Monday, July 25, 2016

የሚፈውስና የሚያሳምም ስም - ኢየሱስ!!


(ከዙፋን ዮሐንስ)
የሆነ ጊዜ ፷፬ ሰው በሚይዝ አገር አቋራጭ አውቶቡስ ተሣፍረን ወደክልል የሁለት ቀን መንገድ ተጓዝን። ቁርስ፣ ምሳ፣ አብሮ ከመብላት፣ አብሮ ከመቀመጥ፣ የተነሳ ሁሉ ዘመድ ቤተሰብ ሆነ። የሆድ የሆዱን ተጫወተ። ስልክ ተቀያየረ፣ እጮኛም ያገኘ አይጠፋም። ያልተነሳ ርእስ አልነበረም። ፖለቲካ፣ የኑሮ ውድነት፣ ስለሳይንስ፣ ሃይማኖት፣ ስለታዋቂ ደራሲያን፣ ዘፋኝ፣ ፈላስፋ፣ ስለሃይማኖት አባት፣ ብዙ ብዙ….ብቻ ያልተወራ አልነበረም። አንዳንዶቹም ወሲብ ቀስቃሽ ቀልዶችን ግጥሞችን አውርተው መኪናው ውስጥ ከጫፍ እስከጫፍ አነቃቅተዋል። የወሲብ ነገር ሲወራ ጆሮውን ቀስሮ ያዳምጣል። የሚያስቅ ከሆነ ይስቃል፣ የሚያሳፍር ከሆነም መስማት ያልፈለገ ይመስል የኮረኮሩት ያህል ግንባሩ ጥርስ በጥርስ ይሆናል። የአለቃ ገ/ሐና ነገር ሲነሳማ የአለቃን ወሲብ ወዳጅነትና ይጠቀሙ የነበረበትን የማማለል ዘዴ እያደነቀ ከልምዳቸው ብዙ የቀሰመው ነገር ያለ ይመስል ተሳፋሪው ይስቃል፣ ያውካካል።

ይህ ሁሉ ሲሆን አንድ ሰው ከዚህ ሁሉ ሳቅና ፍንደቃ ራሱን አግልሎ ከመስኮት ጥግ ተቀምጦ ያነብ ነበር። ድንገት ብድግ ብሎ “ኢየሱስ“ የሚለውን ስም አንስቶ ከመጽሐፍ ቅዱስ እየጠቀሰ አዳኝነቱን፣ ተስፋነቱን፣ አጽናኝነቱን መናገር ሲጀምር ብዙ ፊቶች ተቀያየሩ። አንዳንድ ፊቶች ቲማቲም መስለው ቀሉ። የባሰባቸው አንዳንዶች ደግሞ እንደበርበሬ ቀልተው የቁጣ ብናኛቸው በሰውየው ላይ በተኑ። ስለዝሙት ቀልድ ቦታ ሳይመርጡ ሲያውካኩ የነበረውን ረስተው ስለኢየሱስ ለመስማት ቦታ አጡና “ሰብከት ቦታ አለው“ አሉና ደነፉ። ጫወታችንን አታበላሽ አሉና አጉረመረሙ። ስለፌዝ፣ እርባና ስለሌለው ቀልድና ስለዝሙት ማውራት እንደጥሩ ጫወታ ተቆጥሮ ስለኢየሱስ መስማት ግን ጫወታን እንደማበላሸት ሆኖ ተቆጠረ።
እርግጥ ነው። የሥጋን ነገር መከተል ከእግዚአብሔር የመለየት ጉዳይ ስለሆነ ማበሳጨቱ የሚጠበቅ ነበር።

ሮሜ 8፣7
 “ስለ ሥጋ ማሰብ በእግዚአብሔር ዘንድ ጥል ነውና፤ ለእግዚአብሔር ሕግ አይገዛምና፥ መገዛትም ተስኖታል” እንዳለው ሐዋርያው።

በየትኛውም መመዘኛ “ኢየሱስ” የሚለው ሃይለኛ ስም ሲጠራ ለመቀበል ወይም ላለመቀበል የሰዎች አስተሳሰብ ከሁለት ነገር ውጭ አይሆንም።
አንድም የኢየሱስን ጌትነትና አዳኝነት የሕይወቷ ቤዛ ላደረገችው ነፍስ ሃሴትን ያመጣልና በስሙ መጠራት ይኽች ነፍስ አታፍርም፣ አትቆጣም።
 ሁለትም የኢየሱስ አዳኝነት፣ ጌትነትና አምላክነት ብቸኛ ቤዛዋ ያላደረገችውን ነፍስ ያበሰጫታል፣ ያናድዳታል።

ምክንያቱም ፪ቆሮ ፪፣፲፮ “ለእነዚህ ለሞት የሚሆን የሞት ሽታ፣ ለእነዚያም ለሕይወት የሚሆን የሕይወት ሽታ ነን“ እንደሚል ይኽ ስም ለዘላለማዊ ሕይወት ለተመረጡት የፕሮቴስታንት ይሁኑ የኦርቶዶክስ፣ የካቶሊክ አማኞች ሕይወት፣ ሕይወት የሚሸት ሰላምና እረፍት የሚያመጣ ሲሆን ለጥፋት ለተመረጡት ግን የሚያስቆጣ፣ የሚያነጫንጭ ጥርስ የሚያፋጭ ይሆናል። ዘፈንና ቀልዱ፣ ቧልትና ፌዙ ሲነገር ሁሉ ያለምንም ልዩነት አንድ ሆነው ሲስቁና ሲፈነድቁ እንዳልነበር “ኢየሱስ” የሚለው ስም ሲጠራ የሚያበሳጭበት ምክንያት ለምንድነው? እነዚህ ጴንጤዎች ቦታ የላቸውም እንዴ ማሰኘቱስ ለምን ይሆን? የራሱ የሆነውን ኢየሱስ ያዘጋጀ ሃይማኖት የለም።

ቢያንስ አዳምጦ ከወንጌል ቃል ውጪ የሆነውንና ያልሆነውን መለየት ሲቻል መቃወም ተገቢ አይደለም። ደደግሞም ፌዝና ሥጋዊ ነገርን ከማውራት ስለኢየሱስ መስማት በብዙ መልኩ ይሻላል። ለሁሉ ስለሞተው ስለኢየሱስ መናገር የተወሰኑ ሰዎች ስጦታ ሆኖ ሲያስወቅስ፣ ስለዝሙት መናገር ግን ለሁሉ የተፈቀደ መልካም ተግባር ሆኖ የሚቆጠርበት ምክንያት መኖር አልነበረበትም። ነገር ግን ይኽ ስም ሲጠራ ያስፈራቸውና ሐዋርያቱን፣ “ጀመሩ ደግሞ እነዚህ የተረገሙ!” ያስብል እንደነበር ወንጌል ያስታውሰናል።

1. ስሙን ሲጠራ ለተቀበሉ የሕይወት ሽታ የሆነላቸው። ሐዋ ፰
 ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ፊልጶስ ስለኢየሱስ ሲሰብክለት ልቡ ደስ ተሰኘ። አጥምቀኝ አለው እንጂ “የእናትና አባት ሃይማኖቴን ተከትዬ ከኢትዮጵያ ኢየሩሳሌም ድረስ ያስመጣኝና ተራራ የወጣሁበትን ታላቅ የበረከት ጉዞ አድርጌ ከመመለስ ባለፈ ያንተን ኢየሱስ ለመስማት አልመጣሁም“…ብሎ አልተቆጣም።
በሉቃ ፳፯-፳ ላይም የኤማሁስ መንገደኞች ስለኢየሱስ በመጽሐፍ የተጻፈውን ሲሰሙ ልባቸው ይቃጠልባቸው ነበር። በዚያ በነበርንበት አውቶቡስ ላይ ግን ለብዙዎች ልባቸው የተቃጠለው ለምን ይኄንን ስም ትጠራላችሁ? ብለው በመናደድ ነበር።
ሐዋ ፲-፳፬ ላይ መቶአለቃ ቆርኔሌዎስም ጭራሽ ዘመዶቹንና ወዳጆቹን ጠርቶ ስለኢየሱስ ስበኩኝ ብሎአል። ስለኢየሱስ መስማት ደስ የሚያሰኝ ሆኖ ሳለ ጆሮ የሚያሳክክበት ምክንያት አይኖርም። ቢያንስ ስለአለቃ ገ/ሐና የዝሙት ጥበብና ሴቶችን እንዴት እንደሚያጠምዱ ከመስማት ይልቅ አምነው ባይቀበሉት እንኳን ስለኢየሱስ የሚነገረውን የወንጌል ቃል ማዳመጥ ለዝሙት ልብን ከማነሳሳት ከንቱ ወሬ ሳይሻል አይቀርም።
  በበዓለ ሃምሳ የተሰበሰቡት አይሁድ ስለኢየሱስ ሲወራ ልባቸው ተነክቶ ሐዋርያትን “ምን እናድርግ ?? “ብለው እርዳታ ጠየቁ እንጂ “በየመንገዱ በየአደባባዩ በየባሱ እየሰበካችሁ፣ አታስቸገሩ “ብለው በተቆርቋሪነት ሰበብ የአጋንንትን ቁጣ አልተቆጡም። እነዚህ ስሙን የሰሙና ያልተቃወሙ ሁሉ መጨረሻቸው ያመረ ክርስቲያኖች ሆነው በሰማይ የዘላለም ሕይወትን በምድርም በረከትን አግኝተው ወደጌታ ሄደዋል።

