Monday, January 13, 2014

ጦርነቱ በማጣጣር ላይ ባለው የማኅበረ ቅዱሳን አልሞት ባይነትና እጁን ለመስጠት በተዘጋጀው የቤተ ክህነት ባለሥልጣናት መካከል ነው!!!



እንደወትሮው ስለማኅበረ ቅዱሳን የምናትተው ሰፊ ጽሁፍ የለንም። ማኅበሩ እያጣጣረ ነው። ለጊዜው ትንሽ መቆየቱ የእድገት መጨረሻውን አያስቀጥለውም።  ይሁን እንጂ ይህ የብላቴ ትራፊ «አንዲት ጥይት ወይም ሞት» በማለት የጥንት ቃል ኪዳኑን ለማደስ እየተንፈራገጠ ነው።
ለዚህም በመሞትና በመዳን መካከል እየተንፈራገጠ ያለው ማኅበረ ቅዱሳን ራሱን ለማዳን እየታገለ ይገኛል። ለመዳን የሚያደርጋቸውን ትግሎች በአጭር በአጭሩ በነጥብ ሲቀመጡ ይህንን ይመስላሉ።


1/ በሙስናና በአስተዳደር ብልሹነት ሊጠየቁ የሚገባቸው አስተዳዳሪዎችና ፀሐፊዎች አዲሱን ስልቴን እየተቃወሙት ነው በማለት ራሱን ደብቆ ለቤተ ክህነት የለውጥ ማሻሻያ ህግ አያስፈልጋትም የተባለ አስመስሎ ማሳየት ይፈልጋል።

2/ ህጉ ከየትምና ከማንም ይመንጭ ለቤተ ክህነት ስለማስፈለጉ ብቻ እንተማመን በማለት የሕጉን ምንጭ ማንነት እንዳይገለጥ በአስፈላጊነቱ ስር ሸሽጎ ለማስቀጠል ይፈልጋል።

3/ ከአባ አማቴዎስ፤ ከአባ ሉቃስ፤ ከአባ እስጢፋኖስ እና ለጊዜው ስማቸው መጥቀስ ከማንፈልጋቸው ሌሎች ጳጳሳት ጀርባ ተጭኖ የህጉን አስፈላጊነትን በማጦዝ ሲኖዶሳዊ ለማስመሰል በትጋት ይሰራል።

4/ ስለህጉ እጹብ ድንቅነትና ትንግርታዊነት በመረጃ መረብና በስመ ነጻ ሚዲያ ጋዜጦች ላይ በመለፈፍ የምርጫ ዓይነት ቅስቀሳውን በህዝብ ውስጥ በማስረጽና በጳጳሳቱ መካከል የወደፊት በል  ዘመቻውን ለማስቀጠል  ድፍረት የሚሆናቸውን ኃይል በማስታጠቅ ላይ ተጠምዷል።

5/  በካህናት ሽፋን፤  የጥምቀት ተመላሾችንና የተወሰኑ አባላት ምእመናኑን በማሰለፍ በፓትርያርኩ ላይ ጫና በማሳደር የሰማይ ተሰበረ ሽብሩን በመንዛት ላይ ላይ ይገኛል።
እነዚህ ከብዙ በጥቂቱ የተዘረዘሩት እስትንፋሱን የማስቀጠል ዘመቻው ጊዜ ከሚገዛለት በስተቀር በፍጹም ሊታደጉት አይችሉም። ምክንያቶቹ፤
ሀ/ በቤተ ክህነት አጠቃላይ መዋቅራዊ ማሻሻያና የለውጥ እስትራቴጂ ጥናት አስፈላጊነትን የተቃወመና የሚቃወም ማንም የለም። ሊቃወምም አይችልም።

ለ/ የለውጥ ጥናቱ መምጣት ያለበት  ከሲኖዶስ ውስጥ የሚመነጭ ሆኖ በሊቃውንቱ፤ በምሁራኑ፤ በካህናቱ፤ በአዋቂዎቹና በህግ ባለሙያዎች የሚዘጋጅ እንጂ ከማኅበረ ቅዱሳን ጡንቻ ነጻ የመሆን አቅምና ጠባይ በሌላቸው አባ እስጢፋኖስ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ላይ የማዘዝ ስልጣንን ያገኙትን አጋጣሚ በመጠቀም  ዓላማን የማስፈጸም ግብ ሊሆን አይችልም።

ሐ/ በመሰረቱ ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያኒቷ ምኗም አይደለም። ቤተ ክርስቲያን ነጋዴ አይደለችም። እሱ ግን የሚታይ የሚጨበጥ የንግድ ተቋም ያለው ግልጽ ነጋዴና አትራፊ ድርጅት ነው። በዐውደ ምሕረቷ ላይ የሚነግድ ይህ ድርጅት የንግድ ጠረጴዛው መገልበጥ አለበት። በጅራፍም ሊባረር የተገባው ነው። ስለዚህ በምንም ዓይነት መልኩ ወርቅና አልማዝ አቅርቤአለሁ ቢል ተቀባይነት ሊኖረው አይችልም።

