Wednesday, April 12, 2017

«አሮጌውን እርሾ አስወግዱ፤ ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአልና»

Saturday, April 



(በድጋሚ የቀረበ)

ዕብራውያን     פֶּסַח «ፔሳኽ» ይሉታል። ፋሲካ ማለት ነው።  በወርኀ ኒሳን በዐሥራ ዐምስተኛው ቀን ይከበራል። ሥርዓቱ የሚጀመረው በዐሥራ አራተኛው ቀን ዋዜማ ሲሆን በፋሲካው ሳምንት እርሾ የገባበት ምንም ዓይነት ምግብ መመገብ ክልክል ነው።ዕለቱን ተቦክቶ ወዲያው የሚጋገር እንጂ የኮመጠጠ ወይም የቦካና የዋለ፤ያደረ መመገብ በሕጉ እንደተቀመጠው ከእስራኤል አንድነት ያስወግዳል። ከማንኛውም እርድ ላይ ጥሬ መብላት ወይም ከበሉትም አስተርፎ ማሳደር አይፈቀድም። ለመስዋዕት የሚቀርበው የበግ ወይም የፍየል መስዋዕትም እድሜው ከአንድ ዓመት ያልበለጠ ጤናማና የተመረጠ መሆን ይገባዋል። በዐሥራ ዐራተኛው ቀን ምሽት መስዋዕቱ ይታረዳል።ሥጋውን ደግሞ ሌሊት  ከመራራ ቅጠል ጋር ቀላልቅለው ይበሉታል። 
ደሙን ደግሞ  የበሩን ሁለት ረድፍ «መቃንና ጉበኑን» ይቀቡታል።  ሁለቱን ቋሚ መቃንና የላይኛውን ጉበን ሲቀቡት ይህንን ቅርጽ ይይዛል።