2. የሞት ሽታ የሆነባቸውና ስሙ ሲጠራ የሚያበሳጫቸው የሚያስቆጣቸው ሰዎች እንዲህ የሚሆኑት እነሱ ሳይሆኑ በውስጣቸው የተቀመጠው ክፉ የክርስቶስ ተቃዋሚ መንፈስ ነው። ይኽ ስም ሰዎችን ከሥጋዊና መንፈሳዊ ደዌ ስለሚፈታ ሰይጣን ይጠላዋል። መድኃኒትን ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ሰውነት መድኃኒት ለሞት እንደሚሆንበት ሁሉ ኢየሱስ የሚለውም ስም ለሞት ይኾንባቸዋል። ሐዋርያው ጳውሎስ ከመለወጡ በፊት የአብርሃም፣ የይስሐቅ፣ የያዕቆብን አምላክ እንደሚያመልክ ስለሚያምን “ኢየሱስ” የሚባለው ስም ያበሳጨው ነበር። ይኽንን ስም የሚጠሩትን ያስርና ያስገድል ነበር። ሐዋ ፬:፲፰ “በኢየሱስ ስም ፈጽመው እንዳይናገሩና እንዳያስተምሩ አዘዙአቸው” “ በማለት ፈሪሳዊያን ስሙ የሞት ሽታ እንደሆነባቸው ያሳያል። “ገረፉአቸው፥ በኢየሱስም ስም እንዳይናገሩ አዝዘው ፈቱአቸው።“ በማለት ስሙ እንዳስገረፈ አንብበናል።

ወንድሞቼና እህቶቼ ዛሬም ይህንን ስም መጥራት ያስደነግጣል/ያስፈራል/ኤሌክትሪክ ያስጨብጣል። በስካር መንፈስ ናውዞ ውሃ መውረጃ ቱቦ ስር የሚያድረው ብረቱ፣ አንበሳው ሲባል ዘማዊውና አለሌው ቀምጫዩ እየተባለ ሲሞካሽ፣ ሌባው ቢዝነሳሙ፣ እሳቱ ሲሉት የኢየሱስ ስብከት ሲነሳ ግን ሃይማኖተኛ ሆኖ ሲያፈጥ ማየት በጣም ያሳዝናል። ጫትና ሲጋራ፣ ሀሺሽና ሺሻ የሚያናውዘው ሱሰኛው ሰው ለጥምቀትና ትንሣኤ በአጭር ታጥቆ መንገድ ከሚጠርግ፣ ቄጠማ ከሚጎዘጉዝ፣ ምንጣፍ ከሚያነጥፍ ውስጡ ተጎዝጎዞ ከተቀመጠው ክፉ መንፈስ ኢየሱስን ንጉሡ አድርጎ ቢያኖር ኖሮ ከዐመጻ ተግባራቱ ነጻ በወጣ ነበር። የሕይወቴ መሪ ነው ያለ ሰው ንሰሃ ገብቶ ኢየሱስ ሰው አደረገኝ ይላል እንጂ “ኢየሱስ” ብሎ የሚሰብክን ሰው “መግደል ነበር“ አይልም። እህቴና ወንድሜ ዛሬ ኢየሱስ አንተና አንች ጋር የሞት ሽታ ወይስ የሕይወት ሽታ ነው? ሁላችን ራሳችንን እንመርምር።
 ክብርና ምስጋና ነፍስ ሥጋና መንፈስን ነጻ ለሚያወጣው ሰው ለሚያደርገው ትልቅ ስም፣ ለኢየሱስ ክብር ይሁን! አሜን

Friday, July 15, 2016

ትወደኛለህን?


(ከነገ ድል አለ)
ምላሽ የሚያሻው የክርስቶስ ጥያቄ - ትወደኛለህን? (ዮሐንስ 21)
ይህን ጥያቄ ስናነብ ወደ አእምሮአችን በቶሎ የሚመጣው ምንድን ነው? ምናልባት ምን ዐይነት ጥያቄ ነው? ብለን እናስብ ይሆናል፤ ወይም ጥያቄው የአፍቃሪ ጥያቄ አንደሚሆን ልንገምት እንችላለን። አሊያ እንደዚህ ተብሎ ይጠየቃል ወይ? ብለን ልንጠይቅም እንችላለን። ጥያቄው ረጅም ጊዜ ዐብሮን ከኖረ ሰው፥ በጣም ከሚያውቀንና ከምናውቀው ሰው፥ ለምሳሌ፥ ከባለቤታችን ወይም ከጓደኛችን ቢመጣስ ምን ይሰማናል? ያለ ጥርጥር ምን አይቶብኝ ይሆን? ወይም ምን አይታብኝ ይሆን? ምን ሰምቶብኝ/ምን ሰምታብኝ ይሆን? የሚሉ ጥያቄዎችን ሊያጭርብን ይችላል።
ጥያቄው “አዎን እወድሃለሁ” የሚል ምላሽን ለማግኘት ወይም መወደድን ለማወቅ የተጠየቀ ጥያቄ አይደለም። ጥያቄው ከፍቅረኛ፥ ከትዳር አጋር ወይም ከጓደኛ የመጣ ሳይሆን ከጌታችንና ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ በተለይም ለጴጥሮስ የቀረበ ጥያቄ ነው። ሐዋርያው ዮሐንስ በወንጌሉ በ21ኛው ምዕራፍ አንደ ዘገበልን፥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ያህል “ትወደኛለህን?” ሲል ጠይቆታል።

እወድሃለሁ
“ትወደኛለህን?” የሚለው ጥያቄ ፍቅርን ለማወቅ ወይም ለማረጋገጥ የሚጠየቅ ጥያቄ ቢሆንም፥ ዮሐንስ እንደ ጻፈው ጥያቄው ከዚያ የሚያልፍ መልእክት አለው። በርግጥ ትወደኛለህን? ተብሎ ሲጠየቅ ምላሹ አልወድህም የሚል አይሆንም። በክርስቶስና በጴጥሮስ መካከል የነበረውን ግንኙነት መለስ ብለን ስናስታውስ፥ ጌታ ደቀ መዛሙርቱን በሥጋ ልለያችሁ ነው፤ ልሄድ ነው ብሎ በነገራቸው ጊዜ፥ ጴጥሮስ ‘ተለይተኸን ወዴት ትሄዳለህ? የትም ብትሄድ ዐብሬህ እሄዳለሁ፤ ሞት እንኳ ቢመጣ ከአንተ አልለይም’ ያለው ሰው ነበር (ዮሐ. 13፥36-38)። ጌታ ለጴጥሮስ ንግግር የሰጠው ምላሽ፥ ‘እንኳ ነፍስህን ልትስጠኝ፥ ዶሮ ከመጮኹ በፊት ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ’ የሚል ነበር።

ፍቅር እንዴት ይገለጣል?
እንደሚታወቀው በዓለም ላይ የፍቅር መገለጫ አንድ ዐይነት አይደለም፤ ከማኅበረሰብ ማኅበረሰብ፥ ከባህል ባህል ይለያያል። የፍቅር መግለጫ ቋንቋ፥ የጋለ ጭብጨባ፥ እንባ፥ የቃል ንግግር፥ አበባ ማበርከት፥ መተቃቀፍ፥ መጨባበጥ፥ መሳሳም ሊሆን ይችላል። ከእነዚህ በአንዱ ወይም በሌሎች መንገዶች ፍቅር ይገለጣል። ጌታ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ መላልሶ ሲጠይቀው፥ ጴጥሮስም ሦሰት ጊዜ መላልሶ እወድሃለሁ ብሎታል። እንዲሁም በኋላ ላይ ግራ የገባው በሚመስል መልክ፥ በማዘንም ጭምር እንደምወድህ አንተ ታውቃለህ ብሎታል።

ፍቅርና ተግባር
በአጠቃላይ በወንጌል በተለይም በጌታችን ትምህርትና ሕይወት ውስጥ እንደምንመለከተው፥ የፍቅር ዋና መገለጫ ቃላት ሳይሆኑ ተግባር ነው። ጴጥሮስ “እወድሃለሁ” ቢልም በተግባር ግን ይህን ፍቅር ማሳየት አልቻለም፤ እወድሃለሁ ያለውን ጌታውን ክዶታል። ጌታችን ኢየሱስ በዮሐንስ ወንጌል 15፥13 ላይ ነፍሱን ለወዳጆቹ ከመስጠት የበለጠ ፍቅር እንደሌለና ነፍስን መስጠት የፍቅር ጣሪያ መሆኑን እንዳስተማረ፥ በተግባርም ነፍሱን በመስጠት ፍቅሩን አሳይቷል። ከዚህ በኋላ ነው ጌታ ጴጥሮስን “ትወደኛለህን?” ሲል መላልሶ የጠየቀው። ጴጥሮስም እንደ ቀድሞው፥ “ከአንተ ጋር መሞት እንኳ የሚያስፈልገኝ ቢሆን፥ ከቶ አልክድህም” (ማቴ. 26፥35) አላለም። የራሱን ምላሽ ከመስጠት ይልቅ “እንድወድህ አንተ ታውቃለህ” ነበር ያለው። ጴጥሮስ ፍቅሩን በተግባር መግለጽ ባይችልም፥ ኢየሱስ ፍቅሩን በተግባር ከገለጠና፥ የካደውን ጴጥሮስን በዚህ ፍቅር እንደ ገና ከመለሰው በኋላ አልከሰሰውም። ይልቁንም ሲመልሰውና ወይም እንደ ገና ሲያድሰው፥ ኀላፊነትንም ሲሰጠው እንመለከታለን።

መልእክቱ

“ትወደኛለህን?” የሚለው የጌታ ጥያቄ “አዎን እወድሃለሁ” ከሚል ምላሽ ያለፈ ቀጥተኛ መልእክት አለው። መልእክቱም የምትወደኝ ከሆነ አደራዬን ተወጣ የሚል ነው። ጌታ ሦስት ጊዜ፥ “ትወደኛለህን?” ሲል ከጠየቀው በኋላ ጴጥሮስ “አዎን ጌታ ሆይ፥ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ” የሚል ምላሽ መስጠቱን ተከትሎ፥ ግልግሎቼን አሰማራ፤ ጠቦቶቼን ጠብቅ፤ በጎቼን አሰማራ የሚል ግልጽ አደራ ሰጥቶታል (ዮሐ 21፥15-17)። ይህ ኀላፊነት ወይም አደራ የሕይወት መሥዋዕትነትን የሚጨምር እንደሚሆን ቀጥሎ በተጻፈው ቃል ውስጥ እናነባለን። “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ አንተ ጒልማሳ ሳለህ ወገብህን በገዛ ራስህ ታጥቀህ ወደምትወደው ትሄድ ነበር፤ ነገር ግን በሸመገልህ ጊዜ እጆችህን ትዘረጋለህ፥ ሌላውም ያስታጥቅሃል፤ ወደማትወደውም ይወስድሃል አለው። በምን ዐይነት ሞት እግዚአብሔርን ያከብር ዘንድ እንዳለው ሲያመለክት ይህን አለ።” የዚህ ክፍል መልእክት በእኛም ሕይወት ሊተገበር የሚገባው ነው። ምክንያቱም ክርስቶስ በዕለታዊ ሕይወታችን ተግባራዊ ምላሽን ይጠብቃል። ትወደኛለህን? ለሚለው ጥያቄ በቃል “እወድሃለሁ!!” የሚለውን ምላሽ ከመስጠት ይልቅ፥ ራሳችንን መልሰን መጠየቅ የተሻለ ሳይሆን አይቀርም። በርግጥ ጌታን እንወደዋለን ወይ?

Monday, July 4, 2016

እሳትና ውሃ አጥፊና ጠፊ ቢሆኑም አስፈላጊዎች ናቸው!

(ከኪሩቤል ሮሪሳ ጽሑፍ ተሻሽሎ የተወሰደ)
ነገሥታቶች በሪፐብሊካዊ መንገድ ሥልጣንን በእጃቸው ካስገቡ መሪዎች የበለጠ ቅቡል ነበሩ። የሥልጣን መሠረታቸው መለኮታዊ ነው ተብሎ ስለሚታሰብ ሕዝብ በፈቃዱ ይገዛላቸው ነበር። እነርሱም ሕዝባቸውን ይወዳሉ... ሕዝብም ይወዳቸዋል። በንጉሣዊ አገዛዝ ንጉሡ አባወራ.., ንግሥቲቱ እማወራ... ሕዝብ ደግሞ ልጆች ናቸው። አዋጅ ሲነገር "የምንወድህና የምትወደን ህዝብ ሆይ" ብለው ንግግር ይጀምራሉ። ይኼ ጭምብል ያለው ማታለያ አይደለም። እውነት ነው። በእነዚህ አካላት መካከል እውነተኛ ፍቅር ነበር። ምክንያቱም በታዛዥ ልጅና አባት መካከል ፀብ አይኖርም። ፀቡ የሚጀምረው ልጅ እምቢ ሲል ነው።
ሕዝብ ሁሉንም ነገር እሺ ብሎ በሚቀበልባቸውና ንጉሣዊ አስተዳደር ባለባቸው አገሮች የተሻለ ሰላም አለ። ሕዝብ ጠግቦ ሊበላ ይችላል። ባይበላም ከላይ ከሰማይ የተሰጠን የ40 ቀን እድል ነው ስለሚባልና የመብት ጥያቄዎች ስለማይኖሩ የአገርም አንድነት አይናጋም። እዚህም እዚያም የቦምብ ፍንዳታና ግድያ አይኖርም። የትልቅ አገር (በተለየ አተያይ) ባለቤት የመሆን እድልም ሰፊ ነው። በኛም አገር ከነበሩት የንጉሣዊ አስተዳደር ጥቅሞች መካከል ከላይ የተጠቀሱት ይገኙበታል። ስለዚህ እነኚህን የንጉሣዊ አስተዳደር ጥቅሞችን የቀመሰም ሆነ የሰማ ሰው... ዛሬ ላይ የድሮ ሥርዓት ናፋቂ ነኝ ቢል ላይገርም ይችላል።
ሥልጣንን የመጋራትም ሆነ ሌሎች የዴሞክራሲ ጥያቄዎች መነሳት የሚጀምርባቸው አገሮች ላይ ሰላም አይኖርም። ስደትና እንግልቶች ይኖራሉ። የረጋና ጸጥታ የሰፈነበትን ንጉሣዊ አስተዳደር ወደ ሌላ ሥርዓት የሚቀይረው እምቢታ ነው።
እምቢታ የለውጥ መጀመሪያ ነው። የዓለምን ቅርጽ የቀየረው እምቢታ ነው። የእምቢታ መሠረቱ ደግሞ እውቀት ነው። የንጉሣዊ አስተዳደሮች አገዛዝ ማዕበል አልባ ሐይቅ ነው። የማይንቀሳቀስ ውሃ ከሩቅ ሲታይ ፀጥታው ቢያስጎመዥም ውስጡ ላሉ አሣዎች ግን መራር ነው። ማዕበል ሲቆም አሣዎች መሞት ይጀምራሉ። እንቅስቃሴ አልባ የሆነ ነገር መልካም ቢመስልም ቆይቶ ግን ይገማል... ይሞታልም። ስለዚህ ንጉሣዊ አስተዳደሮች ለለውጥ የማይጋብዙ ስለነበሩ በኃይል መቀየራቸው ግድ ነበር። ሕዝብ በፀጥታው ውስጥ ተኝቶ ነበር። ሕይወት በድግግሞሽ የተሞላች አሰልቺ ነበረች።
በንጉሣዊ የአስተዳደር ሕግ ገዢው ግለሰብ እንጂ ሃሳብ አይደለም። ንጉሣዊ ባልሆነው ዓለም ደግሞ ገዢ የሚሆነው ሃሳብ ነው። የግለሰብ መኖር አስፈላጊ ላይሆንም ይችላል። ፓርቲዎች ሃሳቦችን ሲያመነጩ ሕዝቦች ደግሞ "ገዢ" ለሆነው ሃሳብ ድምፅ ይሰጣሉ። በዚህ የሥርዓት ሂደት... ሕይወት በምርጫ ውሳኔ ውስጥ ትወድቃለች። ለመምረጥ ሁለቱም መኖር አለባቸው። ሁለቱ ነገሮች ተነፃፃሪ እንጂ ተጻራሪ አይደሉም። መጻረር የሚባል ነገር የለም። ሁለቱም ትክክል ናቸው። የተሳሳተ የሚባል ነገርም የለም። አንዱ ከሌለ ምርጫ የሚባል ነገር ይጠፋል። አንዱ ፓርቲ ወንበር ይዞ ይቀርባል። አንዱ ደግሞ ሶፋ። ሕዝብ የፈለገውን መርጦ ያስቀመጥበታል። በዚህ መሃል ፓርቲዎች "ሶፋ ለእንቅልፍ ይጋብዛል" ወይም "ደረቅ ወንበር ለኪንታሮት ሕመም ይዳርጋል" ተባብለው ልዩነቱን ማጦዝ ይችላሉ። ነገር ግን ወንበር፣ ወንበር መሆኑ ሶፋም፣ ሶፋ መሆኑ እሙን ነው። ሁለቱም ይጠቅማሉ። ይህ ዓይነት የፖለቲካ ሥርዓት ፈጠራን አበረታቶ ለለውጥ ይጋብዛል።
ኢትዮጵያ ውስጥ ባለ የፖለቲካ አረዳድ ሶፋ ካለ ወንበር አያስፈልግም። ወንበርና ሶፋ ተጻራሪ እንጂ ተነጻጻሪ አይደሉም። ሁለቱም ጎራዎች ውስጥ በውስጣቸው የተቀበረ ንጉሳዊ መለዮ አለ። እኔ ብቻ ነኝ፣ የሥልጣን ምንጭ የሚል። ልዩነትን እንደጠላት የማየትና የእኔ ብቻ ትክክል የማለት አባዜ አገራችንን ጠፍንጎ ይዟታል። ከንጉሣዊ አስተዳደር ተላቀን ከለውጡ ልናገኝ የነበረውን ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች እነዚህ ሁለት ጎራዎች መና አስቀርተውታል። የለውጡ ችቦ ከተለኮሰ ከ40 በላይ ዓመታት ቢቆጠሩም ዛሬም ፖለቲካችን አዙሪት ውስጥ ነው። የአዙሪቱ ምክንያት አንድ ነው። የመቀያየር ሳይሆን የመጠፋፋት አባዜ። ገዢው የተቃዋሚው.... ተቃዋሚው ደግሞ የገዢው ጠላቶች ናቸው። አንዱ በአንዱ መቃብር ላይ መንገሥ ይፈልጋል።
ይህ በሽታ ወደ አዲሱ ትውልድም እየተዛመተ ነው። ወጣቱ ልዩነትን ባየ ቁጥር፣ ስም መለጠፍ ሥራዬ ብሎ ተያይዞታል። ፍላጎቱ አይታወቅም።
የንጉሣዊ አስተዳደርን ባሕርያት በጥልቀት በማጥናት ለውጡ አስፈላጊ እንደነበረ መረዳትና ወደኋላ ተመልሰን እሱን የምንናፍቅበት መሠረት እንደሌለ ማመን ላይ ገና ብዙ ክፍተት አለ። በዚህ ዘመን ወደኋላ ተመልሶ ንጉሥ መናፈቅ ምን ይባላል?
መነሻው ባለው ላይ በትንሽ ነገር ተስፋ መቁረጥ... እልህና አጉል ጀብደኝነት ነው። የታሰረ ሁላ ጀግና.... ተቃዋሚ ሁላ ሽብርተኛ በማለት ፈርጆ ለመጠፋፋት ምሏል። ለዚህ ሁላ ምስቅልቅል የፖለቲካ ባህል ተጠያቂው ስንፍናና ድንቁርና ነው። በየጊዜው ዓላማችን ሥርዓት ለመቀየር እንጂ እኛ ለመቀየር ፍላጎት የለንም። ያልተቀየረ አስተሳሰብ ደግሞ የተቀየረ ሕብረተሰብ ሊፈጥር አይችልም። መለወጥ ያለበት አተያያችን ነው። እሳትና ውሃን አለቦታው ለመጠቀም መፈለግ የፈጣሪ ስህተት ሳይሆን የኛ ጉድለት ነው።
ውሃን እሳት ውስጥ ብንጨምር ወይም እሳትን ውሃ ውስጥ ብናስገባ ለመጠፋፋታቸው ስህተቱ የማነው? የበረደው ሰው እሳትን በብብቱ ይይዝ ዘንድ አይጠበቅም።
ነገር ግን ውሃንና እሳትን መጥነን በመደጋገፍ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ እንችላለን። ይህ የአስተሳብ ብስለት ነው። ፖለቲካችንን ግን ለምንኖርባት ቤታችን እንደሚመጥን አድርገን አስማምተን መጠቀም አልቻልንም። አጥፊና ጠፊ መሆኑ እስካላከተመ ድረስ አዙሪቱ ደግሞ አይለቀንም። ስለዚህ መለወጥ ያለበት ወንበሩ ሳይሆን ወንበሩን የሚፈልጉ ጭንቅላቶች ናቸው።
መጽሐፍ ቅዱሳችን እንደሚነግረን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ከቀረቡ ክሶች መካከል አንዱ "ንጉሥ ነኝ ይላል" የሚል ነበር። ይኽ ንግግር ደግሞ በወቅቱ በሕዝቡ ላይ ተሹሞ ለነበረው ሰው ትልቅ ራስ ምታት ነው። ምክንያቱም ሥልጣን የሚቀናቀን ሰው ቶሎ መጥፋት አለበት። ከሳሾቹም ይኽንን ያውቃሉ። በአደባባይም የተጠየቀው "አንተ የእስራኤል ንጉሥ ነህን?" የሚለው መቅደሙ መልሱን ለማወቅ ነው። የሚቀናቀን ከሆነ ቶሎ የማጥፋት አስተሳሰብ እስካልተቀየረ ድረስ መጠፋፋት አያቆምም። እርግጥ ነው፣ እንደሥርዓት ዛሬ አፄ የለም። በወንበር ላይ ግን መንግሥትም፣ ተቃዋሚም ሁሉም የአስተሳሰብ አፄ ነው። ትውልድ ከዚህ አስተሳሰብ መውጣት አለበት። እሳትና ውሃ አጥፊና ጠፊ ቢሆኑም በወሰን፣ በክልል፣ በመጠንና በልክ ከተጠቀምንባቸው ሁለቱም የግድ አስፈላጊዎቻችን ናቸው።

