Showing posts with label በእግዚአብሔር ቃል ሲመዘን. Show all posts
Showing posts with label በእግዚአብሔር ቃል ሲመዘን. Show all posts

Saturday, August 12, 2017

ግልጥ የሆነ አውጣኪነት፤ ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ክፍል ሁለት)


« አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን » ??? ግልጥ የሆነ አውጣኪነት፤ ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ክፍል ሁለት)

ወንድሜ ቀሲስ ደጀኔ፥ በክፍል አንድ ጽሑፌ ላይ፥በመካከላችን ስላለው ልዩነትና፥ ምሥጢረ ተዋህዶን ምን ያህል በተሳሳተ መንገድ እንደተረዳኸው ለማስረዳት ሞክሬአለሁ። በተለይም ቄርሎስን በትክክል ባለመረዳትህ፥ መገናዘብን እንደመቀላቀል እንደቆጠርከው፥ የቃልን ገንዘብ ዘርዝረህ የሥጋን ገንዘብ ግን ሙሉ በሙሉ መካድህን አመልክቼህ ነበር። ለዚህም ራሱን ቄርሎስን ምስክር አድርጌ አቅርቤአለሁ። በዚህ በክፍል ሁለት ጽሑፌ እንደተለመደው ያንተን ጽሑፍ በማስቀደም የእኔን መልስ ደግሞ በሥፍራው አስቀምጣለሁ። ስለ ብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት ስለጻፍከው፥ እንዴት በክርስቶስ እንደተፈጸመ አባቶች የሚተረጉሙትን እንዳለ ስላስቀመጥክ፥ከአንዳንድ አንተ ከጨመርካቸው ጥቃቅን ነገሮች በቀር እኔም ስለምስማማበት ለቦታና ለጊዜ ስንል በማለፍ በቀጥታ፥የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት ስለሆነው ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ተናገርከው ታላቅ ስህተት እንመጣለን። ይኸውም በእብራውያን መልእክት ላይ « አብ ሾመው» የሚለውን አንተ ደግሞ በራስህ  « አብ ሾመው ለማለት አይደለም» ብለህ መጽሐፍ ቅዱስን ተጋፍተህ ፥ ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የሚጣረስ ቃል አስቀምጠሃል።  የዛሬው ክፍል ሁለት ጽሑፌ ይህች አደገኛ ሐረግ « አብ ሾመው ለማለት አይደለም» የሚለው ላይ ያተኮረ ነው። ይህን ከራስህ ጽሑፍ እንመልከተው።
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ « እንደ አሮንም በእግዚአብሔር ከተጠራ በቀር ማንም ለራሱ ክብርን የሚወስድ የለም። (እግዚአብሔር እንደ አሮን ከመረጠው በቀር ማንም ተነሥቶ ሥልጣነ ክህነትን ለራሱ ገንዘብ ማድረግ የሚቻለው የለም)።”ብሎአል። =ከዚህም አያይዞ፡-“እንዲሁ ክርስቶስም ሊቀ ካህናት ይሆን ዘንድ ራሱን ያከበረ(የሾመ) አይ ደለም፤ ነገር ግን፡-“አንተ ልጄ ነህ፥እኔም ዛሬ ወለድሁህ፥ያለው እርሱ ነው፤ዳግመኛም፡-እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት የዘላለም ካህን አንተ ነህ፥ይላል፤”ብሎአል።መዝ፡፪፥፯፤፻፱፥፬፣ማቴ፡ ፫፥ ፲፯፤፲፯፥፭።ይህም፡-“አብ ሾመው፤”ለማለት ሳይሆን የባህርይ አባቱ አብ፡-ከእርሱ ጋር አንድ የሆነ ክብሩን መሰከረለት ለማለት ነው።» ብለሃል።
ነገረ መለኮት በተለይም ምሥጢረ ሥጋዌ፥ በመላ ምት ወይም በግምት የሚነገር ሳይሆን፥ የእግዚአብሔርን ቃልና የአበውን ምስክርነት በመያዝ በጥንቃቄ የሚነገር ነው። አሁን ግን በአንተ በቀሲስ ደጀኔ ጽሑፍ ላይ የምመለከተው ድፍረት ነው። ጥንቃቄ የጎደለው ታላቅ ድፍረት ነው። ለየዋህና የቤተ ክርስቲያኒቱን ነገረ መለኮት ለማያውቅ ሰው፥የተደረደረው ጥቅስ የእውነት ማረጋገጫ ሊመስል ይችላል። ከጥቅሱ በስተጀርባ ያለውን ታላቅ ስህተት ግን አያስተውልም። በዚህ በዛሬው ጽሑፌ፥ ምን ያህል የቤተ ክርስቲያኒቱን ቀዋሚ ትምህርት እንደናድከው የማመለክትህ በአንዲቱ ሐረግ ብቻ ነው። « አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን» የምትለውን አባባልህን በጥንቃቄ ተመልከተው። « አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን»? አብ ካልሾመው ታዲያ ማን ሾመው? መጽሐፍ ቅዱሱ « ራሱን የሾመ አይደለም» እያለ የተናገረው ስለምንድነው? ቃሉ እንዲህ በግልጥ እየነገረህ፥ ከቅዱስ ቃሉ ጋር ጦርነት ውስጥ መግባት ለምን አስፈለገ? ይህን እውነት ለመቀበል የከበደህ የምሥጢረ ሥጋዌን ነገር በተለይም የሥጋን ገንዘብ ሙሉ በሙሉ ከአምላክነቱ ቆርጠህ ስለ ጣልክ፥ ወይም ለመለኮት ከተዋሃደው ከትስብእቱ የተነሣ ሊነገርለት የሚገባውን እንዳለ ለመቀበል አለመፈለግህ ነው።
አንተ ጥቅሱን እና የአበውን ትርጓሜዎች ወደ ጎን በማድረግ፥ ሁለት አሳቦችን አቅርበሃል፤ የመጀመሪያው « አብ ሾመው ማለት አይደለም» የሚል ነው። ሁለተኛው ደግሞ፥ « ሾመው» የሚለው ቃል ፥ « ክብሩን መሰከረለት ለማለት ነው» የሚል ነው። ይህን ያስባለህ በተደጋጋሚ የወደቅህበት የአውጣኪ ስህተት ነው። ይህ ባለአዋቂነት የመጣ አሳብ፥ እርሱ በአምላክነቱ ከአብ ጋር እኩል ሆኖ ሳለ እንዴት ይሾማል የሚል ነው። አውጣኪ ያልኩህ የእኛን ሥጋ መልበሱን ፈጽሞ መካድህ፥ መዋቲ ( ሟች) ሥጋ መልበሱን፥ በዚህም« ሕቀ አህጸጽኮ እመላእክቲከ» ከመላእክት ጥቂት አሳነስከው መባሉን መርሳትህ፥ ፍጹም ሰው መሆኑን መዘንጋትህ ነው። ይህን ከአውጣኪ የመነጨውን ስህተት ሙሉ በሙሉ ለመደምሰስና በሥጋው አብ ሾመው ተብሎ ሊነገር እንደሚገባ ለማስረዳት፥ ራስህ መነሻህ ያደረከውን የዕብራውያን ንባብና አሳብ ከአባቶች ትርጓሜና ትምህርት አንጻር መተንተን አለብን፤
አንተ የጠቀስከውን ዕብ ፭፥፭-፯ን አባቶች በትርጓሜ ጳውሎስእንዴት እንደተረጐሙት እንመለክተው፤መጀመሪያ ገጸ ንባቡን እንዳለ አስቀምጣለሁ ከዚያም የአባቶችን ትርጓሜ አስቀምጣለሁ፤ ገጸ ንባቡ እንዲህ ይላል፦ «እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ ሊቀ ካህናት ሊሆን ራሱን አላከበረም ነገር ግን፦ አንተ ልጄ ነህ እኔ ዛሬ ወልጄሃለሁ ያለው እርሱ ነው፤እንደዚህም በሌላ ስፍራ ደግሞ፦ አንተ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘላለም ካህን ነህ ይላል። እርሱም በስጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፥ »
የአባቶች ትርጓሜ ደግሞ እንዲህ ይላል፦
« እንደዚህም ኹሉ ክርስቶስ ሊቀ ካህናት ይባል ዘንድ ራሱን የሾመ አይደለም። አንተ ልጄ እኔ ዛሬ ወለድኩህ ያለው እሱ፥ ዳግመኛ እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ፤ አንድም አንተ ልጄ ነህ ያለው እሱ ዛሬ ወለድኩክ። ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምህ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ። ይህም ሊታወቅ ሰው ኾኖ የሰውነት ሥራውን በሠራበት ወራት፥ ጸሎትን እንደ ላም ስኢልን እንደ በግ አቀረበ።»
አባቶች በግልጥ ያስቀመጡት ይህን ነው። ምንም ሌላ ሐታታ የማያስፈልገው ግልጥና ጥርት ያለ ነው። ንባቡን እናቃናው ብለው ለማጥፋት አልደፈሩም። ያሉት « « ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምክ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ።» ነው ያሉት። አመክንዮ ዘሐዋርያትም ይህን ሲያረግጥ « ወዐረቀ ትዝምደ ሰብእ ምስለ እግዚአብሔር ሊቀ ካህናቲሁ ለአብ። የአብ ሊቀ ካህናት የሚሆን እርሱ ከእግዚአብሔር ጋር አስታረቀን » ይላል። የአብ ሊቀ ካህናት ብሎታል። በአብ ፊት የሚቆምልን የሚታይልን ሊቀ ካህናት ማለት ነው። ከዚህ የተነሣ ስለ ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ስናምንም ሆነ ስናስተምር የሚከተሉትን ሦስት ነገሮች አስረግጠን መናገር አለብን።

፩ኛ. ሊቀ ካህናት የሚለው ስያሜ ለክርስቶስ የተሰጠው ሰው በመሆኑ ነው።

ሊቀ ካህናት የሚለው የሥጋዌ ስሙ ነው፤ ደግሞም የሹመት ስም ነው። የባሕርይ አምላክ ለሆነ ለእርሱ ሹመትን መቀበል ተዋርዶ አይሆንም ወይ? አዎ በሚገባ። ነገር ግን በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት መወሰንን የተቀበለ፥ በየጥቂቱ ያደገ፥ ከእናቱ ጡት ወተትን በመለመን ያለቀሰ፥ በሥጋው ከአባቱ ሹመትን ተቀበለ መባሉ የከበደን ከቶ ለምን ይሆን? ከጽንስ እበየማነ አብ እስከሚቀጥበት እስከ እርገቱ የሠራው የቤዛነት ሥራ ( ማለትም በእኛ ተገብቶ፥ በእኛ ፈንታ ሆኖ መሆኑን) መሆኑን መናገር ያሳፈረን ለምን ይሆን?
ሃይማኖተ አበው እንዲህ ይላል፦ « ፩ዱ ለሊሁ ወረደ ወተሠገወ እምህላዌነ ወኮነነ ሊቀ ካህናት ወአዕረገ በእንቲአነ ሥጋሁ መሥዋዕተ ለአቡሁ ወአብጽሐነ ሎቱ በዘቦቱ ሐመ፤ እርሱ አንዱ ወደዚህ ዓለም ወርዶ ባሕርያችንን ባሕርይ አድርጎ ሊቀ ካህናት ( አስታራቂ) ሆነን፤ ስለ እኛም ሥጋውን መሥዋዕት አድርጎ ወደ አባቱ አቀረበ እንጂ፤ በታመመበት በሥጋው ለርሱ ገንዘብ ለመሆን አበቃን » (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፲፮) ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በግልጥ እንደተናገረው፥ ሊቀ ካህናት ተብሎ የተነገረለት፥ ወደዚህ ዓለም በወረደ ጊዜ ነው።  ቅዱስ ኤጲፋንዮስም እንዲህ ይላል። « በሰው ባሕርይ ሊቀ ካህናት ይሆን ዘንድ፥ ስለ እኛም ራሱን ቍርባን መሥዋዕት አድርጎ ለአባቱ ያቀርብ ዘንድ ወልድ ዋሕድ ሰው ሆነ።» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ኤጲፋንዮስ ም. ፶፮. ክፍል ፬ ቍ. ፱፤

እዚህ ላይ አንድ ጥልቅ እውነትን እንዳስስ፤ ለመሆኑ ሥግው ቃል ሊቀ ካህናት ለመሆን ለምን አስፈለገው? ይህን ድንቅ ምሥጢር ለመረዳት ሰፊ ሐተታ የሚያስፈልገው ቢሆንም ከተነሣንበት ዓላማ አንጻር፥ ካህን ሆኖ ፍጥረት ወደ አምላኩ ለማቅረብ የተፈጠረው አዳም፥ በኃጢአት በመውደቁ ምክንያት፥ ሁለተኛው አዳም ክርስቶስ፥ በእርሱ በኩል፥ ሰው ብቻ ሳይሆን ፍጥረት ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ይገባ ዘንድ ነው። ቅዱስ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ሲገልጥ እንዲህ ይላል። «በክርስቶስ ለማድረግ እንደ ወደደ እንደ አሳቡ፥ የፈቃዱን ምሥጢር አስታውቆናልና፤ በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው።» ( ኤፌ ፩፥፱-፲) በሰማይና በምድር ያለው እንዴት በክርስቶስ እንደሚጠቀለል፥ የሐዋርያት ተከታያቸው የሆነው ሄኔሬዎስ በመጻሕፍቱ የገለጠውን በሰፊው ወደ ፊት እናየዋለን። ለአሁን ግን ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘአርማንያ በጸለየው ጸሎት ላይ አስደናቂ የተዋሕዶን ምሥጢር እንዴት እንደገለጠው እንመልከተው። « የሰውን ባሕርይ እስኪዋሐድ ፥ ዘመዳቸውም ሆኖ ሰውን ሁሉ ወደ እርሱ እስኪያቀርብ ድረስ፥ ሰው ፊትህን አይቶ ሕያው መሆን አይቻለውም ነበርና። ሰዎች መለኮትን ያዩት ዘንድ የበቁ እስኪሆኑ ድረስ በሰው ባሕርይ ተገለጠ። በሥጋ ዘመዳችን ሆኖ ባየነው ጊዜ በአብ ቸርነት የወልድን ጌትነት እናመሰግነዋለንና» ሃይማኖተ አበው ዘጎርጎርዮስ ዘአርማንያ ም. ፲፭. ክፍል ፪. ቍ ፲-፩ አሁንም እኛን ተዛምዶ ወደ እርሱ ያቀረበን ሊቀ ካህናችን ይክበር ይመስገን።
እዚህ ላይ ቀደም ሲል የተናገርኩትን እንደገና አስረግጬ ለመናገር፥ ሐዋርያ፥ ክርስቶስ፥ ሊቀ ካህናት፥ ሰው፥ የሚሉት ስሞቹ በሥጋው ያገኛቸው ስሞች ናቸው። ለምሳሌ ይኸው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይላል። « አብ ከወዲያ ዓለም ወደዚህ ዓለም ስለ ላከው፥ ሐዋርያ አለው፤ ስለ አመንበት በጎ ሥራ ለመሥራት የምንቀና፥ ደግ ወገን አድርጎ ገንዘብ አድርጎናልና፥ ለእኛ ማልዶልናልና ሊቀ ካህናት ( አስታራቂ) አለው» ይለናል። ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፳፮

፪ኛ. ሊቀ ካህናት ሆኖ የተሾመው በአባቱ ነው።

ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ግልጥ አድርጎታል። አንተው የጠቀስከውን ዕብ ፭፥፭ን አባቶች«ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምክ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ።» ብለው ተርጉመውታል። የአባቶችን ትርጓሜ «ልታቃና » ካልሞከርክ በቀር መልሱ ግልጥ ነው። በሌላ ሥፍራም ሐዋርያው « ሕጉ ድካም ያላቸውን ሰዎች ሊቀ ካህናት አድርጎ ይሾማልና፤ ከሕግ በኋላ የመጣ የመሐላው ቃል ግን ለዘላም ፍጹም የሆነውን ልጅ ይሾማል» ይላል። ( ዕብ ፯፥፳፰)  አባቶች ይህን ንባብ ሲተረጉሙ ሰፊ ግንዛቤን የምናገኝበትን ሐተታ ስለሚሰጡበት እዚህ ላይ መመልከቱ መልካም ነው። እንዲህ ይላሉ፦ « ኦሪትሰ ሰብአ ትሰይም ሊቀ ካህናት መዋቴ፤ ኦሪትስ የሚሞት ሰውን ሊቀ ካህናት አድርጋ ትሾማለች። የቀድሞው ሊቀ ካህናት ዕለት ዕለት መሥዋዕት ማቅረቡ፥ የዛሬው ዕለት ዕለት አልማቅረቡ እንደምን ነው ትሉኝ እንደሆነ ኦሪት መዋቲ ( ሟች) ሰውን ሊቀ ካህናት ትሾም ነበረና፥ ደካማ ሰውን ትሾም ነበረና፥ የቀደመው ሊቀ ካህናት አንድ ጊዜ ባቀረበው መሥዋዕት ሥርየት ድኅነት ማሰጠት የማይቻለው ስለሆነ ነው። ወቃለ መሐላሁሰ ዘመጽአ እምድኅረ ኦሪት ሤመ ለነ ወልደ ፍጹመ ዘለዓለም። ከኦሪት በኋላ በመሐላ የተሠራ ሕገ ወንጌል ግን ሕያው ወልድን፥ ኃያል ወልድን ሹሞልናልና። የዛሬ አንድ ጊዜ ባቀረበው መሥዋዕት ስርየት ድኅነት መስጠት የሚቻለው ስለሆነ ነው።»
ሃይማኖተ አበው ደግሞ ግልጥ አድርጎ ምንም ማፈናፈኛ ሳይሰጥ አያስቀምጠዋል፤እንዲህ ይላል፦« ኢየሱስ ክርስቶስ፥ ሐዋርያ ሊቀ ካህናት በአደረገው በአብ ዘንድ የታመነ እውነተኛ ነው አለ። ለወገኖቹ በጎ ማገልገልን እንዲያገለግል ይጐዱም ዘንድ ቸል እንደማይላቸው እኛ እንድናውቅ መናገሩ ነው። ሊቀ ካህናት አደረገው ( ገብሮ) ያለውንም ሐዋርያ ሊቀ ካህናት አድርጎ እንደ ሾመው መናገሩ ነው። በዚህ አንቀጽ ስለ ባሕርየ መለኮት አልተናገረም፤ አምላክ ሰው ስለመሆኑ ሥርዓት ተናገረ እንጂ፥ ሥጋ ፍጡር ነውና።» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፳፯-፳፰
ቀሲስ ደጀኔ እልህ ሃይማኖት ካልሆነብህ በቀር፥ ያነሣኻቸውን ሁለት ነገሮች ይህን የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ጥቅስ ይንድብሃል። የመጀመሪያው « አብ ሾመው፤”ለማለት ሳይሆን » የሚለው አሳብህን፥ ሊቀ ካህናት አደረገው ማለት ሊቀካህናት አድርጎ ሾመው ማለት እንደሆነ ይነግርብሃል ። ሁለተኛ « የባህርይ አባቱ አብ፡-ከእርሱ ጋር አንድ የሆነ ክብሩን መሰከረለት ለማለት ነው።» ብለህ ከራስህ አንቅተህ ያስቀመጥከውን ትርጓሜህን፥ በዚህ አንቀጽ ስለ ባሕርየ መለኮት አልተናገረም፤ አምላክ ሰው ስለመሆኑ ሥርዓት  እንጂ» ይልብሃል።
አሁንም ደጋግሜ በፍቅር የምነግርህ፥ ወደዚህ ታላቅ ክህደት ያገባህ፥ የትስብእትን ገንዘቦች በሙሉ መካድህ ነው። ሾመው ለማለት ያስቸገረህ አዋረድኩት ብለህ ነው። ነገር ግን ዓለም የዳነበት የድኅነት ምሥጢር ይህ ተዋርዶቱ ነው። አንተ ግን በካራ ቆረጥከው፥ ከፈልከው። ተዋህዶን አፋለስከው። ሾመው የተባለው በአምላክነቱ ሳይሆን በሰውነቱ ነው። የፈጠረውን ሥጋ በመልበሱ፥ የፈጠረውን ሥጋ በመዋሃዱ ነው።

፫ኛ. ሊቀ ካህናት ሆኖ የተሾመው ለማስታረቅ ነው።

ቀደም ሲል ባየነው በዕብ ፭፥፭ ላይ፥ሊቀ ካህናት ሆኖ የተሾመበትን ሲተረጉሙ አባቶቻችን በገጸ ንባቡ ላይ በመመርኮዝ የተሾመበትን ምክንያት በሚገባ ግልጥ አድርገው አሳይተውናል። እንዲህ ይላሉ፦ « አንተ ልጄ ነህ ያለው እሱ ዛሬ ወለድኩክ አለ። ዳግመኛም እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሾምህ የዓለሙ አገልጋይ አንተ ነህ አለው እንጂ። ይህም ሊታወቅ ሰው ኾኖ የሰውነት ሥራውን በሠራበት ወራት፥ ጸሎትን እንደ ላም ስኢልን እንደ በግ አቀረበ። » አባቶች ያሉትን አስተውል። ክህነቱ የታወቀው፥ በአስታራቂነቱ፥ ጸሎትንና ስኢልን ( ምልጃን) በማቅረቡ ነው።
የሊቀ ካህናት ዋና ሥራ ምንድነው ስንል፥ ማስታረቅ፥ መማለድ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንደነገረን «. . . ኃጢአታችንን ለማስተስረይ፥ ከአብ ጋር ለማስታረቅ ሊቀ ካህናትም ይሆነን ዘንድ ወደደ እንጂ፤ ስለዚህም [ሐዋርያው]ሰዎችን ሊመስላቸው ይገባል ባለው ነገሩ ላይ ጨምሮ፥ በሁሉ አዛኝ የሕዝቡንም ኃጢአት ለማስተስረይ በእግዚአብሔር ዘንድ የታመነ አስታራቂ ይሆናቸው ዘንድ ነው አለ። ባሕርያችንን ስለተዋሃደ የሰውነቱንም ነገር ያስተምረን ዘንድይህን ተናገረ። ሰው ለመሆን ያበቃው ለማስታረቅ ኃጢአትን ለማስተስረይ ብቻ ነው እንጂ ሌላ ምክንያት የለውም። ከእርሱ ብቻ በቀር ራሱ ብቻውን ኃጢአትን ማስተስረይ የሚቻለው የታመነ አስታራቂ ማነው?» ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪ ቍ. ፲፫-፲፬

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዚህ ሥፍራ አራት መሠረታዊ ነጥቦችን ያነሣል። አንደኛ፥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናት የሆነን ኃጢአታችንን ለማስተስረይና ከአብ ጋር ለማስታረቅ ነው። በሁለተኛ ደረጃ፥ ሊቀ ካህናት የሆነልን እርሱ በሁሉ የሚያዝንልንና የሚራራልን፥ የእኛን ድካም የሚያውቅ በነገር ሁሉ እኛን የመሰለ ነው። ሦስተኛ፥ የሥጋዌው ዋና ተልዕኮ የማስታረቅ አገልግሎት ነው። ሌላ ምክንያት የለውም። አራተኛ፥ ራሱ ብቻውን ኃጢአትን ማስተስረይ የሚቻለው የታመነ አስታራቂ እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። ( ይህን የማስታረቅ አገልግሎት ማለትም የክርስቶስን  ምልጃ፥ ከክርስቶስ መካከለኛነት አንጻር በክፍል ሦስት ጽሑፋችን  በሰፊው እንዳስሰዋለን።)

፬ኛ. ሊቀ ካህንነቱ ለዘላለም ነው።

በብዙው ክርክራችን ውስጥ የዘነጋነው አንድ ታላቅ ጥያቄ አለ። ይኸውም ኢየሱስ ክርስቶስ ዛሬም ሊቀ ካህናት ነው ወይስ አይደለም ? የሚል ነው። ቅዱሳት መጻሕፍትም ሆኑ የቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍት የሚመልሱልን በአዎንታ ነው። የመልክአ ኢየሱስ ደራሲ ይህን እውነታ ሲናገር እንዲህ ይላል፦
« እምሥራቀ ፀሐይ እስከነ ዐረብ ይትአኰት ስሙ ለእግዚአብሔር አምላክነ፤ ኪያከ ወልዶ ዘፈነወ ለነ፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናቲነ፤ አስተጋብአነ ኀበ ትረፍቅ መካነ፤ እስመ ዝርዋን አግብርቲከ ንሕነ።
« አንተን ልጁን የላከልን፥ የአምላካችን የእግዚአብሔር  ስሙ ከመ ጸሐይ መውጫ እስከ መጥለቂያ ይክበር ይመስገንና ሊቀ ካህናችንን የምትሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፥ በመላው ዓለም የተበተን እኛን ( ቤተ ክርስቲያንን) አንተ ባለህበት በዚያ ሰብስበን» በዕለተ አርብ ባቀረበው መሥዋዕት፥ በዚያ በብርቱ ጩኸትና ዕንባ ባቀረበው ጸሎትና ምልጃ፥ ዛሬም ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አባቱ መቅረቢያችን ነው ።
ሞት እንደሚያግደው እንደ አሮን ልጆች ክህነት ሳይሆን፥  ክህነቱ እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ክህነት ለዘላለም ነው የተባለው ለዚህ ነው። በዚህም ምክንያት ቤተ ክርስቲያን ይፍታህ ይህድግ በማለት በወንጌል የተገኘውን ከኃጢአት ነጻ የመሆን አዋጅ ( ሥርየተ ኃጢአትን ስታውጅ) « ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የካህናት አለቃ ( ሊቀ ካህናት) ይቅር ባይ» ብላ ሊቀ ካህንነቱን በመናገር ነው።
ሐዋርያውም በግልጥ «እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤ እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል። ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤ » ብሎአልና ሊቀ ካህናችን አሁንም በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የምመጡትን ፈጽሞ የሚያድናቸው ነው። ዕብ ፯፥፳፫-፳፮
እንግዲህ እስከ አሁን የተማርነውን የዕብ ፭፥፭-፯ን በካታኪዝም ( በጥያቄና መልስ) ብናስቀምጠው ብናቀርበው ይህ ነው። « ሊቀ ካህናት አድርጎ የሾመው ማን ነው? አባቱ እግዚአብሔር አብ። እንዴት ሾመው ተባለ፤ ሥጋን በመልበሱ ምክንያት። ሊቀ ካህናት የሆነው ለምንድነው? ሊያስታርቀን። የሚያስታርቀን ከማን ጋር ነው? በአምላክነቱ ከራሱ ጋር እንዲሁም ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር፤ እንዴት አድርጎ አስታረቀን? በራሱ መሥዋዕትነት ጸሎትና ምልጃን በማቅረብ ነው። ሊቀ ካህንነቱ እስከመቼ ነው? ሊቀ ካህንነቱ እንደ መልከጼዴቅ ባለ ሹመት ለዘላለም ነው። እርሱ ለዘላለም ህያው ሆኖ ይኖራልና፤ በእርሱ በኩል ወደ እግዚአብሔር የሚቀርቡትን ፈጽሞ ያድናቸዋል።