መ/ ማኅበረ ቅዱሳንን የሚደግፉ ሊቃነ ጳጳሳት በግልጽ ቋንቋ ስንናገር፤

ሀ/ በቤተ ክርስቲያኗ ሕግና ደንብ መሰረት ለጵጵስና የሚያበቃ ሥነ ምግባር በጭራሽ የሌላቸው ናቸው።

ለ/ በዘር ፖለቲካ የተለከፉና ኢህአዴግ እንደጉም ተኖ፤ እንደጢስ በኖ  ይጠፋ ዘንድና  የራሳቸውን ሥርወ ቤተ ክህነት ለመትከል የሚናፍቁ ናቸው።  ከዚህ የወጣ  ደጋፊ የለውም።
በተለይ አባ እስጢፋኖስ ለማኅበሩ ጥብቅና የመቆማቸው ነገር በፍቅሩ ስለተቃጠሉ አይደለም።  ጵጵስና ስሙና ታሪኩ ክብር ያጣው ጸሊማን አርጋብ በምግባር /ጥቋቁር እርግቦች/ የሆኑ ቦታውን ከወረሩት በኋላ ነው። አባ እስጢፋኖስ ኮተቤ ያሰሩት የሚሊዮን ብሮች ግምት ቤታቸው የተሰራው በደመወዛቸው ነው?  መነኩሴ እናቱም አባቱም ቤተ ክርስቲያን ናት ስለሚባል እስኪ ለቤተ ክርስቲያን የውርስ ኑዛዜ ይስጡ!!
ስለዚህ እስትራቴጂ፤ ጥናት፤ ስብሰባ፤ ተቃውሞ፤ ስነ ምግባር፤ ሙሰኛ ወዘተ በሚሉ የቃላት ማደናገሪያ ቤተ ክህነቱ እጁ ሲጠመዘዝ አሜን ማለት የለበትም። አካፋን አካፋ ማለት የሚገባው ወቅት ቢኖር አሁን ነው። ቤተ ክህነት ችግሮቿን ታውቃለች። ለችግሮቿም መፍትሄ ማመንጨት አይሳናትም። የወላድ መካንም አይደለችም። ስለዚህ በፓትርያርኩ አመራር ከራሷ ልጆች በወጣ ህግ ለችግሮቿ መፍትሄ መስጠት አለባት እንጂ በማመልከቻና በደጋፊ ብዛት መጠምዘዝ አይቻልም። 
የማኅበረ ቅዱሳን ስፍራው መናገር ካስፈለገ ሼር ካምፓኒ/ የአክሲዮን ማኅበር መሆን ብቻ ነው። አዲዮስ ማኅበረ ቅዱሳን ከማለት ውጪ በዚህ ማኅበር ስንታመስ መቆየት ያብቃ!!  በዚህ ማኅበር ዙሪያ ከቤተ መንግሥቱ የተሰማውን መረጃ በሌላ ጽሁፍ ይዘን እንመለሳለን።

Saturday, January 11, 2014

የእግዚአብሔር መንፈስ እንዲያድርባችሁ ሳር ጋጡ የተባሉ ደቡብ አፍሪካውያን ሳር ሲግጡ ዋሉ!!

የፍጻሜው ዘመን የተቃረበ ይመስላል። ጤናማ አእምሮና በማኅበራዊ ኑሮው ሰላማዊ የነበረ ሕዝብ እንደጋማ ከብት ሳር እንዲግጥ ሲታዘዝ  ሲበላ ዋለ ማለት እጅግ ያስገርማል። ነገሩ በእርግጥ ሆኗል። በደቡብ አፍሪካ ፤ ጋራኑካ በተባለች ከተማ ውስጥ  የተቋቋመችውና ከ1000 በላይ ተከታዮች ያሏት ማኅበር መሪ የሆነው ፓስተር ሌሴጎ ዳንኤል የስብከት መርሐ ግብሩን እንደፈጸመ መገለጥ መጥቶልኛልና ከአዳራሽ ወጥታችሁ የሜዳውን ሳር ጋጡና በመንፈሰ እግዚአብሔር ትሞላላችሁ ባላቸው መሰረት ትእዛዙን ተቀብለው ሳር ለመጋጥ መሰማራታቸውን «ክርስቲያን ፖስት» ጋዜጣና «ቺካጎ ዲፌንደር» ዘግበዋል።


