከሥጋ ሕመሙ ሊፈወስ ይችላል። መንፈሱ ታሥሮ ሥጋው ነጻ ሊወጣ ይችላል ማለት ነው። ለምሳሌ በራስ ምታት፣ በአእምሮ ጭንቀት፣ በእበጥ፣ በሽባነት እራሱ ከመታቸው በኋላ ታዋቂ ወደ ሆነ ነባር ጠንቋይ ሄደው እንዲለማመጡት መስዋእቱን እንዲያደርጉ እንዲሰግዱለት ያደርጋል፤ በሽተኛው ሥጋው ይፈወሳል መንፈሱ ግን ይታሠራል። የሰይጣን አገልጋይ ለመሆን ቃል ይገባል፤ በዚህ ጊዜ በህብረተ ሰቡ ቋንቋ ሰከነለት ይባላል። እርሱም በተራው ታዋቂ ጠንቋይ ይሆናል። ብዙ ጠንቋዮች በሽተኛ የነበሩ ናቸው  ሁሉም የሰከነላቸው አሩሲዋ እመቤት ዘንድ ከሄዱ በኋላ ነው ይባላል። እነርሱን ብትጠይቁአቸው ይህን እውነት አይክዱም።

 ሥርዓቱ ይለያይ እንጂ አጥማቂዎችም የሚያደርጉት ይህንኑ ነው። ምዕመናን ግን ባለማወቅ የእግዚአብሔር ጸጋ ነው ይላሉ። ይህ አባባል እውነት አይደለም። ዛሬ በወረራ መልኩ አጥማቂ ነን የሚሉ ሰዎችን ብናስተውል የማጥመቅ ጥንቆላ የተማሩ እንጂ በእግዚአብሔር የተመረጡ አይደሉም። አጥማቂው ግርማ ቦሌ ጎርጎርዮስ ብሎ ቤተ ክርስቲያን ከፍቶ ሲያጠምቅ ሄጄ ጎብኝቸዋለሁ። በዚያን ጊዜ የርሱ ረዳት የነበሩ ሁለት ግለሰቦች ዛሬ ታዋቂ አጥማቂ ሆነዋል። በተለይ አንዱ የኤምባሲ ሹፌር ሆኖ የኖረ ምንም መንፈሳዊ እውቀት ያልነበረው ነው። የግርማ ረዳት ሆኖ ከቆየ በኋላ በቆይታው ለግርማ የነበረውን ገቢ ሲመለከት አስማቱን ከግርማ ተምሮ አጥማቂ ሆኗል። ዲቁናውንም ቅስናውንም ባጭር ጊዜ ውስጥ ተቀብሎ ቅድስት ሥላሴ ኮሌጅ በማታው ክፍለ ጊዜ መማር ጀምሮ ነበር። በኋላ  ይድራስ ጊዮርጊስ በሰባኪነት ተመድቦ ብዙ ሰው በክሏል። ከዚያም ወደ ፉሪ ሥላሴ ተዛውሮ በዚያ እያጠመቀ ታዋቂ አጥማቂ ሆነ፤ ከዚያም አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በጥንቆላ ተከሶ ከሥራ ታገደ፤ እንዳያጠምቅም ማስጠንቀቂያ ተሰጠው። ዛሬ በትንሣኤ ዘጉባዔ ማተሚያ ቤት ይሠራል።

 የፈረንሳይ ኪዳነ ምህረት አጥማቂ ወጣት ተስፋየ የማጥመቅ ጥንቆላ የተማረው ከግርማ ነው የሚል ግምት አለኝ። ሙያው ተለግሶታል፤ ግርማ ልጁን ሀብት ሰጥቶ ጎጆ እንደሚያወጣ መልካም አባት ልጆቹን ጎጆ ማውጣቱ ነው። የጠንቋይ አገልጋይ ሆነው የቆዩ ግለሰቦች ከጥቂት ጊዜ ባኋላ አስማቱን ወርሰው እራሳቸውን የቻሉ አጥማቂዎች ይሆናሉ።