መደምደሚያ

እንግዲህ ከላይ በዝርዝር ያሳየሁህ፥ በግዴለሽነት፥ « አብ ሾመው ለማለት ሳይሆን» ብለህ ያስቀመጥከው የስህተት ቃል፥ ምሥጢረ ሥጋዌን እንዴት እንደሚያፈልስ ነው። ሁለቱን ግብራት አንዱን በመሰረዝ ወይም በመቀላቀል ወይም መክፈልና በመነጠል የሚደረግ ትንተና አደገኛ በሆነ የስህተት ገደል ውስጥ ይጥላል። ከዚህ ስህተት ራስን ለመጠበቅ ኦርቶዶክሳውያኑ አባቶች የጌታን የማዳን ሥራ የገለጡበትን መንገድ መከተል ያሻል። የጎርጎርዮስ ዘኑሲስን ምክር ልብ በል። « ሁለቱ ግብራት ለርሱ አንድ እንደሆኑ አየህን? ሰው የሆነ አምላክ እርሱ ነው። አንድ ነው ሁለት አይደለም። ፈጣሪ መለኮቱን ፍጡር ወደ መሆን አልለወጠውም። ፍጡር ሥጋውንም ፈጣሪ ወደ መሆን አልለወጠውም። መችም መች አንድ ብቻ ነው። ሁለት አይደለም። የተገዢ ባሕርይን የተዋሐደ በእርሱ ትህትና እኛ እንከብር ዘንድ የተዋረደ እርሱ ነው። ሕማማችንን የታገሠ፥ ደዌያችንን የተሸከመ፥ በደላችንን የተቀበለ፥ ስለ እኛ ራሱን የማያልፍ የማይለወጥ መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበ የማይሻር የማይለወጥ ካህን እርሱ ነው። የሚሠዋ በግ እርሱ ነው። የሚሠዋ ካህን እርሱ ነው። ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም መሥዋዕት የሚቀበል እርሱ ነው።»  ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ም. ፴፮ ክፍል ፬ ቍ. ፳፬-፳፭  ትስብእትንና መለኮትን በተዋህዶ መግለጥ ማለት ይህ ነው። ያለመቀላቀል፥ ያለመክፈል፥ ያለመለወጥ፥ ያለመለየት፤ ተዋህዶ በተአቅቦ ማለት ምሥጢሩ ይህ ነው። ይህን ከተረዳኸው፥ አብ ሾመው፥ ወደ አብ ጸለየ ማለደ የሚል ስታገኝ አይከብድህም፤ ከሁሉም በላይ  እኛን የሰው ልጆችን ለማዳን የእኛን ባህርይ ገንዘብ ባደረገ በእርሱ አታፍርም።  የአብ ሊቀ ካህናት የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ፥  አስደናቂ የሆነውን ሰው የመሆኑን ምሥጢር፥ አሁንም አብዝቶ ይግለጥልን። አሜን።

ማሳሰቢያ፦ በሚቀጥለው በክፍል ሦስት ደግሞ « ይማልዳል ለማለት ሳይሆን » በማለት የእግዚአብሔርን ቃል በመጋፋት የጻፍከውን ስህተት፥ ቅዱሳት መጻሕፍትንና የአበውን መጻሕፍት በመጥቀስ እናርመዋለን። በዚያ ውስጥም መካከለኛነት፥ ምልጃ፥ አስታራቂነት ስለሚሉት ቃላት መጽሐፍ ቅዱስና የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት ያስተማሩትን በሚገባ እናየዋለን።



Monday, July 24, 2017

ግልጥ የወጣ አውጣኪነት፤ ለቀሲስ ደጀኔ የተሰጠ መልስ ( ክፍል አንድ)



ከቀሲስ መላኩ ተረፈ


ለወንድሜ ቀሲስ ደጀኔ፥በዕብ ፭፥፯ ላይ ያለውን ኃይለ ቃል መሠረት አድርገህ ( የብፁዕ አባታችንና የእኔን ፎቶ አስደግፈህ) የጻፍከውን ተመለከትኩት፤ በአንድ በኵል፥ ከተራ አሉባልታና ክስ ወጥተን፥በክርክርም ቢሆን፥  ስለ ክርስቶስ እንድንነጋገር ያደረገንን አምላክ ሳመሰግን፥ በሌላ በኩል አንተና አንተን ተከትለው በቲፎዞ የሚነጉዱት ስለገባችሁበት ከባድ አደጋ ሳስብ አዝናለሁ። ይህ የልጅ ጨዋታ አይደለም። አሁን እያደረጋችሁ ያላችሁት፥ ቤተ ክርስቲያንን ከአኃት አብያተ ክርስቲያናት ጋር የሚያለያይ፥ አባቶቻችን በስንት ተጋድሎ ያቆዩትን የተዋህዶ ምሥጢር የሚያፋልስ ነው። በመሆኑም የሚቀጥለው ጽሑፌ በአንድ በኩል በጥንቃቄ የአባቶችን ትርጓሜና የቤተ ክርስቲያናችንን ትምህርት እንድታጠናው ለማሳሰብ ሲሆን፥ በሌላ በኩል የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የተጋረጠውን አደጋ ለማሳሰብ ነው። ምንም እንኳ እኔን መናፍቅ ብትለኝም፥ አንዳንዱን የአተረጓጎምህን መንገድ ስመለከት መናፍቅ ለማለት ይከብደኛል። ከምርምርና ከዕውቀት ሳይሆን፥ከአላዋቂነት የመጣ ስህተት ነውና የማየው።  በመሆኑም በመጀመሪያ ጽሑፍህን በትምህርተ ጥቅስ ጎላ ብሎ እንዲቀመጥ በማድረግ፥ ለእያንዳንዱ መልስ ለመስጠት  እሞክራለሁ። በአንቀጽ የተከፋፈለ ባይሆንም ለመልስ እንዲረዳኝ ከፋፍየዋለሁ፤ አላስፈላጊ የሆነና አለቦታው የገባውን ንባብ ግን ከጊዜና ከቦታ አንጻር አልፌዋለሁ፤
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ ፦  “ እርሱም በሥጋ ወራት . . . ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤”ዕብ፡፭፥፯። =ይኸንን ኃይለ ቃል የተናገረው፡-ታላቁ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ነው።ይህ ሐዋርያ መልእክ ቶቹን ሁሉ የጻፈው በጸጋ እንደ ተሰጠው ጥበብ መጠን ነው።ይኸንንም፡-የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ፡-“እን ዲህም የተወደደው ወንድማችን ጳውሎስ ደግሞ እንደ ተሰጠው ጥበብ መጠን ጻፈላችሁ፥በመልእክ ቱም ሁሉ ደግሞ እንደ ነገረ ስለዚህ ነገር ተናገረ።በእነዚያ ዘንድ ለማስተዋል የሚያስቸግር ነገር አለ፥ያል ተማሩትና የማይጸኑትም ሰዎች ሌሎችን መጻሕፍት እንደሚያጣምሙ እነዚህን ደግሞ ለገዛ ጥፋታ ቸው ያጣምማሉ።”በማለት ገልጦታል።፪ኛ፡ጴጥ፡፲፭። =ቅዱስ ጴጥሮስ እንደመሰከረው፥መናፍቃኑ፡-አጥፍቶ ጠፊ የሆኑት፥በአብዛኛው፡-የሐዋርያውን መልእክታት በመጠቃቀስ ነው።ይኸውም የንባቡን ትርጓሜና ምሥጢር ካለማስተዋልና መጽሐፍ ቅዱስን እንደ ሌሎች ልበ ወለድ መጻሕፍት ከመመልከት ነው።» ብለሃል።
ግሩም ነው! ስድቡን ቀነስ ብታደርገውም፥ ዛሬም ያችው የተለመደችው መናፍቃን የምትለውን ቃል ፎቶአችንን አስቀምጠህ ተጠቅመሃል።  ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የተናገረው ቃል በእውነትም ቅዱስ ጳውሎስ ያስተማረውን የምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን ነገር ባለማስተዋል የሚያጣምሙትን የገሠጸበት ቢሆንም፥ ዛሬም መጻሕፍትን ለሚያጣምሙት የሚጠቀስ ቃል መሆኑ እሙን ነው። በአንድ በኩል የመጽሐፍ ቅዱስ ገጸ ንባብ ጥሬ ዘሩን ሳይቀር ለመለወጥ የደፈርህ፥ እንዲህ ተብሎ ሊጻፍ አይገባም ያልክ አንተ ነህ፤ በሌላ በኩል የአባቶችን ትርጓሜ እንኳ ሳይቀር፥ ያለምንም ሐፍረት ያጣመምክ አንተ ስለሆንክ « ለገዛ ጥፋታቸው ያጣምማሉ» የተባለው የሚቀጸለው ለአንተ ነው። ትርጓሜ ጳውሎሱን ሳይቀር እንዴት እንዳጣመምከው በግልጥ በማስረጃ አመጣዋለሁ። ወደ እኔ ጽሑፍ ከሄድክ፥ በማስረጃነት ያቀርብኩልህ ትርጓሜ ወንጌልን፥ ሃይማኖተ አበውን፥ የጥንትና የዘመናችን አባቶችን እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስን ነው። ጳውሎሱን አንተም እኔም የምንጠቅሰው ኃይለ ቃሉ ያለበት ስለሆነ ነው። ዛሬም ከእነዚሁ ንጹሐን ምንጮች ነው የምጠቅስልህ፤  መናፍቃኑ ላልከው ግን እኔም እንደ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ እልሃለሁ፤  «ነገር ግን ይህን እመሰክርልሃለሁ፤ በሕጉ ያለውን በነቢያትም የተጻፉትን ሁሉ አምኜ የአባቶቼን አምላክ እነርሱ ኑፋቄብለው እንደሚጠሩት መንገድ አመልካለሁ፤» ሐዋ ፳፬፥፲፬
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ « ለመሆኑ፡-ሐዋርያው መልእክት ትርጓሜ ምንድነው? -“ነገርን ከሥሩ፥ውኃን ከጥሩ፤”እንዲል፡-መልእክቱን ለመረዳት በመጀመሪያ የነገሩን ሥረ መሠረት እንመለከታለን። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡-ዕብራውያን ምዕራፍ አምስትን የጀመረው፥ በብሉይ ኪዳን ዘመን የነበሩት ሊቃነ ካህናት፡-ለአዲስ ኪዳኑ ሊቀ ካህናት፡-ለኢየሱስ ክርስቶስ የነበራቸ ውን ምሳሌነት በማብራራት ነው። በምሳሌውና በአማናዊው መካከል ያለው ልዩነትም የፈጣሪና የፍጡር ነው፥እነርሱ ፍጡራን ፥እርሱ ግን ፈጣሪ ነው፤እነርሱን የሾማቸው እርሱ ነው፥እርሱ ግን ሿሚ የለበትም፤ ሹመት የባሕርይ ገንዘቡ ነው።» ብለሃል።
ይህ ሙሉ የእብራውያንን የሊቀ ካህንነት ትምህርት የገለጠ አይደለም። ለምሳሌ ስለ አዲስ ኪዳኑ ሊቀ ካህናት ስትናገር፥ በምሳሌናው በአማናዊው መካከል ያለው ልዩነት የፈጣሪና የፍጡር ነው ብለሃል፤ መልካም ነው።  ይህ እንዳለ ሆኖ ግን፥ ነገርን ከሥሩ እንዳልከው የዕብራውያን መልእክት በዋናነት የሚያሳየን አንተ ልትናገረው ያልደፈርከውን ነገር ነው። ይኸውም፥ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት፥ በእውነት ሰው የሆነው የእግዚአብሔር ልጅ በእኛ ፈንታ የቆመ፥ ስለ እኛ መከራ የተቀበለ፥ የጮኸ፥ የደከመ፥ የለመነ፥ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበና አሁን በእውነተኛይቱ ድንኳን ያለ አስታራቂያችን ሊቀ ካህናት መሆኑን ነው። ይህን በዕብራውያን መልእክት  ውስጥ በሙሉ እናየዋለን።

አንደኛ፥ ይህ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት፥ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የቆመ ሊቀ ካህናት ነው። « እንግዲህ በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ስላለን፥ ጸንተን ሃይማኖታችንን እንጠብቅ።» ( ዕብ ፬፥፲፬ ) አባቶቻችን ይህን ሲተረጉሙ « ብንመለስ ማን ያስታርቀናል እንዳይሉት፥ ብነ ሊቀ ካህናት አለ፤ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጁ ደግ አስታራቂ ኢየሱስ ክርስቶስ አለን።»  

ሁለተኛ፥ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እኛን የሆነ ነው። «ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም።» ዕብ ፬፥፲፬።  ሊቀ ካህናትም ያሰኘው ይኸው ፍጹም ሰው መሆኑ ነው። « ከግብራችን ሲያወጣው « ዘእንበለ ኃጢአት ባሕቲታ ከኃጢአት በቀር » አለ። ከባሕሪያችን ሲያገባው « ምኩር በኩሉ በአምሳሊነ እንደ እኛ የተፈተነ» አለ» ይለናል፥ ትርጓሜ ጳውሎስ።    ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም በነገር ሁሉ እኛን መምሰሉ እንዴት እንደሆነ ሲናገር፥ « እንደ እኛ ፍጹም ሰው ሆኖ መወለዱ፥ ከኃጢአት ብቻ በቀር፥ እንደ እኛ ለሥጋ የሚስማማውን፥ ሁሉ መሥራቱ ነው እንጂ፤ይኸውም በፈቃዱ ያደረገው መፀነስ፥ መወለድ፥ መብላት፥ መጠጣት፥ መተኛት፥ መድከም፥ መታመም መሞት ነው።» ይላል። ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ም. ፷፫ ክፍል ፪


ሦስተኛ፥ ይህ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት፥ ከኃጢአት በቀር እንደ እኛ የሆነ፥ ስለ እኛ መከራ የተቀበለ ስለሆነ፥  የተቤዣቸውንና ያዳናቸውን « ወንድሞቼ ሊል ያላፈረ፥ « በኵረ አኃው» ነው።  «ብዙ ልጆችን ወደ ክብር ሲያመጣ የመዳናቸውን ራስ በመከራ ይፈጽም ዘንድ፥ ከእርሱ የተነሣ ሁሉ በእርሱም ሁሉ ለሆነ፥ ለእርሱ ተገብቶታልና። የሚቀድሰውና የሚቀደሱት ሁሉ ከአንድ ናቸውና፤ስለዚህም ምክንያት፦ ስምህን ለወንድሞቼ እነግራቸዋለሁ በማኅበርም መካከል በዜማ አመሰግንሃለሁ፤ ደግሞም፦ እኔ በእርሱ እታመናለሁ፤ ደግሞም፦ እነሆኝ እኔን እግዚአብሔር የሰጠኝንም ልጆች ሲል ወንድሞች ብሎ ሊጠራቸው አያፍርም።» ዕብ ፪፥፲-፲፫  ። አስተውል፥ በሥጋዌው ከእኛ ጋር በመዛመዱ፥ « የሚቀድሰውና የሚቀደሱት ሁሉ ከአንድ ናቸው» ተባለ፤ትርጓሜ ጳውሎስ ይህን ሲያብራራው፥ « እነሱን ያከበረ እሱና የከበሩ እነሱ ካንድ ከእግዚአብሔር ካንድ ከአብርሃም ተገኝተዋልና» ይለዋል።

አራተኛ፥ይህ ሊቀ ካህናት በእርሱ መታዘዝ ለእኛም መታዘዝን ያስተማረንና እንደ ሊቀ ካህንነቱ ወደ አባቱ በብርቱ ጩኸትና እንባ ጸሎትንና ምልጃ ያቀረበ ነው።   « እርሱም በስጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፥ እግዚአብሔርንም ስለ መፍራቱ ተሰማለት፤ምንም ልጅ ቢሆን፥ ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ፤ከተፈጸመም በኋላ በእግዚአብሔር እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ሊቀ ካህናት ተብሎ ስለ ተጠራ፥ ለሚታዘዙለት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት ሆነላቸው።» ( ዕብ ፭፥፰-፲)፤ ይህን ገጸ ንባቡን ሆነ የአበውን ትርጓሜ እንዴት እንዳጣመምከው በቦታው እናየዋለን።

አምስተኛ፥ ይህ ሊቀ ካህናት በእርሱ በኩል ወደ አብ የሚቀርቡትን ፈጽሞ የሚያድን ሕያውና ዘላለማዊ ሊቀ ካህን ነው።   «እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል።ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤» (ዕብ ፯፥፳፬-፳፮)፤

ስድስተኛ፥ ዛሬ ይህ ሊቀ ካህናችን በሰማያዊት ድንኳን በእጅ ባልተሠራችው፥ስለ እኛ የሚታይልን ነው። «በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፤ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፥ እርስዋም በሰው ሳይሆን በጌታ የተተከለች ናት።»( ዕብ ፰፥፩-፪) የእኛ አባቶች « ሊቀ ካህናት ዘይቀውም ሎሙ ለቅዱሳን፥ በደብተራ ስምዕ እንተ እግዚአብሔር ተከላ፤» ብለው ያመሠጠሩት ይህን ንባብ ነው።
ሰባተኛ፥ ሊቀ ካህናችን ወደዚህች ሰማያዊት ድንኳን የገባው፥ የገዛ ደሙን ይዞ ነው፤ ። «ነገር ግን ክርስቶስ ይመጣ ዘንድ ላለው መልካም ነገር ሊቀ ካህናት ሆኖ፥ በምትበልጠውና በምትሻለው በእጆችም ባልተሠራች ማለት ለዚህ ፍጥረት ባልሆነች ድንኳን፥ የዘላለምን ቤዛነት አግኝቶ አንድ ጊዜ ፈጽሞ ወደ ቅድስት በገዛ ደሙ ገባ እንጂ በፍየሎችና በጥጆች ደም አይደለም. . .  ክርስቶስ በእጅ ወደ ተሰራች፥ የእውነተኛይቱ ምሳሌ ወደ ምትሆን ቅድስት አልገባምና፥ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ አሁን ይታይ ዘንድ ወደ እርስዋ ወደ ሰማይ ገባ።» ዕብ ፱፥፲፩- ፲፪፡፳፬
ስምንተኛ፥ ሊቀ ካህናችን እርሱ ወደ ገባበት ድንኳን ለመግባት የምንችልበትን ተስፋ ሰጥቶናል፤ ይህችም ተስፋ የነፍሳችን መልሕቅ « እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘለዓለም ሊቀ ካህናት ሆኖ ሐዋርያችን ኢየሱስ ከእኛ በፊት ወደ ገባባት መጋረጃም ውስጥ የምታስገባ ናት።» (ዕብ ፮፥፳፤)

ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ በንባብ፡-“ተሾመ፥ተቀባ፤”የሚል ቢገኝም ምሥጢረ ተዋህዶን ለማመ ልከት(በተዋህዶ አምላክ ሰው፥ሰውም አምላክ መሆኑን ለመግለጥ፥ወልደ አብ ወልደ ማርያም በተዋህዶ መክበሩን ለማስረዳት) ስለሆነ በትርጓሜ ይቃናል።ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲ ያን፡-ወልደ አብ፥ወልደ ማርያም ኢየሱስ ክርስቶስ፡-በተዋህዶ ከበረ የሚሉት ለዚህ ነው። ምክንያቱም ቅዱስ ቄርሎስ እንደተናገረው፡-በተዋህዶ የመለኮት ገንዘብ ለሥጋ፥የሥጋም ገን ዘብ ለመለኮት ሆኖአል። » ብለሃል።
ቄርሎስን በሚገባ ሳይገነዘብ ገደል የገባውን አውጣኪን ሆነሃል የምልህ እዚህ ላይ ነው። የጻፍከውን ጽሑፍ እንደገና መለስ ብለህ ቃኘው፥ እናም  « በተዋህዶ የሥጋ ገንዘብ» ምንድነው? ሁሉንም ክደኸዋል። ቄርሎስ በድርሳኑ ደጋግሞ እንደገለጠው፥ አንድ ባሕርይ ሲል፥ የቃልና የሥጋን መገናዘብ ሲናገር፥ የክርስቶስን ፍጹም ሰውነት ክዶ አይደለም። የመለኮት ገንዘብ፥ የእግዚአብሔር ልጅ መሆን ፥ አምላክነት፥ ሕይወት መስጠቱ ፥ ማዳኑና  እነዚህን የመሣሠሉት ሁሉ የሥጋም ገንዘብ ሆነዋል። በተዋህዶ። የሥጋ ገንዘብ የሆኑት ደግሞ፥ የዕለት ጽንስ መሆን፥ በየጥቂቱ ማደግ፥ መፍራት፥ መራብ፥ መጠማት፥መጸለይ መማለድ፥ ወደ አብ መጸለይ፥ መሞት እነዚህና እነዚህን የመሳሰሉት ወይም እንደ አባቶች አነጋገር፥ በጥንት በበአት፥ በልደት፥ በሕማምና በሞት እኛን የሆነባቸው የሥጋ ሥራዎች ሁሉ የመለኮት ገንዘብ ሆነዋል። በተዋህዶ። አንተ ግን የአምላክነቱን ገንዘቦች ስታምን የሥጋን ገንዘቦች ግን ፈጽሞ ክደኸዋል። እኛ በሥጋው ይህን አደረገ ስንል ለመለኮት ሰጥተን ነው። በአምላክነቱ ይህን አደረገ ስንል ለሥጋ ሰጥተን ነው። ሳናፋልስ፥ ሳንከፍል፥ ሳንቀላቅልና ሳንለውጥ አንዱን በተዋህዶ የከበረውን አምላክ እንዲህ እንመሰክራለን።   ወልደ አብ ወልደ ማርያም በተዋህዶ ከበረ ማለት፥ ተለወጠ፥ተቀላቀለ አያሰኝምና። ትርጓሜህ በሙሉ ተዋህዶን የሚያፋልስ እንጂ ተዋህዶን የሚጠብቅ አይደለም። ላንተ መገናዘብ ማለት የትስብእትን ነገር እንዳለ መካድ ሆኖብሃል። ይህ አደገኛ ነው።   በትርጓሜ እያቃናህ ሳይሆን እያጣመምከው ነውና።
አሁን ከሊቃውንቱ ስለምጠቅስልህ በእርጋታ አስተውል፤ ጎርጎርዮስ ነባቤ መለኮት  በሃይማኖተ አበው ም. ፷፩ ክፍል ፫ እና ፬ ላይ እንዲህ ይላል። «  አስተርአየ በሥጋ እንዘ ኢያስተርኢ በሕላዌ መለኮት፤ በባሕርየ መለኮቱ የማይታይ ሲሆን፥ በሥጋ ታየ . . . በመለኮት ሞት ሳይኖርበት በሥጋ ሞትን ገንዘብ አደረገ፤ በመለኮት መወሰን ሳይኖርበት በሥጋ ተወሰነ፤የማይመረመር ሰማያዊ እርሱ ሥጋን ተዋህዶ በምድር ተገለጠ።» ካለ በኋላ አንተ ደጋግመህ የካድከውን እርሱ እንዴት እንደሚገልጠው ተመልከት እንዲህ ይላል። «የዕለት ጽንስ መሆን፥ በየጥቂቱ ማደግ፥ የሠላሳ ዐመት ጎልማሳ መሆን፥ የመለኮት ሥራ አይደለም። ይህም ምንም ስለ እርሱ ቢነገር፥ የመለኮት ገንዘብ አይደለም። ሰው ስለሆነ እንጂ »
 

