Saturday, April 29, 2017

"ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ" የብርሃኑ አድማሴ የቃላት ዝላይ

የአለት ላይ ዝላይ አያዋጣም!

"ወደ አምላኬና ወደ አምላካቸሁ"
ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በስብከቶች እየተፈራ የሚዘለል የእግዚአብሔር ቃል
+++++++++++++++++++++++++++++++++++++
ሰሞኑን በየቤተክርስቲያኑ ዐውደ ምሕረት የሚነገረው ወንጌል ስለ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ቢሆንም የማቅ ሰባክያነ ወንጌል ተብዬ እንደነ ተስፋዬ ሞሲሳ (ተስፋዬ ስለቃሉ ሞዛዛ) እና ብርሃኑ አድማሴ (ብርሃኑ ቃሉን ደርምሴ) እየዘበራረቁም ቢሆን ተያይዘውታል።
የእግዚአብሔርን ቃል እየቀነሱ እና እየዘለሉ ማስተማር ምን የሚሉት ፈሊጥ ነው?
ጌታ ኢየሱስ ከሙታን መካከል ከተነሳ በኋላ በዮሐ 20፥17 ማርያምን አትንኪኝ አላረኩምና ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሄደሽ፦ እኔ ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ አርጋለሁ ብለሽ
ንገሪአቸው እንዳላት በግልፅ ተፅፎ ሳለ እነዚህ የማቅ አቀንቃ  የክርስቶስ ሰው መሆኑ እንዳበቃ አርገው ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ የሚለውን እየዘለሉ በድፍረት መናገራቸው ያሳዝናል።
ሰው በመሆኑ መከራን ተቀበለ እንጂ ለዘላለም ስጋን ተዋህዶ ይኖራል ብሎ እንደተናገረው ቅዱስ አትናቴዎስ። ሞትን ድል ነስቶ በአብ ቀኝ የተቀመጠው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዛሬም ለዘላለም የማይለወጥ ፍፁም ሰው: ፍፁም አምላክ ነው (ሃይማኖት አበው 1986 ገፅ 80/ ዕብ 13፥8)
ክርስቶስ በአብ ቀኝ ከተቀመጠ በኋላ የሰውነቱን ግብር አቁሞ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር መለኮታዊ ስራውን እየሰራ ይገኛል ብሎ መስብኩ የክርስቶስን መካከለኛነት መቃወም ብቻ ሳይሆን ይኼ አባባል ኢየሱስ በአባቱ ቀኝ እስኪቀመጥ ድረስ መለኮት ስራውን ለስጋ ትቶ ስጋ ብቻ ይሰራ ነበር። አሁን በተራው ሰራውን ስለፈፀመ ስራውን ለመለኮት አስረከበ እንደማለት ነው። ይህ አባባል ደግሞ ሲያረግ ሥጋውን በመለኮት ባህርይ አረቀቀው: መጠጠው የሚለውን የአውጣኪን የክህደትአስተምህሮ መቀበል ይሆናል። ዳሩ ይኄ ስብከት በብዙዎቹ ሰባኪያን ዘንድ ሲነገር ይሰማል። መለኮታዊ ሥልጣኑን በመጠበቅ ሲባል በሥጋ ማረጉን በርቀት ይከላከላሉ። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በኦፊሴል አውጣኪን ብታወግዝም አስተምህሮውን በስልት ትቀበላለች። የምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት አውጣኪያውያን ናችሁ የሚሏትም አለምክንያት አይደለም። የኢየሱስን እርገት የኢት/ኦር/ ቤተክርስቲያን የምትቀበለው በመለኮታዊ ባህርይ ብቻ እንጂ ዛሬም በሥጋው በአብ ቀኝ እንዳለ አይደለም ማለት ነው? በሥጋው አርጓል የምትል ከሆነም በሥጋው የማረጉን ምክንያት በድፍረት ልታስተምር ይገባታል። ከኃጢአት ለመንጻትም ሆነ ሕይወት ወደሆነው ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት አዲስ አማኝ ለመምጣት በስጋው ቀራንዮ ላይ አንዴ በፈፀመው ድኅነት ስለእኛ አሁንም በሰማይ በአብ ይታይ ዘንድ በስጋው አለ ልትል ይገባታል። መለኮት ቃሉ ብቻ ማዳን እየተቻለው ሥጋ የለበሰው በሥጋ ያጣነውን ክብር በልጁ በኩል ልጅነትን እንድናገኝና በሰማያዊ መቅደስ የመግባት ድፍረት እንድናገኝ ስለፈለገ ብቻ ነው።
ይህንንም ሐዋርያው እንደዚህ አስረግጦ ይነግረናል።

" ክርስቶስ በእጅ ወደ ተሰራች፥ የእውነተኛይቱ ምሳሌ ወደ ምትሆን ቅድስት አልገባምና፥ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ አሁን ይታይ ዘንድ ወደ እርስዋ ወደ ሰማይ ገባ።"
(ዕብራውያን 9:24)
ከዚህ ውጪ የሆነው ሁሉ ፍፁም ሰው ፍፁም አምላክ መሆኑን የሚያስክድ ነው።
ኢየሱስ የመጣበትን በእያንዳንዳችን ፈንታ በመስቀል ላይ የማዳንን ስራ ፈፅሞ ሞቶ ከተነሳ በኋላ አምላኬ ማለቱ የማቅን ሰባኪያን አባባል ገደል ከቶታል።
ለዚህም ሃይማኖት አበው 1986 ገፅ 248 እንዲህ ሲል ይመሰክራል
" እኔ ሰው የሆንኩ አምላክ ነኝና እኔም አንድ ነኝና ይህንንም ያንንም እኔ እላለው ይላል፣ የሰውን ባህሪይ ገንዘብ አድርጌአለውና። ኋጢአት የሌለበት እርሱ እኔ ነፍስን ስጋን ተዋህጃለውና ከእኔ ጋር አንድ ላደረኩት ለስጋ ስርዓት እንደሚገባ እንዲህ አባቴን "አምላኬ" ብዬ ጠራሁት "
እናም ተወዳጆች ሆይ ጌታ ኢየሱስ እንዴ ለዘላለም ባፈሰሰው ደስ ዳግም ማፍሰስ ሳይጠበቅበት ሁል ጊዜ ሲያነፃን ይኖራል። እግዚአብሔር እኛን የሚያይበትብቸኛው መንገድ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው።
"የልጁም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል።" 1ኛ ዩሐ 1፥7
ያለፍርሃት የጌታ ምስክሮች እንሁን እኔ ይህን ታዘብኩ እናንተም እስኪ የማቅን ሰባኪያንን የሚፈሩትንና የሚዘሉትን ቃል ንገሩንና ለመማማር እንወያይበት።
የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ፀጋ የእግዚአብሔርም ፍቅር የመንፈስ ቅዱስም ህብረት ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን