Wednesday, August 22, 2012

የብጹእ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ሥርዓተ ቀብር ሐሙስ ይፈጸማል፤ መጪው ዘመንስ ምን ይመስል ይሆን?


ብጹእ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከዚህ ዓለም በሞት ከተለዩ እነሆ አንድ ሳምንት ሊሆናቸው ነው። የሚወዷቸው አዝነዋል፤ የሚጠሏቸውም ደስ ተሰኝተዋል። አንዳንዶች ቢጠሏቸውም እንኳን ሞት የጋራ ርስት መሆኑን በማመን እግዚአብሔር እረፍቱን ይሰጣቸው ዘንድ ከልባቸው ተመኝተዋል።
አብዛኛው ሕዝብ ደግሞ መጪው ዘመን ለቤተክርስቲያንም ሆነ ለሀገሪቱ ምን ይመጣ ይሆን? በሚል ሃሳብ ረጅሙን ጊዜ በማስላት ይጨነቃል። በእርግጥም ሟቾች ጥፋትም ይስሩ ልማት ላይመለሱ ሄደዋል። የነበሩበት ቦታ ትልቅ የመንፈሳዊና የሥጋዊ ሥልጣን ደረጃ በመሆኑ ቤተክርስቲያኒቱን በመንፈሳዊ አባትነት ሊመራ የሚችልን ሰው በማግኘት አንጻር ቢያሳስበን አይገርምም። በስጋዊ ሥልጣን ደረጃም እንደዚሁ በሀገር መሪነት ደረጃ የሚመጣው ሰው የነበሩ ድክመቶችን በማስተካከል፤ የታዩ ጥንካሬዎችን ለማስቀጠል ስለመቻሉ ቢያሳስበን እንደዜጋ ከተገቢነቱ የወጣ አስተሳሰብ አይደለም።
 ቀና ቀናውን አስበን፤ መጪውን ጊዜ ብንፈራ ሰው ነንና ተገቢ ነው።
ይሁን እንጂ ክፉም ሆነ ጨካኝ ገዢ የሚመጣብንና የመጣብን መሪዎች ክፉ ወይም ደግ ለመሆን ስለፈለጉ ሳይሆን ለእንደዚህ ዓይነት ሰዎች ተላልፎ የተሰጠ አምልኰ ስላለን መሆኑን አምነን ልንቀበል ይገባል።
እግዚአብሔር ለዳዊት በተናገረው ቃል ላይ ከወገቡ የሚወጣው ልጅ እንደሕጉ ከሄደ መልካም የሆነው ነገር ሁሉ ከፈጣሪው እንደሚሆንለት፤ ክፋትን በፈጸመ ጊዜ ደግሞ የሰው መቅጫ በትር እንደሚላክበት በመጽሐፍ ቅዱስ ተገልጾ ይገኛል።
2 ሳሙ 714
እኔም አባት እሆነዋለሁ፥ እርሱም ልጅ ይሆነኛል ክፉ ነገርም ቢያደርግ፥ ሰው በሚቀጣበት በትርና በሰው ልጆች መቀጫ እገሥጸዋለሁ
እኛ ደጎችና የእግዚአብሔር ፈቃድ ፈጻሚዎች ሆነን ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር በቅጣት ወይም በመከራ ውስጥ አይተወንም ነበር። ስለዚህ ለሆነውና ለሚሆነው ሁሉ ጥፋተኞች እኛ እንጂ ሌላ ማንም አይደለም። 
ኢዮብ 3412    
በእውነት እግዚአብሔር ክፉ አይሠራም፥ ሁሉንም የሚችል አምላክ ፍርድን ጠማማ አያደርግም።
የሚያሳዝነው ነገር ኢትዮጵያውያን በማንነታችን ስንመዘን ፊታችንን ወደእግዚአብሔር ለመመለስ ፈቃደኞች ያልሆንን እልከኛ ህዝቦች መሆናችን ሲታይ መከራ የምንለው ነገር ማብቂያው ገና ረጅም ነው። ከጣዖት አምልኰ ገና አልተላቀቅንም። አምልኮቶቻችን ብዙዎች ናቸው። እግዚአብሔርን በከንፈሩ የሚያከብር በልብ ግን ከፊቱ የራቅን ሕዝቦች ነን። ከመበላላት ገና አልወጣንም። ሥልጣንን ጠልፎ ለመውሰድ ከሚደረግ የሽንገላና የተንኮል ተግባር ገና አልተላቀቅንም። ቤተክህነቱም ሆነ ቤተመንግሥቱ ለእግዚአብሔር ይገዛ ዘንድ ለፈቀደ ሕዝብ ገና ዝግጁ አይደለም።  ሁሉም ያሰፈሰፈው ለወንበሯ ነው። ሀገሪቱ በሃሳብ ነውጥ ተወጥራለች። ሰላም ነን እያልን ራሳችንን ካልሸነገልን በስተቀር አየሩ በሁከትና በሃሳብ ተበክሏል። ይህ ካልጸዳ የሀገሪቱ ችግር አላባራም ማለት ነው። አዎ መጪው ዘመን ያስፈራል። አመላችንና አኗኗራችን ገና አልተስማማም።

የክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር አስከሬን ወደ ሀገር ቤት ተመለሰ።




የጠቅላይ ሚኒስትሩ አስከሬን ትናንት ማታ አራት ሰዓት አካባቢ ቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ደርሷል። ሚኒስትሮች፤ አምባሳደሮችና ቤተሰቦቻቸው በተገኙበት አስከሬናቸው ታጅቦ ወደ ቤተመንግሥት አምርቷል። ብዙዎችም በልቅሶ ሸኝተዋል። የቀብር ሥርዓቱን የሚያስፈጽሙ አባላት የተዋቀሩ ሲሆን ወደፊት በሚገለጽ መርሃ ግብር ቀብራቸው እንደሚፈጸም ቀደም ሲል ተገልጿል።
ላለፉት 21 ዓመታት የሀገሪቱ መሪ ሆነው ያገለገሉት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውን በመንግሥት ቴሌቪዥን ከተለገጸ በኋላ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፤ ታዋቂ ግለሰቦች፤ የውጭ ሀገራት መሪዎችና ዲፕሎማቶች የሀዘን መግለጫዎቻቸውን እየላኩ ይገኛሉ። የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንም የጠቅላይ ሚኒስትሩ ሥርዓተ ቀብር እስኪፈጸም ድረስ የሀዘን ቀን እንዲሆንና የሀገሪቱም ሰንደቅ ዓላማ ዝቅ ብሎ እንዲውለበለብ መወሰኑን አውጇል።

በዚሁ በተቃራኒ መልኩ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ሞት ደስ የተሰኙ፤ የኢትዮጵያ ነጻነትና የፖለቲካ አፈና አበቃለት የሚሉ፤ እኛ መግደል ቢያቅተን እግዚአብሔር ወይም አላህ ገደልልን የሚሉ ድምጾች እየተስተጋቡ ይገኛሉ። በተለይም ከወደ ዳያስፖራው ያሉ ኢትዮጵያውያን እንኳን ሞቱልን የሚሉ ጥቂቶች አይደሉም።  በተለይም በፓልቶክ የቀጥታ ውይይቶች ላይ «ዛሬ ነው ድሌ» የሚሉ ጭፈራዎችን ሲያስተጋቡ መስማት አስገራሚው  ነው። በእርግጥ አቶ መለስን ጠንካራ፤ ታታሪ፤ ብልህና አዋቂ አድርገው የሚደግፏቸው ጥብቅ  አጋርና ወዳጆች እንዳሏቸው ሁሉ እንደ ማንኛውም ሰውና እንደ አንድ ሀገር መሪ ሊኖርባቸው በሚችል ሰውኛ ድክመቶች፤ የሚወቀሷቸው ወይም ባለባቸው ጉድለት የሚያዝኑባቸውም ጥቂቶች አይደሉም።
ነገር ግን እግዚአብሔር እንደወደደ ባደረገው ስልጣኑ ላይ ገብተው የሚጠሏቸው ሰዎች በመዝፈን፤ በመሳለቅና «ዛሬ ነው ድሌ» በማለት በሞት ላይ ፌሽታ ማድረግ በምንም  መመዘኛ ከሰብአዊነት አእምሮ የሚነጭ ሊሆን አይችልም።
ደጋፊዎችም ጠቅላይ ሚኒስትሩን ፍጹማዊ ሰው እንደነበሩ አድርገው ከማሰብ እንዲርቁ፤ የሚጠሏቸውም በሞታቸው እልል ከማለት የጥላቻ ሁሉ ጥግ እንዲወጡ ለማስገንዘብ እንወዳለን። 
ሞት የሁሉም ሰው ጽዋ ነውና ከፊታችን ባለው ነገር ላይ ደስ ከመሰኘት ይልቅ ከሞት በኋላ ባለው ሕይወት ውስጥ የእያንዳንዳችን ድርሻ ምን ሊሆን እንደሚችል ማሰቡ ላይ ማተኮሩ የተሻለ ነው።