ይህ የተዋህዶ ምሥጢር ወደ ጥልቅ አምልኮ የሚጋብዝ ነው። ከንቱ ከሆነ የቃላት ስንጠቃና ክርክር ወጥተን፥ ክርስቶስ ለእኛ ያደረገውን ነገር እንድናሰላስል የሚያደርግ ነው። ይህ የአእምሮ ጅምናስቲክ አይደለም። የአምልኮ ውበት ነው። እናም ጎርጎርዮስ በ፷፩ኛ ምዕራፉ በክፍል ፭ ላይ እንዲህ ይላል፤ « ቀዳማዊ ዘሀሎ እምቀዲሙ እንበለ ጥንት ኮነ ይእዜ ዘቦቱ ጥንት። ጥንት ሳይኖረው በቅድምና የነበረ ቀዳማዊ እርሱ ዛሬ ጥንት ያለው ሆነ። ዘኢተገብረ አስተርአየ ይእዜ በለቢሰ ሥጋ ዘተገብረ፤ ያልተፈጠረ እርሱ የተፈጠረ ሥጋን ተዋሕዶ ዛሬ ታየ። በከመ ጽሑፍ ዘይብል አእምሩ ዘንተ ሐዋርያ ሊቀ ካህናት እምነትነ ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚእነ ምዕመን በኀበ ዘገብሮ። ሊቀ ካህናት ሐዋርያ ባደረገው በአብ ዘንድ የታመነ የምናምንበት አስታራቂያችን መምህራችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይህን ዕውቁ ተብሎ እንደተጻፈ።  ዘኢያገምሮ መካን አግመረቶ ድንግል በከርሣ። ሰማይ ምድር የማይወስነውን ድንግል በማኅፀኗ ወሰነችው። ባዕል ዘይሁብ ብዕለ ለነዳያን። ብዕል ለሌላቸው ብዕልን የሚሰጥ እርሱ፤  ኮነ ነዳየ በእንተ ሥርዓተ ትስብእት። ሰው ስለ ሆነ ድሀ ተባለ። ከመ አብዓል አነ በንዴተ ዚአሁ። በርሱ ድሀ መባል እኔ እከብር ዘንድ። ነሣዕኩ አርአያሁ ወኢአቀብክዋ እርሱን መም ሰሉን በተፈጥሮ ገንዘብ አደረግሁ፤ ጠብቄም አላስቀረሁትም። ወውእቱሰ ነሥአ ሥጋየ ከመ ያድኅነኒ፥ ሊተ ዘገብረኒ በአርአያሁ ወበአምሳሊሁ። እርሱ ግን በአርአያውና በአምሳሉ የፈጠረኝ እኔን ያድነኝ ዘንድ ሥጋዬን ተዋሐደ። ወረሰዮ ሥጋየ ዘእንበለ ሞት። ሥጋዬንም ሞት የሌለበት አደረገው። . . . ቀዳሚሰ ወሀበነ አርአያሁ ክብርተ። ቀድሞ ክብርን የምታስከትል እርሱን መምሰልን ሰጠን። ወዳግመ ነሥአ ሥጋነ ኅሥርተ። ዳግመኛ ግን ኃሣርን የምታስከትል ሥጋችንን ተዋሐደ። ወዝንቱ ግብር ልዑል። ይህ ሥራ ረቂቅ ነው።»
 በተዋህዶ የከበረው እርሱ ፥ « እከብር የማይል ክቡር፥ እጸድቅ የማይል ጻድቅ ሲሆን»፥ እኔን እና አንተን ያድን ዘንድ በሥጋው ተዋረደ፥ ደሀ ሆነ፥ ወደቀ፥ ጮኸ፥ ማለደ፥ ተሰቃየ፥ ቃተተ፥ አምላኪየ አምላኪየ አለ። በሥጋው።  « ከመ አብዓል አነ በንዴተ ዚአሁ።» በእርሱ ደሀ መባል እኔ እከብር ዘንድ።
ይህን ያህል ስለ ትስብእቱ ሥራ መጨነቃችን ከቶ ለምንድነው? ምክንያቱም የደኅንነታችን ነገር ላይነጣጠል ከእርሱ ጋር ስለ ተያያዘ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለዚህ ሲናገር እንዲህ አለ፤ « ሰው የሆነም ዘመድ ሊሆነን ብቻ አይደለም። ፈጽሞ ይቅር አለን እንጂ፤ ኃጢአታችንን ለማስተስረይ ከአብ ጋር ለማስታረቅ ሊቀ ካህናትም ይሆነን ዘንድ ወደደ እንጂ፤ ስለዚህም ሰዎችን ሊመስላቸው ይገባል ባለው ነገሩ ላይ ጨምሮ በሁሉ አዛኝ የሕዝቡንም ኃጢአት ለማስተስረይ በእግዚአብሔር ዘንድ የታመነ አስታራቂ ይሆናቸው ዘንድ ነው አለ። ባሕርያችንን ስለተዋሃደ የሰውነቱንም  ነገር ያስተምረን ዘንድ ይህን ተናገረ። ሰው ለመሆን ያበቃው ለማስታረቅ ኃጢአትን ለማስተስረይ ብቻ ነው እንጂ ሌላ ምክንያት የለውም። ከእርሱ ብቻ በቀር ራሱ ብቻውን ኃጢአትን ማስተስረይ የሚቻለው የታመነ አስታራቂ ማነው? ለማስታረቅ ኃጢአትን ለማስተስረይ ያቀረበው መሥዋዕትስ ምንድነው መሥዋዕት ለመሆን የነሣው ሥጋው ብቻ ነው እንጂ»   ይላል።
ቀሲስ ደጀኔ ስትጽፍ፦ ባለፈው እንደ ጠቀስነው፡-ለአማርኛው ጥንት ግዕዝ በመሆኑ፥አማርኛውን ከግዕዙ ጋር እያ ገናዘብን እያንዳንዱን ቃል በዝርዝር እንመለከታለን። (አንዳዶች ይኼ የጠፋኝ ለማስመሰል፥ የመጀመሪያው የግሪኩ ነው ይላሉ።እነዚህ ሰዎች ግሪከኛውን በቅጡ ይወቁት አይወቁት አላ ውቅም።ምናልባት የእግዜር ሰላምታ ያህል ጥቂት ሞክረው ይሆናል።ነገር ግን ግዕዙም፥መጻ ሕፍቱም፥ሊቃውንቱም ከእኛ ጋር መሆናቸውን ማስተዋል ይገባል።ከዚህም ጋር ወደ ሌላ የሚኬደው ሲቸግር ብቻ መሆኑን መዘንጋት አይገባም።እኔ እያልኩ ያለሁት፡-ጥንት ቅዱሳት መጻሕፍት የተተረጎሙት ከባዕድ ቋንቋ ወደ ግዕዝ ነው፥ከዚያ በኋላ ደግሞ ወደ አማርኛ ተተርጉመዋል።ስለዚህ በቅድሚያ ማየት ያለብን የአማርኛው ቅጂና ግዕዙ መስማማታቸውን ነው።) » ብለሃል።
እዚህ ላይ ለአንተም ሆነ ለሌሎች ግልጥ የምናደርገው፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም፥ የግእዙ ትርጉም በዓለም ካሉት ትርጉሞች ሁሉ  ቀደምት ከሆኑትና ዛሬም ለምስክርነት የሚፈለግ ትርጉም ነው፤የትርጉሙ ጥንቃቄ፥ ከግሪኩ ጋር ያለው ቅርበት፥  በብዙ ደከመው ለእኛ ያስተላለፉት አባቶች፥ ለቅዱሳት መጻሕፍት ምን ያህል ክብር እንዳላቸው የሚያስረዳ የመንፈሳዊነታቸው ሕያው ምስክር ነው። ። በረከታቸው በእኛ ላይ ይደርብንና ፥ እነርሱ ለእኛ ያስተላለፉትን፥ ዛሬ እናንተ ልታፈልሱት መሞከራችሁ ነው እንድንጮህ ያደረገን።
ባለፈው ጽሑፍህ ስለ ሮሜ ፰፥፴፬ ያስቀመጥከው ከግእዙም ከአማርኛውም የሌለ ነው። ግእዙ ለምሳሌ የሚለው « ወይትዋቀስ በእንቲአነ» ነው። በየትኛው ሰዋስው ነው፥ ወይትዋቀስ በእንቲአነ « ስለ እኛ ይፈርዳል» የሚያሰኘው? በምስጢር ትለኝ ይሆናል። አንተ እኮ እየቀየርክ ያለኸው ገጸ ንባቡን ነው።  የአባቶች ትርጓሜ እንዳትል « ስለ እኛ ይከራከራል» ነው የሚለው እንጂ ስለ እኛ ይፈርዳል አይልም።  በነገራችን ላይ ግእዙና ግሪኩ አንድ ዓይነት አሳብ የያዙ ናቸው። « « ይትዋቀስ ይከራከራል» የሚለውና በግሪኩ “ ἐντυγχάνει  entynchanei “ ይማልዳል ተብሎ የተተርጎመው)  በምስጢር ብቻ ሳይሆን በቀጥታ ትርጉም ይገናኛሉ።  መማለድ ማለት ስለ አንድ ሰው ፈንታ ሆኖ ቆሞ መከራከር ማለት ነውና ። አንዳቸው በአንዳቸው ትርጉም ውስጥ የሚገኙ ናቸው። ይፈርዳል ግን በገጸ ንባቡ በፍጹም የማይገናኝ፥ ከአባቶች መጻሕፍትም ምስክር የማይቀብርለት ነው።  ወደ ግሪኩ የሄድነው አንተ እንደምትለው ግእዙን ንቀን ሳይሆን አሁን ክርክራችን « ይትዋቀስን»  እንዴት እንተርጉመው ስለሆነ ነው።  የአባቶችን ትርጓሜ፥ የቅዱስ ዮሐንስን ትርጓሜ፥ ሃይማኖተ አበውን ወደ ጎን ስላደረጋችሁ፥ ቅዱስ መጽሐፍ ነውና ከመጀመሪያው እንዴት ተጻፈ ማለት የግድ ያስፈልጋል። ቅዱሳት መጻሕፍትን ስለመተርጎም ስናስብ ልንከተለው የሚገባንን አካሄድ  ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃይለ ሥላሴ መጽሐፍ ቅዱስን ባስተረጎሙበት ወቅት በጻፉት መቅድም ላይ በሚገባ ገልጠውልናል። እንዲህ ይላሉ፥ « የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጕም ከመሠረታዊ ቋንቋው ከዕብራይስጥና ከፅርዕ ጋር እየተያየ ሊታረም እንደሚገባው ስለ ተመለከትን፥ በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርት ለዚህ ሥራ ተገቢ የሆኑትን ሊቃውንት መረጥን።»   ይላሉ።  እኛም ስንለው የነበረውን ይህን የንጉሠ ነገሥቱን አካሄድ ነው።
የ፪ሺ ዓመቱም መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ፥ ተርጓሚዎቹ በግልጥ ያስቀመጡት ሐቅ አለ። ይኸውም ከትርጓሜው ይልቅ ፖለቲካው ማለትም የእናንተ ተጽእኖ አስገድዶአቸው መሆኑን ለመግለጥ፥ « በግሪኩ ይማልዳል ይላል» ብለዋል። በተጨማሪ ማለት የነበረባቸው፥« ግእዙም እንዲህ አይልም ተገደን ነው እንጂ»  ነበር። ተርጓሚዎቹ የሚያመልጡበትን መንገድ ቢያስቀምጡም፥ ጥቂት የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችን ለማስደሰት፥ ቤተ ክርስቲያኒቱን በዓለም አቀፍ ደረጃ አንገት የሚያስደፋ ሥራ ነው ነው የተሠራው። ( ይቀጥላል።)

ከቀሲስ መላኩ ተረፈ) ከቀሲስ መላኩ

Saturday, April 29, 2017

"ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ" የብርሃኑ አድማሴ የቃላት ዝላይ

የአለት ላይ ዝላይ አያዋጣም!

"ወደ አምላኬና ወደ አምላካቸሁ"
ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በስብከቶች እየተፈራ የሚዘለል የእግዚአብሔር ቃል
+++++++++++++++++++++++++++++++++++++
ሰሞኑን በየቤተክርስቲያኑ ዐውደ ምሕረት የሚነገረው ወንጌል ስለ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ቢሆንም የማቅ ሰባክያነ ወንጌል ተብዬ እንደነ ተስፋዬ ሞሲሳ (ተስፋዬ ስለቃሉ ሞዛዛ) እና ብርሃኑ አድማሴ (ብርሃኑ ቃሉን ደርምሴ) እየዘበራረቁም ቢሆን ተያይዘውታል።
የእግዚአብሔርን ቃል እየቀነሱ እና እየዘለሉ ማስተማር ምን የሚሉት ፈሊጥ ነው?
ጌታ ኢየሱስ ከሙታን መካከል ከተነሳ በኋላ በዮሐ 20፥17 ማርያምን አትንኪኝ አላረኩምና ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሄደሽ፦ እኔ ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ አርጋለሁ ብለሽ
ንገሪአቸው እንዳላት በግልፅ ተፅፎ ሳለ እነዚህ የማቅ አቀንቃ  የክርስቶስ ሰው መሆኑ እንዳበቃ አርገው ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ የሚለውን እየዘለሉ በድፍረት መናገራቸው ያሳዝናል።
ሰው በመሆኑ መከራን ተቀበለ እንጂ ለዘላለም ስጋን ተዋህዶ ይኖራል ብሎ እንደተናገረው ቅዱስ አትናቴዎስ። ሞትን ድል ነስቶ በአብ ቀኝ የተቀመጠው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዛሬም ለዘላለም የማይለወጥ ፍፁም ሰው: ፍፁም አምላክ ነው (ሃይማኖት አበው 1986 ገፅ 80/ ዕብ 13፥8)
ክርስቶስ በአብ ቀኝ ከተቀመጠ በኋላ የሰውነቱን ግብር አቁሞ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር መለኮታዊ ስራውን እየሰራ ይገኛል ብሎ መስብኩ የክርስቶስን መካከለኛነት መቃወም ብቻ ሳይሆን ይኼ አባባል ኢየሱስ በአባቱ ቀኝ እስኪቀመጥ ድረስ መለኮት ስራውን ለስጋ ትቶ ስጋ ብቻ ይሰራ ነበር። አሁን በተራው ሰራውን ስለፈፀመ ስራውን ለመለኮት አስረከበ እንደማለት ነው። ይህ አባባል ደግሞ ሲያረግ ሥጋውን በመለኮት ባህርይ አረቀቀው: መጠጠው የሚለውን የአውጣኪን የክህደትአስተምህሮ መቀበል ይሆናል። ዳሩ ይኄ ስብከት በብዙዎቹ ሰባኪያን ዘንድ ሲነገር ይሰማል። መለኮታዊ ሥልጣኑን በመጠበቅ ሲባል በሥጋ ማረጉን በርቀት ይከላከላሉ። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በኦፊሴል አውጣኪን ብታወግዝም አስተምህሮውን በስልት ትቀበላለች። የምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት አውጣኪያውያን ናችሁ የሚሏትም አለምክንያት አይደለም። የኢየሱስን እርገት የኢት/ኦር/ ቤተክርስቲያን የምትቀበለው በመለኮታዊ ባህርይ ብቻ እንጂ ዛሬም በሥጋው በአብ ቀኝ እንዳለ አይደለም ማለት ነው? በሥጋው አርጓል የምትል ከሆነም በሥጋው የማረጉን ምክንያት በድፍረት ልታስተምር ይገባታል። ከኃጢአት ለመንጻትም ሆነ ሕይወት ወደሆነው ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት አዲስ አማኝ ለመምጣት በስጋው ቀራንዮ ላይ አንዴ በፈፀመው ድኅነት ስለእኛ አሁንም በሰማይ በአብ ይታይ ዘንድ በስጋው አለ ልትል ይገባታል። መለኮት ቃሉ ብቻ ማዳን እየተቻለው ሥጋ የለበሰው በሥጋ ያጣነውን ክብር በልጁ በኩል ልጅነትን እንድናገኝና በሰማያዊ መቅደስ የመግባት ድፍረት እንድናገኝ ስለፈለገ ብቻ ነው።
ይህንንም ሐዋርያው እንደዚህ አስረግጦ ይነግረናል።

" ክርስቶስ በእጅ ወደ ተሰራች፥ የእውነተኛይቱ ምሳሌ ወደ ምትሆን ቅድስት አልገባምና፥ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ አሁን ይታይ ዘንድ ወደ እርስዋ ወደ ሰማይ ገባ።"
(ዕብራውያን 9:24)
ከዚህ ውጪ የሆነው ሁሉ ፍፁም ሰው ፍፁም አምላክ መሆኑን የሚያስክድ ነው።
ኢየሱስ የመጣበትን በእያንዳንዳችን ፈንታ በመስቀል ላይ የማዳንን ስራ ፈፅሞ ሞቶ ከተነሳ በኋላ አምላኬ ማለቱ የማቅን ሰባኪያን አባባል ገደል ከቶታል።
ለዚህም ሃይማኖት አበው 1986 ገፅ 248 እንዲህ ሲል ይመሰክራል
" እኔ ሰው የሆንኩ አምላክ ነኝና እኔም አንድ ነኝና ይህንንም ያንንም እኔ እላለው ይላል፣ የሰውን ባህሪይ ገንዘብ አድርጌአለውና። ኋጢአት የሌለበት እርሱ እኔ ነፍስን ስጋን ተዋህጃለውና ከእኔ ጋር አንድ ላደረኩት ለስጋ ስርዓት እንደሚገባ እንዲህ አባቴን "አምላኬ" ብዬ ጠራሁት "
እናም ተወዳጆች ሆይ ጌታ ኢየሱስ እንዴ ለዘላለም ባፈሰሰው ደስ ዳግም ማፍሰስ ሳይጠበቅበት ሁል ጊዜ ሲያነፃን ይኖራል። እግዚአብሔር እኛን የሚያይበትብቸኛው መንገድ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው።
"የልጁም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል።" 1ኛ ዩሐ 1፥7
ያለፍርሃት የጌታ ምስክሮች እንሁን እኔ ይህን ታዘብኩ እናንተም እስኪ የማቅን ሰባኪያንን የሚፈሩትንና የሚዘሉትን ቃል ንገሩንና ለመማማር እንወያይበት።
የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ፀጋ የእግዚአብሔርም ፍቅር የመንፈስ ቅዱስም ህብረት ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን

Wednesday, April 12, 2017

«አሮጌውን እርሾ አስወግዱ፤ ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአልና»

Saturday, April 



(በድጋሚ የቀረበ)

ዕብራውያን     פֶּסַח «ፔሳኽ» ይሉታል። ፋሲካ ማለት ነው።  በወርኀ ኒሳን በዐሥራ ዐምስተኛው ቀን ይከበራል። ሥርዓቱ የሚጀመረው በዐሥራ አራተኛው ቀን ዋዜማ ሲሆን በፋሲካው ሳምንት እርሾ የገባበት ምንም ዓይነት ምግብ መመገብ ክልክል ነው።ዕለቱን ተቦክቶ ወዲያው የሚጋገር እንጂ የኮመጠጠ ወይም የቦካና የዋለ፤ያደረ መመገብ በሕጉ እንደተቀመጠው ከእስራኤል አንድነት ያስወግዳል። ከማንኛውም እርድ ላይ ጥሬ መብላት ወይም ከበሉትም አስተርፎ ማሳደር አይፈቀድም። ለመስዋዕት የሚቀርበው የበግ ወይም የፍየል መስዋዕትም እድሜው ከአንድ ዓመት ያልበለጠ ጤናማና የተመረጠ መሆን ይገባዋል። በዐሥራ ዐራተኛው ቀን ምሽት መስዋዕቱ ይታረዳል።ሥጋውን ደግሞ ሌሊት  ከመራራ ቅጠል ጋር ቀላልቅለው ይበሉታል። 
ደሙን ደግሞ  የበሩን ሁለት ረድፍ «መቃንና ጉበኑን» ይቀቡታል።  ሁለቱን ቋሚ መቃንና የላይኛውን ጉበን ሲቀቡት ይህንን ቅርጽ ይይዛል።


ይህ ቅርጽ የዕብራውያን ስምንተኛውን ፊደል «ኼ» የተባለውን ይወክላል። (እንደአማርኛው በጉሮሮ ሳይሆን በላንቃ የሚነበብ ነው) «ኼ» ማለት በዕብራውያን ትርጉም «ሕይወት» ማለት ነው። ዕብራውያንም በፊደላቸው በ«ኼ» ቅርጽ በሚቀቡት ደም የተነሳ ወደፈርዖናውያን ሠፈር የሚያልፈው ሞት አይነካቸውም። ምክንያቱም ሕይወት የሚል ማኅተም በራቸው ጉበንና መቃን ላይ ታትሟልና። ፋሲካ ማለት ይህ ነው። በደሙ ምልክት የተከለሉ በሕይወት ለመቆየት ዋስትና የያዙ ሲሆን ይህንን ማኅተም ያላገኙና ምን እየሆነ እንዳለ የማያውቁ ደግሞ  በሞት የሚወሰዱበት  የፍርድ ምልክት ነው። ደሙ የሞትና የሕይወት መለያ ምልክት ሆኖ አገልግሏል።
ይህ ሥርዓት እስራኤላውያንን ከባርነት፤ ከጠላት አገዛዝና ከመገደል የታደገ የዋስትና መንገድ ነበር። እንደዚሁ ሁሉ የአዲስ ኪዳኑ ፋሲካ ሕዝብና አሕዛብን ከሰይጣን ባርነትና ከዘላለም ሞት የታደገ በመሆኑ ሐዋርያው ጳውሎስ «እንግዲህ ያለ እርሾ እንዳላችሁ አዲሱን ሊጥ ትሆኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ አስወግዱ። ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአልና» 1ኛ ቆሮ 5፤7 በማለት የሚነግረን።  አሮጌውን እርሾ ካላስወገድን ፋሲካችን የሆነውን ክርስቶስ መቀበል አይቻልም። የክርስቶስን ፋሲካ እካፈላለሁ በማለት የበዓሉን አከባበር ማድመቅ፤ እንኳን አደረሰህ/አደረሰሽ መባባል ልምድ እንጂ የመለወጥ ምልክት አይደለም። የክፋት እርሾ የተባሉትን ሐዋርያው ጳውሎስ በቆሮንቶስ መልእክቱ ሲነግረን እንዲህ ይለናል። «ሴሰኛ፤ ገንዘብን የሚመኝ፤ ወይም ጣዖትን የሚያመልክ፤ ወይም ተሳዳቢ ወይም ሰካር ወይም ነጣቂ» ከመሆን መታቀብ ብቻ ሳይሆን ከሆኑትም ጋር አብሮ ባለመብላት ጭምር በመከልከል ከአሮጌው እርሾ ሆምጣጣነት መራቅ እንዲገባን ያስፈልጋል። (1ኛ ቆሮ 5፤11) የእስራኤል ዘሥጋ ፋሲካ መጻጻና የቦካ ይከለክል እንደነበረው ሁሉ የአዲስ ኪዳኑ ፋሲካም እንዲሁ ይከለክላል። በኃጢአትና በዐመጻ የቦካ የውስጣችንን ሆምጣጣ እርሾ ካላስወገድን በስተቀር በፋሲካው የሚገኘውን ሕይወት በፍጹም  አናገኝም።  የቀደመው ፋሲካ እርሾ ያለውን ነገር ከቤቱ ያላጠፋ «ከእስራኤል ጉባዔ ተለይቶ ይጥፋ» የሚል ሕግ ነበረው።  ምድራዊው ፋሲካ ይህንን ያህል ከከበረ ሰማያዊውማ እንደምን የበለጠ አይከብር? ፋሲካን መናገርና ፋሲካን አውቆ መኖር የተለያዩ ነገሮች ናቸው። ስለፋሲካ ብዙ ማስተማርና መናገር ይቻል ይሆናል። ስለፋሲካ የመልካም ጊዜ መግለጫና ስጦታም መለዋወጥ ይቻል ይሆናል። ፋሲካን ማክበር ማለት 2 ወራት በጾም አሳልፎ «እንኳን ጾመ ልጓሙን ፈታልህ/ፈታልሽ» ተብሎ ልጓም አልቦ የመሆኛ ሰዓት ደረሰ በማለት የሰላምታ መሰጣጣት ፕሮግራም አይደለም። ጾሙ ሲፈታ እንደፈለገን ልንበላ፤ ልንጠጣ፤ ልንናገር የልጓም አጥራችን ተከፈተ ማለት ከሆነ በአሮጌው እርሾ ብቻ ሳይሆን ከሰው የልማድ ስርዓት ጋር እንኖራለን ማለት ነው። የክርስቶስ ፋሲካ ግን በእነዚህ ሁኔታዎች ውስጥ አይገኝም። ፋሲካ በስግደትና በወይራ ቅጠል በመጠብጠብ የሚገኝም ጸጋ አይደለም።  ፋሲካ የአንድ ወቅት ራስን ማስገዛትና በጽኑ እሳቤና ጭንቅ ማለፍ ውስጥ የሚመጣም አይደለም።
ፋሲካ በልባችን መቃንና ጉበን ላይ የደሙን ምልክት በመያዝ ዕብራውያን ከሞት እንዳመለጡበት የ «ኼ» ምልክት ማኅተም በመያዝ ብቻ ነው የምንድነው። ያን ጊዜ ብቻ ነው ሞት በራችን ላይ ያለውን የአዲስ ኪዳኑን «ፔሳኽ» አይቶ የሚያልፈው። ይህንን የደም ማኅተም ለመያዝም ከክፋት፤ ከሀሰት፤ ከግፍና ከዐመጻ እርሾ መለየት የግድ ነው። ከዝሙት፤ ከስርቆት፤ ከጉቦ፤ ከምኞትና ከኃጢአት ሁሉ እርሾ ሳንለይ ውስጣችን የሞላውን መጻጻ ተሸክመን የፋሲካ ሕይወት የለም። እስራኤላውያን መዳን የቻሉት የፋሲካቸውን የበግ ደም ምልክት በመያዛቸው ብቻ ነው።  እኛም የአዲስ ኪዳኑ የእግዚአብሔር በግ የክርስቶስን ደም ምልክት ካልያዝን በማንም በሌላ ምልክት ወይም ጻድቅ ዋስትና ልንድን አንችልም። ሁሉም ይህንን የደም ምልክት የመያዝ ግዴታ ስላለበት ማንም ለማንም ዋስትና ሊሆን እንደማይችል ጳውሎስም «ልዩነት የለም፤ ሁሉም የመዳን ጸጋ ያስፈልገዋል» አለን። 

«እርሱም፥ ለሚያምኑ ሁሉ የሆነ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኘው የእግዚአብሔር ጽድቅ ነው፤ ልዩነት የለምና፤ ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል፤በኢየሱስ ክርስቶስም በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ» ሮሜ 3፤22-24
እንግዲህ  ከፋሲካው ተስፋ የምናደርግ ሁላችን እስኪ ራሳችንን እንመርምር። እንደመጽሐፍ ሊያነበን በሚቻለው ከፋሲካችን ክርስቶስ ፊት እስኪ ራሳችንን እናንብበው። በእውነት እነዚህ እርሾዎች በውስጣችን ከሌሉ ከ2000 ዓመት በፊት ለሕይወት የፈሰሰውን ደም ይዘናል ማለት ነው። ያኔም ሞት በኛ ላይ ምንም ሥልጣን እንደሌለው አረጋግጠናል። እስራኤላውያን የበራቸውን ጉበንና መቃን በቀቡ ጊዜ ሞት እንደማይነካቸው እርግጠኞች እንደነበሩ ሁሉ እኛም የበለጠውንና የተሻለውን የሕይወት ደም በእምነት ስለያዝን ለዘላለማዊ ሕይወት እርግጠኞች መሆን እንችላለን። ከዚያ ባሻገር በየዓመቱ በሚመጣ በዓል የሚገኝ የደም ምልክት የለም። በጥብጠባና በስግደትም የሚገኝ የሕይወት ዋስትና እንዳለ ካሰብን የፋሲካውን ምስጢር በልምድ ሽፋን ስተነዋል ማለት ነው። የተደረገልንን ማሰብ አንድ ነገር ሆኖ ሰው ግን ዓይኑን በዚያ በዓል ላይ ተክሎ የዓመቱ ኃጢአት ወይም ሸክም እንደሚወድቅ ማሰብ ስህተት ነው። ዓመቱን ሙሉ ከክፋትና ከግፍ እርሾ በመላቀቅ፤ ለአንድም ሰከንድ የማይለይ ምልክት ልባችን ጉበንና መቃን ላይ ደሙን በእምነት ይዘን መገኘት የግድ ይሆንብናል። ያኔ ነው ፋሲካችን ታርዷል የምንለው። ያኔም ነው ሁልጊዜ በሕይወት መንገድ ላይ እንዳለን የምናውቀው። መንፈሳዊ ሕይወት እንዲኖረን፤ መንፈሳዊ ጉዞ እንዲሰምርልን ዕለት፤ ዕለት መታደስ መታደስ ይገባዋል።
«ስለዚህም አንታክትም፥ ነገር ግን የውጭው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳ የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል» 2ኛ ቆሮ 4፤16 ንስሐ እንግባና እንታደስ።
ፋሲካችን የሆነው ክርስቶስ ኢየሱስ ያደረገልንን ውለታ እያሰብን ውስጣችንን መፈተሽ የግድ ነው። በአምናው እኛነታችንና በዘንድሮው እኛነታችን መካከል የሕይወት ለውጥ ከሌለን ሞት በመጣ ጊዜ ምንም የመዳን ምልክት እንደሌላቸው ፈርዖናውያንን ወደዘላለማዊ ሞት መሄዳችን እውነት ነው። በወይራ በመጠብጠብ 30 እና 40 ለመስገድ ከመሽቀዳደም ይልቅ፤ ከሞት የማምለጫ የፋሲካው ዓርማ ክርስቶስን ከኃጢአት በጸዳ ማንነታችን ውስጥ ዘወትር ይዘነው እንኑር። ዝሙት፤ ውሸት፤ስርቆት፤ ሃሜት፤ ነቀፋ፤ ምኞትና ገንዘብን መውደድ ሁሉ ሳንተው ፋሲካን ማክበር አይቻልም። ከቦታ ቦታ በመዞርም ፋሲካ አይገኝም። ፋሲካ በልባችን ላይ አንዴ የተሰራው የክርስቶስ የእምነታችን ከተማ ነው። በዚያ ላይ የማይጠፋ ብርሃን አለ። ክርስቶስ ባለበት በዚያ የልባችን ከተማ ውስጥ ማስተዋል፤ ደግነት፤ በጎነትና ቅንነት አለ። ከዚያ መልካም ከተማ የሚወጣው ሃሳባችን የተራቡትን ያበላል፤ የታረዙትን ያለብሳል፤ የታመሙትን ይጠይቃል። ኑሮአችን፤ አነጋገራችንና አካሄዳችን በልክ ነው። ዕለት ዕለት በምንኖረው ሕይወት እንጂ በዓመት አንድ ቀን በሚከበር ፋሲካ ክርስቶስን መምሰል አይቻልም። ሞት የደሙ ምልክት የሌለባቸውን እስራኤላውያንን ሁሉ ይገድል ነበርና። እኛም በሰማይ የተሰጠንን ተስፋ እስክናገኝ ድረስ ሞት ከተጠበቀልን ተስፋችን እንዳያስቀረን ፋሲካችን ክርስቶስን ዕለት ዕለት በልባችን ይዘን እንኖራለን። ያኔም በክርስቶስ ያለ ተስፋችን ምሉዕ ስለሆነ ስለመዳናችን አንጠራጠርም። አብርሃም ልጅ ሳይኖረው «ዘርህ ዓለሙን ይሞላል» ሲባል በእምነቱ ተስፋውን ተቀበለ። በክርስቶስ ትንሣዔ ያመንን እኛ ደግሞ እንደምንድን ካመን የተሰጠን የመዳን ተስፋ በሰማይ እውነት ሆኖ ይጠብቀናል።  ምክንያቱም የመዳናችን የእምነት ተስፋ ክርስቶስን በልባችን ዕለት ዕለት ይዘን እንዞራለንና!!