Wednesday, June 22, 2016

ማኅበረ ቅዱሳን ወንጌልን ማቆም ያልቻለው ለምንድነው?


ከዙፋን (ተስተካክሎ የቀረበ)
ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሰረተ 25 አመት ሞላው። ድርጅቱ ከተመሰረተ ጀምሮ የፕሮቴስታንት፣ የካቶሊክና ሌሎች የክርስትና ክፍሎች የወንጌል ስብከት በፊት ከነበራቸው ውስንነት በበለጠ ሲሰፉ እንጂ ሲጠፉ አልታየም።
 በተለይም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች የሆኑና ቤተክርስቲያኒቱ ከወንጌል ጋር አንዳንዴም ከወንጌል በላይ ስፍራ የምትሰጣቸው ትውፊቶች፣ ድርሳናት፣ ገድላት ከዚያም ባለፈ ልዩ ልዩ አስማትና ተረቶች የእግዚአብሔርን የክብር ስፍራ ወስደውና ጋርደው መገኘታቸውን ያስተዋሉና ከውስጥ የተነሱ የተሃድሶ እንቅስቃሴዎች ከነበሩበት ሁኔታ እየሰፉና እያደጉ መጥተዋል። ግንዛቤያቸውን በሁሉም ዘንድ በማዳረስ ረገድ ሰፊ ተቀባይነት በማግኘታቸው ከነበሩበት የተወሰነ ሁኔታ ወጥተው ዛሬ ከማኅበሩ የ25 ዓመታት ቁጥጥር ውጪ ናቸው። ማኅበሩ የተሐድሶ እንቅስቃሴን ለመጨፍለቅ ያልቆፈረው ጉድጓድ፣ ያልፈነቀለው ድንጋይ አልነበረም። ከንግድ ድርጅቶቹ የሚያገኘውን ግዙፍ ገንዘብ፣ የሰው ኃይልና ማቴሪያልም ጭምር ለዚህ ስራ ያውላል። በተሐድሶ ላይ ግንዛቤ ማስጨበጫ፣ ዐውደ ርእይ፣ ስብሰባ፣ ወርክሾኘ፣ በንግሥ በዓላት፣ በዐውደ ምሕረት፣ በፅሑፍ፣ በምስል ወዘተ ልዩ ልዩ መንገዶች ህዝቡን ያስተምራል፣ ያስጠነቅቃል ቪዲዮ ይበትናል፣ ካሴት ይለቃል፣ በራሪ ወረቀቶችን ያሰራጫል። በዩኒቨርሲቲዎች፣ በኮሌጆች፣ በሕጻናት፣ በወጣቶች፣ በጎልማሶች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት ባሉ ሰንበት ት/ ቤት ተማሪዎች ላይ ሥር ነቀል ለውጥ ለማምጣት ሰርቷል። ተጽእኖውና መልእክቱ ያልገባበት ቤት የለም። ተሐድሶ፣ ሃራጥቃ፣ መናፍቃን፣ የአውሬው ተከታዮች፣ ፀረ ማርያሞች፣ ጠላቶች፣ ነካሾች፣ ቡችሎች…ወዘተ ብዙ ስም አውጥቶ ለማስጠላት ሞክሯል። በስለላ፣ በክትትል፣ በጥርጠራና በድጋፍ አብሮት ያልቆመውን ሁሉ ስም እየለጠፈ በማባረርና በማስፈራራት ብዙ ቢጓዝም ትምህርተ ተሐድሶ ግን ሊቀንስ አልቻለም። ከዚህ ሁሉ ልፋት በኋላ በውጤቱም በ25 አመት በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ታይቶ በማታወቅ መልኩ 15 ሚሊዮን ህዝብ በላይ ከኦርቶዶክስ አካውንት ወደ ፕሮቴስታንት እምነት ጎርፏል።
ብዙ ሚሊዮን ኦርቶዶክሳዊያን ምእመናን፣ መምህራን፣ ሊቃውንት፣ ቀሳውስት፣ መነኮሳት፣ ጳጳሳት ሳይቀሩ ባሉበት ቤታቸው ሆነው የተሐድሶ እንቅስቃሴን ደጋፊና አራማጅ ሆነዋል። የተሐድሶ እንቅስቃሴ መጀመር ወደሌላ የእምነት ድርጅት የሚኮበልለውን ምዕመን ቁጥር መቀነስ ችሏል። ችግሩ ያለው ከኦርቶዶክስ መሠረታዊ አስተምህሮ ሳይሆን በጊዜ ብዛት በገቡ የስህተት ትምህርቶችና የፈጣሪን ሥፍራ የተረከቡ የክህደቶች አምልኰዎች የተነሳ መሆኑን ተሐድሶዎች ማሳወቅ በመቻላቸውና ይህንን ለማስወገድ ደግሞ እዚያው ሆኖ በማስተማርና በመለወጥ እንጂ በመኮብለል አለመሆኑን ብዙ በመሥራታቸው የተነሳ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ የሱን የኑፋቄ ጽዋ ለመጨለጥ ያልፈለጉት እዚያው ከሚቆዩ ይልቅ ኮብልለው የትም ገደል ቢገቡለት ይመርጣል። በጀትና ኃይል መድቦ ተሐድሶዎችን ከመከታተል ይልቅ ከበረት አስወጥቶ፣ በረቱ ውስጥ የቆዩለትን በጎች የራሱ የግል ንብረት አድርጎ ለመቆጣጠር ያመቸዋል። ያስቸገረውና ብዙ ድካሙን መና ያስቀረው ነገር የተሐድሶ ኃይል በእውቀት፣ በጥበብና በተዋሕዶ ቀደምት እውነት ሁሉን ማዳረስ መቻሉ ነው።
የማኅበረ ቅዱሳን ትልቁ ችግር ራሱን የእውነትና የእምነት ጫፍ አድርጎ መመልከቱ አንዱ ጉዳይ ሲሆን ሌላው ደግሞ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአስተምህሮ ጥግ ላይ ከማኅበረ ቅዱሳን ውጪ ያለው ለማስተማር መሞከር ማለት አፍን ማሞጥሞጥ እንደሆነ አድርጎ ማሰቡ ነው። እውነታው ግን በተሐድሶ ምሁራንና በማኅበረ ቅዱሳን መካከል ያለው የእውቀት ልዩነት የሰማይና የምድር ያህል የተራራቀ የመሆኑ ጉዳይ ነው። ተሐድሶ አዲሱን የወይን ጠጅ በአዲስ አቁማዳ ይቀመጥ ሲል ማኅበሩ ደግሞ በአሮጌው አቁማዳ አዲሱን የወይን ጠጅ ማስቀመጥ ይቻላል በሚለው የእምነት አስተሳሰብ ልዩነት የተነሳ በተደራጀ አቅምና ሥልጣን በሚያደርገው ሩጫ ተሐድሶን ማስቆም አልቻለም። ተሐድሶ የግለሰቦች አሳብ ሳይሆን የእግዚአብሔር አሰራር መገለጫ በመሆኑ ማንም ድርጅት በትግል ሊያቆመው አይችልም።
“ወልበስዎ ለሐዲስ ብእሲ ዘሐደሶ እግዚአብሔር በጽድቅ፣ ወበርትዕ፣ ወበንጽሕ” ኤፌ 4:24
“ለእውነትም በሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ” የሚለን እግዚአብሔር በቃሉ አማካይነት ነው። በተረታ--ተረትና በእንቶ ፈንቶ ጩኸት በመባከን ፈንታ የወንጌልን እውነት መጨበጥ፣ ባዶ ተስፋ ከሚያስጨብጡ ዝናብ አልቦ ደመናዎች ዝናብ ከመጠበቅ ይልቅ ባለቤቱ ራሱ የሕይወት ውሃ ምንጭ እኔ ነኝ ካለው እውነት ቃሉ በመጠጣት መርካት መቻል ማለት መታደስ፣ መለወጥ፣ አዲስ ሰው መሆን ማለት ነው። እግዚአብሔር ሁሉም ሰው እንዲታደስለት ይፈልጋል። የተሰራነው አንድ ጊዜ ተሞልቶ ፈፅሞ ከማይደክም የባትሪ ኃይል አይደለም።
“ወዘንተ ውስጥነሰ ይትሔደስ ኩሎ አሚረ”
“... የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል” 2ኛ ቆሮ 4:16 እንዳለው መታደስ በመንፈሳዊነት ኃይል እግዚአብሔር እንደሚወደው ሆኖ መሰራት ማለት ነው።
በዚህም የተነሳ ማኅበረ ቅዱሳን የሚታገለው የእግዚአብሔርን ሃሳብ ለማስቆም ነው። ነገር ግን እስካሁንም አልቻለም፣ ወደፊትም አይችልም። ምክንያቱም ተሐድሶ፣