   ግማሹ ሳሩን አጎንብሶ እንደከብት እየጋጠ፤ ገሚሱ ደግሞ እንደጭላዳ ዝንጀሮ እየነጨ ሳሩን ሲበላ የዋለ ሲሆን የሰው ጭላዳ ከሆኑት መካከል አንዷ የሆነችው የ21 ዓመቷ የህግ ተማሪ ሮዝመሪ ፔታ ለጋዜጠኞች እንደተናገረችው «ሳሩን በመጋጤ ለአንድ ዓመት ያህል ሲያሰቃየኝ ከነበረው ከጉሮሮ ቁስለት በሽታ ተፈውሻለሁ» በማለት ያገኘችውን አስደናቂ ተአምርና የሳር መጋጡን ጠቃሚነት የገለጸች ሲሆን የ27 ዓመቷ ዶሪን ጋትል የተባለችው ደግሞ እንዲህ ስትል ስለተደረገላት ተአምር ያገኘችውን ጥቅም ገልጻለች። «በነበረኝ የስትሮክ በሽታ እግሮቼን ላለፉት ሁለት ዓመታት ማንቀሳቀስ ተስኖኝ ነበር። ሳር ብትበሉ በመንፈስ ትሞላላችሁ፤ በማለት ስለሳር መብላት አስፈላጊነት ፓስተሬ ባዘዘኝ ጊዜ በመብላቴ ከበሽታዬ በፍጹም ድኜ እነሆ በሁለት እግሬ ለመሄድ በቅቻለሁ» በማለት ስለተደረገላት ተአምር ለሚዲያ ተናግራለች።

  ይሁን እንጂ የሁለቱንም ሴቶች አባባል የሰሙ ታዛቢዎች በአባባላቸው ስቀዋል። ጤንነታቸውንም ተጠራጥረዋል።  ይህ የማይታመን ቀልድና በእግዚአብሔር ስም ማላገጥ ነው። መንፈስ ቅዱስ እንዲያድርብን ሳር አጎንብሳችሁ ጋጡ ተብለናል የሚሉት ጉዳይ የግድ መቆም ያለበትና ለህብረተሰቡ በመጥፎ አርአያነቱ ካልሆነ በመልካምነቱ የሚታይ አይደለም በማለት የተመለከቱ ታዛቢዎች ተቃውሟቸውን ገልጸዋል ። የሰው ልጅ ሲፈጠር እንደእንስሳ ሳር ለመጋጥና ለመፍጨት የተዘጋጀ የሰውነት አወቃቀር ስለሌለው የተደረገው ነገር ሁሉ ከክርስትና ሃይማኖት ጋር የማይገኛኝና መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሰረት የሌለው በመሆኑ ድርጊቱን እንቃወማለን ሲሉ ስለሳር ጋጮቹ ተናግረዋል።

 ከዚሁ ጋር ተያይዞ ስለሳር መጋጡ ውሎ እንደተዘገበው፤ በመስኩ ላይ ተሰማርተው ሳር ሲግጡ ከዋሉት የሰው ጭላዳዎች መካከል አብዛኛዎቹ ሲያስመልሳቸውና ሲሰቃዩ የዋሉ ሲሆን ገሚሶቹ መብላት አቅቷቸው ሲያለቅሱ ታይተዋል። አንዳንዶቹም ሆዳቸውን ታመው ህክምና እስኪደርስላቸው ድረስ መታመማቸውም ታውቋል። ከዚህ በፊትም ፓስተር ሌሴጎ ዳንኤል በአዳራሹ ውስጥ የተገኙ ተከታዮቹን በጥፊ እንዲጠፋጠፉ ባዘዛቸው ጊዜ ትእዛዙን ተቀብለው፤  ጉንጫቸው ድልህ እስኪመስል በጥፊ መጠዛጠዛቸውም ተዘግቧል።

እንደሚታወቀው ሳር በመጋጥ እንደእንስሳ ይሆን ዘንድ ከእግዚአብሔር ትእዛዝ የወጣበትና ልቡ የተሰወረበት ናቡከደነጾር እንደነበረ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል።  ናቡከደነፆርም ለዚህ የበቃው በትምክህቱና በትዕቢቱ እንጂ ለበጎ ተግባሩ የተሰጠው ልዩ ጸጋ አልነበረም። እና ታዲያ የዘመኑ ሰዎች እንደናቡከደነፆር ወደእንስሳነት ወርደው ሳር በመጋጣቸው የናቡከደነፆር ቤተሰቦች የማይሆኑበት ምክንያት ይኖር ይሆን?
«ልዑሉም በሰዎች መንግሥት ላይ እንዲሠለጥን፥ ለሚወድደውም እንዲሰጠው እስክታውቅ ድረስ ከሰዎች ተለይተህ ትሰደዳለህ፥ መኖሪያህም ከምድር አራዊት ጋር ይሆናል እንደ በሬም ሣር ትበላ ዘንድ ትገደዳለህ፥ ሰባት ዘመናትም ያልፉብሃል አለው» ዳን 4፤32

Wednesday, January 8, 2014

በሰዓሊተ ምሕረት ካቴድራል የተንሰራፋው የክህደት፤ የዘረፋ፤ የሕገ ወጥ መሬት ንግድና ኪራይ ሰብሳቢነት እውን መንግሥትና ሕግ ባለበት ሀገር የተፈጸመ ነው?