Monday, April 3, 2017

ከእንግዲህ የክርስትና ኃይማኖት ተከታይ አትበሉኝ!


አይደለሁምና፤ አዎን አይደለሁም።
የፕሮቴስታንትም ኃይማኖት ተከታይ አትበሉኝ።
አይደለሁምና።
የሆነ ጊዜ መናፍቅ ትሉኝ እንደነበረም አስታውሳለሁ።
ለምን አላችሁኝ ብዬ አልከፋም!
ታላቁ የእምነት ሞዴላችን ቆራጡ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስም በአንድ ጠርጠሉስ በሚባል አእምሮ በደነዘዘው አይሁድ "መናፍቅ!" ተብሏልና።(የሐዋ.ሥራ 24:5)
ግድ የለም።
የክርስትና ኃይማኖት ተከታይ በመሆን መንግሥተ ሰማይ አይገባም።
ክርስቶስም ይህንን ቃል አልገባልንም፣ የአባቱን ፈቃድ የሚፈጽሙትን ነው እንጂ..።
ጌታ ጌታ ስላልክ፥ በሃሌ ሉያ ስላንጋጋህ፥ በፉጨት በእልልታ ስለቀወጥክ፥ ባይብል በእጅህ ስላልተለየ፥ኢየሱስ ኢየሱስ ስላልክ፣ በየማምለኪያ አዳራሽ ስለተገኘህ፥ በአዲስ ቋንቋ ስለተናገርክ፤ ፐ! አንተ የእግዚአብሔር ሰው ስላሉክ፣በሱፍ በከረባት በየአደባባዩ ስለተገለጥክ፥ ከባህር ማዶ ጀምሮ የአገልግሎትህ ኮሜንት "ተባረክ" ስለጎረፈልህ...በቃ ....እንዲያ በማለት ሰማይ የገባክ አይምሰልህ።
ይሄም ዋስትና አይደለም።
አርብ እሮብ ስለጾምክ፥ ይሄም ሳያንስህ ወራትን ሳምንታትን በመላምት ስያሜ እያቆላመጥክ ክርስትና አይሉት ግብዝና በመጾምህ የተመጻደቅክ ቢመስልህ፣በባዶ እግርህ ስለተጓዝክ፣ግሽን፤ ኩክ የለሽን ስለተሳለምክ፥ ደብረ ዳሞን ስለወጣክ፣ ስዕለትህን በሩቅ ሀገር ንግስ ስላደረስክ፣ ሰባት አመትኮ በአንድ እግሩ ቆሞ ፐ! ብለህ ተከታይህ ነኝ ስላልክ አይደለም፥ዳገት ቁልቁለቱን ወጥተህ ስለወረድክ አይምሰልህ።
በቀን 5 ጊዜ ስለሰገድክ፣ ጥፍርህን ስለሞረድክ፣አፍንጫህን አሻሽተህ ሼይጢያንን እያሳደድኩ ነው ብትልና፣ዘካ ስላወጣክ፥ ጁምአ ስለሰገድክ አይደለም መንግሥተ ሰማይ በዚህ አይገኝም።
በዉል ማንነቱን ባታውቅም የአንድ አምላክ ተከታይ ነኝ ስላልክ፣ ይህ ሁሉ የመንግሥተ ሰማይ ዋስትና ሊሆን አይችልም።
አመቱን እያሰላህ በጨረቃ ተመርተህ ወሩን ሙሉ ስለጾምክ፣ ሱሪህን ስላሳጠርክ፣ ቆቡን ስለደፋህ፣ አንቺም ከጥፍር እስከራስ ስለተከናነብሽ፤ በቀዳደa አጮልቀሽ ስላየሽ መንግሥተ ሰማይ መግባት እንዲያ እንዳይመስልሽ። ይህ ሀሉ እንኳን የምትወርሽበት ለመውረስ በሚደረገው ጉዞ አንድ እርምጃ እንኳን አይሸፍንም።

አይሁድ ነሽ ሙስሊም፣ቡዲዝም ነሽ ሂንዱዝም ኦርቶዶክስ ነሽ ጴንጤ ይህ ሁሉ የመደራጃ እድር ነው።

እኔ ግን የክርስትና የኃይማኖቱ ተከታይ አትበሉኝ እያልኩኝ አንድ ነገር የምለው አለኝ፣
ማንም ምንም ብትሆን ማንነትህና ምንነትህ ለኔ ምንምምም ነው።
ነገር ግን እውነት መንገድና ህይወት እነሰ ነኝ ያለውን፤ በእኔ በቀር ወደአብ የሚደርስ ማንም የለም ያለውን፣በእኔ የሚያምን ለዘላለም ይኖራል ያለውን፣በመካከላችን ያለውን የጥል ግድግዳውን በደሙ አፍርሶ የመጣበትን አላማ ጨርሶ ተፈጸመ በማለት ወደሰማይ ያረገውን፡መጥቼም እወስዳችኃለሁ፣ከእኔም ጋር ለዘላለም ትኖራላችሁ በማለት የማናችሁም አምላክ ያልገባላችሁን ታላቅ የማይታጠፍ የተስፋ ቃል የገባልንን ፥ ስለአንተና ስለእኔ ብሎ ወደምድር በመምጣት ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን መቀማት እንደሚገባ ነገር ያልቆጠረውን፤ የአብ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስን ያላመነ ፤ በእርሱም በቃሉ ያልኖረ፤ በወንጌሉም ያላመነ፤ እርሱ በደሙ በመሠረተው በመሠረቱ ያልቆመ፣ጌታና መዲኅን፣የነፍሱም ዋስትና አድርጎ ያልተቀበለ ሁሉ ምንም ዋስትና የለውም። ። ። ።

ምንም የህይወት ዋስትና የለውም። ።

ይህን ስታሟላ ብቻ ነው የመንግሥተ ሰማይን የመውረስ ዋስትና የሚኖርህ።
እኔም የክርስትና አምነት ተከታይ ሳልሆን የክርስትና እምነት የመሥራቹ የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይ ነኝ።
ስለዚህ ከዚህ በኋላ ኢትዮ ቴሌኮምም ቢሆን ክርስቲያናዊ ለሆኑ በዓላት መልካም ምኞታቸውን ሲገልጹ "የክርስትና እምነት ተከታዮች" ከማለት ይልቅ "የክርስቶስ ኢየሱስ ተከታዮች"ቢሉን ደስ ይለናል።

አዎን የክርስቶስ ኢየሱስ ተከታይ ነኝ።
የእግዚአብሔር የመንግሥቱ ሰባኪ፣
የትንሣኤው መስካሪ፣
የክርስቶስ የወንጌሉ ዘማሪ፣
አዋጅ ነጋሪ፣
የአንድ መሪ፣የአንድ አምላክ የአንድ ጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይ ነኝ እንጂ ""የማንም ድርጅት ወይም ቸርች"" ተከታይ አይደለሁም።

በርሱ በማመኔ ብቻ በውድ ደሙ የታጠብኩ የማይሻር ኪዳን የተገባልኝ ምጽአቱንም በማራናታ የምጠባበቅ
እእእ የደሙ ፍሬ ነኝ!!!

( Fitsum @yalkbet )

Wednesday, February 1, 2017

ፈውስ!


Tsige Sitotaw

በሁሉም ቤተ እምነቶች ዘንድ የሚታየው የፈውስ ጉዳይ ብዙ ሰዎችን ጥርጣሬ ውስጥ እያስገባ ነው ።
እስቲ እንደ እግዚአብሔር ቃል እንነጋገርበት
1. ፈውስ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ
ክርስቲያን ፦
በዚች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚታየው የፈውስ ሥነ ሥርዓት ያለ ፀበል የሚከናወን አይደለም ። ስለዚህም በሁሉም አብያተ ክርስቲያናት ፀበል በምንጭም ይሁን ከቧንቧ በተጠለፈ ውኃ የሚጠመቁ በርካታ ናቸው ።
እንዲሁም ፀበል እየተባለ በተለያዩ ቦታዎች እየተዘጋጄ በብዙ ሰልፍ የሚጠመቅ ሕዝብ ቀላል አይደለም ። በዚያ ቦታ ላይ የሚታዩትን ትርዒቶች ማየት አስገራሚ ነው ።
በክፉ መናፍስት የተያዙ ሰዎች አእምሯቸውን እየሳቱ እየወደቁ ከልባቸው እያለቀሱ ራሳቸውን እየሳቱ በብዙ መኃላ እየተገዘቱ ሲወጡና የታመሙት ነጻ ሲወጡ ይታያሉ ።
ይህ ሁሉ የሚሆነው በተለያዩ ቅዱሳን ስም በተሰየሙ ፀበሎች ነው ። ስለሆነም ኦርቶዶክሳውያን ትክክለኛ እምነት እንዳላቸውና ቅዱሳን ያማልዳሉ ለሚለው ማረጋገጫቸው ይኸው ተአምራት የሚታይበት ፀበል ቦታ ነው ።
በተጨማሪም ፦ በክፉ መንፈስ የተያዘው ሰው ራሱን ስቶ መንፈሱ በላዩ ላይ ሆኖ ሲለፈልፍ ከየትና ምን ሲያደርግ እንደያዘው መናገር ይጀምራል ።
ከየት ያዝኸው ሲባል ከጴንጤ ቸርች ምን ሲያደርግ ሲባል ኢየሱሴ ኢየሱሴ እያለ ሲለፈልፍ ትክክለኛው ሃይማኖት የትኛው ነው ሲባል ኦርቶዶክስ ሌላውስ ሲባል የውሼት እያሉ ካስለፈለፉ በኋላ ያንን በካሴት ቀድተው እውነተኛዋ ሃይማኖት ሰይጣን እንኳ የመሠከረላት ቅድስት ተዋሕዶ እያሉ ከሰይጣን በሰሙት መረጃ ሃይማኖታቸውን የሚሰብኩ ሰዎች አሉ ።
እንደገናም ሰይጣኑ ተቃጠልሁ ነደድሁ ልሂድ ልውጣ እያለ ሲጮህ ምስህ ምንድን ነው ? ተብሎ ይጠየቃል እሱም አመድ ወይም አተላ ወይም ደም ወይም ሌላ ነገር እንዲመጣለት ይጠይቃል ያዘዘው ነገር ሲቀርብለት ያንን ጠጥቶ ለቀቅሁ ብሎ ሦስት ጊዜ ጮኸህ ውጣ ዳግም ላትመለስ የሚካኤል ሰይፍ ይቁረጠኝ ብለህ ምለህ ተገዝተህ ውጣ ተብሎ ያንን ቃል ፈጽሞ ሄድሁ ብሎ ይጮሃል ። ከዚያ በኋላ ሕመምተኛው ጤነኛ ሆኖ በአእምሮው ይሆናል ማለት ነው ።
እሺ ነገሩን ተመልክተናል የሚካድም አይደለም ። ግን በመንፈሳዊ ዓይን ሲታይ በእርግጥ ፈውሱ ተከናውኗል ወይ ? ብለን ጠይቀን መልስ ማግኜት አንችልም ።
ምክንያቱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምናደርገውን ሁሉ በማን ስም ማድረግ እንዳለብን አዝዞናል ።
ለምሳሌ ፦ እንደዚህም ያለውን አንድ ሕፃን በስሜ የሚቀበል ሁሉ እኔን ይቀበላል ። የማቴዎስ ወንጌል 18÷5
ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁና ። የማቴዎስ ወንጌል 18÷ 20
የክርስቶስ ስለ ሆናችሁ በስሜ ጽዋ ውኃ የሚያጠጣችሁ ሁሉ፥ ዋጋው እንዳይጠፋበት እውነት እላችኋለሁ ። የማርቆስ ወንጌል 9÷41
ያመኑትንም እነዚህ ምልክቶች ይከተሉአቸዋል፤ በስሜ አጋንንትን ያወጣሉ፤ በአዲስ ቋንቋ ይናገራሉ፤ እባቦችን ይይዛሉ ። የማርቆስ ወንጌል 16÷17
በተጨማሪም የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 14, 15,16 ሁሉንም ብንመለከታቸው በኢየሱስ ስም ብቻ መለመን ወይም መጸለይ እንዳለብን ታዝዘናል።
አጋንንት የሚወጡት በእርሱ ስም ሙታን የሚነሡት ለምጻሞች የሚነጹት ማናቸውም ፈውስ የሚከናወነው በጌታ ስም ብቻ እንደሆነ ታዝዘናል ።
ታዲያ እንዲህ ከሆነ በፀበልና በቅዱሳን ስም እንደሚለቁ ሆነው የሚጮሁት ለምንድን ነው ?
እንግዲያው ሰይጣን እያታለለን እያዘናጋን እንደሆነ ልናውቅበት ይገባል ። ባልተሰበከልን ልዩ ወንጌል ታስረን ከእርሱ ጋር ወደ ገሃነም እንዳንገባ ።
ስለዚህ የምናደርገውን ሁሉ በኢየሱስ ስም ብቻ ። አሜን ። አሜን ። አሜን ። ወአሜን ለይኩን ለይኩን ።
2 . ፈውስ በወንጌላውያን ፦
በአሁኑ ሰዓት እርስ በእርሳቸው የማይተዋወቁ በፕሮቴስታንትነት የሚታወቁ በርካታ ቤተ እምነቶች እየተመለከትን ነው ። አንዳንዶች በሽማግሌዎች ሲመሩ አንዳንዶች ደግሞ በግለ ሰቦች ብቻ የሚመሩ ናቸው ።
በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ተመሳሳይነታቸው ይበዛል ። በአደባባይ የሚፈጸመውን ሥርዓተ አምልኮ ስንመለከትም ጸሎቱ ዝማሬው ስብከቱ አለባበሱ ልሣኑ ትንቢቱ ጥምቀቱ ቊርባኑ ሁሉ አንዱን ከሌላው መለየት አይቻልም ።
ሁሉም ለኢትዮጵያ እንግዶችና መጤዎች የሚያስመስላቸውን እንግዳ ነገር ሲፈጽሙ ይስተዋላል ። ምንም እንኳ ገድልና ድርሳን ባይኖራቸውም አሁን ባሉት አገልጋዮቻቸው በእጅጉ ስለሚደገፉባቸው የተሳሳቱ መልእክቶችን ሊያስተናግዱ ይችላሉ የሚል የብዙ ሰዎች ስጋት አለ ።
ለምሳሌ ፦ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አንዳንድ ትላልቅ የእግዚአብሔር ባሪያዎች የተጠሩበትን ስም በባለቤትነት መያዝ "የግዚአብሔር ሰው" እንዲባሉ መፍቀድና ከሌላው አማኝ ልዩነት ማሳየት ።
ሰውነታቸው ከሁሉም በላይ ወፍሮና ገዝፎ እየታየ እነሱ ግን ከሁሉ በላይ እንደሚጾሙና እንደሚጸልዩ ራሳቸውን መስበክ ቲፎዞ ማብዛት ።
መናፍስትን ከሰው ሲያስወጡ መንፈሱ ለእነሱ እውቅና እንዲሰጥ እድሉን ማመቻቸት ከዚያም ከሕዝቡ ሙገሳን ጭብጨባንና አድናቆትን መቀበል ።
የሚያሳፍረው ግን ሰይጣኑ ሲለቅ ሦስት ጊዜ ጮኸህ ውጣ እየተባለ መታዘዙ ነው "ዝም ብለህ ውጣ" መባል ሲገባው ብዙ ምሥክርነት እንዲሰጥና ሰው ሁሉ እንዲገረም ማድረግና አጋንንትን ለደቀ መዝሙርነት እንደመጠቀም ያስቆጥራል ።
ያልተፈወሱ ሰዎችን ተፈውሳችኋል በማለትና ሐኪም ያዘዘላቸውን መድኃኒት እንዲያቋርጡ በማድረግ ለበርካታ ሰዎች ሕልፈተ ሕይወት ምክንያት መሆናቸውና ይህም በሕግ ፊት ደርሶ እያነጋገረ መሆኑ በተጨማሪም የገንዘብ ብክነት ሁሉ ደርሷል መባሉና በጉዳዩ መንግሥት ጣልቃ እንዲገባበት መገደዱ ሌላው ፈተና ሆኗል ።
እንግዲህ በዚህ ሁሉ ፉክክር እያንዳንዱ ቤተ እምነት ለመተራረም ፈቃደኛ ባለመሆኑ አንዱ በአንዱ እየሳቀ እውነተኛ ፈውስም እየጠፋ ክርስቶስን ከሚያምነው ይልቅ የሚተወው እየበዛ መጥቷል።
አሕዛብን ዝም የሚያሰኝ በሁሉም ዘንድ መገረምን የሚያመጣ ዓይን ለሌለው ዓይን እግር ለሌለው እግር የሞተንና የተቀበረን ከሞት ማስነሣት የተካተተበት ፈውስ እንጂ ጨጓራና አንጀት ብቻ እየተባለ አገልግሎቱ ጥርጣሬ ላይ ይወድቃል እንጂ የትም አይደርስም ።
ስለዚህ በሁሉም ቤተ እምነት የሚከሰቱትን ችግሮች ማስተካከልና እንደ እግዚአብሔር ቃል ማስሄድ ቢቻል ማለፊያ ነው ።
እናንተስ ምን ታዘባችሁ ?

Sunday, May 8, 2016

የፊልም አክተር እንጂ ክርስቶስ አይደለም!!


 በኢትዮጵያ ውስጥ ግን አብዛኞቻችን "የኢየሱስ ክርስቶስ" የመሰለንን ፎቶ በየቤታችን ግድግዳ ለጣጥፈናል። ምንም እንኳን በመለጠፉ ረገድ ኦርቶዶክሳዊያን ቢያይሉም፥ ካቶሊኩም፣ ጴንጠውም፣ ሞርሞኑም፣ ጂሆባውም፣ አድቨንቲስቱም በቃ ሁሉም ለማለት በሚያስደፍረኝ መልኩ በቤቱ ግድግዳ ላይ ወይም የሆነ የሆነ ነገሩ ላይ ለጥፏል። ለምሳሌ በስቲከር መልክ መኪናው ውስጥ፤ ባጃጅ ውስጥ፤ ላፕቶፕ ላይ፤ የሞባይል ስልኩ ላይ እና በመሳሰሉት ላይ ለጥፏል። በነዚህ ሁሉ ባይለጥፍ ደግሞ በየዓመቱ የትንሣኤ በዓልን በማስመልከት የፌስቡክ ግድግዳው ላይ መለጠፉን አይተውም። ከፎቶውም ግርጌ ከሚጻፉ ጽሑፎች መካከል "ያዳነኝ ይኼ ነው፤ የሞተልኝ ውዴ ይኼ ነው፤ የሕይወቴ ትርጉም ይኼ ነው.. ይኼ ነው.. ይኼ ነው" የሚል ይበዛበታል።

   ለመሆኑ ይኽ የሚለጠፈው ፎቶ አንዳንዶች እንደሚሉት ለሰው ልጆች ኃጢአት የሞተው የኢየሱስ ክርስቶስ ፎቶ ነው? እውነታው ግን አይደለም! የኢየሱስ ክርስቶስ ሳይሆን የጂም ካቪዘል መሆኑ መታወቅ አለበት። በመሠረቱ ወንጌልን ለማስረዳትና ለማስተማር ኢየሱስ ክርስቶስን የሚመስል ሰው ማዘጋጀት ነፍሴ ከማትቀበለው ድርጊት መካከል አንዱ ነው። ምክንያቱም እምነት በጆሮህ ሰምተህ፣ በልብህ አምነህ የምትቀበለው እንጂ በሚመስል ነገር ማረጋገጫ ወይም የበለጠ ስዕላዊ ማሳመኛ ሲቀርብልህ “ለካ እንደዚህ ነው?” ብለህ ተደንቀህ፣ የምትቀበለው የማስታወቂያ ውጤት አይደለም። ፊልም ሠሪዎች ገበያቸው ስለሆነ ግድ ላይሰጣቸው ይችላል። ለኔ ለአማኙ የኢየሱስ አዳኝነት በወንጌል ቃል እንደተጻፈው እውነት መሆኑን አምኜ እቀበለዋለሁ እንጂ በጭራሽ እርሱን ሊወክል በማይችል ሰው ትወና ሳለቅስና አንጀቴን ሲበላኝ የማረጋግጠው የፊልም ጥበብ ለውጥ አይደለሁም። ለዚያ ስዕልና ምስል መንበርከክም አይገባንም የምንለው።

ኢየሱስ ምን መልክ አለው? ደም ግባት የሌለው ሆኖልናል ወይስ የአገልጋይና የባርያን መልክ? የውበቱ ነፀብራቅ የሚያበራ ውብ ነው? ወይስ የሕማም ሰው? እኮ የትኛውን ይመስላል። ደቡባዊ አፍሪካውያን ኢየሱስን ጥቁር አድርገው ይስላሉ። ኢትዮጵያውያንም በሚችሉት አቅም የመሰላቸውን ለመሳል ሞክረዋል። በኢየሱስ ላይ ተሳልቆና ፀያፍ ስድብ የጻፈው ሊኦናርዶ ዳቬንቺ ባቅሙ በምሴተ ሐሙስን የነበረውን ሁኔታ ለማስቀመጥ የሞከረበትን ስዕል በየቤታችንና ቤተመቅደሱ ሰቅለናል። ዳቬንቺ በኢየሱስ ላይ የተናገረው ምንድነው? “The Davenci Code” ያነበበ ሰው ከክፉ ሥራው ተባባሪ ሆኖ ዳቬንቺ የሳለውን ስዕል ይቀበል ነበር?




   አንዳንዴ ሀበሻ እያየ ለምን እንደሚታወር፤ እየሰማ ለምን እንደሚደነቁር ግራ ይገባኛል። ይህንን ሰውየ "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" በሚባል ፊልም ላይ ስንመለከተው ኖረናል። በዕድሜአችን በሰል ስንል ግን፥ አንድ ተራ አሜሪካዊ ፊልም ሰሪ መሆኑን አለመገንዘባችን እጅግ ያሳዝናል!! በተለይ ደግሞ በኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ዘንድ ዛሬም ድረስ ሰውየው የኢየሱስ ክርስቶስን ቦታ ወስዶ ስዕሉ በየቤቱ በየቤተ መቅደሱ ሰቅሎ ሲሰገድለት፣ ሲሳለመውና ሲስመው ይገኛል። የተለያየ የሃይማኖት ሥርዓቶች በሚከወንባቸው አድባራት በትልቁ ተስሎ መገኘቱም እጅግ አሳዛኝ ነው። ምክንያቱም ለእግዚአብሔር እንጂ ለፊልም ባለ ሙያ ወይም ለሰዓሊ ሙያ ስገድ የሚል ቃል መጽሐፍ ቅዱስ የለም። ነገር ግን በኢየሱስ ሽፋን የሰው ስዕል እየተመለከ ይገኛል።
    እናም ይኽ አብዛኞቹ ሃይማኖተኞች የሚሰግዱለት ግለሰብ "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" በተሰኘ ፊልም ላይ የኢየሱስ ክርስቶስን ገጸ ባህሪ በመላበስ የተወነ አሜሪካዊ የፊልም አክተር ሲሆን፤ ስሙም ጂም ካቪዘል (Jim caviezel) ይባላል። ወይም ደግሞ በሙሉ መጠሪያው ጃምስ ፓትሪክ ካቪዘል ነው። ሃይማኖቱ ደግሞ የሮማ ካቶሊክ ተከታይ ነው። ተወልዶ ያደገው በአሜሪካ ዋሽንግተን ስቴት ውስጥ ሲሆን ወደ ፊልሙ ኢንዱስትሪ ከመግባቱ አስቀድሞ፥ የተማረባቸውን ትምህርት ቤቶች በመወከል የቅርጫት ኳስ ይጫወት ነበር። በዃላ ግን እግሩ ላይ ጉዳት ስለደረሰበት ሙሉ በሙሉ የቅርጫት ኳስ መጫወቱን ትቶ የፊልም አክተር በመሆን እ.አ.አ በ1991 የመጀመሪያ ፊልሙ ላይ በጥሩ ትወና ተሳትፏል። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" የተሰኘውን ፊልም ጨምሮ ከሠላሳ በሚበልጡ ፊልሞች ላይ ተውኗል (በመሪነት፣በረዳትነት እና..) የተወሰኑ ፊልሞቹን ርዕሳቸውን እና የተሰሩበትን ዓመት እንደሚከተለው መጥቀስ ይቻላል…

My own private idaho – 1991
Diggstown – 1992
Wyatt erap – 1994
Ed – 1996
The rock – 1996
G.j. jane – 1997
The thin red line – 1998
Ride with the devil – 1999
Pay it forward - 2000
Frequency – 2000
Madison - 2000
Angel)
Person of interest- series drama (up to 2011) እና ሌሎችን ፊልሞች ሰርቷል።

   እንግዲህ እውነቱ ይኽ ነው። "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" የተሰኘው ፊልም ዳይሬክተር የሆነው ሚል ጊብሰን፥ ይህን ግለሰብ የኢየሱስ ክርስቶስን ገጸ ባህሪ ተላብሶ እንዲጫወት ያደረገበት ምክንያት፥ ሰውየው ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሆነ ወይም ደግሞ በመልክ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለሚመስለው ሳይሆን፥ አስቀድሞ በሰራቸው ፊልሞች በተለይም "The thin red line" እና "Frequency" በተባሉ ፊልሞች ላይ ባሳየው ጥልቅ የትወና ጥበብ ነው። እውነቱ እንዲህ ሆኖ ሳለ፥ ያገሬ ህዝብ ግን አምላክ አድርጎት ይሰግድለታል። ….እግዚኦ..!!