ይህ ቅርጽ የዕብራውያን ስምንተኛውን ፊደል «ኼ» የተባለውን ይወክላል። (እንደአማርኛው በጉሮሮ ሳይሆን በላንቃ የሚነበብ ነው) «ኼ» ማለት በዕብራውያን ትርጉም «ሕይወት» ማለት ነው። ዕብራውያንም በፊደላቸው በ«ኼ» ቅርጽ በሚቀቡት ደም የተነሳ ወደፈርዖናውያን ሠፈር የሚያልፈው ሞት አይነካቸውም። ምክንያቱም ሕይወት የሚል ማኅተም በራቸው ጉበንና መቃን ላይ ታትሟልና። ፋሲካ ማለት ይህ ነው። በደሙ ምልክት የተከለሉ በሕይወት ለመቆየት ዋስትና የያዙ ሲሆን ይህንን ማኅተም ያላገኙና ምን እየሆነ እንዳለ የማያውቁ ደግሞ  በሞት የሚወሰዱበት  የፍርድ ምልክት ነው። ደሙ የሞትና የሕይወት መለያ ምልክት ሆኖ አገልግሏል።
ይህ ሥርዓት እስራኤላውያንን ከባርነት፤ ከጠላት አገዛዝና ከመገደል የታደገ የዋስትና መንገድ ነበር። እንደዚሁ ሁሉ የአዲስ ኪዳኑ ፋሲካ ሕዝብና አሕዛብን ከሰይጣን ባርነትና ከዘላለም ሞት የታደገ በመሆኑ ሐዋርያው ጳውሎስ «እንግዲህ ያለ እርሾ እንዳላችሁ አዲሱን ሊጥ ትሆኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ አስወግዱ። ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአልና» 1ኛ ቆሮ 5፤7 በማለት የሚነግረን።  አሮጌውን እርሾ ካላስወገድን ፋሲካችን የሆነውን ክርስቶስ መቀበል አይቻልም። የክርስቶስን ፋሲካ እካፈላለሁ በማለት የበዓሉን አከባበር ማድመቅ፤ እንኳን አደረሰህ/አደረሰሽ መባባል ልምድ እንጂ የመለወጥ ምልክት አይደለም። የክፋት እርሾ የተባሉትን ሐዋርያው ጳውሎስ በቆሮንቶስ መልእክቱ ሲነግረን እንዲህ ይለናል። «ሴሰኛ፤ ገንዘብን የሚመኝ፤ ወይም ጣዖትን የሚያመልክ፤ ወይም ተሳዳቢ ወይም ሰካር ወይም ነጣቂ» ከመሆን መታቀብ ብቻ ሳይሆን ከሆኑትም ጋር አብሮ ባለመብላት ጭምር በመከልከል ከአሮጌው እርሾ ሆምጣጣነት መራቅ እንዲገባን ያስፈልጋል። (1ኛ ቆሮ 5፤11) የእስራኤል ዘሥጋ ፋሲካ መጻጻና የቦካ ይከለክል እንደነበረው ሁሉ የአዲስ ኪዳኑ ፋሲካም እንዲሁ ይከለክላል። በኃጢአትና በዐመጻ የቦካ የውስጣችንን ሆምጣጣ እርሾ ካላስወገድን በስተቀር በፋሲካው የሚገኘውን ሕይወት በፍጹም  አናገኝም።  የቀደመው ፋሲካ እርሾ ያለውን ነገር ከቤቱ ያላጠፋ «ከእስራኤል ጉባዔ ተለይቶ ይጥፋ» የሚል ሕግ ነበረው።  ምድራዊው ፋሲካ ይህንን ያህል ከከበረ ሰማያዊውማ እንደምን የበለጠ አይከብር? ፋሲካን መናገርና ፋሲካን አውቆ መኖር የተለያዩ ነገሮች ናቸው። ስለፋሲካ ብዙ ማስተማርና መናገር ይቻል ይሆናል። ስለፋሲካ የመልካም ጊዜ መግለጫና ስጦታም መለዋወጥ ይቻል ይሆናል። ፋሲካን ማክበር ማለት 2 ወራት በጾም አሳልፎ «እንኳን ጾመ ልጓሙን ፈታልህ/ፈታልሽ» ተብሎ ልጓም አልቦ የመሆኛ ሰዓት ደረሰ በማለት የሰላምታ መሰጣጣት ፕሮግራም አይደለም። ጾሙ ሲፈታ እንደፈለገን ልንበላ፤ ልንጠጣ፤ ልንናገር የልጓም አጥራችን ተከፈተ ማለት ከሆነ በአሮጌው እርሾ ብቻ ሳይሆን ከሰው የልማድ ስርዓት ጋር እንኖራለን ማለት ነው። የክርስቶስ ፋሲካ ግን በእነዚህ ሁኔታዎች ውስጥ አይገኝም። ፋሲካ በስግደትና በወይራ ቅጠል በመጠብጠብ የሚገኝም ጸጋ አይደለም።  ፋሲካ የአንድ ወቅት ራስን ማስገዛትና በጽኑ እሳቤና ጭንቅ ማለፍ ውስጥ የሚመጣም አይደለም።
ፋሲካ በልባችን መቃንና ጉበን ላይ የደሙን ምልክት በመያዝ ዕብራውያን ከሞት እንዳመለጡበት የ «ኼ» ምልክት ማኅተም በመያዝ ብቻ ነው የምንድነው። ያን ጊዜ ብቻ ነው ሞት በራችን ላይ ያለውን የአዲስ ኪዳኑን «ፔሳኽ» አይቶ የሚያልፈው። ይህንን የደም ማኅተም ለመያዝም ከክፋት፤ ከሀሰት፤ ከግፍና ከዐመጻ እርሾ መለየት የግድ ነው። ከዝሙት፤ ከስርቆት፤ ከጉቦ፤ ከምኞትና ከኃጢአት ሁሉ እርሾ ሳንለይ ውስጣችን የሞላውን መጻጻ ተሸክመን የፋሲካ ሕይወት የለም። እስራኤላውያን መዳን የቻሉት የፋሲካቸውን የበግ ደም ምልክት በመያዛቸው ብቻ ነው።  እኛም የአዲስ ኪዳኑ የእግዚአብሔር በግ የክርስቶስን ደም ምልክት ካልያዝን በማንም በሌላ ምልክት ወይም ጻድቅ ዋስትና ልንድን አንችልም። ሁሉም ይህንን የደም ምልክት የመያዝ ግዴታ ስላለበት ማንም ለማንም ዋስትና ሊሆን እንደማይችል ጳውሎስም «ልዩነት የለም፤ ሁሉም የመዳን ጸጋ ያስፈልገዋል» አለን። 