በሌላ መልኩም «ደጀ ሰላም» ብሎግ የቅዱስ ፓትርያርኩ የጠለቀ ሀዘኑን በመግለጽ የብሎጉን የፊት ገጽ ለዚሁ መግለጫ ማዋሉን ስንመለከት ደጀ ሰላም ብሎግ፤ ፓትርያርኩ ከሞቱለት በኋላ እንደዚህ ፍቅር ያሲያዘው ነገር አልገለጽ ብሎናል። ምክንያቱም ስማቸውን ሲያጠፋ፤ የሙስና አባት፤ የቤተክርስቲያኒቱ ጠላቶች ወዳጅ፤ የተሀድሶዎች ጋሻ እያለ ሲጠራቸው እንዳልነበርና፤ በስልጣን ላይ እስካሉ ድረስ የቤተክርስቲያን ሰላም የለም ይል የነበረውን ዘገባዎቹን ሁሉ ትቶ አሁን የልብ ወዳጄና ዘላለማዊ እረፍት ሊያሰጣቸው የሚችል የመልካም ስራ ባለቤት ናቸው ብሎ ያመነ በመምሰል ከአብርሃም እቅር ይረፉልኝ ማለቱ ተሳልቆ ካልሆነ በስተቀር ሲወዳቸው ለኖረ አባት የቀረበ ጸሎት አይደለም። ድሮም ክፉ ሰው በከንፈሩ ይሸነግላል ተብሎ ተጽፏልና ይህ ሸንጋይ ድረ ገጽ ከሞቱልኝ ወዲህ ምን አገባኝ፤ ከአብርሃም እቅፍ ያኑርልኝ የማልል፤ ባለቤቱ ከፈለገ እንጦሮጦስ ይጨምራቸው የሚል የክፉ ሰው ሽንገላ ጸሎት ካልሆነ በስተቀር ደጀ ሰላምና አባ ጳውሎስ ዓይንና ናጫ እንደሆኑ እስከሞታቸው ድረስ መዝለቃቸውን ማንም ኅሊና ያለው ሰው ያውቀዋል። አንድም ቀን በሰላም አባትነት፤ በእምነት አባትነት፤ በፍቅር አባትነት፤ አመስግኗቸው እንደማያውቅ የማናውቀው ይመስለው ይሆን?

ደጀ ሰላም ሆይ እስኪሞቱልህ ድረስ ስትወቅሳቸው ኖረህ፤ ከሞቱልህ በኋላ መጸለይህ ለእሳቸው ያለህን ፍቅር እየገለጽህ ነው ወይስ ቋሚዎቹን ሰዎች እንደምወዳቸው እወቁልኝ ለማለት ነው? የልብንማ እግዚአብሔር ይመረምራል።

Tuesday, August 21, 2012

ሰበር ዜና፤ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው ተገለጸ።




ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ አረፉ።
ሕወሀትን በመምራትና ኢህአዴግን በማዋቀር ትልቅ ሚና የነበራቸውና ከደርግ ውድቀት በኋላም የሀገሪቱ ርእስ መንግሥት ሆነው ላለፉት 21 ዓመት የቆዩት፤ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውን ዛሬ ነሀሴ 15/2004 ዓ/ም በይፋ ለሕዝብ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ተነግሯል።
አቶ መለስ ዜናዊ እድሜአቸውን ሙሉ በትግል ያሳለፉ፤ በዚሁ ትግል ውስጥ እያሉ በሞት የተለዩ ትልቅ መሪ ነበሩ። በሞታቸው ሃዘናችንም ጥልቅ ነው።
እግዚአብሔር ለወዳጅ ኢትዮጵያውያን ሁሉ የሀዘን ጽናቱን ይስጥ!

Monday, August 20, 2012

ሰበር ዜና፤ በማኅበረ ቅዱሳን ትእዛዝ የተሰበሰበው ሲኖዶስ አቡነ ናትናኤልን በዐቃቤ መንበርነት ሾመ።



ሸምቆ ወጊው ማኅበር ብጹእ አቡነ ናትናኤልን ዐቃቤ መንበር ለማድረግ ዛሬ 14/12/ 2004 ዓ/ም  ሲኖዶሱን በጠራው ዘመቻ መሠረት ይህንኑ አስፈጽሞ ዓላማውን አሳክቷል።
ከዓውደ ምሕረት ብሎግ ያገኘነውን ዘገባ እንዳካፈልናችሁ ሁሉ ጉዳዩን በቅርብ ስንከታተል ቆይተን የዛሬው የሲኖዶስ ጉባዔ በማኅበረ ቅዱሳን እቅድ መሠረት ብጹእ አቡነ ናትናኤልን ዐቃቤ መንበር ማስደረግ እንደቻለ ምንጮቻችን አስረድተዋል። ብጹእ አቡነ ናትኤል ከእርጅና የተነሳ ራሳቸውን መቆጣጠር ከማይችሉበት ደረጃ መድረሳቸው እየታወቀ በአስቸኳይ መምረጥ ያስፈለገው አቅም ኖሯቸው ስራ ይሸፍናሉ ተብሎ ሳይሆን ከሳቸው ጀርባ የሚፈለገውን ስራ ለማከናወን እንዲቻልና የፓትርያርክነቱን ስልጣን በእነ አቡነ ጢሞቴዎስ አቀናባሪነት ወደ አቡነ ማትያስ እንደማቅ እቅድ ደግሞ ወደ አቡነ ሉቃስ ላይ ለመወርወር እቅድ እንደተያዘ ውስጥ አዋቂ ምንጮቻችን አስረድተዋል።

የሲኖዶሱ ዋርካ አቡነ ጳውሎስ ከወደቁለት ወዲህ ሸምቆ ወጊው ማኅበር «አልጋ ባልጋ ነው መንገዱ፤ ወደ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰርጎ ለመግባት ሲሄዱ» የሚል መዝሙር መዘመር ከሚችልበት ደረጃ ላይ ደርሷል ማለት ይቻላል። ተጨማሪ ዘገባ እንደደረሰን እናቀርባለን።

ሰበርዜና፡-በማኅበረ ቅዱሳን እየተዘወረ ያለውና መሪውን ያጣው ሲኖዶስ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስን ከአመራር ሰጪነት ለማውረድና ዐቃቤ መንበር በአፋጣኝ ለመሰየም ለነገ ቀጠሮ ይዟል