1. የእግዚአብሔር ሃሳብ ነው።

 በመጨረሻው ዘመን የክርስቶስ ወንጌል በምድር ሁሉ ሊሰበክ ግድ ነው። ሉቃ 12:49 “በምድር ላይ እሳት ልጥል መጣሁ “ እንደሚለው ጌታ የጣለው እሳት ይነዳል እንጂ አይጠፋም። ሐዋ 5-38
  “ይህ አሳብ ከሰው እንደ ሆነ ይጠፋልና፤ ከእግዚአብሔር እንደሆነ ግን ታጠፉአቸው ዘንድ አይቻላችሁም፣ ከእግዚአብሔር ጋር ስትጣሉ እንዳትገኙ” እንዳለው ከእግዚአብሔር ስለሆነ ሊጠፉ አልቻሉም፣ አይጠፉምም ።

2. የአብርሖት (enlightenment) ዘመን በመሆኑ፣

ይህ ዘመን ትምህርት የተስፋፋበት ብዙዎች ከመሃይምነት ነጻ የወጡበት መረጃ የበዛበት ነው። የሰዎች መንፈሳዊ ረሃብ በማይረዱት ግእዝ የማያውቁትን ነገር ተቀብለው ወደቤት ከመሄድ ባለፈ መጽሐፍ ቅዱስና መንፈሳዊ ፅሑፎችን በማንበብ ማብራሪያና መልስ የሚፈልግበት ዘመን ነው። ትውልዱ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ልምምድን በመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ይፈትሻል። ለእምነቱ በቂ ማብራሪያ ይሻል። ያነጻጽራል። መጽሐፍ ቅዱስን በሞባይሉ አስጭኖ የትም ቦታ ያነባል። እንደ መጨረሻ ባለሥልጣን ቃልም ያየዋል። ከዚህ ቃል ጋር የሚጋጭ ወይም ለማስታረቅ የሚሞክርን ማንኛውንም ውሸት ለመቀበል አይፈልግም። ይህንን ዘመነ አብርሖት ከእውነት ጋር በመስማማት እንጂ በመሸፋፈን ወይም ትቀሰፋለህ፣ በሰይፍ ትቆረጣለህ በሚል ማስፈራራት ማስቆም አይቻልም።

3. ዛሬም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መዳንና ፈውስ ስላለ፣

 እግዚአብሔር በአንድ ቃልና በጸሎት በአንዴ መፈወስ ያቃተው ይመስል ለሥጋዊ ፈውስ ሸንኮራ፣ ጻድቃኔ፣ግሼን፣ሚጣቅ፣ ሺፈጅ፣ ኩክየለሽ፣ ግንድአንሳ፣ ከድንጋይ አጣብቅ፣ መሿለኪያ፣ መንከባለያ፣ ገልብጥ፣ ሰንጥቅ ወዘተ አዳዲስ የፈውስ መደብር እየፈጠሩ የአንዱ ወረት ሲያልቅ ሌላ እየፈለሰፉ ገንዘብ ጉልበት ጊዜ ጨርሶ መፍትሄ በማሳጣት ተራራ ለተራራ መንከራተት ስለሰለቸው ሰው ከዚህ እንግልት ማረፍ ፈልጓል። ከ 5 ትውልድ ወደ10 ትውልድ፣ ወደ 30 የማይጨበጥ ቃል ኪዳን ለመጨበጥ ሲያበላልጥ በክርስቶስ ላይ ብቻ አንዴ ታምኖ በመኖር ዕረፍትን ፈልጓል።

4. ትውልዱ ከሱስ መፈታትን ስለሚፈልግ

የጫት፣ የሲጋራ፣ የሺሻ፣ የሃሺሽና የመጠጥ ሱስ በየመንደሩ ብዙ ወጣቶችን ተብትቧል። ሴተኛ አዳሪነት፣ ስርቆትና ዝሙት አንገቱ ላይ ያሰረው ክር ወይም መስቀል ነፃ ሊያወጡት አልቻሉም። የጠለንጅ ወይም የጊዜዋ ቅጠል ማጫጫስ መፍትሄ አልሆኑትም።
 44 ታቦት ባነገሠ ማግሥት ከነበረበት ሕይወት ሊፈታ ባለመቻሉ ከተስፋ መቁረጥ የሚያድነውን ይፈልጋል። ይኼውም ያልተቀላቀለበት የእውነት ወንጌል መስማት መቻሉ ነው።
2 ቆሮንቶስ 4፣2
“ነገር ግን የሚያሳፍረውን ስውር ነገር ጥለናልና በተንኮል አንመላለስም፣ የእግዚአብሔርንም ቃል በውሸት አንቀላቅልም፤ እውነትን በመግለጥ ግን በእግዚአብሔር ፊት ለሰው ሕሊና ሁሉ ራሳችንን እናመሰግናለን”

5. ለሥራ ስለሚያነሳሳ፣

 እምነቱን ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ያስተካከለ ሁሉ ለበጎ ሥራ የተነሳሳ ሰው ነው። ከወንጌል ሥራን እንጂ ስንፍናን አይማርም። ዐባይን ብቻዋን እንድትጠቀም ግብጽ በሕዝባችን ላይ የጫነችው የስንክሳር የበዐላት ሸክሟን ከራሱ ላይ አራግፎ በመሥራት ራሱንና ወገኖቹን የሚጠቅም ትውልድ እንጂ ስለአባ እገሌ እያለ የሚለምን ዜጋ ሊኖር አይችልም። ትንሽ ሠርቶ ያገኛትን ደግሞ በፍትሃት ድግስ እያራገፈ፣ ብዙውን ጊዜ ደግሞ ዛሬ መልአከ እገሌ፣ ነገ አባ እገሌ፣ በዓታ፣ ጸአታ፣ ፍልሰታ፣ ልደታ፣ ግንቦታ፣ እያለ አበሻ ሥራ ቢሰራ የተለየ ቀሳፊ የተመደበበት ይመስል ዐዛሬ ቅጠል አልበጥስም” እያለ ይኖርበት ከነበረው ዘመን ተፈትቶ በዘመነ ተሐድሶ ነፃ እየወጣ የዕለት እንጀራውን ለማግኘት ሌሊትና ቀን እየሰራ ነው። በዐል ሳያከብር ፈረንጅ ያመረተውን ስንዴና ዘይት በእርዳታ የሚለምን በዐል አክባሪ እንደአበሻ ግብዝ የት ይገኛል?

ስለዚህ የዘመነ ተሐድሶ የክርስቶስን ወንጌል የሚቋቋም ማንም አይኖርም። የክርስቶስን ወንጌል የሚያቆም ከሰማይ በታች ምንም ዓይነት ኃይል ወይም ማኅበር የለም። ይሁን እንጂ ወርክሾፕ፣ ስልጠና ፣ አቅም ግንባታ፣ ሕንጻ ግንባታ፣ ኤግዚብሽን ግንባታ፣ ዐውደ ርእይ ወዘተ መደረጉ አይቀርም፣ ይኽ መደረጉ የእግዚአብሔርን የተሐድሶ ሐሳብ አያቆመውም። ማኅበረ ቅዱሳን የብር ኢዮቤልዩውን እንዲህ ካሳለፈ ዕድሜው ከሰጠው የወርቁን ደግሞ አመራሩ ራሱ ከኑፋቄ ወጥቶ ኢየሱስ ክርስቶስን ብቻ በማምለክ ያከብረው ዘንድ የእግዚአብሔር የተሐድሶ እቅድ መሆኑን አንጠራጠርም።

Wednesday, June 15, 2016

በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው!!


የቁልቁለት መንገድ ተጀምሯል!

ይህ ጽሑፍ በመጋቢት ወር 2004 በመካነ ጦማራችን ላይ የወጣ ነው። ደግመን ማውጣት ያስፈለገን፤ ሞት የሁሉም ሰው ጽዋ ቢሆንም ማኅበረ ቅዱሳን ፓትርያርክ ጳውሎስን በደጋፊ ጳጳሳቱ በኩል እስከሞት እያዋከበ መቆሚያና መቀመጫ እንዳያሳያቸው እነሆ ፓትርያርክ ማትያስን በተራቸው እስከሞት እየተዋጋ ለመቆየት መቁረጡ በዳበረ ልምዱ ሲሰራበት መቆየቱን ለማሳየት ነው። እንዲህ ብለናቸው ነበር። አንዳች ነገር ሳያደርጉ ሞት ወሰዳቸው፤ ማኅበሩም ሰፋለት። (አመኑንም አላመኑም ፓትርያርክ ጳውሎስ፤ አንድ ነገር አስረግጠን እንነግርዎታለን። በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው) ዛሬም ፓትርያርክ ማትያስን ለተመሳሳይ ጽዋ  በወከባና በአድማ እያንደረደረ ይገኛል። ማኅበሩ የሚተዳደርበት አዲስ ሕግ ሳይጸድቅ፤ በዐቃቤ መንበርና በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የሥልጣን ነጠቃውን ጀምሯል። ወደፊትስ?

በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ማኅበረ ቅዱሳን ከተራ ማኅበርነት ወደ ሀገረ ስብከትነት  አደገ። በዚህም የተነሳ ሲኖዶሱ ሙሉ በሙሉ በማኅበረ ቅዱሳን እጁን ተጠምዝዞ እንደሚሰራ አስመሰከረ። የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ተጠሪነቱ ለቅዱስ ሲኖዶስ ሆኖ  የየሀገረ ስብከቶቹ  ጠቅላይ ጽ/ቤት ሆኖ ያገለግላል። ይህ ጽ/ቤት ደግሞ የሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ በየ3 ዓመቱ በሚያደርገው ምርጫ በሚመድበው ሊቀጳጳስ ነው። እንግዲህ ማኅበረ ቅዱሳን ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና አሥኪያጅ ሆነ ማለት ራሱን የቻለ ሀ/ስብከት  ሆነ ማለት ነው። የጠቅላይ ቤተክህነቱ መምሪያዎች ሊያዙት አይችሉም። ከዚያም በላይ ቅዱስ ፓትርያርኩ ሊያዙት፤ ሊናገሩትና ሊቆጡት አይችሉም ማለት ነው። በቀጥታ በቅዱስ ሲኖዶስ በሚመደበው ሊቀጳጳስ በኩል ግንኙነቱ ከቅዱስ ሲኖዶሱ ጋር ብቻ ይሆናል ማለት ነው። እንዲህ ነው እንጂ ሹመት፤ መሾም ካልቀረ!! አንድ ማኅበር ባንድ ጊዜ እመር ብሎ አናት ላይ ፊጢጥ ብሎ ከመቀመጥ ወዲያ ሹመት ከወደየት ይገኛል? ከእንግዲህ  ከተቀመጠበት ደረጃ አንጻር ማኅበር መባሉ ዝቅ የሚያደርገው ስም ስለሆነ የቅዱሳን መምሪያ ወይም የወጣቶች ሀ/ስብከት እንዲባል ሲኖዶሱ በነካካው እጁ ስሙንም ማሻሻል ይገባዋል። ከዚያም አያይዞ ለዚሁ አዲስ ሀ/ስብከት አንድ ሊቀጳጳስ እንዲመድቡለትም ጥቆማውን እናቀርባለን። አንድ ነገር ታዘብን። ቤተክርስቲያኒቱ ሲኖዶስ የሚባል አካል እንደሌላት ተረዳን። በአንድ ተራ ማኅበር እየተመሩ የእሱን ጉዳይ ብቻ ሲያነሱና ሲጥሉ ሦስትና አራት ቀናት ስብሰባ መወዘፍን ምን ይሉታል? ስንት ስራ መስራት እየቻሉ ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ማውረድ እስኪያቅታቸው ድረስ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን አጀንዳ ይዞ መከራከርን እውነት ሰዎቹ በመንፈስ ቅዱስ ነው የሚመሩት እንድንል ያደርገናል። ይህ ማኅበር ባይኖር ኖሮ ስለምን ጉዳይ ሊሰበሰቡ ነበር፤፤
ይህ ማኅበር እስካሁን እየታዘዘ እንዳልቆየ የተጻፉለት ደብዳቤዎች አረጋጋጮች ናቸው። እሱ ራሱ አልቀበልም ብሎ በደብዳቤ አረጋግጧል። አንዴ ከኢህአዴግ፤ አንዴ ደግሞ ከተቃዋሚ ነኝ እያለ፤ ሌላ ጊዜ ከሀገር ቤቱ ሲኖዶስ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ ገለልተኛ እየመሰለ የተጓዘበትን ሁላችንም እናውቃለን። የወንድሞች ከሳሽና አሳዳጅ ስለመሆኑም ግፉን የቀመሱ ሁሉ ይመሰክራሉ። የተጓዘባቸውን ስልቶች ሁሉ ያጠናው መንግሥት ከሽብር አቀንቃኝ  ከሰለፊያ ጋር በአንድ ረድፍ አንዳስቀመጠው ነግሮናል። ስለሆነም አቡነ ጳውሎስ ይህንን የአድማና በጥቅም የተሳሰረ ውሳኔ አልፈርምም በማለት ውድቅ ሊያደርጉት ይገባል። ማኅበሩ አስቀድሞ ከሰለፊያ ተግባር ነጻ ስለመሆኑ ማረጋገጫ ማምጣት ይጠበቅበታል። ደጋፊዎቹ ጳጳሳትን በማስረጃና በሰው ምስክር ተጠንተው ብቁ ሆነው ያልተገኙ ካሉ ከማዕርጋቸው መሰናበት አለባቸው።  ቄስ የነበሩ፤ ልጆች የወለዱ፤ ቅምጥ ያላቸው እንዳሉ ይወራል፤ የአንዳንዶቹም ይታወቃል።  እየተሸፋፈነ መቀመጡ ለቤተክርስቲያን ጠንቅ የሆነ ውሳኔ ለማስወሰን ያልተመለሱ ሰዎች ስብስብ መሆኑ ከታየ ውሎ አድሯል።  ነውራቸውን ለመሸፈን እንኳን ከድመት አንሰዋል።
በአንድ ወቅት አባ ገብርኤል፤ አቶ ኢያሱ ተብለው ከማዕርጋቸው ተገፈው እንደነበረው፤ ማንነታቸው እንደገና ተመርምሮ  አስቸጋሪ በሆኑት ላይ ዛሬም ተመሳሳይ ውሳኔ ሊሰጥባቸው ይገባል። ጨከን ያለ የሥርዓት ማስከበር አካሄድ መውሰድ ካልተቻለ ሲኖዶሱን በነሱ በኩል እያወከ ነገ ፓትርያርክነቱን አስቀድሞ ከዚያም ቤተመንግሥቱን እንደሚረከብ የሚጠራጠር ካለ የማኅበሩን አካሄድ የማያውቅ ብቻ ነው። አመኑንም አላመኑም ፓትርያርክ ጳውሎስ፤ አንድ ነገር አስረግጠን እንነግርዎታለን። በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው። ከሆነለት ፓትርያርክነቱን ለሚታዘዝ  ሰው  ሰጥቶ ወደ ቤተመንግሥት ሰተት ብሎ ለመግባት ከጽዋ ማኅበርነት ወደ መምሪያ ተገዳዳሪነት፤ አሁን ደግሞ ወደ ሀገረ ስብከትነት ማደጉ ከምንም በላይ ማሳያ ነው።  ታዲያ ከእንግዲህ የቀረው ምንድነው? ይህ ሁሉ ለጽድቅ ነው እንዳይትሉንና እንዳንስቅ ጥቂት እዘኑልን። ነጋዴና  ሸቃጭ የሆነ  ቅዱስ ማኅበር  አራት ኪሎ የለም ። እያየነው በትንሽ በትንሹ የወጣው ይህ ሐረግ ቤተ ክህነቱን አንቆ ወዳሰበበት በመጓዝ ላይ ነው። እግዚአብሔር ለዚህ ክፉ ማኅበር አሳልፎ ከሰጠ በእውነትም ቤተክርስቲያኒቱ ለፈተናና ለውድቀት ተመርጣለች ማለት ነው። ተወደደም፤ ተጠላ ሲኖዶስ በየዓመቱ ያለህውከት ማለፍ አይችልም።
ሰውዬው «ሁሉን ለማየት መቆየት»እንዳለው የሚሆነውን ለማየት ከዕድሜው አይንፈገን!

Monday, June 13, 2016

"ፓ" ይላል ምዕመኑ!!!



«በዘውድአለም ታደሰ»
ነብይ ነኝ ባዩ የቤተክርስቲያን ደላላ!