    በርግጥ በኦርቶዶክስ ሃይማኖት አስተምህሮ መሰረት በየአድባራቱ ብዙ ታሪክ ያዘሉ ቅርጻ ቅርጾች እና ሥዕሎች እንዳሉ ይነገራል.. ይህንንም አስመልክቶ ዲ/ን ዳንኤል ክብረት SUNDAY, APRIL 25, 2010 "የቤተክርስቲያን ሥዕሎች ታሪካዊ ፋይዳ" በሚል ርዕስ በጻፈው ጽሁፉ እንዲህ ብሎ ነበር፦

"…የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የሀገሪቱን (የኢትዮጵያን) ባሕል እና ታሪክ ለትውልድ ካቆየችባቸው መንገዶች አንዱ ሥዕሎቿ ናቸው፡፡ በዚያ ፎቶግራፍ እና ፊልም ባልነበረበት ዘመን የነበረውን ባሕል፣ሥርዓት እና ታሪካዊ ሁነቶች የምናገኘው በቤተ
ክርስቲያን መጻሕፍት እና ግድግዳ ላይ በሚገኙ ሥዕሎች ነው፡፡ ለምሳሌ በሆሎታ ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ግድግዳ ላይ የሚገኙት እና ከ100 ዓመታት በላይ ያስቆጠሩት ሥዕላት ለዚህ ምስክር ናቸው፡፡ ከአዲስአበባ 44 ኪሎሜትር በሆሎታ ከተማ የምትገኘው ይህች ቤተክርስቲያን በዐፄ ምኒሊክ አማካኝነት በ1895 ዓ.ም የተገነባች ሲሆን ታቦቷ የገባችው በዚሁ ዓመት የካቲት 16 ቀን ነው፡፡ ሥዕሉን የሳሉት አለቃ ሐዲስ መሆናቸውን ከመቅደሱ ምሥራቃዊ ግድግዳ ላይ ከሣሉት ሥዕል ላይ «ለዛቲ ሥዕል እንተ ሰዓላ አለቃ ሐዲስ እምቤተ ሌዊ፣ ወዘተምህረ በጎንደር» በሚለው ማስታወሻቸው ይታወቃል፡፡
  ሰዓሊው የቤተክህነቱን እና የቤተመንግሥቱን ወግ እና ሥርዓት በሚገባ የሚያውቁ መሆናቸው በአሣሣላቸው ይታወቃል፡፡ ለምሳሌ ወለተ ሄሮድያዳን ሲሥሏት አለባበሷን እና የፀጉር አቆራረጧን ኢትዮጵያዊ አድርገውታል፡፡ ሹሩባ ተሠርታለች፣ነጭ ሻሽ አሥራለች፣ አሸንክታብ ሠትራ እስክስታውን ታስነካዋለች፡፡ የሄሮድስን የቤተ መንግሥት ሥርዓት ሲስሉት በምኒሊክ ቤተመንግሥት ሥርዓት ነው። ቢላዋው፣የእንጀራው አጣጣል፣ ሙዳ ሥጋው የዘመኑን የግብር ሥርዓት በሚገባ ነው የሚያሳየው፡፡"
   አንባቢ ሆይ ልብ በል፥ እንደ ዳንኤል ክብረት ገለጻ ከሆነ በመጽሐፍ ቅዱስ ውሰጥ የምናውቃት ሄሮድያዳ ኢትዮጵያዊ መስላ ስትሳል ምናልባት ሰዓሊው በነበረበት ዘመን የኢትዮጵያ ሴቶች ምን እንደሚመስሉ ሊገልጽ ይችል ይሆናል። ነገር ግን የመጽሐፍ ቅዱሷ ሄሮድያዳን እና የመጽሐፍ ቅዱሱን ታሪክ ያበላሸዋል። ሲቀጥል ደግሞ የምኒልክን ቤተ መንግሥት ለማሳየት የሄሮድስን ቤተ መንግሥት ማረሳሳት ተገቢ አይሆንም። እንግዲህ በየአድባራቱ ታሪክ አዝለዋል የሚባሉ ሥዕሎች ሁሉም እንደዚህ ዓይነት ከሆኑ መሆናቸው ለማወቅ ፈላስፋ ወይም የነገረ መለኮት ምሁር መሆንን አይጠይቅም። በአንድ ዘመን የተከናወነውን መንፈሳዊ ድርጊት ለማስታወስ ወይም ሃሳባዊ እይታን ለማሳየት ተብሎ የሚሳለው ስዕል የእውነታው ነፀብራቅ እንደሆነ አድርጎ በመሳል ለስዕሉ መስገድ፣ መንበርከክና መማፀን ኢክርስቲያናዊ አምልኮ ነው። ያሳፍራል.። ያሳዝናልም!!
ሲጠቃለል ስዕል ለአንክሮ፣ ለተዘክሮና ለማስተማሪያነት ከሚያገለግል በስተቀር በየቤተ መቅደሱ ተሰቅሎ አይታጠንም፣ አይሰገድለትም። መንበርከክና ከፊት አቁሞ መማፀን የወንጌል አስተምህሮ አይደለም። አንዳንዶች ለጥፋታቸው መሸፈኛ “የኪሩብ ምስል በታቦቱ ላይ ነበር” ይላሉ። የኪሩቡን ምስል ማን አዘዘ? ከምን ይቀረፅ፣ ስንትስ ነበረ? ለማን በተሰጠ ኪዳን ላይ ታዘዘ? በቂ መልስ የላቸውም። የዛሬውን ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ጋር ለማገናኘት መሞከር ሰማይና ምድር ለማጣበቅ እንደመሞከር ይቆጠራል። እግዚአብሔር አእምሮውን ለብዎውን ያሳድርብን።

   

Friday, April 29, 2016

«በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር…»!

የራስ ቅል ኮረብታ በ19ኛው ክ/ዘመን 

የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?» ገላ 3፤1
ኢየሱስ ክርስቶስ በየዓመቱ የሚከበርለትን የመታሰቢያ ትንሣኤ ሊመሠርት እንዳልመጣ እሙን ነው። የከበረ እንጂ የሚከብር፤ የሚፈጸም እንጂ የሚታሰብ ትንሣኤ ትቶልን አልሄደም። እንደዚያማ ከሆነ ከሕግ አገልግሎት ገና አልወጣንም ማለት ነው። ለዚህም ነው ሐዋርያው ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች እንደዚህ ያላቸው።

 «የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?»ብሎ ይጠይቃቸዋል።
 እውነት ነው፣ የኢየሱስ ክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ዕለት፤ ዕለት በዓይናችን ፊት እንደተሰቀለ ሆኖ የሚታይ እንጂ በማስታወሻ መልክ በየዓመቱ «ዬ፤ዬ፤ዬ» እያልን የምናስበው የአንድ ሳምንት አጀንዳ አይደለም። የኦሪት ሕግ በዓላት በተወሰነላቸው ቀናት በየዓመቱ ይከበራሉ። ከዚያን ቀን ውጪ የሕጉ በዓላት በሰው ሕይወት ላይ የተደነገገላቸውን ኃይል ሊፈጽሙ ሥልጣን የላቸውም። አይሁድ ፋሲካቸውን  ከግብጽ ምድር የወጡበትን ዕለት በማሰብ በየዓመቱ ለአንድ ሳምንት በወርኀ ሚያዚያ ያከብራሉ። ያልቦካና እርሾ ያልገባበትን ኅብስት የሚመገቡት በፋሲካ ሳምንት ብቻ ነው። ከዚያ በኋላ የፋሲካው የሕግ ሥልጣን ስለሚያበቃ ወደቀደመው አመጋገብና መደበኛ ኑሮ ይመለሳሉ። የክርስቲያኖች ፋሲካ ግን በአማኞች ሕይወት ላይ ያለምንም የብልጫ ቀናት ልዩነት በእምነት የሚፈጸምና ዓመቱን ሙሉ ኃይልና ሥልጣን ያለው አገልግሎት ነው። እንደገላትያ ክርስቲያኖች ወደ ሕግ ሥርዓት ተመልሰን በዓመት የምናስበውና የምንዘክረው እንዲሁም ከጥሉላት በስተቀር ሌላውን ገድፈንና የገደፍነውን መልሰን የምንረከብበት፣ እስከሆድ ድረስ የምግብ ዓይነት ነጻነታችንን የምናስከብርበት ዘመቻ ምግብ ፋሲካ አልተሰጠንም።  ፋሲካችን «እንኳን አደረሰህና እንኳን አደረሰሽ» በመባባል ያልደረስንበት የድነት ቀን ያለ ይመስል የሚታወስ የአንድ ሳምንት የስጦታ ካርድ መለዋወጫ በዓል በላይ የላቀ ሰማያዊ ነው።
ሐዋርያው ጳውሎስ እንዳለው: «በመንፈስ ብትመሩ ግን ከሕግ በታች አይደላችሁም። የሥጋ ሥራም የተገለጠ ነው እርሱም ዝሙት፥ ርኵሰት፥ መዳራት፥ ጣዖትን ማምለክ፥ ምዋርት፥ ጥል፥ ክርክር፥ ቅንዓት፥ ቁጣ፥ አድመኛነት፥ መለያየት፥ መናፍቅነት፤ ምቀኝነት፥ መግደል፥ ስካር፥ ዘፋኝነት፥ ይህንም የሚመስል ነው። አስቀድሜም እንዳልሁ፥ እንደዚህ ያሉትን የሚያደርጉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም"

«ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአል» ስንል እነዚህን የሥጋ ሥራዎች ሁሉ ከሕይወታችን አስወግደን በመንፈሱ ሥልጣን እየተመራን ነው ማለታችን ነው። እነዚህን ደግሞ የምናስወግደው በየዓመቱ በሚከበር ፋሲካ ሳይሆን ዕለት፤ ዕለት የኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ በፊታችን ተስሎ ሲገኝ ብቻ ነው። አለበለዚያ ከገላትያ ሰዎች የበዓል አከባበር አስተሳሰብ ገና አልወጣንም ማለት ነው። የገላትያ ሰዎች «አባ፤ አባት» ብሎ ለመጣራት የሚያበቃ የተሰጣቸውን የልጅነት ሥልጣን ትተው በባርነት ቀንበር ሥር ወደምትጥል ወደወር፤ ቀንና ዘመንን የማክበር ቁልቁለት ወርደው በተገኙ ጊዜ የተናገራቸው ቃል በዚህ ዘመንም ቦታ አግኝቶ መታየቱ ምን ዓይነት አዚም ቢወድቅብን የሚያሰኝ ነው።

«ቀንንና ወርን ዘመንንም ዓመትንም በጥንቃቄ ትጠብቃላችሁ። ምናልባት በከንቱ ለእናንተ ደክሜአለሁ ብዬ እፈራችኋለሁ» ገላ 4፤ 1-11

ክርስቲያኖች እግዚአብሔርን ፍለጋ የት መሄድ ይገባናል? የእግዚአብሔር መገኛው የት ይሆን? ከምድራዊት ቤተ መቅደስ? ከገሪዛን፤ ከጌባል? ወይስ በኢየሩሳሌም?
 አንዳንዶች ኢየሩሳሌምን የተሳለመ የ40 ቀን ሕጻን ይሆናል ይላሉ። የቆረበ ደግሞ የበለጠ የ40 ቀን ሕጻን እንደሚሆንም ይሰበካል። ከተሳለመ የ40 ቀን ሕጻን በመሆንና ከቆረበ የ40 ቀን ሕጻን በመሆን መካከል ያለው ልዩነት አይገባኝም።  ኢትዮጵያ በመቁረብና ኢየሩሳሌም ከጎልጎታ ሄዶ በመቁረብ መካከልስ ያለው ልዩነት ምንድነው?  ሰዎች ክርስትናን እንደሕግ ሥርዓት ማክበር ሲጀምሩ የሕግ የብልጫ ልዩነት ክርስትናውን መውረስ ይጀምረዋል። ኢየሩሳሌም ሄዶ በመሳለም ወይም በመቁረብና ኢትዮጵያ በመቁረብ መካከል ልዩነት የሚመጣውም ለዚህ ነው። መቱ ባለች ቤተ ክርስቲያን ጓሮ በመቀበርና ደብረ ሊባኖስ በመቀበር መካከል ያለው የመብት ልዩነትም ውጤቱ የሕግ ተፋልሶ ክርስትናውን በመዋጡ የመጣ ነው። የወንጌል እውነት ግን ያንን እንድል አይነግረንም። እግዚአብሔር መንፈስ እንጂ በቦታና በሥፍራ የሚወሰን አምላክ አይደለም። ስለዚህም እግዚአብሔር በመንፈስ ይመለካል፤ በእምነትም፤ የመንፈስ  የሆነ ሥራ በሕይወታችን ላይ ሊገለጥ ይገባዋል። ያኔ ዲላ ሚካኤል ተቀበርን፤ ደብረ ሊባኖስ፤ ደሴ ቆረብን ሞቻ በማንነታችን ላይ ለውጥ የለውም። በሕይወቱ የክርስትና ማንነት የሌለው ሰው ደብረ ሊባኖስ ጓሮ መቀበሩ በፍርድ ወንበር ፊት ለውጥ አያመጣለትም። ሰው ሲሞት ይዞት የሚሄደው በምድር የነበረውን ሥራ እንጂ በሰማይ የሚፈጸም የክርክር ዳኝነት የለም። «እስመ አንተ ትፈድዮ ለኩሉ በከመ ምግባሩ» እንዳለ ዳዊት በመዝሙር 62፤12
ስለዚህ እግዚአብሔር በመንፈስ ይመለካል፤ በመንፈስ ይሰገድለታል፤ በመንፈስ ይታመናል እንጂ በቦታና በሥፍራ አይደለም። እሱን ይይዝ ዘንድ የሚችል ምድራዊ መቅደስ የለንም። «ለእኔ ምን ዓይነት ቤት ትሠራላችሁ? ይላል ጌታ» የሐዋ 7፤50

«ወትቤሎ፤ አበዊነሰ በዝንቱ ደብር ሰገዱ፤ ወአንትሙሰ ትብሉ ከመ በኢየሩሳሌም መካን ውእቱ ኀበ ይሰግዱ። ወይቤላ ኢየሱስ፤ እመንኒ ብእሲቶ ከመ ትመጽእ ሰዓት አመ ኢበዝንቱ ደብር፤ ወኢበኢየሩሳሌም ዘይሰግዱ ለአብ፤ አንትሙሰ ትሰግዱ ለዘኢታአምሩ፤ ወንሕንሰ ንሰግድ ለዘናአምር፤ እስመ መድኃኒት እምነ አይሁድ ውእቱ። ወባሕቱ ትመጽእ ሰዓት፤ ወይእዜ ይእቲ፤ እመ እለ በርቱዕ በአማን ሰጋድያን፤ ይሰግዱ ለአብ በመንፈስ ወበጽድቅ እስመ አብኒ ዘከመዝ የኀሥሥ እለ ይሰግዱ ሎቱ። እስመ እግዚአብሔር መንፈስ ውእቱ፤ እለሂ ይሰግዱ ሎቱ በመንፈስ ወበጽድቅ ሀለዎሙ ይሰግዱ ሎቱ»

ትርጉም፤ 
«አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰገዱ፤ እናንተም፦ ሰው ሊሰግድበት የሚገባው ስፍራ በኢየሩሳሌም ነው ትላላችሁ አለችው። ኢየሱስም እንዲህ አላት፦ አንቺ ሴት፥ እመኚኝ፥ በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም ለአብ የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል። እናንተስ ለማታውቁት ትሰግዳላችሁ፤ እኛ መዳን ከአይሁድ ነውና ለምናውቀው እንሰግዳለን። ነገር ግን በእውነት የሚሰግዱ ለአብ በመንፈስና በእውነት የሚሰግዱበት ጊዜ ይመጣል አሁንም ሆኖአል፤ አብ ሊሰግዱለት እንደ እነዚህ ያሉትን ይሻልና፤ እግዚአብሔር መንፈስ ነው፥ የሚሰግዱለትም በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል» ዮሐ 4፤20-24

የኢየሱስ ስቅለት የሚታሰበው በመንፈስ መሆኑን ለማመልከት ጳውሎስ ለገላትያ  ሰዎች እንዲህ አላቸው። ኢየሱስ የተሰቀለው ኢየሩሳሌም እንጂ ገላትያ አለመሆኑን እያወቀ ለገላትያ ሰዎች ግን «በዓይናችሁ ፊት እንደተሰቀለ ሆኖ ተስሎ ነበር» እያለ ይወቅሳቸዋል። ምክንያቱም ስቅለቱ በአማኞች ፊት የሚታየው በየዓመቱ ለሁለት ወር በሚደረግ ጾምና ለአንድ ሳምንት በሚታሰብ  የሕማማት ሳምንት ሳይሆን በየትኛውም ቦታ ብንሆን ያለምንም ዕረፍት በዘመናችን ሙሉ ነውና።
 የሕማማቱ ሳምንት ካለፈ በኋላስ? በዓለ ፍስሐ ወሀሴት፤ በዓለ ድግስ ወግብዣ፤ በዓለ ምግብ ወመጠጥ ነው? የኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ ለሁለት ወር ከምግብ የመከልከል ማዕቀብና ለሁለት ወር ተከልክለው የነበሩ ምግቦች በተራቸው ድል የሚቀዳጁበት በዓል አይደለም። ዓመቱን ሙሉ በፊታችን እንደተሰቀለ ሆኖ የምናስብበት፤ በመንፈስና በእውነት የምንሰግድለት ቋሚ የሕይወታችን መርህ እንጂ በአርብ ቀን የወይራ ጥብጣብ የሚያበቃ ዓመታዊ ልምምድ ካደረግነው ከገላትያ ሰዎች በምን እንሻላለን? 

ለዚህም ነው፤ ብዙ ክርስቲያኖች ከነገሠባቸው የሥጋ ሥራ ሳይላቀቁ ፋሲካን እያከበሩ ዘመናቸውን ሁሉ የሚፈጽሙት። ጋብ ብሎ የነበረው የሥጋ ሥራ ከፋሲካ በዓል በኋላ ይደራል። ዝሙቱ፤ ውሸቱ፤ ስርቆቱ፤ ማጭበርበሩ፤ ሃሜትና ነቀፋው ያለማንነት ለውጥ እንደነበረው ይቀጥላል። ዓመቱን ሙሉ ያጠራቅሙትን ኃጢአት የፋሲካ ጾም ሲመጣ ለማራገፍ እንደሚቻልበት አመቺ ጊዜ ጠብቀው ብዙ ሰዎች ጥሬና ቆሎ ቋጥረው በየዋሻውና ፍርክታው ልክ እንደሽኮኮ ይመሽጋሉ። ሀብት ያላቸው ኢየሩሳሌም ሄደው ለመሳምና ለመቁረብ ገንዘባቸውን በየዓመቱ ይከሰክሳሉ። የክፉ ቃል ምንጭ የሆነውን አንደበቱን ሳይዘጋ ሥጋ መሸጫ ቤቱን የሚዘጋ የት የለሌ ነው። ከተማውን ሁሉ የወረረው የሚዛን መሥፈሪያ በፈሪሃ እግዚአብሔርና ያለማጭበርበር ሳይሰሩበት ጾም የሚሉትን ፈሊጥ የሚጠብቁት ለምንድነው?   አቤት! የዘንድሮ ሚዛን የሚባለው የድሮና የዚህ ዘመን ሚዛን ልኬታ የተለየ ሆኖ ይሆን?

የሕዝብና የመንግሥት ሀብት የሚዘርፉ የሕግ ፋሲከኞች ቁጥራቸው ብዙ ነው። የቤተ ክርስቲያን ደወል ሲደወል የሚከንፉ ነገር ግን የቤታቸውን የፍቅርና የሰላም ደወል የተነጠቁ ቤቱ ይቁጥራቸው። ሠራተኞቻቸውን የሚያስጨንቁ፤ በፍትህ አደባባይ ፍርድን የሚጨፈልቁ፤ በመማለጃም የእንባን ዋንጫ የሚጎነጩ የሁለት ወር ጸዋሚዎችና ተሃ ራሚዎች አያሌ ናቸው። የልምድ ክርስቲያኖች የሕይወት ምስክርነት በሥራቸው ሊታይባቸው አይችልም።  ስለዚህም ይመስለኛል፤ በክርስቲያን ቁጥር ብዙ ሆነን በበረከት መትረፍረፍ አቅቶን እድሜ ልካችንን ከእምነት የለሾች ምጽዋት ጠባቂ ሆነን የቀረነው። እንደእምነት የለሾቹ፤ እምነት የለሾች ብንሆን ያለእምነት ስለሚፈረድብን በሥጋ ረሃብ ባልተገፋንም ነበር። እግዚአብሔርን እየጠራን፤ እንደፈቃዱ ለመኖር ባለመቻላችን በራሳችን የእምነት ጉድለት በሥጋችን እንቀጣለን።  ብዙ ባወቅህ ቁጥር ብዙ ሥራ ይጠበቅብሃል። ካልሰራኸው ግን ባታውቅ ቢቀርብህ ይሻልህ ነበር። ስለዚህ ማወቅህ ለመዳንህ ዋስትና የሆነውን ነገር ካላትርፈረፈልህ ክርስትናህ ምንድነው? ኢየሱስ በባዶ ተስፋ አልተወንም። እኛ ግን አስሮ በያዘን በገላትያውያን አዚም ፈዘን ሳለ ስለገላትያ አዚም እናስተምራለን።

  የኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለትና ትንሣኤ በየዓመቱ እየዞረ የሚመጣ በዓል ሳይሆን ዕለት፤ ዕለት በፊታችን ተስሎ የሚታየን የሕይወታችን አካል ነው መሆን ያለበት። በቦታ፤ በሥፍራና በጉዞ ብዛት የሚከበር ሳይሆን በእውነትና በመንፈስ እንድናመልከው የተደረገልን የማዳን ሥራ ነው። በአዲስ ሰውነት ለውጥ እንጂ በሕግ ሥነ ሥርዓት ልናሳልፈው አይገባም።  ሰላምና እርጋታ በውስጡ መኖሩን መንፈስ ቅዱስ የሚመሰክርለት አማኝ ሀገር ለሀገር፤ ተራራ ለተራራ ትንሣኤውን ፍለጋ ሲዞር አይገኝም። ምክንያቱም፤ ሁል ጊዜ በዓይኑ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ይታየዋልና»! ከተያዝንበት አዚም ተላቀን በልባችን የተሳለውን ትንሣኤ፤ በኑሮአችን ፍሬ የሚታይበት እንዲሆን እግዚአብሔር ይርዳን! አሜን።

Friday, April 8, 2016

ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም!!!


ማቴ 7፣21
በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ፥ ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም። እንዳለው ጌታችና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌላውያን ነን ባዮቹ የእግዚአብሔርን ቃል እንዲሰደብ እያደረጉ. "ጌታ ሆይ፣ ጌታ በማለታቸው የዳኑ ቢመስላቸውም የተጠበቁት ለፍርድ ነው። በነሱም የከፋ አድራጎት ሰዎች ወደተገለጠው እውነት እንዳይደርሱ በማድረግ ላይ ተጠምደዋል። በተለይም በአፍሪካ ክፍለ አህጉር ክርስቲያን ነን በሙሉ ፓስተሮች እየተፈፀመ ያለው ዘግናኝ ድርጊትና በቤታችን በኢትዮጵያ ላይ መርገም የሚያመጣ ፀረ ክርስትና ሁኔታ እየተፈፀመ ነው። ሌብነት፣ ዝሙት፣ የእግዚአብሔርን ቃል ማጣመም፣ መዋሸት፣ አድማና ክፍፍል ዋነኛ መለያ ሆኗል።  ከዚህ በታች የቀረበው ጽሁፍ (ከምስባከ ጳውሎስ) የፌስቡክ ገጽ የተወሰደ ሲሆን ነገሩ ከዚህ በፊት እየታየ ከቆየው አሳፋሪ ተግባራት አንዱ ክፍል ነው።

ነገሩ መታወቅ የጀመረው እንዲህ ነው፡፡ አንድ ወዳጃችን በራሱ ምክንያት “ፓስተር” ተዘራ ያሬድ ወደሚያስተዳድሯት ቤ/ክ ይሄዳል፡፡ በዕለቱ የአምልኮ ፕሮግራም እየተካሄደ ነበር፡፡ መባ እና ዐሥራት ተሰበሰበ፤ ከዚያ በኋላ ማስታወቂያ ተነገረ፡፡ ማስታወቂያው ይህን መሳይ ነው፤ “ፓስተራችን የተዘራ ያሬድ ዳግመኛ የተወለደበትን ዕለት በየዓመቱ እንደምናከብር ይታወቃል፡፡ ለዚህም ዓመት ክብረ በዓል ብዙዎቻችሁ ገንዘብ ማዋጣታችሁ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን ገንዘብ መስጠት እየፈለጋችሁ ሳትሰጡ ለገንዘብ ማሰባሰቡ የተመደበው ጊዜ ያለፈባችሁ ሰዎች መቸገራችሁን ነግራችሁናል፡፡ በመሆኑም ፓስተራችንን ተጨማሪ ዕድል እንዲሰጣችሁ ለምነነው፣ አንድ ዕድል ብቻ - ይኸውም ዛሬን ሰጥቶናል፡፡ ስለዚህ ገንዘብ መስጠት የምትፈልጉ ሰዎች ዛሬ ካልሰጣችሁ በቀር ሌላ ዕድል አይኖራችሁም፡፡ ምናልባት የተለየ ፈቃድ በፓስተራችን ካልተሰጠ በቀር …”፡፡

ከዚያ ደግሞ፣ ሌሎችም መረጃዎች በየጊዜው ብቅ ብቅ ማለት ጀመሩ፡፡ በእርግጥ ፓስተሩ ለልደታቸው ራቭ4 መኪና ስጦታ የተሰጣቸው በመሆኑ፣ በልደት ማክበር ስም የሚገኘው ጥቅማጥቅም ይጠፋቸዋል ተብሎ አይታሰብም፡፡

በቅርቡ ለማጣራት እንደ ተሞከረው ደግሞ፣ መዳናቸውን እንኳን ከሰውዬው መዳን ጋር የሚያስተሳስሩ አባላት መኖራቸው ነው፡፡ ለልደቱ ገንዘብ የሚያዋጡት መዳናቸውን እያሰቡ ነው!

እኚህ “ፓስተር” “ሬማና ሎጎስ” የተሰኘ መጽሐፍ ሲኖራቸው፣ ለጉባኤያቸው እንደተነናገሩት ከሆነ፣ “ማንም ሰው መጽሐፋቸውን አንብቦ መጠቀም የሚችል ሲሆን ከዚያ ባሻገር ግን መጽሐፋቸውን የመተቸትም ሆነ የመቃወም መብት እንደሌለው፣ ለዚህም ከፌዴራል መንግሥት ፈቃድ እንደ ተሰጣቸው” ይናገራሉ፡፡ “ፓስተር” ተዘራ፣ ከአባላቶቻቸው መካከል በርካታ የደኅንነት አባላት መኖራቸውንና የሚፈልጉትንም ነገር በቀላሉ ማስፈጸም እንደሚችሉ በድፍረት በመናገር ይታወቃሉ፡፡

እንዲህ ዐይነት አገላለጾች “ፓስተር” ተዘራ ያሬድ ስለ ራሳቸው ያላቸውን ግምት የት ድረስ የተወጠረ እንደሆነ ያስረዱናል፡፡

Saturday, February 27, 2016

የዛሬ ታቦትና ጽላት ከሙሴ ዘመን ጋር በጭራሽ አይገናኝም!

አንዳንዶች ከአበው የተረከብነው አስተምሕሮና ሕግ በማለት ሁሉን ነገር እንደወረደ እንድንቀበለው ይፈልጋሉ። አዎ፣ አበው ብዙ ነገር አስተላልፈውልናል። ነገር ግን የተላለፈልን ነገር ሁሉ ጠቃሚ ነው ማለት አይደለም። ለእግዚአብሔር ይቀርብ የነበረ የቤተመቅደሱ መስዋእት በመቅደሱ ሚዛን ይለካ እንደነበረው ሁሉ የተላለፈልን የአበው አስተምሕሮ ሁሉ በእግዚአብሔር ቃል ሚዛን መሰፈር አለበት። ምክንያቱም ከኛ በፊት ያለፉ ሁሉ በእድሜ አበው ቢሆኑም በአስተምሕሮ ግን በአበው ከለላ የስሕተት አስተምህሮ በስማቸው ሊገባ ይችላልና ነው። ስለሆነም በጅምላ አባቶቻችን ማለት ብቻውን ከስሕተት አያድንም። የአባቶች ትምሕርት ከመጻሕፍት ውጪ እንዳይኾኑ መጠንቀቅ ያስፈልጋል። በአንድ ወቅት አይሁዳውያን የኢየሱስ ክርስቶስን ትምሕርት እንዲኽ እንደዛሬው የተቃወሙት እኛስ ከአባታችን ከአብርሃም ነን እያሉ ነበር። አብርሃም አባታቸው መሆኑን ቢናገሩም በአብርሃም ስም ከመነገድ በስተቀር የአብርሃምን ስራ የማይከተሉ ነበሩ ተግባራቸው ይመሰክር ነበር።

ዮሐንስ 8፣39
መልሰውም፦ አባታችንስ አብርሃም ነው፡ አሉት። ኢየሱስም፦ የአብርሃም ልጆች ብትሆኑ የአብርሃምን ሥራ ባደረጋችሁ ነበር፣ ብሏቸዋል።
ዛሬም ከሙሴ የተቀበልነው የታቦት ሕግ አለን የሚሉ አሉ። ነገር ግን ለሙሴ የተሰጠውንና ያደረገውን ሥራ አያደርጉም። ግን በሙሴ ስም ይነግዳሉ፣ ያታልላሉ፣ ይዋሻሉ። ሙሴን አውቀውትማ ቢኾን ኖሮ ሙሴ ያደረገውን ባደረጉ ነበር። ሙሴ የታዘዘውና ያደረገውን ይኽንን ነበርና።

ዘጸአት 25፣10
ከግራር እንጨትም ታቦትን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፥ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን።
ሙሴ ለጽላቱ ማኅደር ይሆን ዘንድ እንዲሰራ የታዘዘውና የሰራውም ታቦት ልኩ ይኼው የተጠቀሰው ሆኖ ቤተመቅደሱ ፈርሶ አገልግሎቱ እስከተቋረጠበት እስከ 70 ዓ/ም ድረስ ለ 2000 ዘመን ይህ ልኬታ ተሻሽሎና ተቀይሮ ስለመገኘቱ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ላይ አልተጻፈም። ነገር ግን ዛሬ የጽላቱ ማደሪያ የሆነው ታቦት አለን የሚሉ ወገኖች በሙሴ ሽፋን የሚሰሩት ታቦት ርዝመቱም፣ ቁመቱም፣ ወርዱም እንደጠራቢው ችሎታና እንደአስጠራቢው ፍላጎት እንጂ የተወሰነ መጠን በሌለው ልቅ ፍላጎት ሲጠቀሙ ይታያሉ። የእግዚአብሔርን የመሥፈሪያ ሚዛን ሊጠቀሙ ይቅርና ለሚሰሩት የስሕተት ሥራ እንኳን አንድ ወጥ የሕግ ሚዛን ለራሳቸው የላቸውም። ጠራቢዎቹም የእግዚአብሔር መንፈስ እንደሞላባቸው በሙሴ እንደተመረጡት አልያብና ባስልኤል ሳይሆን ቤተክርስቲያን አነውራ የምትጠራቸው፣ ቆብና ቀሚስ የጣሉ መነኮሳት፣ ያፈረሱ ቄሶችና ደጋሚ ደብተራዎች፣ የሚያስገኘውን ገቢ የቀመሱ አወዳሾች መሆናቸው የአደባባይ ምስጢር ነው።   በመኖሪያ ቤቱ የእንጨት ማሽን ተክሎ፣ ከጣውላ አቅራቢዎች ምንነቱ ያልታወቀ ጥርብ እየገዛ በሚቀርቡለት የፈላጊዎች ትእዛዝ መሠረት ጽላት የሚባለውን የዘመኑን የሰዎች መሻት እየቀረጸ የሚያከፋፍል ሰው የዚኽ ጽሑፍ አቅራቢ ያውቃል። ከሥራዎቹም የተወሰነውን ለማየት ችሏል። ከታች በገብርኤል ስም ከጣውላው የተቀረጸ ምስል ለአብነት ይመለከቷል።   እግዚአብሔር በሚሰራውና ጥንት ባደረገው ነገር ሁሉ ከመረጣቸው ሰዎች ማንነት ጀምሮ የተለዩና በሚሰሩትም ሥራ ጥንቃቄና ትእዛዙን የጠበቀ ስለመሆኑ ለአፍታ የሚዘነጋ ጉዳይ አይደለም።  ዛሬስ? በ 0% የቀደመ ሥርዓት ላይ ሆነው በሙሴ ሕግ ሥር የመደበቅ ዘመን አብቅቷል። በትውልዱም የተሸፈነው መገለጡ አይቀርም። በስተመጨረሻም የእግዚአብሔርም ትእግስት ሲሞላ ውርደት መከተሉ ሳይታለም የተፈታ ነው። በዋጋ መሸጪያ ተመን ገበያ ወጥቶለት በገንዘብ የሚገዛ ጽላት በጭራሽ ሊኖር አይችልም።
እንደእውነቱ ከሆነ በዚህ ዘመን በአባቶች እያሳበቡ የእግዚአብሔርን ቃል በመቀየር በትውልድ ላይ ለመጫን መሞከር ማብቃት አለበት።
 ሙሴ የዕንቁውን ጽላት አሮን ባሰራው የጥጃው ጣኦት ላይ ከሰበረ በኋላ አስመስለኽ ቅረፅና አምጣ ተብሎ በእግዚአብሔር ሲነገረው ለጽላቱ ማደሪያ ተብሎ አስቀድሞ የተሰጠው የታቦቱ ርዝመት፣ ቁመትና ወርድ ላይ የተሰጠ የለውጥ ትእዛዝ አልነበረም። ምክንያቱም የተሰበረው ጽላቱ እንጂ ታቦቱ አይደለምና።  ስለዚህ "ቀር ከመ ቀዳሚ"  የተባለው ጽላቱን እንጂ ማደሪያውን ታቦት ካልሆነ ሙሴ ያላሻሻለውን ታቦት ዛሬ ያሻሻሉት ከየት ባገኙት አምላካዊ ትእዛዝ ነው?  ውሸታቸውን ለማጽደቅ የፈረደበት የሙሴን ስም አቅርበው ሊሞግቱን ይዳዳሉ።
ስለማኅደሩ መሻሻል የተነገረ ካልነበረ እነዚህኞቹ በራሳችን ሥልጣን አሻሽለናል ይበሉን እንጂ ሙሴን ለሐሰት ምስክርነት አይጥሩብን።
ከዚያም ሌላ ሙሴ የፊተኞቹን ጽላቶች አስመስሎ ከቀረጸ በኋላ ይዞ የሄደው ወደሲና ተራራ ነው። በዚያም እግዚአብሔር በጣቶቹ 10ቱን ትእዛዛት ጻፈባቸው እንጂ ሙሴ በጭራሽ አልጻፈም።

ዘዳግም 10፣3-4
ከግራርም እንጨት ታቦትን ሠራሁ፥ እንደ ፊተኞችም ሁለት የድንጋይ ጽላቶች ጠረብሁ፤ ሁለቱንም ጽላቶች በእጄ ይዤ ወደ ተራራው ወጣሁ።
ስብሰባ ተደርጎ በነበረበትም ቀን እግዚአብሔር በተራራው ላይ በእሳት ውስጥ ሆኖ የተናገራችሁን አሠርቱን ቃላት ቀድሞ ተጽፈው እንደ ነበረ በጽላቶቹ ላይ ጻፈ፤ እግዚአብሔርም እነርሱን ለእኔ ሰጠኝ።
ይለናል መጽሐፍ ቅዱሳችን።

እዚህ ላይ እንደምናነበው ጽላቶቹ ላይ የጻፈባቸው እግዚአብሔር ራሱ ሆኖ ሳለ ሙሴ እንደጻፈ አድርጎ በሙሴ ላይ መዋሸት ለምን አስፈለገ?  አስመስለኽ ቅረጽና አምጣ መባሉን ልክ እራስኽ እየጻፍክባቸው አባዛ የተባለ ማስመሰል በእግዚአብሔር ላይ መዋሸት አይደለምን? ያልተባለውን እንደተባለ፣ ያልተነገረውን እንደተነገረ አድርጎ በማቅረብ የራስኽንም ስሕተት እንደማጽደቂያ መሳሪያ አድርጎ መጠቀም የከፋ ክሕደትና ሕዝቡን በስሕተት መንገድ መንዳት ነው።  ሙሴን ያላደረገው ነገር አድርገኻል ማለት መሳደብ ነው፣ እግዚአብሔርንም ለሙሴ አንተው ጻፍባቸው ያላለውን እንዳለ ማስመሰልስ ዋሾ ማድረግ አይደለምን?
 ጽላቶቹ ላይ የተጻፈባቸውና ሙሴ የተቀበላቸው 10ቱን ትእዛዛት ሆኖ ሳለ የሰው ስም ወይም የሰው ምስል ያለበት አድርጎ በማቅረብ በዚህ ዘመን እኛ የምንፈልገውን የልባችን ፈቃድ ለማሳካት ማጭበርበርስ ለምን ይሆን? በየትኛውስ ቃል እንደገፋለን? የምናስደስተው ሰውን ወይስ እግዚአብሔርን? መቼም ቢሆን እግዚአብሔር ያላለውን ብለኻል በሚሉ ዋሾዎች ተደስቶ አያውቅም። ሊደሰትም አይችልም። ከራሱ አንቅቶ የሚናገረው የሐሰት አባት የሆነው ዲያብሎስ ብቻ ነው።
እግዚአብሔር የሰጠውን ሕግ የሚያጸናውና የሚሽረው ራሱ እግዚአብሔር ሆኖ ሳለ ሰው እንዴት የኪዳኑን ሕግ ራሱ ለራሱ ስሜት ያሻሽላል?
የሙሴን ታቦተ ሕግ ተከትለናል ማለት እግዚአብሔር ያላለውን በራስ ፍላጎት እንደሚመች አድርጎ ማቅረብ ነው እንዴ?
ሌላው መነሳት ያለበት ነገር፣ ዛሬ የኪዳኑን ጽላት እንጠቀማለን የሚሉ ሰዎች የኦሪቱ የጽላት ሕግ፣ ቃል ኪዳን የተሰጠው ለማነው? የሚለው ነው።

 በማያከራክር መልኩ የቃልኪዳኑ ታቦት ሕግ የተሰጠው ለእስራኤል ዘሥጋ ብቻ ነው። ይኽ ሆኖ ሳለ እናንተን ያ የኪዳን የሕግ ውል የጨመራችሁ በየትኛው የብሉይ ኪዳን ቃል ላይ ነው?  እግዚአብሔር ውሉን በሙሴ ፀሐፊዎች አማካይነት በአራቱ ብሔረ ኦሪት ጽፎ ሰጥቷቸዋል። የእናንተስ ውል በነማን በኩል፣ መቼና የት ቃል ተገባላችሁ? ብለን እንጠይቃቸዋለን።
ምክንያቱም እስራኤላውያን አፋቸውን ሞልተው እንዲህ ሲሉን እናገኛቸዋለን።
ዘዳግም 5 ፣2
አምላካችን እግዚአብሔር በኮሬብ ከእኛ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ።

ያ ቃልኪዳን ከፈረሰና የመስዋእቱ አገልግሎት ከተቋረጠ 2ሺህ ዘመን አልፎታል። ከዚያ በኋላ ከእስራኤላውያን ውጪ እግዚአብሔር የታቦት ቃልኪዳን የገባላቸው ሌላ ሕዝቦች የሉም። ኧረ በጭራሽ አይኖርምም። ምክንያቱም ያ ውል የተገባው ለተወሰነ ሕዝብ ብቻ ስለሆነ ሁሉን ያካተተ አዲስ ውል ያስፈልግ ስለነበር ለተወሰነ ሕዝብ በድጋሜ ቃል የሚገባበት ምክንያት የለም።
ሮሜ 9፣4
እነርሱ እስራኤላውያን ናቸውና፥ ልጅነትና ክብር ኪዳንም የሕግም መሰጠት የመቅደስም ሥርዓት የተስፋውም ቃላት ለእነርሱ ናቸውና"

ነገር ግን ሕዝቤ ያልተባለን ሕዝቤ ለማለት አህዛብ ሁሉ ወደመጠራቱ እንዲገቡ አዲስ ቃል ኪዳን አስፈልጓል።
ሮሜ 9፣26 እናንተ ሕዝቤ አይደላችሁም በተባለላቸውም ስፍራ በዚያ የሕያው እግዚአብሔር ልጆች ተብለው ይጠራሉ፥ ይላል።

በዚህም ምክንያት ለአንድ ሕዝብ ብቻ ተሰጥቶ የነበረው ሕግ ቀርቶ ሁሉን የሚመለከት ሕግ እንዲመጣ ማስፈለጉን በአዲስ ኪዳን የኦሪቱ የመስዋእት አገልግሎት ከእንግዲህ አይታሰብም ተብሎ ትንቢት ተነግሯል።

ኤርምያስ 31፣31
እነሆ፥ ከእስራኤል ቤትና ከይሁዳ ቤት ጋር አዲስ ቃል ኪዳን የምገባበት ወራት ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር።

 ለምን አዲስ ቃልኪዳን መግባት አስፈለገው? ምክንያቱም፣

ኤርምያስ 31፣32
ከግብጽ አገር አወጣቸው ዘንድ እጃቸውን በያዝሁበት ቀን ከአባቶቻቸው ጋር እንደ ገባሁት ያለ ቃል ኪዳን አይደለም፤ እነርሱ በኪዳኔ አልጸኑምና፥ እኔም ቸል አልኋቸው፥ ይላል እግዚአብሔር።

ስለዚህ በሰማያዊው መስዋእት በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተሻለ ኪዳን ስለተገባልን አሁን ልንናገርበት ጊዜው ባልሆነ የዚህ ምድር ሥርዓት አይደለንም። ጳውሎስ ድሮ ነበረ፣ አሁን ግን የለም ይለናል።

ዕብራውያን 9፣5
በላይዋም ማስተስሪያውን የሚጋርዱ የክብር ኪሩቤል ነበሩ፤ ስለ እነዚህም ስለ እያንዳንዳቸው ልንናገር አሁን አንችልም።
ምክንያቱም፣
ዕብራውያን 7፣22
እንዲሁ ኢየሱስ ለሚሻል ኪዳን ዋስ ሆኖአል።
ስለዚህ አብርሃም አባታችን፣ ሙሴ መሪያችን፣ እግዚአብሔር አምላካችን በማለት ለስሕተት መሸፈኛ አድርጎ ማቅረብ አያድነንም። አብርሃም አባታችን፣ እግዚአብሔር አምላካችን ይሉ የነበረ፣ ነገር ግን የሚነገራቸውን ቃል እኛ ከሁሉ ቀድመን ያወቅን ነን በሚል ትምክህት ለመቀበል ያልፈለጉትን ሊቃውንተ አይሁድን እንዲህ ብሏቸዋል።

ዮሐንስ 8፣47
ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል፤ እናንተ ከእግዚአብሔር አይደላችሁምና ስለዚህ አትሰሙም።

ስለዚህ በዚህ ዘመንም የቀደመችው ሃይማኖት በማለት ራስን በመካብ ብልጫ አይገኝም። ከአይሁድ የቀደመ ሃይማኖት የለምና። ነገር ቀድሞ በመገኘት አብርሃም አባታችን፣ ሙሴ ፈለጋችን ነው፣ ማለት ከስህተት አያርቅም። ምክንያቱም አብርሃምና ሙሴ የተቀበሉትንና የፈፀሙትን ሕገ እግዚአብሔር ሳይሸራርፉና ሳያሻሽሉ በማድረግ እንጂ የነሱ ተከታይ መሆን የሚቻለው በስማቸው በመነገድ ግን በሕጉ በሌሉበት ሁኔታ የሙሴ ተከታዮች በማለት ራስን ካልሆነ ማንንም ማታለል አይቻልም።
ስለሆነም የዛሬ ታቦትና ጽላት ከሙሴ ዘመን ጋር በጭራሽ አይገናኝም። እንዲቀየርና እንዲሻሻል ከእግዚአብሔር የተሰጠ ሕግ አልነበረም። ፊተኛውና ኋለኛው ጸሐፊ ራሱ እግዚአብሔር፣ ጽሕፈቱም ሕግጋቶች ነበሩ። የተጻፈውም በሲና ተራራ ነጎድጓዳማ ድምጽ መካከል እንጂ በጥቃቅንና አነስተኛ የእንጨት መላጊያ ውስጥ አልፎ የዚህ ምድር በሆነች እጅ ብልሃት አይደለም።
የእጅ ብልሃት ይኽ ነው።

Tuesday, February 23, 2016

ቃል ኪዳን!


“ከመረጥኹት ጋራ ቃል ኪዳኔን አደረግኹ” (መዝ. 88/89፥3)።
በዚህ ቃል ሽፋንነት የገባው የስሕተት ትምህርት፥ የክርስቶስን የመካከለኛነት ስፍራ ለፍጡራን አሰጥቷል። እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ዘመን ከተለያዩ ቅዱሳን ጋር ስለ ልዩ ልዩ ጕዳዮች የገባውን ቃል ኪዳን መነሻ በማድረግና፥ “ከመረጥኹት ጋራ ቃል ኪዳኔን አደረግኹ” የሚለውን ቃል በመታከክ፥ በዐዲስ ኪዳንም ኀጢአተኞች ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚገቡበትን የተለያየ ቃል ኪዳን ለቅዱሳን ሰጥቷል የሚሉ አሉ።
በቅዱሳን ስም በተደረሱት ገድላትና ድርሳናት ውስጥ፥ ከራስ ዐልፈው ሰባትና ከዚያም በላይ ያለውን ትውልድ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገቡ ቃል ኪዳኖች እንዳሉ ተገልጧል። ቃል ኪዳኖቹ የተመሠረቱትም በቅዱሳን ስም የተለያዩ ሥራዎችን በመሥራት ላይ ነው። ሌላው ቀርቶ የአንዱን ቅዱስ ገድል የጻፈ፥ ያጻፈ፥ ያነበበ፥ የተረጐመ፥ የሰማ፥ ያሰማ እንኳ መንግሥተ ሰማያትን እንደሚወርስ ተስፋ የሚሰጡ ገድላት በርካታ ናቸው። ይህም በራእ. 1፥3 ላይ፥ “ዘመኑ ቀርቧልና፥ የሚያነብበው የትንቢቱን ቃል የሚሰሙትና በውስጡ የተጻፈውን የሚጠብቁ ብፁዓን ናቸው” ከሚለው የተኰረጀ ሊኾን ይችላል።
በመዝሙረ ዳዊት 88/89፥3 ላይ የተገለጠው፥ እግዚአብሔር ከዳዊት ጋር የገባውን ቃል ኪዳን እንጂ ሌሎችን አይወክልም። በቍጥር 4 ላይ፥ “ለባሪያዬ ለዳዊት ማልኹ፤ ዘርኽን ለዘላለም አዘጋጃለኹ፤ ዙፋንኽንም ለልጅ ልጅ እመሠርታለኹ” ማለቱም ይህንኑ ያስረዳል። ቃል ኪዳን የገባው የማይዋሽ እግዚአብሔር በመኾኑ፥ “ኪዳኔንም አላረክስም፤ ከከንፈሬም የወጣውን አልለውጥም። ዳዊትን እንዳልዋሸው አንድ ጊዜ በቅዱስነቴ ማልኹ። ዘሩ ለዘለዓለም፥ ዙፋኑም በፊቴ እንደ ፀሓይ ይኖራል። ለዘለዓለም እንደ ጨረቃ ይጸናል። ምስክርነቱ በሰማይ የታመነ ነው” ብሎ ነገሩን እንዳጻናለት ይናገራል (ቍጥር 34-37)።
ይህ ስለ ዙፋኑ መጽናት የተገባው ቃል ኪዳን ለጊዜው ጥላነቱ በሰሎሞን ሲታይ፥ በክርስቶስ ግን ተፈጽሟል (2ሳሙ. 7፥12-16፤ ሉቃ. 1፥32፤ ዕብ. 1፥5፡8፤ ራእ. 22፥11)። እግዚአብሔር ለቃል ኪዳኑ ታማኝ አምላክ በመኾኑ፥ ዳዊት ከሞተ በኋላ ልጁ ሰሎሞን በቃል ኪዳኑ ውስጥ የነበረውን ውል አፍርሶ በመገኘቱ መንግሥቱ መቀደድ ቢኖርበትም፥ እግዚአብሔር ግን ለዳዊት የገባውን ቃል ኪዳን ዐስቦ ይህን በሰሎሞን ዘመን አላደረገበትም (ዳን. 9፥4፤ 1ነገ. 9፥5-7፤ 11፥1-13)።
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ (በብሉይ ኪዳን መጻሕፍት) ቃል ኪዳን ከተገባላቸው መካከል ዋናዎቹ፥ አዳም፥ ኖኅ፥ አብርሃም፥ ሙሴና ዳዊት ናቸው። ለአዳም የተሰጠው ቃል ኪዳን መልካሙንና ክፉውን በሚያስታውቀው ዛፍ ምልክትነት፥ ዘላለማዊ ሕይወትን የሚያስገኝ ተስፋን የያዘ ነበር። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች አዳምና ሔዋን በኪዳኑ ስላልጸኑ ሞት ገዛቸው (ዘፍ. 2፥8-17፤ ሆሴ. 6፥7)።
ከአዳም ቀጥሎ ቃል ኪዳን የተሰጠው ለኖኅ ሲኾን፥ ምድር ዳግመኛ በጥፋት ውሃ እንዳትጠፋ የቆመ ኪዳን ነው። ይህ በምድር ላይ የመኖርን ተስፋ የያዘው ኪዳን፥ በቀስተ ደመና ምልክትነት ተገልጦ ለዓለም ሕዝብ ኹሉ ያገለግላል (ዘፍ. 9፥1-17)።
እግዚአብሔር ከአብርሃም ጋር የገባው ቃል ኪዳን፥ በብሉይ ኪዳን ጐላ ያለ ስፍራ ከተሰጣቸውና በዐዲስ ኪዳን ፍጻሜ ካገኙት ቃል ኪዳኖች መካከል ይጠቀሳል። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች ለጊዜው ምድራዊቱን ከነዓንን የወረሱት አብርሃምና በይሥሐቅ በኩል የተቈጠሩት ዘሮቹ ኹሉ ሲኾኑ፥ ፍጻሜው ግን አይሁድ፥ አሕዛብ ሳይባል አብርሃምን በእምነት በመምሰላቸው የአብርሃም ልጆች የኾኑት ኹሉ ናቸው (ገላ. 3፥7-9፡29፤ ሮሜ 4፥11-12፤ 9፥7-8)። የዚህ ቃል ኪዳን ምልክት ግዝረት፥ የቃል ኪዳኑ ተስፋ ደግሞ በዘሩ የአሕዛብ መባረክና ከነዓንን መውረስ ነው (ዘፍ. 17፥1-21፤ ሮሜ 4፥11)።
የምድር አሕዛብ ኹሉ የተባረኩበት የአብርሃም ዘር ክርስቶስ፥ የምድራዊቱ ከነዓን አማናዊት የኾነችውን ሰማያዊት ኢየሩሳሌምን የሚያወርስ በመኾኑ፥ ለቃል ኪዳኑ ፍጻሜን ሰጥቷል (ገላ. 3፥16)። እግዚአብሔር በክርስቶስ ያደረገው ኹሉ ለአብርሃም በገባው ቃል ኪዳን መሠረት መኾኑንም ቅዱሳን መስክረዋል (ሉቃ. 1፥54፡73)።
በመቀጠል ደግሞ ለሙሴ የተሰጠውን ቃል ኪዳን እናገኛለን (ዘፀ. 19፥5-6፤ 24፥7-8)። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች የኾኑት ሕዝበ እስራኤል፥ የአብርሃምን የቃል ኪዳን ምልክት ተከትለው ሰንበታቱን መጠበቃቸው ለዚህ ቃል ኪዳን ምልክት ኾኗል (ዘፀ. 31፥13፤ ሕዝ. 20፥10-17)። በቃል ኪዳኑ የተሰጣቸው ተስፋ በአገራቸው ሕይወትን ማግኘት ነው። ይህንም ገና ከምድረ ግብጽ ሳይወጡ በነበረው ዕለት ምሽት ላይ ያረዱት የፋሲካ መታሰቢያ በግ ደም አረጋግጦላቸዋል (ዘፀ. 12፥21-28)።
ከግብጽ ምድር ወጥተው ወደ ሲና ተራራ ሲደርሱ፥ ሕጉን በድንጋይ ጽላት ጽፎ ይጠብቁትና በእነርሱና በእግዚአብሔር መካከል ቃል ኪዳን ይኾን ዘንድ ለሙሴ ሰጠው። ይህም ብሉይ ኪዳን ተብሎ የተጠራው ነው (ዘፀ. 19፥20፤ 31፥18፤ 20፥1-17፤ 34፥28፤ ዘዳ. 4፥13)። በእንሰሳት ደም የቆመው ብሉይ ኪዳን ወደ ፊት ለሚመጣው ዐዲስ ኪዳን መንገድ ጠራጊ እንጂ በራሱ ቋሚነት አልነበረውም። የጽላቱ ተሰብረው መተካታቸው፥ የማደሪያው ድንኳን ሰሎሞን በሠራው ቤተ መቅደስ መተካቱ፥ የመሥዋዕት መደጋገምና የመሳሰሉት ኹኔታዎች ለጊዜያዊነቱ ምልክቶች ተደርገው ይወሰዳሉ። ይበልጥ ደግሞ ትንቢቱ ይህን አረጋግጧል (ዘዳ. 18፥15፤ ኤር. 31፥31)።
ቃል ኪዳን የሚጸናው ኹለቱም ወገኖች ሲጠብቁት ብቻ ነው። ከኹለቱ አንዱ ጠብቆ ሌላው ቢያፈርሰው ቃል ኪዳን መኾኑ ይቀራል። ብሉይ ኪዳን ጊዜያዊነቱ ሳያንስ ሕዝቡ ሊጠብቀው ባለመቻሉ ቃል ኪዳንነቱ ቀረ። እግዚአብሔርም ከዚህ በብዙ መንገድ የተሻለውን ዐዲስ ቃል ኪዳን እንደሚገባ ተናገረ (ኤር. 31፥31-34)። ይህም ስለ ዐዲስ ኪዳን የተነገረ ትንቢት በመኾኑ፥ በዕብራውያን 8 ላይ ተፈጻሚ ኾኖ ተጠቀሰ። ዐዲስ ኪዳን የተሻለና የበለጠ ኪዳን በመኾኑ ብሉይ ኪዳን ከነጓዙ ፍጻሜ አግኝቶ እንደሚቀርና የሚጠቀምበት ቀርቶ የሚያስበው እንኳ እንደማይኖር እግዚአብሔር በአጽንዖት ተናገረ (ኤር. 3፥16)።
እግዚአብሔር እስከዚህ ድረስ ለተለያዩ ቅዱሳንና ለአጠቃላዩ የእስራኤል ሕዝብ ገብቶ የነበረውን ቃል ኪዳን ኹሉ በመጠቅለል፥ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ዐዲስና ለዘላለም የማይፈርስ፥ ተጨማሪ የማያስፈልገው ቃል ኪዳን ገባ። እርሱም በገዛ ደሙ የመሠረተው ዐዲስ ኪዳን ነው (ሉቃ. 22፥19-20፤ ኢሳ. 42፥6-7)። ይህ ኪዳን በክርስቶስ ለሚያምኑ ኹሉ የተሰጠ ሲኾን፥ የዘላለም ሕይወትን ተስፋ የያዘ ቃል ኪዳን ነው። የተስፋው ምልክቶችም ጥምቀትና ቅዱስ ቍርባን ናቸው (ማር. 16፥16፤ 1ቆሮ. 11፥23-26፤ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት 1972፣ ገጽ 80)።
ዐዲስ ኪዳን ብሉይ ኪዳንን በከፊል ሳይኾን ሙሉ በሙሉ ተክቷል። ዐዲስ ኪዳን የእግዚአብሔር ዘላለማዊ ክብሩ የጸናበት፥ ኹሉ የተፈጸመበት ታላቅ ቃል ኪዳን መኾኑን በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መሠረት የቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍትም መስክረዋል፤ “ወበምክረ ዚኣከ ወልድከ ዋሕድ ኢየሱስ ዘተሰቅለ በእንተ መድኀኒትነ ዘበቃለ ኪዳንከ ቦቱ ገበርከ ሠሚረከ ቦቱ። - ለድኅነታችን በተሰቀለው በአንድያ ልጅኽ በኢየሱስ በባሕርይኽ ምክር ደስ ተሰኝተኽበት ቃል ኪዳንኽን ኹሉ በእርሱ አድርገኻል” (መጽሐፈ ቅዳሴ 1984፣ ገጽ 65)።  
እንዲሁም በእልመስጦአግያ፥
“ከመ ታእምሩ ፈቃዶ ለኢየሱስ ክርስቶስ ወትሌብዉ ምስጢረ መድኀኒትክሙ ኦ አንትሙ እደው ወአንስት ቅዱሳት እለ ሀሎክሙ ውስተ ተመክሖ በክርስቶስ፥ ወኩኑ አሐደ ምስለ ብእሲ ዘውስጥ አንትሙኬ እለ አጽንዐ እግዚአብሔር ኪዳኖ ምስሌክሙ ወሤመ መንፈሶ ውስቴትክሙ፡፡”
ትርጓሜ፥ “የኢየሱስ ክርስቶስን ፈቃድ ታውቁ ዘንድና የደኅንነታችኹን ምስጢር ታስተውሉ ዘንድ፥ በክርስቶስ ትምክሕት ያላችኹ እናንተ ወንዶችና ቅዱሳት ሴቶች ሆይ፥ ከውስጣዊ ሰውነት ጋር አንድ ኹኑ፤ እግዚአብሔር ኪዳኑን ከእናንተ ጋር ያጸና መንፈሱንም በውስጣችኹ ያሳደረ እናንተ ናችኹ እኮ” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 24)።
የእግዚአብሔር የባሕርይ ምክርና ሐሳቡ ለአንዴም ለመጨረሻ ጊዜም በክርስቶስ በኩል በገባው ዐዲስ ኪዳን በኩል ተፈጽሟል። እግዚአብሔር ከሰው ልጆች ጋር ባለው ታሪክ የገባው የመጨረሻው ቃል ኪዳን ዐዲስ ኪዳን ብቻ ነው። በዚህ ኪዳን ያልተፈጸመለት ወይም የቀረው ነገር ኖሮ፥ በሌላ ቃል ኪዳን ለመፈጸም በማሰብ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገባ ሌላ ቃል ኪዳን ገብቷል የሚለው ትምህርት ልብ ወለድ ከመኾን አይዘልም፤ ምክንያቱም የዘመን ፍጻሜ በኾነው ባለንበት ዘመን፥ እግዚአብሔር ለማድረግ ያሰበው፥ ነገሮችን ኹሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል እንጂ ሌላ ቃል ኪዳን ለመግባት አይደለም (ኤፌ. 1፥10)።
ከላይ ለማሳየት እንደ ተሞከረው፥ ለቀደሙት አበው የገባው ቃል ኪዳን፥ ከወቅቱ ኹኔታ ጋር በተያያዘ መንገድ፥ ወይም ስለ ወደ ፊቱ ተስፋ ነበር እንጂ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገባ ቃል ኪዳን አልነበረም፤ እንዲህ ያለውን ቃል ኪዳን ከማንም ፍጡር ጋር አልገባም። ምናልባት ለአዳም የገባው ቃል ኪዳን በአዳም ባይፈርስ ኖሮ፥ ለዘላለም በሕይወት መኖርን የሚያስገኝ ቃል ኪዳን ይኾን ይኾናል። ከሰው ልጅ ውድቀት በኋላ ወደ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበትን ቃል ኪዳን የገባው ግን በክርስቶስ በኩል ብቻ ነው።
በሐሰት ለቅዱሳን በዐዲስ ኪዳን ተገባ በሚባለው ቃል ኪዳን መሠረት፥ እንዲህና እንዲያ ያደረገ ይህንና ያን ያገኛል የሚል ተስፋ በብዙ አዋልድ መጻሕፍት በስፋት ተጽፎ እናነባለን። አብዛኛው ቃል ኪዳን ተሰጠ ተብሎ የሚተረከው ቅዱሳኑ ሊሞቱ ሲሉ በመጨረሻዋ ሰዓት ላይ ነው። እንዲህ ከኾነ ታዲያ በዐዲስ ኪዳን መጥምቁ ዮሐንስ፥ ቀዳሜ ሰማዕት እስጢፋኖስ፥ እና ያዕቆብ በግፍ የተገደሉ ቅዱሳን ናቸው፤ ሊሞቱ ሲሉም ኾነ ከዚያ በፊት ቃል ኪዳን እንደ ተገባላቸው በሐዲስ ኪዳን ውስጥ አናገኝም (ማቴ. 14፥10-12፤ ሐ.ሥ. 7፥6 12፥2)። ለነዚህ ቅዱሳን ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጪ ሰዎች ከልባቸው አንቅተው (አመንጭተው) በደረሱላቸው ድርሰትና ገድላት ውስጥ ግን፥ የተለያዩ ቃል ኪዳኖችን ጻጽፈው ሊያስነብቡን ቢከጅሉም አንድም እውነትነት የለውም።
ዛሬ ብዙዎቹ ከእግዚአብሔር ዘንድ ባልኾነ ቃል ኪዳን ተታለዋል። ስለዚህ በክርስቶስ አዳኝነት አምነው ከመጽደቅና በእርሱ ኖረው መልካም የሥራ ፍሬን ከማፍራት ይልቅ፥ በኀጢአት ላይ ኀጢአትን በመጨመር ከእግዚአብሔር ባልኾነው ቃል ኪዳን እየተኵራሩ፥ ‘በእገሌ ቃል ኪዳን መሠረት እንዲህ ካደረግኹ አልኰነንም’ ብለው ራሳቸውን ይሸነግላሉ። የእግዚአብሔር ቃል ግን እንዲህ ይላቸዋል፤ “ለዐመፀኞች ልጆች ወዮላቸው፥ ይላል እግዚአብሔር። ከእኔ ዘንድ ያልኾነ ምክር ይመከራሉ። ኀጢአትንም በኀጢአት ላይ ይጨምሩ ዘንድ ከመንፈሴ ዘንድ ያልኾነውን ቃል ኪዳን ያደርጋሉ።” (ኢሳ. 30፥1)።
ምንጭ፦ የተቀበረ መክሊት 3ኛ ገጽ 106