 የደርግ  ርዝራዥ የሆነው ማኅበረ ቅዱሳን፤ ደርግ ሲያስተጋባ እንደነበረውና « ተፈጥሮን ሁሉ በቁጥጥራችን ስር እናደርጋለን» ሲል እንደነበረው ሁሉ ብላቴ ጦር ካምፕ ላይ ከውትድርና ወደ ስመ ቅድስና ሺፍት በማድረግ ቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ስሩን የዘረጋው ማኅበር፤ የቅዱስ የፓትርያርኩ ሞት ሳይታሰብ እንደተገኘ ሎተሪ በመቁጠር የራሱን ንጉሥ ቀኑ ሳይመሽ ለማሾም የሞት ሽረት ትግሉን እያደረገ «ቤተክርስቲያንን በቁጥጥራችን ስር እናደርጋለን» በሚል መንፈስ እንደአባቱ ደርግ እየሰራ ይገኛል። ቁጭ ብለው የሰቀሉት፤ ቆሞ ማውረድ እስኪቸግር ድረስ ይህ ማኅበር ጳጳሳቱን እያስፈራራና በገመናቸው ሳቢያ እያሸማቀቀ ተሰብሰቡ ሲላቸው፤ የሚሰበሰቡ፤ ተበተኑ ሲላቸው የሚበተኑ የምስኪናን ጉባዔ ሆነዋል። የቅዱስ ፓትርያርኩ ሥርዓተ ቀብር ከተፈጸመ በኋላ ዐቃቤ መንበር እንዲሾም፤ እስከዚያው ድረስ በዋና ሥራ አስኪያጁ አቡነ ፊልጶስና ቋሚ ሲኖዶስ እንዲመራ የተወሰነ መሆኑ ቢታወቅም የዚህንን ቆይታ ጊዜ በማስላት ተጠቃሚ ሊሆን እንደማይችል ያረጋገጠው ክፉው ማኅበር፤ ሲኖዶሱ በአስቸኳይ ተሰብስቦ አስተላልፎ የነበረውን ውሳኔ እንዲሽርና አቡነ ናትናኤልን ዐቃቤ መንበር አድርጎ እንዲያስቀምጥለት ባስተላለፈው ትእዛዝ መሠረት አቤት፤ ወዴት እያሉ ለመሰብሰብ ፈቃደኛ ሆነውለታል።  እግዚኦ መሃረነ ክርስቶስ የሚባለው ዛሬ ነው። አስተዳዳሪዎች፤ ካህናትና፤ዲያቆናት፤ አበው መነኮሳት ዛሬ ያልተናገራችሁ ነገ መራራ ዘመናችሁ ከደጃችሁ ቆሟል።
የዓውደ ምሕረትን ዘገባ ከታች አቅርበንላችኋል። መልካም ንባብ!

ማኅበረ ቅዱሳን አቡነ ናትናኤል ይሁኑልኝ ብሏል።

(ዐውደ ምሕረት፤ ነሐሴ 13 2004 ዓ.ም. / www.awdemihret.blogspot.com //www.awdemihret.wordpress.com) የአቃቤ መንበሩን ምርጫ ከብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ሥርዓተ ቀብር በኋላ ይፈጸማል ብሎ የነበረው ቅዱስ ሲኖዶስ የአቡነ ፊሊጶስ የሰሞኑ አካሄድ በማኅበረ ቅዱሳን በኩል ስላልተወደደ የአቃቤ መንበሩን ምርጫ በነገው ዕለት ለማድረግ ዛሬ ማምሻውን ወስኗል ተባለ።
     ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በሕይወት እያሉ መልካም ሥራዎቻቸውን እያኮሰሱና እንከን እየፈለጉባቸው ክፉኛ ሲያብጠለጥሏቸውና ሲያሳዝኗቸው የነበሩ ብዙዎች፣ ቅዱስነታቸው ካንቀላፉ በኋላ የእርሳቸው መልካም ስራዎችና ተሸክመው የነበሩት ትልቅ ሀላፊነት ከባድ መሆኑንና ብዙ ኅልፈታቸው እንዳጎደለ ለመረዳት ጊዜ አልፈጀባቸውም፡፡ በመሆኑም ያለማንም አስገዳጅነት የቅዱስነታቸውን መልካምነት በመመስከር ሥራ ተጠምደዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ይጠቀሳሉ፡፡
   በማኅበረ ቅዱሳን ወዳጅነታቸው የሚታወቁትና ማህበሩ አውጆት በየአዳራሹ ሲያካሂድ ለነበረው የተሀድሶ ግንዛቤ ማስጨበጫና ገቢ ማሰባሰቢያ ጉባኤ ባራኪ የነበሩት ብፁዕነታቸው አሁን የቅዱስነታቸውን በአይን የሚታይ በእጅ የሚዳሰስ መልካም ገጽታቸውን መገንባታቸው በማኅበረ ቅዱሳን ዘንድ አልተወደደም፡፡ ስለዚህ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስን ከዚህ ወሳኝ ጨዋታ ውጪ ለማድረግ ሲባል፣ ከቅዱስነታቸው ስርአተ ቀብር በኋላ ሊከናወን ቀጠሮ የተያዘለት የዐቃቤ መንበር ምርጫ በነገው ዕለት እንዲካሄድ በማኅበረ ቅዱሳን እየተዘወረ የሚገኘውና ሁነኛ መሪውን ያጣው ሲኖዶስ መወሰኑን ውስጥ አዋቂዎች ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡
     ቅዱስ ሲኖዶሱ አቡነ ጳውሎስ ካረፉ በኋላ ባደረገው የመጀመሪያ ስብሰባው ብጹዕ አቡነ ፊልጶስ እስከ ሥርዓተ ቀብር ድረስ በሲኖዶስ ሰብሳቢነት እንዲቆዩ ወስኖ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፣ አሁን ግን በፓትርያርኩ ድንገተኛ ሞት የተነሳ ቤተክርስቲያኒቱ ወደ አለመረጋጋት እንዳትሔድ ብጹዕ አቡነ ፊልጶስና መሰሎቻቸው በሚያደርጉት አዎንታዊ እንቅስቃሴ ለማህበረ ቅዱሳን ፍላጎቶች በበቂ ሁኔታ ተገዢ ባለመሆናቸው እና ማኅበርዋ ባቀደችው መሰረት ነገሮች ሊሄዱላት ስላልቻሉ፣ በሰብሳቢነት እንዲቆዩ ከተወሰነ ከሁለት ቀን በኋላ የዐቃቤ መንበሩ ምርጫ በነገው ዕለት እንዲደረግ ተወስኗል።
     ቅዳሜ ዕለት የቀብር አስፈጻሚ ኮሚቴው የቅዱስነታቸው ቀብር በስራ ቀን ስለተደረገ ወደቅዳሜ ይዘዋወርልን የሚል ጥያቄ ሲያቀርብ “አንዴ ለሚዲያ የተናገርነውን ነገር አንሽርም ህጻናት አይደለንም።” በማለት ውድቅ ያደረጉት ጳጳሳት አሁን ግን የማኅበረ ቅዱሳንን ፍላጎት ለመፈጸም ሲሉ የአቃቤ መንበሩን ሹመት ከቅዱስነታቸው ቀብር በኋላ ይፈጸማል በማለት ለሚዲያ የተናገሩትን ቃላቸውን ሽረው በእነሱው አነጋገር “የሕጻን ስራ” ሰርተዋል።
     ማኅበሩ መንግስትን በጣልቃ ገብነት እየከሰሰና ስሙን እያጠፋ ራሱ ግን ይህን ዕድል ተጠቅሞ የራሱን ሰው ለማስመረጥ መንገድ ጠራጊ የሚሆኑለትን በዐቃቤ መንበርነት ለማስመረጥ ተግቶ እየሰራ ሲሆን፣ ስውሩም ግልጹም አመራር በከፍተኛ ስብሰባ ተጠምደዋል፡፡ አንዳንዶቹ ሥራቸውን ሁሉ ትተው በጉዳዩ ላይ ተግተው እየሰሩ መሆናቸው ታውቋል፡፡
   ከቀድሞ ጀምሮ በጳጳሳቱ በኩል ያለውን ስራ በማከናወን የሚታወቀውና አቡነ ጳውሎስን አምርሮ የሚጠላው ማንያዘዋልም ጳጳሳቱን የማግባባት ስራውን እየተወጣ ሲሆን፣ ማኅበረ ቅዱሳንም ያመነበትን ሰው ለማስቀመጥ ከዚህ የተሻለ ጊዜ እንደሌለው አውቆ በከፍተኛ ሁኔታ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። በነገው ዕለት ሊደረግ ለተወሰነው የአቃቤ መንበር ምርጫ ሊመረጡ የሚገባቸው አቡነ ናትናኤል መሆናቸውን ዛሬ ማምሻውን እየዞሩ ጳጳሳቱን በማግባባት ስራ ተጠምደው ያሉት አቡነ ህዝቅኤል እና በማኅበረ ቅዱሳን በኩል ለፓትርያርክነት ተስፈኛ የተደረጉት አቡነ ሉቃስ መሆናቸው ታውቋል።
   አቡነ ናትናኤል ከእርጅና ብዛት ሽንታቸውን እንኳ መቆጣጠር የማይችሉ አባት ሲሆኑ ስብሰባ የመምራትም ሆነ ተናግሮ የማሳመን ብቃት የሌላቸው ሰው መሆናቸው ይታወቃል። በእሳቸው በኩል ያሉት ጉድለቶች እና የጤና እክላቸው የታወቀ ቢሆንም የማኅበረ ቅዱሳንን አላማ በማስፈጸም ረገድ የተሻሉ ሰው በመሆናቸው እንዲመረጡ የማግባባት ስራው ተጀምሯል። የማኅበሩ አላማ እሳቸውን ዝም ብሎ አስቀምጦ በ2001 ዓ.ም. ቅዱስ ፓትርያርኩን ከስልጣን ለማውረድ ተቋቁሞ የነበረው አቡነ ጢሞቴዎስ፣ አቡነ ሳሙኤል አቡነ እስጢፋኖስ እና አቡነ ሉቃስ የሚገኙበት የማኅበረ ቅዱሳን ታማኝ የሆኑ ጳጳሳት ኮሚቴ እንዲመራው ለማድረግ ነው።

Sunday, August 19, 2012

ፓትርያሪክ መርቆሪዮስ ወደ መንበራቸው ይመለሱ!



ዲ/ን ሙሉጌታ ወልደገብርኤል 
የፓትርያሪክ ጳውሎስ ሞት ከአወዛጋቢነት አልፎ አስደንጋጭ ዜና እየተሰሙ ነው። ፓትሪያሪኩ ህይወታቸው ለህልፈት እስከተዳረገች ዕለት ድረስ በተለይ የዕለቱ ውሎአቸው እስከ ሥርዓተ ቁርባን ድረስ ምንም ዓይነት ችግርና እንዲሁም የድካም መንፈስ ያልታየባቸውና ያልተስተዋለባቸው ሲሆኑ ቅዱስቁርባኑን ከወሰዱበት ቅጽበት ጀምሮ ግን በሰውነታቸውን ላይ የመዛል፣ በሚታይ የሰውነት ክፍላቸውም በላብ የመጠመቅ ዓይነት ምልክት እንደታየባቸው በትናት ዕለት ካነጋገርቸው በዕለቱ አብሮአቸው ቤተ- መቅደስ ውስጥ ነበሩ ከተባሉ ካህናት ተጨባጭ ምስክርነት ለማግኘት ተችለዋል።
በሁኔታው ግራ የተጋቡ የዓይን ምስክሮች ጨምረው እንዳወሱልኝም ከሥርዓተ ቁርባኑም ሆነ ከዚያ በፊት የነብሩ ቀናት ፓትሪያሪኩ እንደ ወትሮ የዕለተ ዕለት ግዴታዎቻቸውን በሚገባ ሲያከናውኑ እንደሰነበቱና ምንም ዓይነት ለሞት ሊዳርግ የሚያስችል ዓይነት ሕመም እንዳልነበራቸውም ለማወቅ ተችለዋል። ታድያ ገዳያቸው ማን ሊሆን ይችላል? ቤተ- ክርስቲያን እነሆ ደመ ክርስቶስ ብላ ለስዎች ልጆች ሕብረት በምታቀርበው በጽዋ ላይ ገዳይ መርዝ ጨምሮ ጭቃኔ በተሞላበት አረመንያዊ ድርጊት የሰው ነፍስ ለህልፈት ዳርጎ ሲያበቃ ተጠቃሚ የሚሆነው ማን ሊሆን ይችላል? የቤተ- ክርስቲያኒቱ አባቶችና ሊቃውንት መምህራን በመግደልስ የጥቅም መርበቡን በቤተ- ክርስቲያን ላይ የመዘርጋትና እውን የማድረግ ዓላማ አነግቦ የተነሳ ነፍሰ ገዳይ ማን ይሆን? ለሚሉና ሌሎች ተያያዥ ጥያቄዎች በሰፊውና በተጠናከረ መልኩ ሳምንት እመለስበታለሁ።
በዛሬው ዕለት ግን ህልፈተ ሥጋ ፓትርያሪክ ጳውሎስ ተከትሎ በብዙሐን ዘንድ አነጋጋሪ ከሆኑት ርዕሰ ጉዳዮች መካከል በቀዳሚነት እያነጋገረ የሚገኘውን የፕትርክና መንበሩ/መቀመጫው ማን ይተካው? የሚለው ጥያቄ ዙሪያ ላይ አጭር መልስ/መፍትሔ ለመጠቆም ነው። ስህትት በስህተት ለማረም ወይንም ደግሞ ለማስተካከል እንደማይቻል ከሌላው በተሻለ ኢትዮጵያውያን ብዙ ማለት እንደምንችል አመናለሁ። ይኸውም ስህተትን በስህተት ለማስተካከበል በሞከርናቸው ዘመናት ሁሉ እርምጃዎቻችን ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው አመዝኖ ዛሬ ምድራችንም ሆነ ሕዝባችን የሚገኝበት አሳፋሪ ገጽታና የተመሰቃቀለ ህይወት ማየቱ በቂ ማስረጃ ነው ብዬ አምናለሁ።
እዚህ ላይ አጽንዖት ሰጥቼ ለማስተላለፍ የምወደው መልዕክት ቢኖር ቤተ- ክርስቲያን በተለይ በሀገር ውስጥ የሚገኘውን ሲኖዶስ ከቀድሞ ስህተት ይልቅ የባሰ ስህተት እንዳይሰራ ከወዲሁ እርምጃዎችን ይመረምር ዘንድ ነው የሚጠየቀው። ፓትሪያሪክ ጳውሎስ አልፈዋልና አዲስ መሾም ያስፈልጋል በማለት በጥድፍያ የሚሆን ነገር እንደሌለ በመገንዘብ በተለይ በሁለቱ አብያተ ክርስቲያናት መሪዎች መካከል የተጀመረውን የዕርቀ ሰላም አጀንዳ በሁለቱም አካላት በጎ ተነሻሽነት በአስቸይ ፋይሉን በመክፈት ቤተ -ክርስቲያኒቱ አንድ የምትሆበትና ወደ ቀድሞ አንድነትዋ የምትመለስበት እንዲሁም የቀድሞ ፓትሪያሪክ ወደ መንበራቸው የሚመለሱበት መንገድ በርትቶና ተግቶ መስራት እንደሚጠበቅበት ነው የማምነው። ይህን አይነቱ እርምጃ ደግሞ ከየትኛውም አቅጣጫ ለማየት ቢሞከር ሀገራዊም ሆነ መንፈሳዊ ጠቀሜታውም የጎላ ነው
በተጨማሪም የመንፈሳዊያን መሪዎችም ሆነ የቤተ- ክርስቲያን አጀንዳ ሰላምና ሰላም እስከሆነ ድረስ ለዓመታት የዘለቀውን ቀውስና ትርምስ መግታትና ማስቆም የሚቻለው መንበሩ ከፖትሪያርክ መርቆርዮስ አልፎ ለማንም ሊሆን እንደማይችልና እንደማይገባ በማመን ፓትሪያሪክ መርቆሪያስ ወደ ቀድሞ መቀመጫቸው ለመመልስ በሚሳየው በጎ ተነሳሽነት ነው። ይህም የምለው ያለ ምክንያት አይደለም። በቤተ- ክርስቲያኒቱ ጉዳይ ላይ የሚመለከተውም የማይመለከተውም አፉን በከፈተ ቁጥር ለዚህ ሁሉ ዕንቅፋትና መሰናክል መዋቹ ፓትሪያሪክ ጳውሎስ ብቸኛ ተጠያቂ ያደርግ እንደነበረ ማናችንም አንስተውም። ታድያ አሁን ማንን ተጠያቂ ልናደርግ ነው? በህይወት ባሉ ፓትሪያሪክ ላይ ፓትሪያሪክ ለመሾም አይደለም ሊሞከር ፈጽሞ ሊታሰብም አይገባውም። ፓትርያሪክ መርቆሪዮስ ወደ መንበራቸው ይመለሱ!
መቀመጫው አሜሪካ ላያደረገ የአበው ጉባኤ (ሲኖዶስ):
ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዮስ ብጹዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ሆይ! ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ሮሜ ሰዎች ምዕ 12 :17 በሰው ሁሉ ፊት መልካም የሆነውን አስቡ። ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ ሲል እንደ ጻፈላቸው ዛሬ ደግሞ እኛ ባለተራዎች በእኩል ኃይል ሥልጣንና መንፈስ ቃሉ ከፍ ባለ ድምጽ ሰላምን እናወርድ ዘንድ አፍ አውጥቶ እየጮኸ ይገኛል። ሳሙኤል ገና ብላቴና በነበረበት ዘመን እግዚአብሔር በስሙ ይጠራው ነበር። ሳሙኤልም ገና የእግዚአብሔር ድምጽ ለይቶ ካለማወቁ የተነሳ እግዚአብሔር በጠራው ቁጥር ብድግ እያለ ወደ ኤሊ በመሄድ እነሆ የጠራኸኝይለው ነበር። ታድያ ከዕለታት አንድ ቀን ነገሩ የገባው ሊቀ ካህን ሳሙኤልን ሄደህ ተኛ ቢጠራህም አቤቱ ባሪያህ ይሰማልና ተናገር በለው በማለት አሰናብቶታል። 