«እርሱም፥ ለሚያምኑ ሁሉ የሆነ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኘው የእግዚአብሔር ጽድቅ ነው፤ ልዩነት የለምና፤ ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል፤በኢየሱስ ክርስቶስም በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ» ሮሜ 3፤22-24
እንግዲህ  ከፋሲካው ተስፋ የምናደርግ ሁላችን እስኪ ራሳችንን እንመርምር። እንደመጽሐፍ ሊያነበን በሚቻለው ከፋሲካችን ክርስቶስ ፊት እስኪ ራሳችንን እናንብበው። በእውነት እነዚህ እርሾዎች በውስጣችን ከሌሉ ከ2000 ዓመት በፊት ለሕይወት የፈሰሰውን ደም ይዘናል ማለት ነው። ያኔም ሞት በኛ ላይ ምንም ሥልጣን እንደሌለው አረጋግጠናል። እስራኤላውያን የበራቸውን ጉበንና መቃን በቀቡ ጊዜ ሞት እንደማይነካቸው እርግጠኞች እንደነበሩ ሁሉ እኛም የበለጠውንና የተሻለውን የሕይወት ደም በእምነት ስለያዝን ለዘላለማዊ ሕይወት እርግጠኞች መሆን እንችላለን። ከዚያ ባሻገር በየዓመቱ በሚመጣ በዓል የሚገኝ የደም ምልክት የለም። በጥብጠባና በስግደትም የሚገኝ የሕይወት ዋስትና እንዳለ ካሰብን የፋሲካውን ምስጢር በልምድ ሽፋን ስተነዋል ማለት ነው። የተደረገልንን ማሰብ አንድ ነገር ሆኖ ሰው ግን ዓይኑን በዚያ በዓል ላይ ተክሎ የዓመቱ ኃጢአት ወይም ሸክም እንደሚወድቅ ማሰብ ስህተት ነው። ዓመቱን ሙሉ ከክፋትና ከግፍ እርሾ በመላቀቅ፤ ለአንድም ሰከንድ የማይለይ ምልክት ልባችን ጉበንና መቃን ላይ ደሙን በእምነት ይዘን መገኘት የግድ ይሆንብናል። ያኔ ነው ፋሲካችን ታርዷል የምንለው። ያኔም ነው ሁልጊዜ በሕይወት መንገድ ላይ እንዳለን የምናውቀው። መንፈሳዊ ሕይወት እንዲኖረን፤ መንፈሳዊ ጉዞ እንዲሰምርልን ዕለት፤ ዕለት መታደስ መታደስ ይገባዋል።
«ስለዚህም አንታክትም፥ ነገር ግን የውጭው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳ የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል» 2ኛ ቆሮ 4፤16 ንስሐ እንግባና እንታደስ።
ፋሲካችን የሆነው ክርስቶስ ኢየሱስ ያደረገልንን ውለታ እያሰብን ውስጣችንን መፈተሽ የግድ ነው። በአምናው እኛነታችንና በዘንድሮው እኛነታችን መካከል የሕይወት ለውጥ ከሌለን ሞት በመጣ ጊዜ ምንም የመዳን ምልክት እንደሌላቸው ፈርዖናውያንን ወደዘላለማዊ ሞት መሄዳችን እውነት ነው። በወይራ በመጠብጠብ 30 እና 40 ለመስገድ ከመሽቀዳደም ይልቅ፤ ከሞት የማምለጫ የፋሲካው ዓርማ ክርስቶስን ከኃጢአት በጸዳ ማንነታችን ውስጥ ዘወትር ይዘነው እንኑር። ዝሙት፤ ውሸት፤ስርቆት፤ ሃሜት፤ ነቀፋ፤ ምኞትና ገንዘብን መውደድ ሁሉ ሳንተው ፋሲካን ማክበር አይቻልም። ከቦታ ቦታ በመዞርም ፋሲካ አይገኝም። ፋሲካ በልባችን ላይ አንዴ የተሰራው የክርስቶስ የእምነታችን ከተማ ነው። በዚያ ላይ የማይጠፋ ብርሃን አለ። ክርስቶስ ባለበት በዚያ የልባችን ከተማ ውስጥ ማስተዋል፤ ደግነት፤ በጎነትና ቅንነት አለ። ከዚያ መልካም ከተማ የሚወጣው ሃሳባችን የተራቡትን ያበላል፤ የታረዙትን ያለብሳል፤ የታመሙትን ይጠይቃል። ኑሮአችን፤ አነጋገራችንና አካሄዳችን በልክ ነው። ዕለት ዕለት በምንኖረው ሕይወት እንጂ በዓመት አንድ ቀን በሚከበር ፋሲካ ክርስቶስን መምሰል አይቻልም። ሞት የደሙ ምልክት የሌለባቸውን እስራኤላውያንን ሁሉ ይገድል ነበርና። እኛም በሰማይ የተሰጠንን ተስፋ እስክናገኝ ድረስ ሞት ከተጠበቀልን ተስፋችን እንዳያስቀረን ፋሲካችን ክርስቶስን ዕለት ዕለት በልባችን ይዘን እንኖራለን። ያኔም በክርስቶስ ያለ ተስፋችን ምሉዕ ስለሆነ ስለመዳናችን አንጠራጠርም። አብርሃም ልጅ ሳይኖረው «ዘርህ ዓለሙን ይሞላል» ሲባል በእምነቱ ተስፋውን ተቀበለ። በክርስቶስ ትንሣዔ ያመንን እኛ ደግሞ እንደምንድን ካመን የተሰጠን የመዳን ተስፋ በሰማይ እውነት ሆኖ ይጠብቀናል።  ምክንያቱም የመዳናችን የእምነት ተስፋ ክርስቶስን በልባችን ዕለት ዕለት ይዘን እንዞራለንና!!