የደ/ም ሰዓሊተ ምሕረት ቅ/ማርያም ካቴድራል
እኩይ ዓላማውን ይዞ ገለልተኛ ቤተክርስቲያን መፍጠር የሚለውን የመናፍቃን ሐሳብና መንግሥትን በሽምቅ ለመዋጋት የሰአሊተ ምህረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል የመቃብር ሥፍራ የተሸሸገገው ቡድን 2 ፓትርያርኮች ፣ 3 ጳጳሳትንና ፣ 3 ሥራ አስኪያጆች ደክመውበት መፍትሔ ሳይሰጡት  በአክሲዮንነት ቤተክርስቲያኗን በመዋጋት  አሁንም ቤተክርስቲያኗን እየበጠበጠ ነው፡፡
ሰንበቴዎቹ በ 70 ሺህ ብር ለኢ አማንየን ፤በ50 ሺ ብር ከውጭ ለሚመጣ አስክሬን፤ በ 35 ሺህ ብር ለሀገር ውስጥ የሚሸጡትን ፉካ ንግድ አላቆሙም።




በመንፈሳዊ ቅብብሎሽ ሲያያዝ የመጣ የቤተክርስቲያን የታሪክ መዝገብ የሚያውቀው ትውፊት ስለሆነ በሀገራችን ተጠብቆና ተከብሮ እስከ አሁን መቆየቱ የሚያስመሰግን ነው፡፡ የሚያኮራም ነው፡፡
ነገር ግን በዚህ መንፈሳዊ ትውፊት ውስጥ የግል ፍላጐትን ለማሳካት ነቀፋን የሚያስከትሉ ጠብ፣ ክርክር ወይም ሌላ ሥጋዊ ፍላጎት ወይም የቤተክርስቲያኗን ዶግማ ቀኖናና ትውፊት ያልጠበቁ ድርጊቶች ሰርገው ገብተው ዛሬ ሰንበቴ ማኅበራት መንግሥት ግብር የማይቀበልበት በአቋራጭ መክበሪያ እና የመናፍቃን መሰብሰቢያ ሆኗል፡፡ በምስራቃዊ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የምትገኘው ደብረ ምጥማቅ ሰአሊተ ምህረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል በ1969 ዓ.ም ስትመሰረት በወቅቱ ገጠር ልትባል የምትችል ደብር ነበረች፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ መስፋፋት ጋር ተያይዞ እንዲሁም በ1997 ዓ.ም ተመርቆ አገልግሎት በመስጠት ላይ በሚገኘው ካቴድራል ግንባታ ቦታው በአዲስ አበባ ከተማ ከሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት አይን ማረፊያ ለመሆን በቃ፡፡ ከዚህም በላይ በማንኛውም አብያተክርስቲያናት የሌለ 200.000.00 (ሁለት መቶ ሺህ) ካሬ ሜትር ይዞታ ባለቤት መሆነኗ ግን ብዙ ሺህ ጠላቶች በቦው ላይ እንዲነሱ አደረጋቸው በቅድሚያ በቁጥር 11 የሚሆኑ አገልጋዮቿ ከካቴድራሉ ይዞታ 18.000.00 (አሥራ ሰስምንት ሺህ ካሬ ሜትር ) ቦታ በመውሰድ ለግል ጥቅማቸው በማዋላቸው ከ 8 ዓመት በላይ በቆየ የፍርድ ቤት ክርክር ከፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት እስከ ሰበር ሰሚ ይዞታው ለቤተክርስቲያኗ ተፈረደ ይህን ተከትሎ አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባለ አደራ  ካቢኔ ከይዞታዋ ላይ በአውደ ምህረቱ ትክክል 7000 ካሬ ሜትር ለግዮን ጋዝ ኃ.የተ.የግ ማኅበር በሊዝ ሸጠው ይህንን ሁሉ ችግር እያለ በሰንበቴ ሽፋን የገቡ 7 ሰንበቴዎች እያንዳንዳቸው ከ1000 ካሬ ሜትር በላይ ቦታ በመያዝ ከዚያው ከቤተክርስቲያኑ በወጣ የድንጋይ ማእድን ትልልቅ አዳራሾችና የቀብር ፉካ በመገንባት የይዞታ ተቀናቃኝ ሆኑ፡፡ (ይህ ቦታ አሁን ባለው የሊዝ ዋጋ ከ850 ሚሊዮን ብር በላይ ይገመታል ) ለእነዚሁ ሰንበቴዎች ቦታውን ከፋፍሎ በመስጠት ጉልህ ስፍራ የነበረው ወልዴ የሺጥላ የተባለው የህንጻ ኮሚቴ ሊቀ መንበር ሲሆን ኤርትራዊው ፎርማን አቶ ጸሐዬ እራሱን ኢንጂነር ብሎ በመጥራት ልኬቱን አከናውኗል፡፡ አቶ ወልዴ የህንጻ ሊቀ መንበር ሆኖ ቤተክርስቲያኗ ላይ ሲያዝና ሲናዝዝ ኖረ ቀድሞ የቴሌ ጉርድ ሾላ ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ ሲሆን በአሁኑ ወቅት በቂ የትምህርት ዝግጅት ስለሌለው አለኝ ብሎ ባቀረበው ሰርተፍኬት በሽያጭ ሰራተኝነት ተመድቦ ኮተቤ ቅርንጫፍ የሚሰራ ግለሰብ ነው ይህ ግለሰብ  ለሰንበቴ ቦታ አከፋፍሎ ሲጨርስ ለእሱና ለሚስቱ ማረፊያ የሚሆን ዘመናዊ ሰርቪስ ቤት እና 26 የቀብር ፉካ ለቤተክርስቲያኑ ሕንጻ ማሰሪያ ከመጣው ሲሚንቶና አሸዋ  በመገንባት የፉካ ንግዱን ተቀላቀለ፡፡ 


ዛሬ ወልዴ ቅዳሴ የሚያስቀድሰው በቤተክርስቲያኒቱ  ቤተልሔም ጎን በሰራው ሰርቪስ ሳሎን ሶፋ ላይ ጋደም ብሎ ሲሆን መሸት ሲል ደግሞ አየር ለመቀበል ወደ መኝታ ቤት ይገባል፡፡ ለቤተክርስቲያን መላ ዘመናቸውን የደከሙ የቀድሞ ነገስታት እንኳ ያላደረጉትን ድፍረት በመድፈር በቅድስት ቤተክርስቲያን ውስጥ ለራሱ መኖሪያ የሰራ በ 21 ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከእሱ ሌላ መገኘቱን እጠራጠራለሁ፡፡ ሕንጻው ከተመረቀ ከ 6  ዓመታት በላይ አንዳች የልማት ተግባር ሳያከናውን በሊቀ መንበርነት ሕንጻ ኮሚቴ ብሎ የሰየመውን የቤተክርስቲያኗን ሐብት የሚዘርፍበት ኮሚቴ   ከመሰሎቹ ጋር ቤተክርስቲያኗን በአጽሟ አስክትቀር ድረስ ከዘረፋት በኋላ በዚያ ገንዘብ አያት ግቢ ውስጥ ዘመናዊ ባለ ሁለት ፎቅ መኖሪያውን ገዝቶ የቀድሞ ቤቱን አከራይቶ ሲኖር ንቡረ እድ ኤልያስ አብርሃ በነባሩ ሰበካ ጉባዔ አባላት በቀረበላቸው ጥቆማ ቀደም ሲል ጀምሮ ሲፈርምበት ለነበረው ባንክ እግድ በመጻፍ ቋሚ የዘረፋ ገቢውን እንዲቆም አደረጉ፡፡ በወቅቱ የነበረው ሰበካ ጉባዔም ያላለቀውን ቤተክርስቲያን ለማስፈጸም ጥረት ያደረገ ሲሆን ቀድሞ ኮሚሽን የተቀበለባቸውን የሥዕል ሥራ ለሌላ ባለሙያ በመስጠት እንዲጠናቀቅ ከማድረጉም በላይ አጥር የሌላትን ቤተክርስቲያን በአጥር እንድትከበር፤ ዶሙ ዝናብ ያስገባ የነበረውን ሕንጻ 4 ዶሞች አሉሚኒየም በማልበስ ዘመናዊ መጠለያ በመስራት ለካቴድራሉ አቋቋምና ዜማ ትምህርት ቤት የተማሪዎች መኖሪያ የአረንጓዴ አጸዶች ሥራ የመጠለያ ግንባታ እና ወደ ካቴድራሉ በ 3 አቅጣጫ የሚያስገቡ ዘመናዊ ኮብል ስቶን መንገዶችና ሌሎችም  ሥራ ሰርቷል፡፡ የቤተክርስትያኑ አስተዳዳሪ እና የሥራ ባልደረቦቻቸው ለረጅም ዘመን በጭቅጭቅ የቆየውን ይህንን ቦታ በካርታ ለማስከበር ከፍተኛ መስዋእትነት ከፍለው 200.000.00 ካሬ ሜትሩን የሚያረጋግጥ ካርታ ተቀብለውበታል፡፡ በቀጣይ ሰንበቴዎቹ ያለ ከልካይ የሚያደርጉትን ሕገ ወጥ ተግባር ሥርዓት ለማስያዝ በወቅቱ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስን በመውሰድ የሰንበቴዎቹን ይዞታና ሕገ ወጥ ድርጊት አሳይቷቸዋል፡፡ ቅዱስነታቸውም እንባ እየተናነቃቸው በንዴት ከግቢው እንደወጡ ይዞታውን የወሰዱና ተከራክረው በፍርድ ቤት የተረቱ 13 ሰራተኞች ከቦታው እንዲነሱ በማድረግ ሰንበቴዎቹ ላይ ሕግ እንዲወጣ መመሪያ ሰጡ፡፡
-    ሰንበቴ ማኅበራቱ በካቴድራሉ ግቢ ሚገኘውን የድንጋይ ማእድን እንደፈለጉ   አስፈልጠው በመሸጥ ከፍተኛ ገንዘብ በመሰብሰባቸው፡፡
-    ያለ ፈቃድ በገነቧቸው ሰፋፊ አዳራሾች ውስጥ በኪራይ ኗሪዎችን በማፈራቸው
-    ያለ ቁጥጥር በሚሸጡት ፉካ ከፍተኛ ገቢ በማግኘታቸው