Monday, January 25, 2016

ተሐድሶ ወደቀደመ የወንጌል ቃል መመለስ ማለት ነው!

(ተሐድሶ ተስፋዬ)

ለኦርቶዶክስ የተከለከለ ፅሑፍ !!
ድንገት እንኳ ብታነቡም እንዳትጨርሱት !!

በሰላም አለቃ በክርስቶስ ኢየሱስ ስም ሰላም ብያለሁ፣ሰላሙ ይብዛላችሁ !! እስኪ ደግሞ ትንሽ ለክርስቶስ ብዬ ልሰደብ !!

የኦርቶዶክስ ህዳሴ በኛ በልጆቿ ከግብ ይደርሳል !! አሜን የምትሉ ለምልሙልን !! እንደምንም አንብቧት ።
ከተሀድሶ እንቅስቃሴዎች ዉስጥ በትንሹ ላካፍላችሁ...

1.1. ""ማርታን ወደ ማርያም የመቀየር ተሐድሶ""

ሰዎች ወደ እግዚአብሔር ቃል ካልተመለሱ ወደ እግዚአብሔር አይመለሱም፤ ጌታ እንዳለው
“የሚያስፈልገው ግን ጥቂት ወይም አንድ ነገር ነው፤ ማርያምም መልካም ዕድልን መርጣለች፤ ከእርስዋም አይወሰድባትም አላት ።” (ሉቃ.10፥42)፡፡ እነማርታ ቤተ ክርስቲያኑን ሞልተውታል፤ ዳቦ ጋግሩ፤ ወጥ ሥሩ፤ልብስ እጠቡ፤ከበሮ ምቱ ሲባሉ አይሰለቻቸውም፤ የክርስቶስን ወንጌል ተማሩ ሲባሉ ግን እንኳንስ ሊማሩ የሚማሩ እኅቶችና ወንድሞችን እንኳን ማየት አይፈልጉም፡፡ በዓመት አንድ ቀን የጥምቀት በዓል ሲመጣ ለማይሰማ ታቦት መንገድ ይጠርጋሉ፤ ምንጣፍ ያነጥፋሉ፤ ጉልበታቸውን ሳይሰስቱ ያገለግላሉ፤ የሚሰሙት ወንጌል ግን የለም፤ የእነዚህ ሰዎች አገልግሎት የቅናት እንጅ የእምነት አይደለም፡፡
ለእግዚአብሔር ቃል ቅድሚያ ካልሰጡ ደግሞ ለማይሰማና ለማያይ ታቦት ምንጣፍ እንዳነጠፉ፣ ግብር እንደገበሩ ይኖራሉ እንጅ ዕረፍትን አይገኙም፡፡ እነዚህ ሰዎች ለጊዜው ደስተኞች ናቸው፡፡ ዐሥር ዐመት በዚህ መልኩ ካገለገሉ በኋላ “አሁን ለመዳናችሁ እርግጠኞች ናችሁን?” ብለን ብንጠቃቸው እንኳንስ እርግጠኞች ሊሆኑ እንዲያውም ፍርሐታቸው ጨምሮ እናገኛቸዋለን፤ ስንጠይቃቸው የሚሰጡን መልስ “ማንም ከመሞቱ በፊት ለመዳኑ እርገጠኛ መሆን አይችልም” የሚል ነው፡፡
እነዚህ ሰዎች ይንም አይነቱን ወንጌል ከየት እንዳገኙት እናውቃለን፡፡ አዲሱ ትምህርት ነው፤ ሐዋርያት ያወገዙት፣ “ማንም እኔ ካስተማርኋችሁ የተለየ ወንጌል ቢያስተምራችሁ የተወገዘ ይሁን” (ገላ.1፡8) ብለው ያስጠነቀቁን ትምህርት ይህ ነው፡፡
ስለ ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ክርስቶስ ለመሄድ መናፈቅ አልሰሙም ማለት አንችልም፤ የሰሙትን እንዳላመኑት ግን እናያለን፡፡ ክርስቶስ በቃሉ “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘለዓለም ሕይወት እንዲኖረው እንጅ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወድዶአልና፤ በእርሱ የሚያምን አይፈረድበትም ፤ በእርሱ የማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስላላመን አሁን ተፈርዶበታል ” (ዮሐ.3፡16-17) ያለው ቃል ዕረፈት ካልሰጠና እርግጠኛ ካላደረገን በምን እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን? ከዚህ ከጸና እውነት ያንሸራተተንና ከዓለቱ ነቅሎ በአሸዋ ላይ የሠራን ማነው? ይህን ከእግዚአብሔር እውነት የሚነቅል ትምህርት በእግዚአብሔር ቃል መዋጋት ተሐድሶ ነው፡፡
ብዙዎቻችን “የአገልግሎት ማኅበራት አባላት ነን” እያልን ከበሮ ለመምታት፣ ለመዘመር፣ ታቦት ለማክበር፣ ምንጣፍ ለማንጠፍ፣ የቤተ ክርስቲያን ቅጥረ-ግቢ ለማጽዳት፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ታቦት የሚሄድባቸውን መንገዶች ተከትሎ ለማጽዳትና ሰንደቅ ዓላማ ለመስቀል እንጅ የእግዚአብሔርን ቃል ለመስማት ጊዜ የለንም፡፡ ቃለ እግዚአብሔርን መስማት እግዚአብሔርን ማገልገል ነው ብለን የምናምን ስንቶቻችን ነን? ማርታ ማርያምን ለምን ተቃወመቻት? ቃለ እግዚአብሔርን መስማት እግዚአብሔርን ማገልገል እንደሆነ ስላልገባት ነበር፡፡ ክርስቶስ ግን ለሁሉ የሚበቃውን አንድ ታላቅ አገልግሎት አከበረ፤ እርሱም ቃሉን መስማት ነው፡፡ ተሐድሶ የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት የመታደስ አገልግሎት ነው፡፡
የጸጋ ስጦታዎቻችን የተለያዩ ናቸው፤ ለአንዱ የተሰጠው ለሌላው ላይኖረው ይችላል፤ የሚዘምር ላይሰብክ፣ የሚሰጥ ላያስተምር ይችላል፤ ለሁላችንም የተሰጠን ጸጋ ግን የእግዚአብሔርን ቃል የመስማት አገልግሎት ነው፤ በዚህ አገልግሎት ውጤታማ ያልሆነ ሰው ደግሞ በሌላ አገልግሎት ውጤታማ መሆን አይችልም፡፡ እግዚአብሔርን ስለማያውቀው የሚያገለግለው የሚያውቀውን ራሱን፣ አለቃውን፣ ታቦቱን፣ ገንዘብን፣ ክብርንና እውቅና መፈለግን፣ ተቃውሞን፣ ሥርዐትንና ታሪክን፣ እኔ ብቻ ትክክል ነኝ ማለትን እንጂ እግዚአብሔርን ሊያገለግል አይችልም፡፡ ተሐድሶ ከዚህ አይነት እስራት ነጻ ወጥቶ እግዚአብሔርን እንደቃሉ በእውነትና በመንፈስ ማምለክ (ማገልገል) ነው፡፡
.
1.2. የሚያስፈልገን ጸበል ወይስ ወንጌል?

ለነማርታ እነርሱ ካልደከሙ የእግዚአብሔር ጸጋ አይበቃም፡፡ የእነርሱ ማሰሮ የምትሞላው የእግዚአብሔር ጸጋ ሲፈስስባት ሳይሆን እነርሱ የፈጩት ዱቄት ሲጨመር ብቻ ነው፡፡ ቃሉን መማር መሥዋዕት አይደልም፤ ጸበል ካልጠጡ፣መክፈልት ካልበሉ እግዚአብሔርን አላገለገሉትም፡፡ ቃሉን ካልሰሙ ቤተ ክርቲያን መሳለም ምንድን ነው? ጸበል ውሃ አይደለምን? ህሊናችንን ከሞተ ሥራ ሊያነጻ የሚችል መለኮታዊ ጸበል የእግዚአብሔር ቃል ነው፤(ዕብ.9፡14) ዲያቆናት በኩስኩስት ጸበል ከሚቀዱ ይልቅ ከመለኮታዊው ጸበል ከቃሉ ለምእመናን የማጠጣት አገልግሎት ቢጀምሩ ምናለበት? እስከመቼ ምእመናን በውሃ እየተታለሉ ይኖራሉ? የሕይወት ውሃ መጽሐፍ ቅዱስ ተከድኖ ወይም አልባሌ ቦታ ተጥሎ ዘወትር የውሃ መቅጃ ኩስኩስት ስናጥን የምንኖረው እስከ መቼ ነው? ኧረ ተዉ ጎበዝ የእግዚአብሔር ፍርድ ሳይገለጥ ወደ ቃሉ እንመለስ! ተሐድሶ ከውሃና ከመክፈልት ወደ ሕይወት ውሃ ወደ እግዚአብሔር ቃል መመለስ ነው፡፡
እግዚአብሔር የሕይወት ምግብ አዘጋጅቶ እየጠበቀን እኛ እግዚአብሔር የሰበሰበውን ሕዝብ የሚያልፍ ምግብ ያውም ውሃ አጠጥተን የምንልከው እስከመቼ ነው? ወደ እግዚአብሔር ቃል ከመመለስ የበለጠ ምን ተሐድሶ አለ? ሰውን ወደ እግዚአብሔር ቃል ከመመለስ የበለጠ አገልግሎትስ የት ይገኛል? ተሐድሶ አዲስ ነገር አይደልም፤ እግዚአብሔር ተረስቷልና ይታሰብ፤ እግዚአብሔር ክብሩንና ቦታውን ተነጥቋልና ወደ ክብሩ ይመለስ የሚል ተጋድሎ ነው፡፡ ክብሩን ለማንም እንደማይሰጥ የተናገረው እግዚአብሔር ያስነሳው አገልግሎት እንጂ አንዳች የሰው ፍላጎት የለበትም፡፡ እናውቃልን ስንዴ፣ ሰልባጅ፣ ብር ፈልገው የሚሠሩ፣ የፕሮቴስታንት ተላላኪዎች እንደምንባል፡፡ እኛ ግን የቤተ ክርስቲያኒቱ መቆሳቆል፤ የነገሮች ቅጥ ማጣት፣ በእግዚአብሔር ቦታ የማይሰሙና የማያዩ ታቦታት መቀመጥና መክበር፣ ንስሓ መግባት አለመቻላችን ቤተ ክርስቲያናችንን እየጎዳ ያለ መሆኑ፣ ያሳሰበን የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንጂ በምንም ምክንያት በቤተ ክርስቲያን ላይ ክፉ አሳብ ያለን ሰዎች አይደለንም፡፡ እንዲውም በአመንነው እውነት ምክንያት ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር የሚጠቅም ልዩ ሸክም (ራእይ) ያለን ሰውች ነን፤ ራእያችን እንዳይዘገይ፣ መባረካችን እንዲፈጥን በመንገዳችን እንቅፋት አትሁኑብን እንላለን እንጂ በፍጹም እግዚአብሔር የማይፈልገው፣ ቤተ ክርስቲያንንም ሆነ ሀገርን የሚጎዳ አጀንዳ የለንም፡፡ አገልግሎታችን ሰማያዊና የከበረ መሆኑን እናውቃለን፤ ለዚህም ነው በነገር ሁሉ ስንፈተን “የማምነውን አውቀዋለሁ” ብለን ጸንተን እየተጓዝን፣ በየጊዜው ደግሞ እየበዛን ያለነው፡፡ የሚያበዛን የሕይወት ቃል የሆነው የእግዚአብሔ ቃል ነው፡፡ በተሐድሶ ያለ ሕዝብ በውሃ ዳር የተተከለ ዛፍ ነው፤ ቅጠሉ አይጠወልግም፤ ዘወትር ያፈራል እንጂ የመድረቅ ሥጋት የለበትም፡፡ ተሐድሶ ይህ ነው!
.
1.3. የምንሰብከው እግዚአብሔርን ወይስ የእኛን ሥነ ምግባር?

የሚያስፈልገው ነገር አንድ ነው፤ የእግዚአብሔር ቃል፡፡ የእኛ ገድልና ድርሳን፣ የእኛ አመለካከትና ዕወቀት፣ የእኛ ቅኔና ትርጓሜ በቦታው ጠቃሚ ቢሆንም በእግዚአብሔር ክብር ላይ መጋረጃ ሲሆን ግን ጉዳት እንጂ ጥቅሙ አይታየንም፤ የሕይወት መንገድ የተገለጠበት መጽሐፍ “መጽሐፍ ቅዱስ” ነው፡፡ ይህን እውነት ማንም ማስተባበል እንደማይችል እናምናለን፡፡ ወደ እግዚአብሔር ቃል እንመለስ! (Back to the word of God!) ምንም ብንሰብክ፣ ምንም ብንቀኝ፣ ምንም ብናከማች የእግዚአብሔር ቃል ካልሆነ ይበተናል፡፡
ይህ ነገር ለምን ያሳስበናል? ሰዎች እንዲለወጡ፣ ንስሓ እንዲገቡ፣ እንደእግዚአብሔር ቃል እንዲመላለሱ እግዚአብሔር ይፈልጋል፤ ይህ ሊሆን የሚችለው ደግሞ እግዚአብሔርን በቃሉ መሠረት ስናውቀው ብቻ ነው፡፡ የግብፅ ፓትርያርክ የነበሩት አቡነ ሺኖዳ የተናገሩትን ምሳሌ አድረገን እንመልከት፤ “I confess before You, O Lord that I ought to have changed my trend of writing. I confess-in shame-that I often talked to people about virtue but little did I talk to them about you, though you are all in all” (The release of the spirit p.14) መልእክቱ ወደ አማርኛ ሲመለስ እንዲህ የሚል ነው፡፡ “ከአሁን በፊት ስጽፍበት የነበረውን ልማዴን መለወጥ እንደነበረብኝ አቤቱ በፊትህ እናዘዛለሁ፤ ለሕዝቡ ስለ ምግባራት (ስለመልካም ምግባር) ዘወትር ብዙ እንደ አስተማርሁ፣ ብንም እንኳን አንተ ሁሉ በሁሉ ብትሆንም ስለአንተ ግን ጥቂት እንደነገርኋቸው በሐፍረት እናዘዛለሁ፡፡” ስለ እግዚአብሔር ሳይሆን ስለ ሥነ ሥርዐት ስንሰብክ ከኖርን የምናልመውን ለውጥ ማምጣት አንችልም፤ የሚለውጠው እግዚአብሔር እንጅ የእኛ ቃል አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ በቃሉ እንጅ በእኛ የስብከት ጥበብ አይሠራም፡፡ እግዚአብሔር በቃሉ እንጂ በእኛ ተረት ለመጽናት ቃል ኪዳን የለውም፡፡
ዛፉን እየነቀልንና እያደረቅን ፍሬ የምንፈልገው ከየት ነው?
እስኪ ልብ በሉ! እግዚአብሔርን ከሰው ልብ የሚያፈናቅል (እንደዛፍ ተክል የሚነቅል) ትምህርት እያስተማርን በጎ ምግባር የምናገኘው ከምኑ ነው? አቡነ ሺኖዳ እንዳሉት ስለ እግዚአብሔር ሳይሆን ስለ በጎ ሥራ ስንሰብክ የምንኖረው እስከመቼ ነው? መቼም ቢሆን የሰይጣንን አሳብ አንስተውም፤ ዛሬስ ብሎ ብሎ ተሐድሶ መልካም ሥራን መቃወም ጀመረን? ተመልከቱ! ተሐድሶ ለየለት! የሚል ሰው አይጠፋም፡፡ እያልን ያለነው በዛፉ የማይኖር ፍሬ አያፈራም፤ ሰውን ከዛፉ የሚቆርጥና የሚያደርቅ ለመጥፋትና ለመቃጠል የሚያዘጋጅ የሐሰት ትምህርት ከቤተ ክርስቲያን ይራቅ፤ ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት ትታደስ ነው፡፡ይህ ነው ተሐድሶ!
በክርስቶስ የምንኖረው በቃሉ ስንኖር ብቻ ነው፤ ቃሉን እየተቃወምን ወይም ቃሉን ከአትሮንስ አውርደን የእኛን ተረት አትሮንስ ላይ የምንሰቅል ከሆነ፣ ዐውደ ምሕረቱን እንደ ስሙ የምሕረት ማወጃ አደባባይ ሳይሆን የሚያስር ትብትብ መስበኪያ ካደረግነው፣ እግዚአብሔር በቃሉ ነጻ ሊያወጣው የሚፈልገውን ሕዝብ የበለጠ የእስራት ቀንበር ከጫንንበት የት አለ የእኛ የክርስቶስ መልእክተኞች መሆን? የምንሟገተው ለማን ነው? ለራሳችን ወይስ ለክርሰቶስ? ለክርስቶስ ከሆነ ቃሉን ለምን አናጠናም/አንሰብክም? ዓለምን መቃወም የምንችለው በቃሉ ብቻ ነው፡፡ ለእኛ የተለየ ጥበብ የለንም፤ያለን ማረጋገጫ ቃሉ ብቻ ነው፡፡ ተሐድሶ ይህ ነው! ወደ እግዚአብሔር ቃል መመለስ! እግዚአብሔር ይመልሰን! የቤተ ክርስቲያናችንን የተሐድሶ ተስፋ በቃሉ እንደገና ወደ ክብሯና ቅድስናዋ የመመለስዋን ትንሣኤ ለማየት ነው!!!
ኢየሱስ ያድናል !!

Wednesday, January 20, 2016

ተቀባይነት ያጣ እውነት!



ብዙ ብለናል፤ ብዙ ተብሏል።  ችግሩ ያለው የሚነገር እውነት አለመኖሩ ሳይሆን እውነቱን የሚቀበል መጥፋቱ ላይ ነው። ተቀባይነት ያጡ እውነቶችን መጽሐፍ ቅዱስን ዋቢ አድርገን እናቀርባለን።

1/ ታቦት

ታቦት ማለት ማደሪያ፤ማኅደር ማለት ነው።  ቃልኪዳናዊ አሠራሩም ከዚህ የሚከተለውን ይመስላል።
«እኔ እንደማሳይህ ሁሉ፥ እንደ ማደሪያው ምሳሌ እንደ ዕቃውም ሁሉ ምሳሌ፥ እንዲሁ ሥሩት። ከግራር እንጨትም ታቦትን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፥ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን። በውስጥና በውጭም በጥሩ ወርቅ ለብጠው፤ በእርሱም ላይ በዙሪያው የወርቅ አክሊል አድርግለት። አራት የወርቅ ቀለበቶችም አድርግለት፥ እነርሱንም በአራቱ እግሮቹ ላይ አኑር፤ በአንድ ወገን ሁለት ቀለበቶች፥ በሌላው ወገን ሁለት ቀለበቶች ይሁኑ። መሎጊያዎችንም ከግራር እንጨት ሥራ፥ በወርቅም ለብጣቸው። ለታቦቱ መሸከሚያ በታቦቱ ጐን ባሉት ቀለበቶች መሎጊያዎቹን አግባ። መሎጊያዎቹም በታቦቱ ቀለበቶች ውስጥ ይኑሩ፥ ከቶም አይውጡ። በታቦቱም ውስጥ እኔ የምሰጥህን ምስክር ታስቀምጣለህ። ከጥሩ ወርቅም ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ የስርየት መክደኛ ሥራ። ሁለት ኪሩቤል ከተቀጠቀጠ ወርቅ ሥራ፥ በስርየት መክደኛውም ላይ በሁለት ወገን ታደርጋቸዋለህ» ዘጸ 25፤10-18
ይህንን የእግዚአብሔር መመሪያ ያላሟላ ታቦት፤ ታቦት ሊባል አይችልም። ከዚህ የሚጨመርም፤ የሚቀነስም ከእግዚአብሔር  ቃል ያፈነገጠ ነው። ይህ አንዱ ታቦት ሁለቱን የምስክር ጽላቶች ይይዛል። ካህናቱ ሲሸከሙም በመሎጊያዎቹ ጽላቱ ውስጥ እንዳለ አራት ሰዎች በአንድ ጊዜ ይሸከሙታል እንጂ አናት ላይ ቁጢጥ የሚል ጽላት የለም። ይህ ያፈጠጠ ያገጠጠ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ነው። ይህ የእግዚአብሔር ቃል እንዲሻሻል የተነገረበት ጊዜ የለም። ዛሬ ታቦት የሚባለው ከየት የመጣ ነው? ዓላማው፤ አሰራሩ፤ እቅድና ግቡ ምንድነው? ብዙ ሰዎች ስለተከተሉት ወይም እድሜ ጠገብ ስለሆነ ውሸት መቼም ቢሆን እውነት ሊሆን አይችልም። ታቦትን የተመለከተ የእግዚአብሔር ዓላማ በዚህ ዘመን ለማንም አልተሰጠም።

2/ጽላት፤

 ጽላት ሁለቱ የኪዳን ሰሌዳዎች ናቸው። 10ቱ የእግዚአብሔር ትዕዛዛት የተጻፈባቸው ሰሌዳዎች ስለሆኑ ጽላት ተብለዋል። ሙሴ ጽላቶቹን ሊቀበል ሁለት ጊዜ ወደተራራ ወጥቷል። የመጀመሪያውን ጽላት የቀረጸውና በጣቱ የጻፈባቸው እግዚአብሔር ራሱ ነው። «እግዚአብሔርም ከሙሴ ጋር በሲና ተራራ የተናገረውን በፈጸመ ጊዜ በእግዚአብሔር ጣት የተጻፈባቸውን ከድንጋይ የሆኑ ሁለቱን የምስክር ጽላቶች ሰጠው» ዘጸ 31፤18
የመጀመሪያዎቹ ከተሰበሩ በኋላ ጽላቱን ከእብነ በረድ ዳግመኛ የቀረጸው ሙሴ ራሱ ሲሆን በላዩ ላይ ትዕዛዛቱን በጣቱ የጻፈባቸው ግን እግዚአብሔር ነው።
 «ሙሴን አለው፦ ሁለት የድንጋይ ጽላቶች እንደ ፊተኞች አድርገህ ጥረብ፤ በሰበርኻቸው በፊተኞቹ ጽላቶች የነበሩትን ቃሎች እጽፍባቸዋለሁ» ዘጸ 34፤1   ዘዳ10፤4
መጽሐፍ ቅዱስ ስለጽላት በተናገረበት የትኛውም አንቀጽ ውስጥ ሙሴ ጽላቶቹ ላይ ጻፈ የሚል ገጸ ንባብ የለም። ከእብነ በረድ አስመስለህ ቅረጽ የተባለውን ትዕዛዝ አንተው ጻፍባቸው የተባለ በማስመሰል ራሳቸው የሚጽፉባቸው ከየት በተገኘ ትዕዛዝ ነው? በወቅቱም ጽላቶቹ ላይ እግዚአብሔር ራሱ የጻፈባቸው ትዕዛዛት እንጂ ምስል ወይም ስዕል አይደለም። ይህስ ከማን የተገኘ ትምህርት ነው? ስንት ጽላት? ስንት ታቦትስ? እግዚአብሔር ሰጥቷል?

3/ ምልጃና ማስታረቅ

«አማላጅ» የሚለው ቃል የተገኘው «ማለደ» ከሚል ግስ ሲሆን «ማለደ» ማለት ደግሞ «ለመነ» ወይም «ጸለየ» ማለት ይሆናል። « መማለድ ፤ ማማለድ… » ማለት  «መለመን ፣ ማስታረቅ» ሲሆን «አማላጅ» ደግሞ ይህን ተግባር የሚያከናውን ነው፡፡ ተግባሩ ደግሞ «ምልጃ» ይባላል፡፡
አዳም ከእግዚአብሔር ፊት በኮበለለ ጊዜ ወዴት ነህ? ሲባል እነሆ በዚህ ተሸሽጌአለሁ አለ።                         «እግዚአብሔር አምላክም አዳምን ጠርቶ፦ ወዴት ነህ? አለው።እርሱም አለ፦ በገነት ድምፅህን ሰማሁ፤ ዕራቁቴንም ስለ ሆንሁ ፈራሁ፥ ተሸሸግሁም» ዘፍ 3፤9-10
ይህ የኮበለለው ሰው፤ አዳም ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ነበረበት። መቼ? ማንስ? ያስታርቀዋል?
በዘመነ ብሉይ የማስታረቅ አገልግሎት የተሰጠው ለካህናቱ ወገን ብቻ ነበር። የኃጢአት ማስተሰሪያ መስዋዕትም ዕለት ዕለት ይቀርብ ነበር።
« ዕለት ዕለትም ስለ ማስተስረይ ለኃጢአት መሥዋዕት ወይፈኑን ታቀርባለህ፤ ማስተስረያም ባደረግህ ጊዜ መሠዊያውን ታነጻዋለህ ቅዱስም ይሆን ዘንድ ትቀባዋለህ» ዘጸ29፤36 ይህ የማስታረቅ አገልግሎት ፍጹማዊ አገልግሎት አይደለም። በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የተጋረደውን የጥል ግድግዳ ማፍረስ የማይችል ጊዜአዊ አገልግሎት ነበር። ስለዚህም በአዳምና በልጆቹ ላይ የእግዚአብሔር ቁጣ ነበረ። ይህ የበደል ቁጣ ሊመለስ የሚችለው ይህንን መሸከም የሚችል መስዋዕት ሲኖር ብቻ ነው። ለዚህም አገልግሎት ብቁ መሆን የሚችለው ደግሞ ከኃጢአት በቀር በሁሉ የተፈተነ ሊሆን ይገባዋል።
«ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም» ዕብ 4፤15
ስለዚህም ሰማያዊ ሊቀካህን ኢየሱስ ከእግዚአብሔር ፊት ለኮበለልነው ለአዳም ልጆች ሁሉ አስታራቂ መስዋዕት ሆነ። ይህንንም ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ አለ።«ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ»ኢሳ53፤12
ኢየሱስ ክርስቶስ አስታራቂና ማላጅ ባይሆን ኖሮ ሥጋ ከለበሰ ከሰው ልጅ ማንም ቢሆን የማስታረቅ አልገልግሎትን ሊፈጽም አይችልም ነበር። የክርስቶስ ኢየሱስን አስታራቂነት ልዩ የሚያደርገው የማማለድ ብቃቱ ብቻ ሳይሆን ዕለት ዕለት የሚደረገውን የማስታረቅ አገልግሎት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማስቀረት መቻሉ ነበር።
«ሊቀ ካህናትም ሁሉ ዕለት ዕለት እያገለገለ ኃጢአትን ሊያስወግዱ ከቶ የማይችሉትን እነዚያን መሥዋዕቶች ብዙ ጊዜ እያቀረበ ቆሞአል እርሱ ግን ስለ ኃጢአት አንድን መሥዋዕት ለዘላለም አቅርቦ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ» ዕብ 10፤11-12
ስለዚህ የኢየሱስ ክርስቶስ የማስታረቅ አገልግሎት አንዴ የተፈጸመ፤ ነገር ግን ዕለት ዕለት ወደእግዚአብሔር የሚመጡትን ሁሉ የሚያድን የዘላለም መስዋዕት ስለሆነ ዛሬ አዲስ የሚፈጸም የልመናና የማስታረቅ አገልግሎት የለም። አንዳንዶች ዛሬም የሚለምን ያለ የሚመስላቸው አሉ። አንዳንዶች ደግሞ አንዴ የፈጸመው አገልግሎት አብቅቷል፤ ከእንግዲህ አይሰራም የሚሉ አሉ።  አማላጅነትን ለሰዎች ያስረከቡ ሁሉ የክርስቶስን ዘላለማዊ ብቃት ይክዳሉ። በሌላ መልኩም የሰዎችን አማላጅነት ለመከላከል ሲሉ ኢየሱስን ዛሬም የሚማልድ አድርገው የሚስሉም አሉ። ሁለቱም ጽንፎች የኢየሱስን ማንነት ካለማወቅ የሚመነጭ አስተሳሰብ ነው።እውነቱ ግን ዕብራውያን መጽሐፍ እንዳለው፤
«እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤ እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል። ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤ እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና» ዕብ 7፤23-27
ስለዚህ በአጸደ ነፍስ ያሉ ቅዱሳን፤  ሰዎች ከበደል ወደ ጽድቅ፤ ከኃጢአት ወደቅድስና ሰዎች እንዲመለሱ ይማልዳሉ፤ ይለምናሉ ማለት ለኃጢአተኛው ምትክ ሆነው ያድኑታል ማለት አይደለም። አንዴ የተፈጸመው የማማለድና የማስታረቅ አገልግሎት በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው።

Saturday, December 19, 2015

ኢየሱስ፤ ኢየሱስ እየተባለ ቢጠራ ያሳፍራል እንዴ?

መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና!
የሐዋ 4፤12

Wednesday, November 4, 2015

የመጽሐፍ ሕግ ይከበር!!!


ልሳን በሚነገርበት ጊዜ መጽሐፍ ቅዱሱ “በማኅበር መካከል ዝም ይበልና ለራሱና ለእግዚአብሔር ይናገር” እያለ (1ኛ ቆሮ 14፡28)፤ ፓስተር ዳዊት ደግሞ ያውም በመንፈስ ተመስጦ ሳይሆን ሰዓቱን እያየ በተናገረው ልሳን ላይ “እጅ ለእጅ ተያያዙ” እና “አንዴ ለሁለት ደቂቃ ሁሉም ሰው በልሳኑ ይጸልይ” በማለት ትእዛዝ አስተላለፈ፡፡ ሁሉም በማልሰማው ልሳን ይጮሁ ጀመር፤ ፓስተር ዳዊት እና መጽሐፍ ቅዱሱ የሚሉት ለየቅል ሆኖብኛል፡፡ ለመሆኑ በማኅበር መካከል ዝም ይበል እያለ የሚያዝዘው ትእዛዝ በእኛ ጉባኤ መቼ ነው የሚከበረው? ? ?
በመጽሐፍ ቅዱስ የሚነገር ልሳን እየተነገረን ከሆነ፤ እስቲ የፓስተር ዳዊትን ልሳን በ1ኛ ቆሮ 14፡27 “በልሳን የሚናገር ቢኖር ሁለት ወይም ቢበዛ ሦስት ሆነው በተራቸው ይናገሩ አንዱም ይተርጉም” ይላልና ትተረጉሙልኝ ዘንድ በትሕትና እጠይቃችኋለሁ ልሳኑ እነሆ፡-


1. አሞላቫንቶስሳክራቶሊያ
2. ሂላሞሪያማሳንቶኮትራቫሎዣንታ
3. ዚንትሮቪዲያሎማንቴስቴኬፕላዶራስ
4. ማዶሎሎስ ሲያማማንዶስሶኮዶጆኖሎሞስ
5. ኢንሞሎዲያናማሳንቶ
6. ኦላሪያማሴንታዲያካላቫሶንታ
7. ማርዶሎሞሲያናታኪቫ
8. ሃሊቮሪያማሳንቶ … ናሚያኖራሳንታ ….
9. ማትራቫዶላማንሳ
10. ሜሮቫንዶሶትራቮላ
11. አሪዞሞሜንቶኮትሬጅሪዮማንዴ
12. ዚልቮንቶቶድጄኔስቫፓሮዳ
13. አጉልቮኖንቴስቴቮዶሞሞንዶ
14. ሳልቬርኖማንቶሴትራዲያቮላ
15. ሀሞራማሺንዶሎሮሪያማንዳ
16. ዚላቮታካሮማንዲያላማሳ
17. አማሎናንቴኤልቬሌንቶስቶትሮቮሎኮዛ
18. አሙላዢቫዚያንዴ
19. ሪቫልዶሎትሮኮሎዞማንዳ
20. ኬልፕሮቫዶስ

መጽሐፍ ቅዱስ “አንዱም ይተርጉም” በሚለው መሠረት፤ ትርጉሙን በቁጥር በቁጥር ለሚተረጉምልኝ፤ አስቀድሜ ስለ ትብብሩ አመሰግናለሁ፡፡

Thursday, September 10, 2015

ቅዱሳን መላእክትና ቅዱሳን ሰዎች በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ መገኘት ይችላሉን?

ክፍል ሁለት
በክፍል አንድ ያቆምንበትን ሃሳብ ይዘን ከመቀጠላችን በፊት አንዳንድ ተቺዎች ባነሱልን ሞገት ዙሪያ ለዛሬ ጥቂት ማለት እንደሚያስፈልግ ስላመንን በዚያ ዙሪያ እንቆያለን።
 ሞጋቾቹ የሚያቀርቡት ማስረጃ በመዝሙር 34፤7 ላይ ያለውን ጥቅስ ነው።

«የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል»

ይህንን ጥቅስ በመያዝ ቅዱሳኑ መላእክት ሁልጊዜ በሰዎች ዙሪያ ሰፍረው ስለሚገኙ ማዳን፤ ጸሎት መቀበልና መልስ መስጠት የዘወትር ሥራቸው ነው ይላሉ። በሌላ ደግሞ መላእክት የሚኖሩበት ከተማ ኢዮር፤ ራማና ኤረር እንደሆነም ይናገራሉ። መላእክት ዘወትር በዚህ ምድር ባሉ ሰዎች ዙሪያ ሰፍረው የሚገኙ ከሆነ በኢዮር፤ ራማና ኤረር የሚኖሩት መላእክት ምንድናቸው? ወይስ መላእክት በሰማይም በምድርም በአንድ ጊዜ ይገኛሉ ማለት ነው? ተብለው ሲጠየቁ የመላእክትን ውሱን ተፈጥሮ ለማመን ይዳዳሉ። ነገር ግን በተግባር ይህንን ይቃረናሉ። ለምሳሌ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በተፈጥሮ ሥፍራው በሰማይ እያመሰገነ ሳለ በማእዘነ ዓለሙ ሁሉ ስሙን የሚጠሩትን  ሰዎች ልመና ይሰማል? መልስም ይሰጣል ወይ? ተብለው ሲጠየቁ አዎ ይሰማል ለማለት አያፍሩም። እንዲያማ ከሆነ ቅዱስ ሚካኤል በአንድ ጊዜ በሁሉም ሥፍራ ይገኛል ማለት ነው። ይህ ደግሞ ትልቅ ስህተት ነው። ፍጡር በተፈጥሮው ውሱን የመሆኑን ማንነት ይንዳል።

  እርግጥ ነው፤ ቅዱሳኑ መላእክት ሰዎችን ይራዳሉ፤ ያግዛሉ። ይህንን ስንል መጋቤ ፍጥረታትየሆነውን  እግዚአብሔርን በሥራ ያግዙታል ማለት አይደለም።  ይህች ያለንባት ምድር ትሁን ዓለማት በሙሉ የሚተዳደሩት በእግዚአብሔር ብቃትና ሥልጣን እንጂ በመላእክት አጋዥነት አይደለም። እግዚአብሔር ብቻውን በቂ ነው። ሁሉን ተአምራት የሠራ እርሱ ብቻውን ነው።
«እርሱ ብቻውን ታላቅ ተኣምራትን ያደረገ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና» መዝ 136፤4
የተአምራትና የድንቅ ነገር ሁሉ ባለቤት እግዚአብሔር ብቻ ነው። ስለሆነም መላእክቱ ከእግዚአብሔር ትእዛዝ አንጻር ያደረጉትን እያየን መላእክቱን በውዳሴና በስባሔ የምናቀርብላቸው አምልኮ የለም። ደግሞም ቅዱሳኑ መላእክት የሚኖሩባቸውን ዓለመ መላእክት ትተው በዚህ ምድር የሚዞሩበትም ሁኔታ እንዳለ መጽሐፍ ቅዱስ አይነግረንም። ይልቁንም ይህችን ምድር ያለመታከት የሚዞርባት ሰይጣን ብቻ ነው።
 ምክንያቱም ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጪ የፈረጠጠ እሱ ብቻ ስለሆነ ተቆጣጣሪ አልቦ ሆኖ ይኖራል። በራሱ ፈቃድ የት፤ የት እንደሚዞር ለፈጣሪው እንዲህ ሲል እናገኘዋለን።
«እግዚአብሔርም ሰይጣንን፦ ከወዴት መጣህ? አለው። ሰይጣንም፤ ምድርን ሁሉ ዞርሁአት፥ በእርስዋም ተመላለስሁ ብሎ ለእግዚአብሔር መለሰ» ኢዮብ 1፤7
ምድርን ለመዞር፤ በእሷ ላይም ለመመላለስ ፈቃድ አይጠይቅም። «ከወዴት መጣህ?» የሚለው የእግዚአብሔር ጥያቄ የሚያስረዳን አፈንጋጭና በፈቃዱ ያለትእዛዝ የሚዞር መሆኑን ነው። ቅዱሳን መላእክቱ ግን እንደዚህ አይደሉም። በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ሥራ አላቸው፤ ትእዛዝ ይቀበላሉ፤ ትእዛዝ ይተገብራሉ እንጂ እንደሰይጣን በሰዎች ስለተጠሩ ወይም ባይጠሩም ስለፈለጉ የትም አይዞሩም፤ ያለትእዛዝም አይንቀሳቀሱም። በሁሉም ሥፍራም በምልዓት አይገኙም።

  መጽሐፍ ቅዱስ በትንቢተ ዳንኤል ላይ የመላእክትን ውሱንነት፤ መውጣት፤ መውረድ በደንብ የሚያስረዳን ቃል እንዲህ ይላል።
«እነሆም፥ አንዲት እጅ ዳሰሰችኝ፥ በጕልበቴና በእጄም አቆመችኝ። እርሱም፦ እጅግ የተወደድህ ሰው ዳንኤል ሆይ፥ እኔ ዛሬ ወደ አንተ ተልኬአለሁና የምነግርህን ቃል አስተውል፥ ቀጥ ብለህም ቁም አለኝ። ይህንም ቃል ባለኝ ጊዜ እየተንቀጠቀጥሁ ቆምሁ። እርሱም እንዲህ አለኝ። ዳንኤል ሆይ፥ አትፍራ ልብህ ያስተውል ዘንድ፥ ሰውነትህም በአምላክህ ፊት ይዋረድ ዘንድ ካደረግህበት ከመጀመሪያው ቀን ጀምሮ ቃልህ ተሰምቶአል እኔም ስለ ቃልህ መጥቻለሁ። የፋርስ መንግሥት አለቃ ግን ሀያ አንድ ቀን ተቋቋመኝ እነሆም፥ ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ እኔም ከፋርስ ነገሥታት ጋር በዚያ ተውሁት» ዳን 10፤10-13
ነቢዩ ዳንኤል ያከናወነው መንፈሳዊ ተጋድሎ በእግዚአብሔር ዘንድ ስለተወደደ ስሙ ያልተጠቀሰ አንድ መልአክ የተሰጠውን መልእክት ሊነግረው መጥቷል።   መልእክቱ ለዳንኤል ከመድረሱ በፊት የፋርስን መንግሥት የተቆጣጠረው የተቃዋሚ መንፈስ አለቃ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከውን መልአክ 21 ቀን መንገድ ላይ እየተዋጋ አዘግይቶታል። ያንንም የእግዚአብሔር መልአክ ሊያግዘው ቅዱስ ሚካኤል እንደመጣና ውጊያው ከቅዱስ ሚካኤል በዚያ እንደተወውና ወደእርሱ እንደወረደ መልአኩ ለቅዱስ ዳንኤል ሲነግረው እናነባለን።

ከዚህ ምንባብ የምንረዳው ፤
1/ መላእክት የሰዎች መልካም ሥራና ተጋድሎ በእግዚአብሔር ሲወደድ የማናውቀው መልአክ ሊረዳን፤ ሊያግዘን፤ ሊያድነን ከእግዚአብሔር ዘንድ ሊላክ እንደሚችል፤
2/ መላእክቱን ለእገዛና ለረድኤት የሚያመጣቸው የኛ ስራ በመላእክቱ ዘንድ ተቀባይነትና ተወዳጅነት በማትረፉ እንዳልሆነ፤
3/ አንድ መልአክ ወደተላከበት ስፍራ ሲሄድ የነበረበትን ሥፍራ እንደሚለቅ፤ በቦታ እንደሚወሰን፤ ባለጋራ ሊዋጋው እንደሚችል፤
4/ መላእክት እንደሚተጋገዙ፤ አንዱ ከአንዱ በኃይልና በሥልጣን እንደሚበልጥ፤
5/ መውጣትና መውረድ እንዳለባቸው፤ በሁሉም ስፍራ እንደማይገኙ ያስረዳናል።
ስለሆነም ቅዱሳን መላእክት ይራዱናል፤ ያግዙናል፤ ያድኑናል ሲባል ሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር ባላቸው ግንኙነት የተነሳ በተልእኮ ሲመጡልንና ሲደርሱልን ብቻ ነው። ከዚያ ባሻገር ሰዎች ስም እየመረጡ፤ የኃይል ሚዛን እያበላለጡ ስለጠሯቸው የሚመጡ አይደለም።
እነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች የሚያስረዱን በእግዚአብሔር ትእዛዝ የሚላኩ መሆናቸውን ነው።
«የሰማይ አምላክ እግዚአብሔር፥ እርሱ መልአኩን በፊትህ ይሰድዳል» ዘፍ 24፤7  «እግዚአብሔር መልአኩን ከአንተ ጋር ይልካል፥ መንገድህንም ያቀናል»ዘፍ 24፤40  «እግዚአብሔርም መልአኩን አዘዘው፥ ሰይፉንም በአፎቱ ከተተው» 1ኛ ዜና 21፤27  «እግዚአብሔርም ጽኑዓን ኃያላኑንና መሳፍንቱን አለቆቹንም ከአሦር ንጉሥ ሰፈር እንዲያጠፋ መልአኩን ሰደደ» 2ኛ  ዜና 32፤21  «መልአኩን የላከ፥ ከአምላካቸውም በቀር ማንም አምላክ እንዳያመልኩ» ዳን 3፤28  «አምላኬ መልአኩን ልኮ የአንበሶችን አፍ ዘጋ» ዳን 6፤22
አምላክ፤ ወልደ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ የማልኮስን ጆሮ ለቆረጠው ጴጥሮስ እንዲህ ብሎት ነበር። «
«ወይስ አባቴን እንድለምን እርሱም አሁን ከአሥራ ሁለት ጭፍሮች የሚበዙ መላእክት እንዲሰድልኝ የማይቻል ይመስልሃልን?» ማቴ 26፤53
 ለኢየሱስ በስቅለቱ ሰሞን የመያዝ፤ የመገፋት፤ የመንገላታት የመገረፍ መከራ ሁሉ ከአብ ዘንድ ትእዛዝ ሳይወጣ የሚያግዙት መላእክት አይመጡም ነበር። ፈቃዱን ሳይሆን የአብን ፈቃድ ለመፈጸም የመጣውም ይህንን ሁሉ ሊቀበል ነውና። ከዚህ ከኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት የምንረዳው እውነታ ቅዱሳን መላእክቱ ከአብ ትእዛዝ ሳይሰጣቸው የትም መሄድ የማይችሉት ወልድ የመጣው የአብን ፈቃድ ሊፈጽም ስለሆነ ነው። ተገቢ ለሆነው የሰዎች ልመናና ጸሎት የሚያስፈልገውን የሚያደርገው ሁሉን አዋቂ በሆነው በእግዚአብሔር ትእዛዝ ሲላኩ ብቻ ነው።
የሰዎች ድርሻ ወደእግዚአብሔር መጮኽና መለመን ሲሆን ምላሹን ደግሞ የሚያውቀው እርሱ ብቻ ነው። «መላእክቱን በስማቸው ስንለምንና ስንማጸናቸው ይሆንልናል፤ ይደረግልናል»የሚሉ ሰዎች ቆንጽለው የሚያቀርቧት የመዝሙር 34፤7 ጥቅስ «የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል» የሚለውን ነጥለው በማውጣት ቢሆንም የዚህ አጋዥ መከራከሪያ ጥቅስ ሙሉ ማስረጃ ግን ከላይ ከፍ ባለው ቁጥርና ከታችም ዝቅ ብሎ በተጻፈው የምንረዳው፤ እግዚአብሔር ላይ ብቻ እንድንታመን የሚያደርጉ ናቸው። ሙሉ ጥቅሱ ይህንን ይመስላል።
«ይህ ችግረኛ ጮኸ፥ እግዚአብሔርም ሰማው፥ ከመከራውም ሁሉ አዳነው።
የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል።
እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ እዩም በእርሱ የሚታመን ሰው ምስጉን ነው።
የሚፈሩት አንዳችን አያጡምና ቅዱሳኑ ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ፍሩት» መዝ 34፤ 6-9

ነቢዩ ዳዊት በደረሰው ችግር ወደእግዚአብሔር ጮኸ፤ እግዚአብሔርም ሰማው፤ ከመከራውም አዳነው። የእግዚአብሔርም መልአክ እግዚአብሔርን በሚፈሩ ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፤ በታዘዘም ጊዜ ያድናል። ምክንያቱም በእግዚአብሔር የሚታመኑና እሱንም የሚፈሩት አንዳች አያጡምና። ቁጥር 8 እና 9  በእግዚአብሔር መታመንና መፍራትን ገንዘብ ያደረጉ ሁሉ ምላሽ እንደሚያገኙ ያስረዳናልና።

«ቅዱሳን መላእክቱ በዚህ ምድር እየዞሩ ለሰዎች የሚራዱና የሚያግዙ በመሆናቸው በስማቸው የሚደረገውን የሰዎችን ልመናና ጸሎትም ይሰማሉ» የሚል ክርክር የሚያነሱ ሰዎች መላእክቱ በቀጥታ ታዘው ያደረጉትን መነሻ በማድረግና በማድነቅ እንጂ ቅዱሳኑ መላእክት ራሳቸው ምሥጋናንና ውዳሴን ተገቢያቸው እንደሆነ ሽተው እግዚአብሔርን ከሚያውቁ ሰዎች ሲቀበሉ አናይም። እንዲያውም በራእይ መጽሐፍ ላይ እንደምናነበው ቅዱስ ዮሐንስ፤ እግዚአብሔር በመልአኩ በኩል ስላደረገለት፤ ስለነገረውና ስላሳየው ነገር ሁሉ በፊቱ ወድቆ በሰገደ ጊዜ የተሰጠው ማስጠንቀቂያ እንዲህ የሚል ነበር።

«ልሰግድለትም በእግሩ ፊት ተደፋሁ። እርሱም፦ እንዳታደርገው ተጠንቀቅ፤ ከአንተ ጋር የኢየሱስም ምስክር ካላቸው ከወንድሞችህ ጋር አብሬ ባሪያ ነኝ፤ ለእግዚአብሔር ስገድ፤ የኢየሱስ ምስክር የትንቢት መንፈስ ነውና አለኝ»       ራእ 19፤10
ዛሬ ግን ሰዎች «ለእግዚአብሔር ስገድ» የሚለውን የመልአኩን የማስጠንቀቂያ መልእክት ወደጎን ትተው «ለመልአኩም ስገድ» እያሉ ሲሰብኩ ይገኛሉ። መልእክት አድራሹ መልአክ ከዮሐንስ በተሻለ ስለመልእክቱ ምንነት እውቀት እንዳለው እርግጥ ነው። ከዐውደ ንባቡ እንደምንገነዘበውም ስለመልአኩ ቢያንስ ሁለት ዐበይት ነገሮችን እንረዳለን። አንድ፤ መልእክቱን በቀጥታ ከእግዚአብሔር እየሰማ ለዮሐንስ የሚያደርስ መሆኑን። ሁለትም፤ መልአክቱ ከዮሐንስ ዘንድ ከመድረሱ በፊት በመልአኩ ዘንድ የተሰማና የታወቀ መሆኑን ነው። ስለሆነም ዮሐንስ ስግደትን ለመልአኩ መስጠት የፈለገው መልአኩ የፈጣሪ የቅርብ ባለሟል በመሆኑና የሚያየውን ግርማ በመፍራት እንዲሁም ይዞለት የሚመጣው መልእክቶቹ እጅግ ከባድና ከዚህ በፊት በሕይወቱ ሰምቶአቸው የማያውቅ ከባድ የሕይወት ልምምድን የሚያሳዩ በመሆናቸው የተነሳ እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል።
ስለዚህ «ተጠንቀቅ» ያለውን ቃል መጠበቅ ብልህነት ነው።
ክፍል ሦስት ይቀጥላል …..