ይሄ ሰውዬ "ጎሳ" ይባላል። በተለያየ ጊዜ የተለያዩ ቸርቾች ሲሰብክ አይቼዋለሁ። (ጎፋ መድሃኒአለም ፣ ዘፀአት ፣ FBI ፣ ወዘተ... ) የሚደክም አይነት ሰው አይደለም። ውሃ ሳይጎነጭ በተከታታይ ለሶስት ሰአታት የማውራት አቅም አለው! የምእመኑን ሳይኮ በልቶታል። ህዝቤን ምን እንደሚያስጮሀት ስለሚያውቅ አዳራሹን በጩኸት መናጥ ለነብይ ጎሣ ቀላል ነው!
ብዙ ግዜ ቸርቾች ይህን ሰውዬ ሚጋብዙት ገንዘብ ክፉኛ ሲያስፈልጋቸው ነው። ወይ መሬት ሊገዙ ሲያስቡ ... አሊያም የተሻለ አዳራሽ ሊከራዩ ሲፈልጉ ... ብቻ የሆነ የፈንድ ሬይዚንግ ጉዳይ ሲኖር ጎስሻን ይጠሩትና በዚያች ጮሌ ምላሱ የራሱንም ሆነ የሌሎች ሰዎችን ታሪክ እያጋነነ በመስበክ የዚህን ምስኪን ምእመን ኪስ ያራቁትላቸዋል!
«ነኝ ያልኩ ኮንትራክተር ነበርኩ፣ ነፍፍ መኪኖችና ብዙ ሰራተኞች ነበሩኝ፣ ጌታ ሲገባኝ ግን ንብረቶቼን ሸጬ ለቸርች ሰጠሁ» ብሎ ይጀምራል ተረት ተረቱን።
«ፓ» ይላል ምእመኑ!
«ከዛ ክፉኛ ተቸገርኩና፣ ምልስ ምቀምሰውን አጣሁ፣» ብሎ ለፅድቅ ሲል የከፈለውን መከራ እያጋነነ ያወራል!
«በከተማዋ ስሜ የተጠራ ኮንትራክተር እንዳልነበርኩ ምልስ ምቀምሰውን አጥቼ ተቸገርኩ» ሲል ረሃብን የሚያውቀው የዚህ ህዝብ አንጀት በሀዘኔታ ይላወሳል።
የሰዉን አቴንሽን ማግኘቱን ሲያረጋግጥ ታዲያ ... እንዴት ተአምራዊ በሆነ ሁኔታ እግዜር ሀብታም እንዳደረገው፣ እንዴት እንዳበለፀገው ትረካ በሚመስል ሁኔታ ያወራ ያወራና የህዝቡን አእምሮና ስሜት በሚገባ እንደተቆጣጠረ ሲረዳ እንዲህ ይላል ..
«ጌታ እንዲህ ሲል ተናግሮኛል» ብሎ ይጀምራል ነብይ ጎሳ። (ማን ነብይ እንዳረገው እንጃለቱ)
«ጌታ ዛሬ በዚህ አዳራሽ ውስጥ ያላችሁትን ሁላችሁን እባርካለሁ ብሎኛል» ሲል እቺ በረከቷን ከአርያም ሳይሆን መድረክ ላይ ከቆመው አረም የምትጠብቅ ምእመን አዳራሹን በጩኸት ታቀልጠዋለች! በጭብጨባው የሚሟሟቀው ጎሲሻም «አንዳንዶቻችሁ ከዚህ አዳራሽ ስትወጡ ከበረከታችሁ ጋር ትገናኛላችሁ» ሲል አዳራሹ በአንድ ድምፅ «አሜን» ይላል።
«አንዳንዶቻችሁ ደግሞ ቤታችሁ ስትገቡ በረከታችሁ ቁጭ ብሎ ይጠብቃችኋል»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ ስራ ቦታችሁ ላይ»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ የዛሬ ሳምንት»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ የዛሬ ወር»
«አሜን»
«እግዜር በተራራው ላይ ሙሴን ሲያገኘው በእጅህ ላይ ምን አለ? ብሎ ነው የጠየቀው ወገኖቼ። እግዜር እጃችን ላይ ባለ ነገር ነው ሚሰራው። ዛሬ በእጃችሁ ላይ ምን አለ?» ይላል ብልጣብልጡ ጎሳ!
ይሄ የዋህ ሁን ሲባል ሞኝ የሆነ ህዝብም እውነት መስሎት እጅና ኪሱን ያያል! ከዛማ በቃ አዋራው ይጨሳል .... ፒፕሉ በረከቱን በስጦታው ለመግዛት ይጋፋል! አዳሜ ወርቋን ከአንገቷ ላይ እየበጠሰች፣ ገንዘቧን ከቦርሳዋ እያራቆተች፣ ምንም የሌላት ደግሞ የእጅ ስልኳን ሳይቀር መባ እቃ ውስጥ እየጨመረች የማይፈፀም ትንቢት ታቅፋ እርቃኗን ከአዳራሹ ትወጣለች ... ልትባረክ ነዋ ሃሃሃሃ
ከላይ እንዳልኩት ነብይ ጎሳ ነብይነቱን ከየት እንዳገኘው ማንም አያውቅም። የሚያወራው ታሪክም እውነት ስለመሆኑ ምንም ማረጋገጫ የለም። ይህን ሰውዬ የሚጋብዙት ስግብግብ የቤተክርስቲያን አገልጋዮችም የሰውየው ምስክርነት እውነት የተፈፀመ ይሁን አይሁን ለማረጋገጥ ምንም አይነት ጥረት አያደርጉም! እነሱ ሚፈልጉት በሱ ጅንጀና የሚዘንበውን የገንዘብ ዶፍ ነው። የስብከቱ መለኪያ በሱ ስብከት አማካኝነት የገባው የገንዘብ መጠን ነው እንጂ የእግዚአብሔር ቃል አይደለም!
አሁን ቤተክርስቲያን በጎሳና ጎሳን በሚመስሉ መንፈሳዊ ደላሎች እየታመሰች የምትገኝበት ሰአት ላይ ትገኛለች። መፅሀፉ ጎሳንና መሰል አገልጋዮችን «ለመንጋው የማይራሩ» ይላቸዋል!
እንዲጠብቁት የተሰጣቸውን ምእመንና እረኛ የሆኑለትን መንጋ ስጋ እየበሉ ሰብተው ቆዳውን ገፍፈው ይለብሳሉ! በአስራትና በበኩራት፣ በመባና በፍቅር ስጦታ ስም፣ ገንዘቡ ወደካዝናቸው ይጋዝ እንጂ የገንዘቡ አመጣጥ እነሱን አያስጨንቃቸውም። በምእመኑ ፍራንክ ትልልቅ እቅዶች ያቅዳሉ፣ የህዝቡን መሶብ አራቁተው ሰማይ ጠቀስ ፎቆችን ይገነባሉ፣ በሊትር ሶስት ኪሎሜትር የሚሄዱ ላግዥሪ መኪኖችን ይነዳሉ። ይሄ ተስፈኛ ምእመን ግን ከሰማይ መና እየጠበቀ በደረቅ ምድረ በዳ ደረቅ ትንቢታቸው ታቅፎ ከቃዴስ ቃዴስ ሲንከራተት ይኖራል።
በአብዛኞቹ የወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያኖች ዘንድ ምድር ምድር የሚሸት ስብከት በዝቷል። ሰባኪው ሁሉ የ prosperity Gospel (የብልፅግና ወንጌል) አቀንቃኝ ሆኗል፣ ምእመኑም በረከቱን የሚለካው በምድራዊና ቁሳዊ ሀብት ብቻ ነው! «ሀገሬ በሰማይ ነው» አይነት ንግግሮች ከምእመኑ አንደበት መደመጥ አቁመዋል። ኢየሱስ የሞተው ለቼቭሮሌት መኪናና ለግራውንድ ፕላስ ስሪ ፎቅ ይመስል ወሬው ሁሉ ቤት ስለመስራትና ቤት ስለማፍረስ ሆኗል ... እንደ ዊነርስ ቻፕል አይነት ቸርቾችማ ወሬው ሁሉ ሱሪ ስለመቀየርና መኪና ስለመንዳት ከሆነ ቆየ። «በመንፈስ መኪና የመንዳት» ፕሮግራም ሁሉ ያካሂዳሉ አሉ! ሃሃሃ
ነብያቶች በዝተዋል። ነብይነት ግን ከሞተ ቆየ! ሰባኪዎችም አሸን ናቸው። ስብከት ግን ስልሳዎቹ ላይ ቆሟል! በየመድረኩ ተኳኩለው እንጣጥ እንጣጥ የሚሉ (ባለብዙ ሚስት ዘማሪዎች እልፍ ናቸው) መንፈሳዊ ማንነትን የሚያንፅ መዝሙር ግን ከመድረኩ ነጥፏል!
በፅድቅና በቅድስና የሚያገለግሉ አንዳንድ አገልጋዮች እንዳሉ አይጠፋኝም። ግን እነዚህ አገልጋዮች ከጎሳውያኑ ጋር ሲተያዩ በገምቦ ውስጥ እንዳሉ ጥቂት ጠብታዎች ናቸው! ስለዚህ ባህር ውስጥ እንዳሉ አይቆጠሩም። እኔ ማወራው ባህሩን ስለሞሉት የተበከሉ አሳዎች ነው!
 ቸርቾች በየመቶ ሜትሩ ከተማ ውስጥ ፈልተዋል። ደቀመዝሙር ማፍራት የማይችሉ ውሀ አልባ ምንጮች ናቸው እንጂ! ክርስቲያን ያልሆኑ የክርስቶስ ሰባኪዎችና ክርስቶስን የማያውቁ አገልጋዮች ይሄን ምስኪን ምእመን እንደአሻንጉሊት እየተጫወቱበት ነው! አገልግሎታቸው ያከበራቸውን ህዝብ በመናቅና በማስፈራራት ላይ የተመሰረተ ነው! «ለምን?» ብሎ ጥያቄ የሚያነሳ ሲመጣ «ጌታ በቀባው ላይ እጅህን አታንሳ» በማለት በጥቅስ ያስፈራሩታል። በፅድቅ ለማገልገል ከላይ እታች እያሉ የጅብ ድግሳቸው ላይ የማይሳተፉትን ንፁሀን ደግሞ የተለያየ ስም ጀርባቸው ላይ በመለጠፍ ከአገልግሎት ያግዷቸውና የሚከተላቸውን ምእመን ኑሮ እየቀሙ ይኖራሉ! ሳቁን መንትፈው ይስቃሉ! ደስታውን አራቁተው ይደሰታሉ! እውነትም ለመንጋው የማይራሩ ሆዳሞች!
ዘመኑ የባቢሎናውያኑን ዘመን ይመስላል። ትርምስ እንጂ መረጋጋት የለም! ጩኸት እንጂ መግባባት ጠፍቷል። ግራ የተጋቡ ባለራእዮችና ያልተማሩ አስተማሪዎች መሬት ባልረገጠ የትምህርት ወጀብ ህዝቡን እየናጡት ነው። በተቀየጠ ዶክትሪንና በስህተት አስተምህሮ ምእመኑን ከወንጌል አርቀው አይኑን በማሰር ወደቁልቁለት እየነዱት ነው! ነብያት ነን ባዮቹ ወንዝ በማያሻግር ትንቢት ሲወራጩ መድረኮቻችን ላይ ውለው ያድራሉ። ዝናብ የሌላቸው ደመናዎች በተራ ፉከራና ሽለላ የተሞሉ ፍሬ አልባ ደረቅ መሬቶች ናቸው!
በተለያዩ ቤተክርስቲያኖች እየተጋበዘ ህዝቡን የሚያራቁተው ደላላው ነብይ .... «ነብይ ጎሳም» ከላይ ለጠቀስኳቸው ሆዳም አገልጋዮች እውነተኛ ምልክት ሊሆን ይችላል ባይ ነኝ!

እቀጥላለሁ!‎

Saturday, June 4, 2016

ማኅበረ ቅዱሳን አሁን የቤተ ክርስቲያን፤ ቆይቶ የመንግሥት መጥበሻ ምድጃ ነው!