-    በአዳራሾቹ ያልተፈቀዱ ፖለቲካ ስብሰባ በማካሄዳቸው
-    ቤተክርስቲያኗን ሥርዓት በመጣስ በቅዳሴ ሰዓት ግቢን በ40 እና 80 ቀን መታሰቢያ ድግሶች ከድርገት በፊት ምግብ እንዲበላ በማድረጋቸው፡፡
-    ባልተፈቀደ የንግድ ተግባር በመሰማራታቸው
-    በሕገ ወጥ መልኩ ቦታ በመውረር ለብዙኃኑ ጥቅም መስጠት የሚገባውን ቦታ ለግል ጥቅም በማዋላቸው
-    ከቀብር የሚያገኙትን ገንዘብ በሕይወት መድን ዋስትና ዓይነት ለአባላት በጥሬ ገንዘብ የሚከፍሉ በመሆናቸው፡
-    ሁሉን እምነት ያቀፍን ነን ለማለት ወደ በጎ አድራጎት ማኅበርነት ለመቀየር በመንቀሳቀሳቸው፡፡
-    ዛሬም ማንነታቸው በውል የማይታወቅ በወንጀል ጭምር የተገደሉ ሰዎች ከተለመደው የጥቁር አንበሳ መዝገበ ሙታን ውጪ ሳይመዘግቡ የሚቀብሩ መሆናቸው፡
-    በጥበቃ ስም ባስገቡዋቸው ግልሰቦች ምክንያት ቤተክርስቲያን ውስጥ ከፍተኛ ወንጀል እንዲፈጸም የሚያደርጉ በመሆናቸው፡፡
ነበር ሕግ ያስፈለጋቸው፡፡
ነገር ግን ይህን ቤተክርስቲያን ዓመታት ብቻ 10 አለቆች ተደብድበው የተባረሩ ሲሆን ሊቀ ጉባዔ ኤርሚያስ ወልደኢየሱስ፣ መላከ ሰላም ዘለዓለም እሰይ እና መልአከ ሣህል አወቀ ተጠቃሽ አስተዳዳሪዎች ናቸው፡፡
እነዚህ ሰንበቴ ማኅበራት መካከል ዋነኛው የመድኃኔዓለም ሰንበቴ ማኅበር ሊቀ መንበር የደርግ የፖለቲካ ትምህርት ቤት መምህር የመቶ አለቃ አባቡ መሰል የደርግ ዘመን ጓደኞቹን በመጥራት ጥቅማቸውን ለማስቀጠል በቡድን ተደራጁ እዚህ ቡድን ውስጥ የሴት ሰባኪ ሆነችውና ሕጋዊ ባሏንና ሥራዋን ጥላ ከእድሜ አባቶቿ ጋር  በካቴድራሉ ግቢ የቀን ቀን ኑሮዋን የመሰረትችው ቅድስት አሳልፍ ስትገኝበት የቀድሞ የደርግ የምስራቅ ጎጃም አስተዳዳሪውና በቅርቡ ከእስር ተፈታው ስመ ገናናው አንሙት ክንዴ የቀድሞ የደርግ የቀጠና  2 አስተዳዳሪና የአንሙት ክንዴ ዘመድ አስማረ ዋሴ በ1997 ምርጫ የቅንጅት ፓርቲ የወረዳ ኃላፊ ሙሉ በለጠ በቀድሞ መንግሥት ካድሬ አብቡ ታከለው በመሪነት የተሳተፉበት እና ሌሎችም በመንግሥት ላይ ያኮረፉ አብዮታዊ ጡረተኞች ያሉበት ሲሆን በቤተክርስቲያኗ የተዘጋጀውንና ካለ ቤተክርስቲያኗ ፈቃድ ቀብር እንዳይፈጸም፣ በሰንበቴ አዳራሾቹ በካቴድራሉ ግቢ በጥበቃና በጽዳት ስም የሚያኖሩዋቸውን ተዋልደው በካቴድራሉ ውስጥ መንደር የመሠረቱ ግለሰቦችን  በማስወጣት በቤተክርስቲያኗ ሃይማኖታዊ ተቋም ባቻ ሆና እንድትቀጥል፡፡ መናፍቃንን በ70 ሺ ብር መቅበር እንዲቀር፣ የቤተክርስቲያኗን የድንጋይ ማእድን መሸጥ እንዲቆም የሚያዘውን ሕግ እንደማይቀበሉ አስታወቁ፡፡ ጉዳዩ ወደ ፍርድ ቤት ሲያመራ እነዚሁ ቀድሞ መንግሥት መኮንኖችና መናፍቃን ይዦታው የቤተክርስቲያኗ አይደለም በማለት መቃወሚያ አቀረቡ፡፡ ዳኛው እነዚህን ቡድኖች አንድ ጥያቄ ጠየቁ ለመሆኑ ቀብር ትፈጽማላችሁ ሲሉ “አዎ ” አሉ የሰንበቴ ቡድኖች ታድያ ቤ/ክ ግቢ አይደለንም ካላችሁ ቀብር የምትፈጽሙት መንገድ ላይ ነው መልስ አልነበራቸውም ፍርድ ቤቱ ቤተክርስቲያኗ በራሷ ሕግና ሥርዓት አደብ ታስገባቸው ሲል ሥልጣኑን ለቤተክርስቲያኗ ሰጠ፡፡ እስከ ሰበር በደረሰው የፍርድ ሂደት ይኸው ውሳኔ ጸና፡፡ እነ አቶ ወልዴ በዚህ ወቅት አማራጭ ያደረጉት ሟቹን ፓትርያርክ በሚያውቋቸው ሰዎች ማግባባት ነበር፡፡ እናም ፓትርያርኩን የሚያውቁ ግለሰቦችና ባለሥልጣናትን ይዘው ገብተው ፉካ መነገዳቸው ቤተክርስቲያኗን እንደማይጎዳ እና ለማስፋፊያ ቦታ እንዲጨምሩላቸው አነጋገሯቸው ፓትርያርኩም ‹‹የሥራ ተነሳሽነታችሁ መልካም ነው ነገር ግን ይህንን የቢዝነስ ሐሳባችሁን ወደ መንግሥት ውሰዱት በጠቃቅንና አነስተኛ ተደራጅታችሁ ብትሞክሩት ይሻላል እኔ የምላችሁ ይህንን ነው›› በማለት መለሱላቸው ሕጉ ይጎዳናል በማለት ቅሬታቸውን ለወቅቱ ጳጳስ ለአቡነ ቀውስጦስ አቀረቡ አቡኑም እኔ የቤተክርስቲያን ይዞታ ልጠብቅ እንጂ ልሸጥ አልመጣሁም አሏቸው፡፡ ጉዳዩ እልባት ሳያገኝ ፓትርያርኩን አረፍተ ዘመን ገታቸው አቡነ ዳንኤልም የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ሆኑ ሥራ አስኪያጃቸው ሊቀ ኅሩያን ሰርጸ ጋር በመሆን ጉዳዩ ለሀገረ ስብከቱ አስተዳደር ጉባዔ ቀረበ ጉባዔውም በሰንበቴ ስም ተደራጅቶ መነገድ አግባብ አይደለም ቤተክርስቲያኗም በይዞታዋ ተጠቃሚ መሆን አለባት ቀብር መፈጸምም የሰንበቴ ድርሻ ተግባር አይደለም በማለት አስተዳደራዊ ውሳኔ ሰጥቶ ለሰንበቴዎቹ መተዳደሪያ ሕግና መመሪያ አውጥቶ ላከ፡፡ በካቴድራሉ ከሚገኙ 11 ሰንበቴ ማኅበራት 5 የሚሆኑት ሕጉን ተቀብለናል ሲሉ ለሀገረ ስብከቱ አስታወቁ 7 የቀድሞ መንግሥት ወታደሮች የሚመሯቸው  ሰንበቴዎች ግን የሥራ ጊዜውን በጨረሰው የሰበካ ጉባዔ ምትክ ምርጫ እንዲደረግና እነሱ በምርጫው ሊቃነ መናብርቶቻቸውን በማስመረጥ ሕጉ ተግባራዊ እንዳይሆን ለማድረግ ምርጫ ይደረግ ሲሊ ለአዲስ የአቡነ እስጢፋኖስ አስተዳደር አቤት አሉ ፡፡ አቡነ እስጢፋኖስና ሥራ አስኪያጃቸው መጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት እንዲሁም የእሳቸው አስተዳደር ጉባዔ ከመከረ በኋላ ቀደም ሲል በአቡነ ዳንኤል የሚመራው ጉባዔ ያሳለፈውን ውሳኔ መልሶ በማጽደቅ ሰንበቴዎቹ በ 70 ሺህ ብር ለኢ አማንየን በ50 ሺ ብር ከውጭ ለሚመጣ አስክሬን በ 35 ሺህ ብር ለሀገር ውስጥ የሚሸጡትን ፉካ ንግድ እንዲያቆሙ ለተለያዩ የፖለቲካ ስብሰባዎች፣ ለሰርጋና ለቅሶ አዳራሽ በማከራየት መነገዳቸው እንዲያቆሙ አዘዘ፡፡
