Sunday, May 8, 2016

የፊልም አክተር እንጂ ክርስቶስ አይደለም!!


 በኢትዮጵያ ውስጥ ግን አብዛኞቻችን "የኢየሱስ ክርስቶስ" የመሰለንን ፎቶ በየቤታችን ግድግዳ ለጣጥፈናል። ምንም እንኳን በመለጠፉ ረገድ ኦርቶዶክሳዊያን ቢያይሉም፥ ካቶሊኩም፣ ጴንጠውም፣ ሞርሞኑም፣ ጂሆባውም፣ አድቨንቲስቱም በቃ ሁሉም ለማለት በሚያስደፍረኝ መልኩ በቤቱ ግድግዳ ላይ ወይም የሆነ የሆነ ነገሩ ላይ ለጥፏል። ለምሳሌ በስቲከር መልክ መኪናው ውስጥ፤ ባጃጅ ውስጥ፤ ላፕቶፕ ላይ፤ የሞባይል ስልኩ ላይ እና በመሳሰሉት ላይ ለጥፏል። በነዚህ ሁሉ ባይለጥፍ ደግሞ በየዓመቱ የትንሣኤ በዓልን በማስመልከት የፌስቡክ ግድግዳው ላይ መለጠፉን አይተውም። ከፎቶውም ግርጌ ከሚጻፉ ጽሑፎች መካከል "ያዳነኝ ይኼ ነው፤ የሞተልኝ ውዴ ይኼ ነው፤ የሕይወቴ ትርጉም ይኼ ነው.. ይኼ ነው.. ይኼ ነው" የሚል ይበዛበታል።

   ለመሆኑ ይኽ የሚለጠፈው ፎቶ አንዳንዶች እንደሚሉት ለሰው ልጆች ኃጢአት የሞተው የኢየሱስ ክርስቶስ ፎቶ ነው? እውነታው ግን አይደለም! የኢየሱስ ክርስቶስ ሳይሆን የጂም ካቪዘል መሆኑ መታወቅ አለበት። በመሠረቱ ወንጌልን ለማስረዳትና ለማስተማር ኢየሱስ ክርስቶስን የሚመስል ሰው ማዘጋጀት ነፍሴ ከማትቀበለው ድርጊት መካከል አንዱ ነው። ምክንያቱም እምነት በጆሮህ ሰምተህ፣ በልብህ አምነህ የምትቀበለው እንጂ በሚመስል ነገር ማረጋገጫ ወይም የበለጠ ስዕላዊ ማሳመኛ ሲቀርብልህ “ለካ እንደዚህ ነው?” ብለህ ተደንቀህ፣ የምትቀበለው የማስታወቂያ ውጤት አይደለም። ፊልም ሠሪዎች ገበያቸው ስለሆነ ግድ ላይሰጣቸው ይችላል። ለኔ ለአማኙ የኢየሱስ አዳኝነት በወንጌል ቃል እንደተጻፈው እውነት መሆኑን አምኜ እቀበለዋለሁ እንጂ በጭራሽ እርሱን ሊወክል በማይችል ሰው ትወና ሳለቅስና አንጀቴን ሲበላኝ የማረጋግጠው የፊልም ጥበብ ለውጥ አይደለሁም። ለዚያ ስዕልና ምስል መንበርከክም አይገባንም የምንለው።

ኢየሱስ ምን መልክ አለው? ደም ግባት የሌለው ሆኖልናል ወይስ የአገልጋይና የባርያን መልክ? የውበቱ ነፀብራቅ የሚያበራ ውብ ነው? ወይስ የሕማም ሰው? እኮ የትኛውን ይመስላል። ደቡባዊ አፍሪካውያን ኢየሱስን ጥቁር አድርገው ይስላሉ። ኢትዮጵያውያንም በሚችሉት አቅም የመሰላቸውን ለመሳል ሞክረዋል። በኢየሱስ ላይ ተሳልቆና ፀያፍ ስድብ የጻፈው ሊኦናርዶ ዳቬንቺ ባቅሙ በምሴተ ሐሙስን የነበረውን ሁኔታ ለማስቀመጥ የሞከረበትን ስዕል በየቤታችንና ቤተመቅደሱ ሰቅለናል። ዳቬንቺ በኢየሱስ ላይ የተናገረው ምንድነው? “The Davenci Code” ያነበበ ሰው ከክፉ ሥራው ተባባሪ ሆኖ ዳቬንቺ የሳለውን ስዕል ይቀበል ነበር?




   አንዳንዴ ሀበሻ እያየ ለምን እንደሚታወር፤ እየሰማ ለምን እንደሚደነቁር ግራ ይገባኛል። ይህንን ሰውየ "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" በሚባል ፊልም ላይ ስንመለከተው ኖረናል። በዕድሜአችን በሰል ስንል ግን፥ አንድ ተራ አሜሪካዊ ፊልም ሰሪ መሆኑን አለመገንዘባችን እጅግ ያሳዝናል!! በተለይ ደግሞ በኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ዘንድ ዛሬም ድረስ ሰውየው የኢየሱስ ክርስቶስን ቦታ ወስዶ ስዕሉ በየቤቱ በየቤተ መቅደሱ ሰቅሎ ሲሰገድለት፣ ሲሳለመውና ሲስመው ይገኛል። የተለያየ የሃይማኖት ሥርዓቶች በሚከወንባቸው አድባራት በትልቁ ተስሎ መገኘቱም እጅግ አሳዛኝ ነው። ምክንያቱም ለእግዚአብሔር እንጂ ለፊልም ባለ ሙያ ወይም ለሰዓሊ ሙያ ስገድ የሚል ቃል መጽሐፍ ቅዱስ የለም። ነገር ግን በኢየሱስ ሽፋን የሰው ስዕል እየተመለከ ይገኛል።
    እናም ይኽ አብዛኞቹ ሃይማኖተኞች የሚሰግዱለት ግለሰብ "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" በተሰኘ ፊልም ላይ የኢየሱስ ክርስቶስን ገጸ ባህሪ በመላበስ የተወነ አሜሪካዊ የፊልም አክተር ሲሆን፤ ስሙም ጂም ካቪዘል (Jim caviezel) ይባላል። ወይም ደግሞ በሙሉ መጠሪያው ጃምስ ፓትሪክ ካቪዘል ነው። ሃይማኖቱ ደግሞ የሮማ ካቶሊክ ተከታይ ነው። ተወልዶ ያደገው በአሜሪካ ዋሽንግተን ስቴት ውስጥ ሲሆን ወደ ፊልሙ ኢንዱስትሪ ከመግባቱ አስቀድሞ፥ የተማረባቸውን ትምህርት ቤቶች በመወከል የቅርጫት ኳስ ይጫወት ነበር። በዃላ ግን እግሩ ላይ ጉዳት ስለደረሰበት ሙሉ በሙሉ የቅርጫት ኳስ መጫወቱን ትቶ የፊልም አክተር በመሆን እ.አ.አ በ1991 የመጀመሪያ ፊልሙ ላይ በጥሩ ትወና ተሳትፏል። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" የተሰኘውን ፊልም ጨምሮ ከሠላሳ በሚበልጡ ፊልሞች ላይ ተውኗል (በመሪነት፣በረዳትነት እና..) የተወሰኑ ፊልሞቹን ርዕሳቸውን እና የተሰሩበትን ዓመት እንደሚከተለው መጥቀስ ይቻላል…

My own private idaho – 1991
Diggstown – 1992
Wyatt erap – 1994
Ed – 1996
The rock – 1996
G.j. jane – 1997
The thin red line – 1998
Ride with the devil – 1999
Pay it forward - 2000
Frequency – 2000
Madison - 2000
Angel)
Person of interest- series drama (up to 2011) እና ሌሎችን ፊልሞች ሰርቷል።

   እንግዲህ እውነቱ ይኽ ነው። "ዘ ፓሽን ኦፍ ክራይስት" የተሰኘው ፊልም ዳይሬክተር የሆነው ሚል ጊብሰን፥ ይህን ግለሰብ የኢየሱስ ክርስቶስን ገጸ ባህሪ ተላብሶ እንዲጫወት ያደረገበት ምክንያት፥ ሰውየው ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሆነ ወይም ደግሞ በመልክ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለሚመስለው ሳይሆን፥ አስቀድሞ በሰራቸው ፊልሞች በተለይም "The thin red line" እና "Frequency" በተባሉ ፊልሞች ላይ ባሳየው ጥልቅ የትወና ጥበብ ነው። እውነቱ እንዲህ ሆኖ ሳለ፥ ያገሬ ህዝብ ግን አምላክ አድርጎት ይሰግድለታል። ….እግዚኦ..!!

    በርግጥ በኦርቶዶክስ ሃይማኖት አስተምህሮ መሰረት በየአድባራቱ ብዙ ታሪክ ያዘሉ ቅርጻ ቅርጾች እና ሥዕሎች እንዳሉ ይነገራል.. ይህንንም አስመልክቶ ዲ/ን ዳንኤል ክብረት SUNDAY, APRIL 25, 2010 "የቤተክርስቲያን ሥዕሎች ታሪካዊ ፋይዳ" በሚል ርዕስ በጻፈው ጽሁፉ እንዲህ ብሎ ነበር፦

"…የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የሀገሪቱን (የኢትዮጵያን) ባሕል እና ታሪክ ለትውልድ ካቆየችባቸው መንገዶች አንዱ ሥዕሎቿ ናቸው፡፡ በዚያ ፎቶግራፍ እና ፊልም ባልነበረበት ዘመን የነበረውን ባሕል፣ሥርዓት እና ታሪካዊ ሁነቶች የምናገኘው በቤተ
ክርስቲያን መጻሕፍት እና ግድግዳ ላይ በሚገኙ ሥዕሎች ነው፡፡ ለምሳሌ በሆሎታ ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ግድግዳ ላይ የሚገኙት እና ከ100 ዓመታት በላይ ያስቆጠሩት ሥዕላት ለዚህ ምስክር ናቸው፡፡ ከአዲስአበባ 44 ኪሎሜትር በሆሎታ ከተማ የምትገኘው ይህች ቤተክርስቲያን በዐፄ ምኒሊክ አማካኝነት በ1895 ዓ.ም የተገነባች ሲሆን ታቦቷ የገባችው በዚሁ ዓመት የካቲት 16 ቀን ነው፡፡ ሥዕሉን የሳሉት አለቃ ሐዲስ መሆናቸውን ከመቅደሱ ምሥራቃዊ ግድግዳ ላይ ከሣሉት ሥዕል ላይ «ለዛቲ ሥዕል እንተ ሰዓላ አለቃ ሐዲስ እምቤተ ሌዊ፣ ወዘተምህረ በጎንደር» በሚለው ማስታወሻቸው ይታወቃል፡፡
  ሰዓሊው የቤተክህነቱን እና የቤተመንግሥቱን ወግ እና ሥርዓት በሚገባ የሚያውቁ መሆናቸው በአሣሣላቸው ይታወቃል፡፡ ለምሳሌ ወለተ ሄሮድያዳን ሲሥሏት አለባበሷን እና የፀጉር አቆራረጧን ኢትዮጵያዊ አድርገውታል፡፡ ሹሩባ ተሠርታለች፣ነጭ ሻሽ አሥራለች፣ አሸንክታብ ሠትራ እስክስታውን ታስነካዋለች፡፡ የሄሮድስን የቤተ መንግሥት ሥርዓት ሲስሉት በምኒሊክ ቤተመንግሥት ሥርዓት ነው። ቢላዋው፣የእንጀራው አጣጣል፣ ሙዳ ሥጋው የዘመኑን የግብር ሥርዓት በሚገባ ነው የሚያሳየው፡፡"
   አንባቢ ሆይ ልብ በል፥ እንደ ዳንኤል ክብረት ገለጻ ከሆነ በመጽሐፍ ቅዱስ ውሰጥ የምናውቃት ሄሮድያዳ ኢትዮጵያዊ መስላ ስትሳል ምናልባት ሰዓሊው በነበረበት ዘመን የኢትዮጵያ ሴቶች ምን እንደሚመስሉ ሊገልጽ ይችል ይሆናል። ነገር ግን የመጽሐፍ ቅዱሷ ሄሮድያዳን እና የመጽሐፍ ቅዱሱን ታሪክ ያበላሸዋል። ሲቀጥል ደግሞ የምኒልክን ቤተ መንግሥት ለማሳየት የሄሮድስን ቤተ መንግሥት ማረሳሳት ተገቢ አይሆንም። እንግዲህ በየአድባራቱ ታሪክ አዝለዋል የሚባሉ ሥዕሎች ሁሉም እንደዚህ ዓይነት ከሆኑ መሆናቸው ለማወቅ ፈላስፋ ወይም የነገረ መለኮት ምሁር መሆንን አይጠይቅም። በአንድ ዘመን የተከናወነውን መንፈሳዊ ድርጊት ለማስታወስ ወይም ሃሳባዊ እይታን ለማሳየት ተብሎ የሚሳለው ስዕል የእውነታው ነፀብራቅ እንደሆነ አድርጎ በመሳል ለስዕሉ መስገድ፣ መንበርከክና መማፀን ኢክርስቲያናዊ አምልኮ ነው። ያሳፍራል.። ያሳዝናልም!!
ሲጠቃለል ስዕል ለአንክሮ፣ ለተዘክሮና ለማስተማሪያነት ከሚያገለግል በስተቀር በየቤተ መቅደሱ ተሰቅሎ አይታጠንም፣ አይሰገድለትም። መንበርከክና ከፊት አቁሞ መማፀን የወንጌል አስተምህሮ አይደለም። አንዳንዶች ለጥፋታቸው መሸፈኛ “የኪሩብ ምስል በታቦቱ ላይ ነበር” ይላሉ። የኪሩቡን ምስል ማን አዘዘ? ከምን ይቀረፅ፣ ስንትስ ነበረ? ለማን በተሰጠ ኪዳን ላይ ታዘዘ? በቂ መልስ የላቸውም። የዛሬውን ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ጋር ለማገናኘት መሞከር ሰማይና ምድር ለማጣበቅ እንደመሞከር ይቆጠራል። እግዚአብሔር አእምሮውን ለብዎውን ያሳድርብን።