በታሪክ አጋጣሚ የደርግን መውደቅና ግርግርን ተተግኖ የተፈጠረው ማኅበረ ቅዱሳን የመጥበሻ ምድጃ ከሆነ እነሆ 23 ዓመታት አለፉት። ብዙዎችን በትኗን፤ አሳዷል። ዳግም እንዳይመለሱ በማድረግ እንደተዋጊ በሬ እየበጠበጠ ከበረት አስወጥቷል። በማወቅም ይሁን ባለማወቅ አፋፍተው ያሳደጉትን አቡነ ጳውሎስን ሳይቀር በአድማ የመጥበሻ እሳት እየለበለበ እስከመቃብር ሸኝቷል። የአሁኑን ፓትርያርክ የአቡነ ማትያስን ወንበር በተሾሙ ሰሞን ለመረከብ ተፍ ተፍ ብሎ ሳይሳካለት ቢቀር በተለመደ የመጥበሻ ምድጃው ላይ አስቀምጦ ላለፉት 3 ዓመታት  በአድማው ግሪል / GRILL/ እየጠበሰ ይገኛል።

ፓትርያርክ ማትያስ ብቻቸውን ሆነው ይህንን መጥበሻ ምድጃ ሊያስወግዱ ብዙ ታግለዋል። ነውራም ጳጳሳቱ እዳ በደላቸው በዚህ ማኅበር የኃጢአት መዝገብ ላይ ስለሰፈረ ከፓትርያርኩ በተጻራሪ ቆመው ውግንናቸው ለማኅበሩ ሆኖ ታይቷል። የማኅበሩ ሥፍራ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የት ነው? በሚለው ነጥብ ላይ ጥያቄ ያላቸው ፓትርያርክ ማትያስ ድርሻውን፤ አቅሙንና ተጠሪነቱን የሚወስን አዲስ መተዳደሪያ ደንብ እንዲወጣለት ያደረጉት ተጋድሎ ላይ ውሃ በመቸለስ የሲኖዶስ ጉባዔ በመጣ ቁጥር የሚያጨቃጭቅ አጀንዳ እያስገባ ሲሾልክ ቆይቷል። ዘንድሮም ይህን የቤት ሥራ ሰጥቶ በአንድ አጀንዳ ላይ ለ4 ቀናት ካጨቃጨቀ በኋላ የሲኖዶስ አባል የሆነው የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር መፍትሄ አስምጦ ሊገላግላቸው ችሏል። ይህ ሁሉ የሆነው በማኅበሩና በጉዳይ ፈጻሚ ጳጳሳቱ የተነሳ ነው።

የእንደራሴ መኖር አለመኖር ለማኅበረ ቅዱሳን አሳሳቢው አይደለም። ነገር ግን በዘንድሮው ጉባዔ ላይ ማንሳት ያስፈለገው የራሱ ስሌት ስላለው እንጂ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ድክመት ከሱ መኖር በላይ አስቸጋሪ ፍጡር ስለመጣ አይደለም። በዚህም የተነሳ በአቅም ማነስ ሰበብ ፓትርያርኩን አሸመድምዶ በማስቀመጥ ለ3 ዓመታት ያህል እሳት ካነደዱበት ሥጋት ነጻ ለመውጣት የተያዘ መላ ከመሆን አይዘልም። ከዚህም በፊት እንዳልነው ጳጳሳቱ በሀገረ ስብከታቸው መሥራት ያልቻሉትን የመንፈሳዊና ሥጋዊ የልማት ሥራዎች  እንደራሴው እየዞረ የሚሰራላቸው አለመሆኑንም በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል። ማኅበረ ቅዱሳን እስካለ ድረስ ታዛዥ ያልሆነ የትኛውም የቤተ ክርስቲያኒቱ ባለሥልጣን  ማኅበሩ ባዘጋጀው መጥበሻ ላይ ይጣዳል። ምርጫቸው ከማኅበሩ ጋር መቆም አለያም በተጻራሪ ሆነው ለመጥበሻው ራሳቸውን ከማዘጋጀት የግድ ነው። አባ ሳዊሮስ ከአዲስ አበባ ማኅበረ ካህናት ጋር ቆመው ማኅበሩን ሲያጋልጡ ምድጃውን አዘጋጅቶ መጥበስ ሲጀምር እጃቸውን አንስተው ለማኅበሩ ለማስረከብ መገደዳቸውን አይተናል። አባ ፋኑኤል ማኅበሩ የሌለበት ቦታ የት ሄጄ ልሥራ? እንዳላሉ ሁሉ ምርኮኝነታቸውን ካረጋገጡ በኋላ ግን ከማኅበሩ መጥበሻ ግሪል ላይ ወርደው እረፍት ሊያገኙ ችለዋል። ሌሎቹ ግን የሚደርስባቸውን እሳት አስቀድመው ስለሚያውቁ ቃላቸውን አክብረው የጫናቸውን በማራገፍ ግንቦትና ጥቅምት በመጣ ቁጥር በማኅበሩ አጀንዳ አስፈጻሚነታቸው ቀጥለዋል።

 ማኅበረ ቅዱሳን በስመ ተሐድሶና ሙሰኛ ነጠላ ዜማው የፈጃቸውና ያቃጠላቸው ካህናት ቁጥራቸው ብዙ ነው። ስለቅድስናና መንፈሳዊ ንጽህና በዋለበት ያልዋለ የዋልጌዎች ስብስብ ይህ ማኅበር ስም እያጠፋ ያሳደዳቸው፤ ስለኃጢአታቸው ንስሐ የሚገቡበትን በር እየዘጋ ተስፋ በማስቆረጥ ያስወጣቸው የትየለሌ ናቸው። የሚገርመው ግን ነውራም ጳጳሳቱን በቅድስና ካባ ሸፍኖ ለአገልግሎቱ የሚጠቀምባቸው የከባቴ አበሳ ተፈጥሮ ስላለው ሳይሆን እስካለገለገሉት ድረስ ብቻ ነው። እያንዳንዱ የማኅበሩ አባል በተለይም አመራሩ እነአቡነ እገሌ እስከምን ድረስ የጉስቁልና ባሕር ውስጥ እንደሰጠሙ እያወቀ በስምምነት አብሮ ይሰራል። ነገር ግን ከማኅበሩ አቋም ካፈነገጡ ከዚህ በፊት እንዳደረገው የእዳ ደብዳቤአቸውን ከማንበብ አይመለስም። ይህ በተግባር የተረጋገጠ እውነት ነው።

አንዳንዶች ማኅበሩን የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር ብቻ አድርገው ያያሉ። ነገር ግን ማኅበሩ  እንደግብጹ የሙስሊም ወንድማማቾች ማኅበር በፖለቲካው መድረክም የረቀቀ ተልእኮ ያለው ማኅበር ነው። በአባልነት ያቀፋቸው ሚኒስትሮች፤ ከፍተኛ ባለሥልጣኖች፤ ሥራ አስኪያጆች፤ ፖሊሶች፤ ዳኞች፤ የሕዝብ አገልግሎት ሠራተኞች፤ መምህራንና ተማሪዎች፤ የሙያ ማኅበራት፤ በ44 አኅጉረ ስብከት ውስጥ ያሉ ሚሊዮኖች የሰንበት ት/ቤት አባላት፤ የጥምቀት ተመላሽ ተጠባባቂ ጦር የመሳሰሉትን በአባልነት እየመለመለ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም የራሱን ዶክትሪን በመጋት ማኅበረ ቅዱሳን፤ ማኅበረ ቅዱሳን ካሰኛቸው ውሎ አድሯል። ዛሬ ከሲኖዶስ ወይም ከፓትርያርኩ በላይ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ተቆርቋሪና ጠባቂ ከማኅበሩ በላይ የለም የሚለው አስተሳሰብ በእያንዳንዱ ሰው አእምሮ ውስጥ እንዲሰርጽ በሰፊው ተሰርቷል። ዘመናዊ የክርስቲያን ብራዘር ሁድ ማለት ማኅበረ ቅዱሳን ነው።

ሌላው የማኅበሩ ተንኮል አሁን ካሉት ታማኝና ታዛዥ ጳጳሳት በተጨማሪ ከእንግዲህ የሚሾሙ ኤጲስ ቆጶሳት በራሱ መስፈርት የተመለመሉና ወደፊት ችግር እንደማይፈጥሩ የተረጋገጠላቸው ብቻ እንዲሆኑ ይፈልጋል። እነዚህ የማኅበሩ እጩ ኤጲስቆጶሳት ያለፈ ታሪካቸው የቱንም ቢመስል አሳሳቢ አይደለም። ተቀባይነታቸው አርአያነት ባለው ሁኔታ ቢሆንም፤ ባይሆንም ለማኅበሩ አስጊ እስካልሆኑ ድረስ እንዲመረጡ አጥብቆ ይሰራል። ነገር ግን በተቃራኒ ማኅበሩን የሚፋለሙ ከሆነ እንደአባ ሠረቀብርሃን ወ/ሳሙኤልን የመሳሰሉት በልዩ ልዩ ስምና ወንጀል በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ እጃቸውን ካልሰጡ በስተቀር ለእጩነት ሊቀርቡ አይችሉም።

በአጠቃላይ ማኅበሩ በታሪክ አጋጣሚ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የተገኘ መጥበሻ ምድጃ ነው። በዚህ ምድጃ ዲያቆናት፤ ቀሳውስት፤ መነኮሳት ተጠብሰዋል። ሰባኪያነ ወንጌልና አስተዳዳሪዎች ተጠብሰዋል። ጳጳሳትና ፓትርያርኮች ተጠብሰዋል። እውነቱን እያወቁ ከመናገር ብዙዎች የተቆጠቡት ማኅበሩ መጥበሻው ላይ ከጣዳቸው የሚያወርዳቸው ስለሌለ ነው። ልክ እንደ መንግሥታዊ የስለላ መዋቅር የማኅበሩን ስም በተቃውሞ በአውቶቡስ፤ በታክሲ፤ በሬስቶራንት፤ በየካፌውና በሕዝብ መሰብሰበቢያ ቦታዎች መጥራት ከማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። መንግሥት ላይ ምን ዓይነት የአንኮበር መድኃኒት እንደተረጨበት ባናውቅም እሱም በፍርሃት ይሁን በድንዛዜ ፈዞ ቀርቷል።  እውነታው ግን ማኅበሩ ለየትኛውም ወገን መጥበሻ ምድጃ መሆኑ በተግባር የተረጋገጠ ነው።