 ባሕታዊ ፍቅረ ማርያም የተባለው አጥማቂ የደብረ ሊባኖስ የቆሎ ተማሪ ነበር። የአባቱ ዛር አርፎበት ከታመመ በኋላ ወዴት እንደ ደረሰ ሳይታወቅ አጥማቂ ሆኖ ብቅ አለ። በአዲስ አበባ ቶታል አካባቢ ዳግማዊት ጻድቃኔ ማርያም ብሎ ማንም ጳጳስ ያልባረከው ቤተ ክርስቲያን ከፍቶ ሲያጠምቅ ቆይቷል። በርካታ ሕዝብ ወደ እርሱ እየሄደ በመጠመቅ የረጅም ጊዜ በሽታ ተሸክሟል። ይህ አጥማቂ ሰዎች የተጠመቁበትን ውሃ ካጠራቀመ በኋላ መልሶ በማጠጣት ግፍ የሠራ የኢትዮጵያ ጠላት ነው። በኋላ አንዳድ የእግዚአብሔር ሰዎች ባካሄዱት ጠንካራ ጸሎትና ተቃውሞ ሥፍራውን እንዲለቅና ወደ ዱከም እንዲሰደድ ተደረገ። ቤተ ክህነቱ ባቀረበበት ክስ ሁለት መቶ ሃያ አምስት ሺህ ብር ጉቦ ከፍሎ ነጻ ወጥቷል። ዛሬ ቤተ ክርስቲያኒቱን ቤተ ክህነቱ ተረክቦ እያስተዳደራት ይገኛል። ባሕታዊው ግን በዱከም እያጠመቀ ትልቅ ባለሀብት ሆኖ በርካታ አውቶቢሶችን ገዝቷል፤ የርሱ መኪኖች ወደ ግሸን ለሚሄዱ ተሳላሚዎች አገልግሎት ሲሰጡ፤ የባሕታዊው መኪኖች እየተባሉ የታቦት ያህል ሲከበሩ ተመልካቻለሁ።

 ብዙ አብያተ ክርስቲያናት የጠንቋይ አጥማቂዎችን ቀጥረው ሲያሠሩ የወንጌል ሰባኪዎችን ግን ያሳድዳሉ። ይህ ከባድ የቤተ ክርስቲያን ሙስና ነው እላለሁ። አቶ ግርማ የእስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ጠንቋይ ነው። በነገራችን ላይ አብያተ ክርስቲያናቱ አጥማቂዎችን የሚቀጥሩበት ምክንያት ቤተ ክርስቲያኑ ገንዘብ ሲቸግረው ነው። ሕንጻ ጀምሮ ከሆነ ማስጨረሻ ሲያጣ፣ ለካህናቱ ደሞዝ ለመክፈል ሲቸገር፣ ወይም በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ገንዝብ ፈላጊ የማፍያ ቡድን ሲኖር ነው። ጠንቋዩ ሲቀጠር ከቢሮ ሰራተኞች ጋር በፐርሰንት ሊከፈለው ውል ከፈጸሙ በኋላ ነው። አጥማቂ እንደማነኛውም አገልጋይ በደሞዝ ሊቀጠር ከቶ አይችልም። በአስማት ከሚያመጣው ገንዘብ በፐርሰንት ይከፈላዋል እንጂ። ዛሬ አጥማቂዎች ባለፎቅና ባለ መኪና የሆኑት በደሞዛቸው ነው ብሎ የሚያስብ ካለ ያው የተጠመቀና በመንፈሱ የታሰረ ማስተዋሉ የተወሰደበት ነው።


 ይህን ሁኔታ ማጋለጥ ለምን አስፈለገ?


የጌታ ቃል ክፉውን ከመካከላችሁ አውጡት 1ቆሮ 514 ከጨለማ ሥራ ጋር አትተባበሩ ይልቁንም ግለጡት እንጂ ስለሚል። ኤፌ 511 ይልቁንም ኢትዮጵያዊ ወገናችንን ስለምንወድ ከዚህ ክፉ የአጋንንት ሥራ እንዲጠነቀቅ ለማድረግ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ በውስጧ የያዘቻቸውን አደገኛ ጠንቋዮች እንድትለይና እራሷን እንድታጸዳ ለማሳሰብም ነው። ቤተ ክርስቲያን ሰላሟ የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን የሚሰብኩ ደቀ መዛሙርትን እያወገዘች ጠንቋዮችን ግን በከፍተኛ ገንዝብ ቀጥራ ትገኛለች። በግፍ የሚሰበሰበው ገንዘብ ሰላሟን ነስቷታል፤ ወንጌልን ይዛ ድሃ ብትሆን ይሻላት ነበር። ሰላሟ ክርስቶስ ነውና።

 የተወደዳችሁ የክርስቶስ ቤተ ሰቦች፦

ቤተ ክርስቲያናችን ተሃድሶ ያስፈልጋታል። ብዙ ቆሻሻ የሆኑ የአጋንንት ሥራዎች፤ የሥጋና የደም ትምህርቶች፤ ልዩ ልዩ ባዕድ አምልኮዎች እንደ ልማድ ሆነው ይዘወታራሉ። እነዚህ ሁሉ አጸያፊ ነገሮች ንጹሕ በሆነው በእግዚአብሔር ቃል እየተመረመሩ መወገድ አለባቸው። ይህ ባይሆን ግን ጥፋታችን ሩቅ አይደለም። የመስቀሉን ነገር አጉልተን በመግለጥ ጠላታችንን ከእግራችን በታች እንጣለው።     

በክርስቶስ ያመለጥሁ ደብተራ ነኝ