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰላምና አንድነት ጉባኤ ጽ/ቤት የተሰጠ የኃዘን መግለጫ



ነሐሴ 11/2004 /     /Aug 17/2012
ክቡር ሞቱ ለጻድቅ በቅድመ እግዚአብሔር” (መዝ 1156)
የአምስተኛውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ  የብፁዕ ወቅዱስ / አቡነ ጳውሎስን ዕረፍት አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  የሰላምና አንድነት ጉባኤ /ቤት የተሰጠ የኃዘን መግለጫ።
ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ
አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ
እንዲሁም በቅድስት ሀገር ኢትዮጵያና በመላው ዓለም ለሚኖሩ የኢትጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ምዕመናን በሙሉ።

        በሰሜን አሜሪካ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰላምና አንድነት ጉባኤ በአምስተኛው ፓትርያርክ በብፁዕ ወቅዱስ / አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፤ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም፤ ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዝዳንትና የዓለም የሰላም አምባሳደር ድንገተኛ ዕረፍት ምክንያት የተሰማውን ከፍተኛና ትልቅ ኃዘን ይገልጻል። እንደሚታወቀው ቅዱስነታቸው   ለቤተ ክርስቲያናችን ዕድገትና መሻሻል፣ መጠናከርና መስፋፋት የሚጠቅሙ በርካታ መንፈሳዊ ተግባራትን ያከናወኑ  ታላቅ የቤተ ክርስቲያናችን አባትና  የሥራ ሰው ነበሩ። በመሆኑም ቅዱስነታቸው በአገልግሎት ዘመናቸው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያከናወኗቸው ዘርፈ ብዙ ሐዋርያዊ ተግባራት ምን ጊዜም ሕያውነታቸውን ሲያስታውሱ ይኖራሉ። ቅዱስነታቸው ብሔራዊውን የአብነት ትምህርትና ዘመናዊውን ዕውቀት አገናዝበው የተማሩ ታላቅ ሊቅ ስለነበሩ ለቤተ ክርስቲያን እጅግ አስፈላጊ ቅዱስ አባት ነበሩ፤ ይልቁንም ባለንበት ዘመን ቤተ ክርስቲያናችንን በዓለም መድረክ ወክለው ያከናወኗቸው ብዙ ሥራዎች ዘወትር ሲታሰቡ ይኖራሉ። ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን እኒህን ታላቅ አባት በድንገት በማጣቷ ልባዊ ኃዘናችንን በድጋሚ እንገልጻለን። በእውነቱ የቅዱስነታቸው  ድንገተኛ ዜና ዕረፍት ለቤተ ክርስቲያን ትልቅ  ኃዘን ነው።
          ይልቁንም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰላምና አንድነት ጉባኤ በቅዱስነታቸው አባታዊ ቡራኬና በቅዱስነታቸው በሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መልካም ፈቃድ ሦስተኛውን ዙር የሰላምና አንድነት ጉባኤ ለማካሄድ በዝግጅት ላይ ሳለ ይህንን ቤተ ክርስቲያንን አንድ የሚያደርግ ታሪካዊ ሒደት ለፍጻሜ ሳይበቃ የቅዱስነታቸው ዜና ዕረፍት መስማቱ ጉባኤውን በእጅጉ አሳዝኖታል፤ ሊያስከትል የሚችለው ውጣ ውረድም ከወዲሁ አሳስቦታል። ቅዱስነታቸው የጀመሩትን የቤተ ክርስቲያን ሰላምና አንድነት ጥረት የመጨረሻ ፍሬ ሳያዩ በድንገት በማለፋቸው ኃዘናችን ወሰን የለውም። የሰላምና አንድነት ጉባኤው በቅዱስነታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት ላይ ተገኝተው የጉባኤውን የኃዘን መግለጫ የሚያደርሱ ልዑካንን  ሰይሞ ለመላክ በአንድነት ወስኗል።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰላምና አንድነት ጉባኤ ቤተ ክርስቲያንን አሁን ካለችበት አሳሳቢ የልዩነት ፈተና ይበልጥ ወደ ባሰና ወደ ከፋ ችግር እንዳትሄድ ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ተቀዳሚ ሥራው በማድረግ ለዘመናት በአንድነቷ ጽንታ የኖረችውን ቤተ ክርስቲያን የቀድሞ ታሪኳን ለመመለስና ለማደስ ተገቢውን ሥራ በአንድነት እንዲሠራና እስካሁን ድረስ የቆየው የልዩነት ምዕራፍ እንዲዘጋ፣ በቅዱስነታቸውና በቅዱስ ሲኖዶስ በጎ ፈቃድ የተጀመረውን የሰላምና አንድነት ሒደትም ለፍሬ ያበቃው ዘንድ ጉባኤው ከታላቅ አደራ ጋር ይማጸናል።
በመሆኑም የሰላምና አንድነት ጉባኤው ለቅዱስ ሲኖዶስና ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መላው ካህናትና ምእመናን ወምእመናት ከዚህ የሚከተለውን መልእክት ያስተላልፋል።
1/ በቅዱስነታቸው ድንገተኛ ዕረፍት ምክንያት የተሰማንን ጽኑ ኃዘን እየገለጽን ከምንም በላይ በቅዱስ ሲኖዶስ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ዋነኛውና አንገብጋቢው ጉዳይ ቤተ ክርስቲያንን አንድ ማድረግ መሆኑን በአጽንኦት እንገልጻለን፤  እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰላምና አንድነት ጉባኤ ባለፈው ሐምሌ ወር ሦስተኛውን ጉባኤ አበው ለማካሄድ ተገቢውን ቅድመ ዝግጅት በማድረግ ላይ ነበር። ይሁን እንጂ በግንቦቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የላክነው ደብዳቤና ባለ ሰባት ነጥብ የመፍትሔ ሐሳቦች በአገር ውስጥና በውጭው ዓለም የሚገኙት አባቶቻችን በዕርቀ ሰላም ውይይቱ ላይ ለመገኘት ሙሉ ፈቃዳቸው መሆኑን ገልጸውልን ነበር። በዚህ መካከል ግን በአዲስ አበባ በኩል በሰላምና አንድነት ጉባኤው የቀረቡትን ሰባቱን የመፍትሔ ሐሳቦች አስመልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ በወርኃ ሐምሌ መግቢያ ላይ ተነገጋሮባቸው በአፋጣኝ መልስ እንደሚሰጠን በደብዳቤ ተገልጦልን ነበር።

Saturday, August 18, 2012

ከኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የፓትርያርክ ምርጫ ምን እንማራለን?


የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ የምርጫ ሂደት በ1957 ዓ/ም ተሻሽሎ የወጣ ነው። ምርጫው የቤተክርስቲያኒቱ አባል የሆነው በሙሉ ያካተተ እንዲሆን የተሞከረበት ህገ ደንብ አለው። በእርግጥም ምርጫው በሲኖዶስ ፈቃድና እጣ የሚያበቃ  ሳይሆን ከየትኛውም ዘርፍ ያለውን አባሏን የሚያሳትፍ በመሆኑ እውነተኛ አባት ለመምረጥ አስቸጋሪ አልሆነባቸውም። ቢያንስ ቢያንስ አሁን ባለው የፖፕ ሺኖዳ ምትክ ምርጫ ላይ እንኳን ወደ 14 ሰዎች በግልና በጥቆማ ከቀረቡት የፓትርያርክ እጩዎች ውስጥ የማይፈለጉ ሰዎች ወደዚያ መንፈሳዊ ወንበር ሾልከው እንዳይወጡ ማስቀረት የሚችልበት የምርጫ ወንፊት ስላለው እስኪጣራ ድረስ ሂደቱን ሊያዘገይ አስችሎታል። መዘግየቱ ለመንበረ ሥልጣኑ ክፍት ሆኖ መቆየት አስቸጋሪ መሆኑ ባይካድም ክፍት እንዳይቆይ ተብሎ በሆይ ሆይ ቢሾም ደግሞ  የማይፈለጉ ሰዎች በቡድንና በድጋፍ ተጠግተው ሥልጣኑ ላይ ከወጡ በኋላ ሳያስለቅሱ ማውረድ እንዳይቸግር ከወዲሁ በወንፊት የማበጠሩ ጉዳይ መኖሩ ኮፕቶችን ቢጠቅማቸው እንጂ አይጎዳቸውም። ከዚያው ያገኘናቸው መረጃዎች የሚጠቁሙት ያንን ነው። እኛም የበሰለ ነገር ቢበሉት ሆድ አይጎረብጥምና ነገሩን አብስላችሁ ማቅረባችሁ ይበል የሚያሰኝ ነው እንላለን።
ወደኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስንመጣ የራሷን ፓትርያርክ ስትሾም እድሜው እንደጥንታዊነቷ አይደለም። የዚያን እንዴትነት እስከነ ሰፊ ታሪኩ ትተን ፓትርያርክ መሾም ከጀመረችበት ጊዜ አንስቶ ያለውን ሁኔታ በግብጽ አጽዳቂነት የተከናወኑትን ስንመለከት የድክመቶቻችን ውጤት እንጂ ስኬታችን ትልቅነት አድርጎ መመልከቱ ሚዛን አይደፋም። ራሳችን መሾም ጀምረናል ካልንበት ጊዜም ጀምሮ ቢሆን የመንግሥት እጅ በጓሮ በር ሳይገባበት የተከናወኑ ምርጫዎችን ለማግኘት ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ ስለሚሆን አልፈነዋል። እንደዚያም ሆኖ በመገዳደል፤ በመከፋፈልና በመሰነጣጠቅ፤ በመወጋገዝ  የተሞላ መሆኑ የአሳዛኝ ገጽታው አንዱ ፈርጅ ሆኖ ዘልቋል። ዛሬም ከዚያ አዙሪት ስለመውጣታችን እርግጠኞች አይደለንም። ቤተክርስቲያኒቱን በማስቀደም ሳይሆን የሥልጣን ጥምን ለመወጣትና የመንፈሳዊ ማንነት ጉድለቱ ግዝፎ በመታየቱ ችግሮቻችን በአጭሩ የፕትርክና ታሪካችን ውስጥ የሺህ ዓመት ጥላሸትን አኑሯል።
ለመሆኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የፓትርያርክ አሿሿም ልምዷ ከጥንታዊነቷ ጋር የሰማይና የምድር ያህል የተራራቀ ቢሆንም  እንኳን ፓትርያርኳን ለመሾም የግድ የ1000 ዓመት ልምምድ ያስፈልጋታል ወይ? ብለን እንጠይቃለን።
« ሞኝ ሰው ከራሱ ስህተት ይማራል፤ ብልህ ሰው ግን ከሞኝ ሰው ስህተት ይማራል» እንዲሉ  የሌሎችን ልምድ ቀምረን እኛ የተሻለ ሥራ ለመስራት እንደብልሁ ሰው መሆን ባንችል እንኳን እንደሞኝ ሰው ከስህተቶቻችን መማር ለምን እንደከበደን ሳስብ ግራ ይገባኛል።
በ21ኛው ክ/ዘመን ዲሞክራሲን ለመማር እንደአሜሪካ 200 ዓመት እስኪሞላ የምንጠብቅ ከሆነ ከሉላዊነት አስተሳሰብ ውጪ ነን ማለት ነው። አሜሪካ ውስጥ የተመረተ ሸቀጥ ኢትዮጵያ እስኪደርስ 200 ዓመት ይፈጅበታል ብሎ እንደማሰብ ይሆናል። እንደዚሁ ሁሉ ከኮፒቲክ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የፓትርያርክ አሿሿም ሕገ ደንብ ለመማር የግድ የግብጽ ጳጳሳት እንደገዙን 1600 ዓመት ልንጠብቅ አይገባም።  የፓትርያርክነት የምርጫ አዙሪት  በመገምገም መፍትሄው በቅርቡ ሊሆን ይችል ይሆን? ለሚለው ጥያቄ መልሱ ሩቅ ይሆንብኛል።
አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ ሲሆኑ በምርጫው ላይ የነበሩ ጳጳሳት ዛሬም አሉ። አቡነ መርቆሬዎስ ሲባረሩም፤ የመባረራቸውን ተገቢነት የደገፉ  አሁንም አሉ። አቡነ ጳውሎስ በተባረሩት ምትክ ሲሾሙ የመረጡ አሉ። አቡነ ጳውሎስን የመረጡ ተመልሰው የጠሏቸው፤ አሁን ሲሞቱ ደግሞ ተመልሰው ለመመረጥ ወይም ለመምረጥ ያሰፈሰፉ አሉ። እንግዲህ አቋሟቸው ለመገለባበጥ እንጂ ሊኖር በሚገባ ሃይማኖታዊ ጽናት ለመቆም በማይችሉ ሰዎች በሞላበት ሲኖዶስ ተስፋ የሚጣልበትና እግዚአብሔር የወደደውን ምርጫ ለማካሄድ ገና መቶ ዓመታትን ሊፈጅ ይችላል። ለዚያውም ሰማይና ምድር ሳያልፉ ከጠበቀን ነው። ዛሬ እንኳን ለምርጫው በውስጠ ምስጢር በመንግሥት በኩል የታለሙትና አውሬው ደግሞ በከተማይቱ እያስተጋባ የሚገኘውን ድምጽ ስናዳምጥ ነገም ልቅሶአችን ቀጣይ መሆኑን አመላካች ነው። በዚህ ዓይነት መልኩ ከሄድን ደግሜ እላለሁ፤ ነገንም ከእንባ አንላቀቅም።
የኛ ጉዳይ እንደዚህ ነው። የሚሆነውንና የሚመጣውን ከማያልቅበት እድሜ አይንፈገንና ሁሉን እናይ ይሆናል። እስከዚያው እስኪ ከኮፕቶች የፓትርያርክ ምርጫ ደንብ ጥቂት እንመልከት።
1/ ፓትርያርኩ ባረፉ በ7ኛው ቀን  የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና የጠቅላይ ምክር ቤት አባላት ባሉበት በጵጵስና ቀዳሚ የሆነው ሊቀጳጳስ ዐቃቤ መንበር ሆኖ ይሰየማል። የዐቃቤ መንበሩ ምርጫ እንዳበቃ  የፓትርያርክ አስመራጭ ኮሚቴ ይዋቀራል። አስመራጭ ኮሚቴው 18 አባላት ያሉት ሆኖ 9 ጳጳሳት ከሲኖዶሱ፤ 9 አባላት ደግሞ ከጠቅላይ ምክር ቤቱ ይመረጣሉ።
 ጠቅላይ ምክር ቤት ማለት በፓትርያርኩ ሊቀመንበርነት የሚመራ በመንበረ ፓትርያርኩ ስር የተዋቀረ ሲሆን  የሲኖዶስ አባላት፤ ቤተክርስቲያኒቱን በገንዘብ፤ በጉልበትና በእውቀት የሚደግፉ ምእመናን፤ አገልጋይ ካህናትና ዲያቆናት፤ የሰንበት ት/ቤት አባላት፤ ያሉበት የ24 አባላት ምክር ቤት ነው።

Friday, August 17, 2012

በአቡነ ጳውሎስ እረፍት የማኅበሩ ምኞት ሰፋ ወይስ ጠበበ?



ፓትርያርክ ጳውሎስን እስከህይወታቸው ኅልፈት ድረስ ሲራገማቸው፤ ሲያዝንባቸው፤ ሲዘልፋቸው፤ ሲያሽሟጥጣቸውና በታመሙ ቁጥር አሁንስ የሚተርፉ አይመስልም እያለ ሲዘግብባቸው የቆየው ማኅበር አሁን እፎይ፤ ግልግል እንደሚል የደረሰበት የጥላቻው ጥግ ጽሁፎቹ ያረጋግጡልናል።
ደጀ ሰላም፤August 14, 2012
 እግራቸው ከጉልበታቸው በታች በከፍተኛ ደረጃ መጎዳቱንና የጤናቸው ኹኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱ የሚነገርላቸው ፓትርያርኩ÷ ጤናቸውን ለመከታተል የሚያደርጉት ሳምንታዊ ወጪ ከስድሳ ሺሕ ብር በላይ ማሻቀቡን መዘገባችን ይታወሳል፡፡
የደጀሰላም ወዳጅ አስተያየት ሰጪ- August 16, 2012 2:06 PM
Anonymous said...ግልግል ለተዋህዶ የተስፋ ጮራ ነው!ፈርኦን ሆይ ህዝቤን ልቀቅ ሲባል ካልሰማ የእግዚአብሔር እጅ ትዘረጋለች። ከቁጣው እሳት ማምለጥ የሚቻለው ማን ይሆን?
የፓትርያርኩ ሕመም ሳይሆን ፓትርያርክ ሆነው ለህክምና 60 ሺህ ብር ማውጣቱ ያስቆጨውን ማኅበር ምን ይሉታል? ገንዘቡ ከወጪ እንዲድን ቶሎ ይሙቱልን ማለቱ አይደለምን? በሳምንት ይህንን ያህል እየወጣ ነው የሚለውን ገንዘቡን ወጪ ከህመማቸው ጋር ማነጻጸር ቆይታቸው ከወጪ በስተቀር ምንም ትርፍ የለውም ማለቱ ነው እስከሚገባን ድረስ።
ማኅበሩ ፓትርያርኩን እንደሚጠላ ይታወቃል፤ ግን አሳዛኙ ነገር እሳቸውን በሚያይበት ዓይን ወዳጆቻቸውንም እንደዚያው መመልከቱ አስገራሚ ነው።
ማኅበሩ እነ እገሌ ጳጳሳት ነደ እሳት ናቸው፤ እነ አቶ እገሌም መኪና ሸለሙኝ እያለ የራሱን ወዳጆች ከፍ፤ ከፍ እያደረገ ስማቸውን ለአፍታም ከአፉ እንደማያሳርፈው ሁሉ በተነጻጻሪው አቡነ ጳውሎስ ደግሞ ከወዳጆቻቸው መካከል አንዳንድ ሰዎችን ቢያቀራርቡና ቤተኛ ቢያደርጉ ይህ የሰው ባህርያዊ ፍላጎት መሆኑን በመካድ ማኅበሩ ፓትርያርኩን ሲያወግዝና ሲራገም፤ ወዳጆቻቸው ሲያጣጥል መገኘቱ ያሳዝናል።  ማኅበሩ የራሱን ወዳጆች እንደሚቀርባቸው ሁሉ አቡነ ጳውሎስ የልብ ወዳጆቻቸውን ማቅረባቸው ምን ክፋት አለው? ማኅበሩ የራሱ ስራ ሌላ፤ የሰዎቹ መወዳጀት ሌላ ! በየትኛው ርስቱ ላይ ነው፤ ይህ ማኅበር እንደዚህ አድርጎ የሚነጫቸው?
ከእነዚህ ተረጋሚ ሰዎች ከማኅበሩ ድረ ገጾች ስማቸው እስካሁን እረፍት ያላገኘውና ወደፊትም እንደ አቡነ ጳውሎስ በሞት ከሄዱም በኋላ የማኅበሩ እርግማን ይለያቸዋል ተብሎ የማይታሰበው ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ፤ አባ ሠረቀ ብርሃን ወ/ሳሙኤል፤ መጋቤ ሐዲስ በጋሻው ደሳለኝ፤መምህር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል፤ ሊቀ ስዩማን ኃ/ጊዮርጊስ ጥላሁን፤ መምህር አእመረ አሸብር፤ ንቡረ እድ ኤልያስ እና ሌሎች  ስማቸው ከማኅበሩ አገልጋይ ድረ ገጾች ላይ ለእረፍት አይወርዱም።
ማኅበሩ እነዚህን ሰዎች የሚረግማቸው ከአቡነ ጳውሎስ ጋር ባላቸው ቅርበት እንጂ ማኅበሩ እንደማኅበር የሚንቀሳቀስበትና የሚሄድበት መንገድ ከእነዚህ ሰዎች ጋር የሚገናኝ ስለሆነ አይደለም። አንዳንዶቹም ከአቡነ ጳውሎስ ጋር ገጥመዋል ብሎ ከሚጨነቅበት ባሻገር በምርኮኝነት እጃቸውን ሰጥተው የማኅበሩ አገልጋይ መሆን ስላልፈለጉ ቅናት እየሸነቆጠ ስላስቸገረው ነው። ለምሳሌም ያህል በጋሻውን፤ ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤልንና ኃ/ጊዮርጊስ ጥላሁንን ማንሳት ይቻላል። ጥፋታቸው አንፈልግህም ማለታቸው ብቻ ነው።
ከደጀ ሰላም ስድብና እርግማን መካከል አንዱን እንመልከት።
ቅዱስ ሲኖዶስ በታሪክ እጅግ ሊያስመሰግነው በሚችል መልኩ በተሐድሶ ድርጅቶች እና አራማጆች ላይ የውግዘት ቃሉን ባስተላለፈ ማግሥት ቅዱስነታቸው ቀንደኛውን ተሐድሶ በአሜሪካ የሾሙበት ምክንያት የንፁሐን ኦርቶዶክሳውያንን ቅስም ለመስበር እንዲሁም ወደ ውጪ አገር ሰው በመላክ ሰበብ የሚያጋብሱትን ገንዘብ በታማኛቸው አማካኝነት ለማካሔድ በማሰብ መሆኑን ምንጮች አብራርተዋል። (ደጀ ሰላም፤ ግንቦት 24/2004 ዓ.ም፤ ጁን 1/ 2012/
ቡነ ጳውሎስ ገንዘብ ለመዝረፍ ኃ/ጊዮርጊስን ወደ አሜሪካ ለመሾም የሚገደዱት በምን ስሌት ነው? የተሾሙ ሁሉ ገንዘብ ዘራፊዎች ናቸው? ኃ/ጊዮርጊስስ የማንን ገንዘብ ይዘርፋል? የማኅበሩ የጥላቻ ጥግ ጥቂት እንኳን ወደ እውነቱ አይቀራረብም።
ኃ/ጊዮርጊስ ቀድሞ የማኅበሩ ወዳጅ ነበር። ኃ/ጊዮርጊስ የጋብቻ ወረቀታችንን ቀደናል ባለ ማግስት ጀምሮ ማኅበሩ የዘመቻ ሰይፉን አንስቶበታል። ማኅበሩ ከእሱ የተለየ ሃሳብና መንገድ ያለውን ማንኛውንም ሰው እንደ ሰው የሚቀበልበት ተፈጥሮ የለውም። አሜን ብሎ የመገዛት ግዴታ፤ አለበለዚያም ከምድረ ገጽ እስኪጠፋ ድረስ የመዝመት ተልእኮ ያለው ማኅበር መሆኑን ስራዎቹ ራሳቸው ይመሰክራሉ።
ይህ ማኅበር በእሱ እርግማን ይሁን በእግዚአብሔር ፈቃድ የአቡነ ጳውሎስ ህልፈተ ህይወት የሆነበትም ምክንያት ለራሱ እንደመሰለው ቢያስብም፤  ነጋ ጠባ የሚጨቀጭቃቸው አባትከእንግዲህ በፊቱ የሉም።  በቀጣይ ወዳጆቻቸውን እስኪያጠፋ ድረስ ለጊዜው  ቤቱን ዘግቶ  የደስታ ከበሮ የመደለቅ መብቱ የተከበረ ነው። ይሁን እንጂ በአቡነ ጳውሎስ ሞት የተሰማውን ደስታ አጣጥሞ ሳይጨርስ፤ የፓትርያርኩ ወዳጆች ናቸው ብሎ የሚገምታቸውን ገና ካሁኑ ስማቸውን እየጠራ ዘመቻውን ጀምሯል።
(ደጀ ሰላም፤ ነሐሴ 10/2004 ዓ.ም፤ ኦገስት 16/ 2012
ፋውንዴሽኑ› መቋቋም ያስፈልጋል የተባለውን ገንዘብም እንደተለመደው ከስፖንሰርሽፕ፣ ከአድባራትና ገዳማት እንዲሁም ከተለያዩ የቤተ ክርስቲያኒቱ ኢኮኖሚያዊ ምንጮች ለመሰብሰብ ሲዘጋጁ መቆየታቸውን የገለጸው የመረጃ ምንጩ÷ ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነን፣ መልአከ ፀሐይ በቀለ ተሰማን (ቤቴል ቅዱስ ሚካኤል)፣ ሰሎሞን በቀለን (ቦሌ መድኃኔዓለም)፣ ቀሲስ ግሩም መልአክ ታዬን (ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት፣ ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤልን (ጠቅላይ ቤተ ክህነት) በዋና አደራጅነት ጠቅሰዋል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጽ/ቤት በጉዳዩ ላይ በመንግሥት የፀጥታ ኀይሎች በመታገዝ ጠንካራ ክትትል በማድረግ የወይዘሮዋንና ሌሎች አካላትን ችግር ፈጣሪነት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማቆም እየሠራ እንደሚገኝ ተዘግቧል፡፡

Thursday, August 16, 2012

ሰበር ዜና፤ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አረፉ።



ብጹእ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውን ያገኘነው ዘገባ አረጋግጧል። በሳምንቱ መጀመሪያ ገደማ ለሕክምና ዳጃች ባልቻ ከገቡ በኋላ አንዳንዶች ህመማቸውን እንደህመማቸው ቆጥረው ሳይሆን መታመማቸው ይፋዊ ዜና እንዲሆንላቸውና መጨረሻቸውም በሚፈልጉት መንገድ ሲያበቃ ለማየት የቋመጡ  ያህል ሲዘግቡ የሰነበቱበት እውን ሆኖ   በ9/12/ 2004  ዓ/ም ንጋት ላይ  አርፈዋል።
የቅዱስ ፓትርያርኩን ሞት ለረጅም ዘመን ሲጠብቁ የቆዩ ደስ ሲላቸው እስከ ሰውኛ ድክመታቸው ፓትርያርኩ ለዚህች ቤተክርስቲያን የሚችሉትን ያህል ሰርተዋል የሚሉ ደግሞ ማዘናቸው አይቀርም። ደጀ ብርሃን ብሎግ አቡነ ጳውሎስ ከስህተትና ከሰውኛ የድካም ጠባይዓት ፍጹም ነጻ ነበሩ ብላ ባታምንም  ቤተክርስቲያኒቱን ደከመኝ፤ ሰለቸኝ ሳይሉ በማገልገል፤ የተወረሱባትን ሃብትና ንብረት በማስመለስ ረገድ ትልቅ ስራ መስራታቸውን፤ በቅዳሴ አገልግሎት በህመም ውስጥ እንኳን እያሉ ማገልገላቸውን ትመሰክራለች።
አቡነ ጳውሎስን በአስተዳደር፤ በገንዘብ ጉዳይ፤ በዘረኝነት የሚወቅሱ ወገኖች አሁን በሞት ሁሉን ነገር ትተውላቸው ሲሄዱ ፍላጎታቸውን ሊያሟላ የሚችል ጳጳስ በመፈለግ «ትሻልን ሰድጄ ትብስን አመጣሁ» እንዳይሆን ከወዲሁ ትልቅ ፍርሃት አለን።
 በቀጣይ ጽሁፋችን ሙሉ ታሪካቸውን ይዘን የምንቀርብ ሲሆን እግዚአብሔር የወደደውን እንዲያደርግ ከማሰብ ባሻገር በጥላቻም ይሁን መጠን ባለፈ ምስጋና ውስጥ እንዳንሆን አንባቢዎቻችንን ለማሳሰብ እንወዳለን።
እግዚአብሔር በዐጸደ ቅዱሳን እረፍቱን ይስጥልን!

Tuesday, August 14, 2012

ሃሌ ሉያ

የሕይወታችን ባለቤት፤ የመዳናችን ዋስትና፤ የዘላለማዊነት ርስት ለሆነው ለእግዚአብሔር ብቻ የተገባ ይህንን የግጥም ምስጋና ስለወደድነው ከቤተ ጳውሎስ ብሎግ ላይ ወስደን አካፍለናችኋል። ለመዳናችን ሌላ ምስጋና ለማን? ዳዊትም ያለው ይህንን ነው።

መዝ 44፤20-21
የአምላካችንን ስም ረስተንስ ቢሆን፥ እጃችንንም ወደ ሌላ አምላክ አንሥተንስ ቢሆን፥
እግዚአብሔር ይህንን አይመረምርም ነበርን? እርሱ ልብ የሰወረውን ያውቃልና።

ቤተ ጳውሎስ ማክሰኞ ሐምሌ 8/2004 ዓ.ም.

ሃሌ ሉያ ለአብ
ሃሌ ሉያ ለወልድ
ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ
ሃሌ ሉያ በአርያም ላለኸው
ሃሌ ሉያ በልቤ ለነገሥከው
ሃሌ ሉያ ለጥልቁ መሠረት
ሃሌ ሉያ ለምጥቀቱ ጉልላት
ሃሌ ሉያ ለዳርቻዎች ወሰን
ሃሌ ሉያ ከአድማስ ወዲያም ላለኸው
ሃሌ ሉያ ዓመታትን ላስረጀው
ሃሌ ሉያ ሕዝቡን ለታደግኸው
ሃሌ ሉያ ብርሃናትን ለፈጠርከው
ሃሌ ሉያ ስሜን ለለወጥከው
ሃሌ ሉያ ለድካሜ ምርኩዝ
ሃሌ ሉያ ለምስኪንነቴ ሞገስ
ሃሌ ሉያ ለተጨነቁት ዕረፍት
ሃሌ ሉያ ለታወኩት ፀጥታ
ሃሌ ሉያ ሸክም ለተጫናቸው ወደብ
ሃሌ ሉያ ስንጥቁን ልቤን ገጥመህ ለያዝከው
ሃሌ ሉያ በመጽናናትህ ለጎበኘኸኝ
ሃሌ ሉያ ከጥልቁ ስጮህ ለሰማኸኝ
ሃሌ ሉያ ከደጅ ስፈልግህ በውስጤ ላገኘሁህ
ሃሌ ሉያ በማይቻለው ቀን ለቻልኩብህ
ሃሌ ሉያ ለባልቴቲቱ ዳኛ
ሃሌ ሉያ ለሙት ልጅ ሰብሳቢ
ሃሌ ሉያ ለበረሃ ጥላዬ
ሃሌ ሉያ ለምድረ በዳው ጓደኛዬ