አዲሱ ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ማትያስ በቦታው ተገኝተው የሰንበቴ ማኅበራቱ (አክሲዮን ማኅበራቱ) ሕንጻ እና ሕገ ወጥ የቀብር ሥፍራ ከተመለከቱ ባኋላ ባስተላለፉት መመሪያ ይህ ቦታ የቤተክርስቲያን ብቻ ነው ማንም አለአግባብ ሊጠቀምበት አይገባም ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡
ጠቅላይ ቤተክህነት በዋና ስራ አስኪያጁ በብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ አቡነ ሉቃስ አማካኝነት በሰንበቴ ማኅበራቱ የካቴድራሉን ይዞታ ለመንጠቅ ክስ የመሰረተ ግለሰቦች በተመራጭነት እንዳይሳተፉ መመሪያ አስተላለፉ ፡፡ በዚህ ሁኔታ የአጥቢያው ሰንበት ትምህርት ቤት በሰራው ከፍተኛ ቅስቀሳ ብዙ መራጭ የእነዚህን ነጋዴ ሽማግሌዎች ሐሳብ በመረዳት በተጻራሪነት በምርጫው ስፍራ ተገኘ፡፡ ከሰንበቴዎቹ ጋር በመሆን በእብነበረድ ሽያጭ የተሰማራ እና የደህንነት አባል ነኝ በማለት ጳጳሳቱን ጭምር የሚያስፈራራቸው አለማየሁ ከልል የተባለ ግለሰብም ከደህንነት ተወክያለሁ በማለት ምርጫው ውስጥ የሚሳተፉ ግለሰቦችን ስም ዝርዝር አዘጋጅቶ በስፍራው ተገኘ፡፡ ምርጫው በቤተክህነቱ ቀላል ግምት ስላልተሰጠው መስከረም 8 ቀን ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ በስፍራው ተገኙ የሀገረ ስብከቱ ሁሉም የመምሪያ ኃለፊዎችም በእለቱ በአውደ ምህረቱ ተሰየሙ በፉካ ንግድ የተሰማሩት ግለሰቦች አመጽና አድማ በመፍራት የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አባላት ስፍራው ላይ በተጠንቀቅ ቆሙ፡፡ ነጋዴዎቹ አበል ከፍለው ያመጡት ሕዝብ በቁጥር አንሶ ለቤተክርስቲያን የቆመው ወጣት ቁጥሩ በልጦ ሲያዩ ምርጫውን መበጥበጣቸው አልቀረም ነገር ግን ጳጳሳቱ እምነታቸው ዘብ ቆመው ዋሉ፡፡ በዚህ ሁናቴ ምርጫው በሰላም መካሄዱን ሲመለከቱ ብዙዎቹ የተቃዋሚ ሰንበቴ አመራሮች ምርጫውን ረግጠው ወጡ፡፡ መናፍቋ ቅድስት አሳልፍ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስን ‹‹ገዝቼዎታለሁ ›› በማለት ኦፈ ግዝት እርግማን አወረደች፡፡ እሳቸውም ገዘተው አወገዟት፡፡ ምርጫውም በሰላም ተጠናቆ አዲስ አመራር ቤተክርስቲያኗና የእነዚህን ነውጠኛ ቡድኖች መካል ተመረጠ፡፡ ማንኛውም የቤተክርስቲያን አካል እነዚህን ቡድኖች በመፍራት ወደ ሰአሊተ ምህረት ቅ/ማርያም ካቴድራል ለመዛወር ፈቃደኛ አይደለም፡፡ ከመንግሥት የጸጥታ አካላት በላይ የሚፈሩ ቤተክህነቱን እንደ እንስራ ውሃ ባሻቸው ጊዜ እያንቦጫቦጩት 2 ፓትርያርኮች 3 ሊቃነ ጳጳሳትና 3 ሥራ አስኪያጆችን ሲሻቸው እጠሳደቡና እያስፈራሩ ዛሬ ላይ ደርሰዋል፡፡
አሁንም እነዚህ ቤተክርስቲያን ብር ከልዩ ልዩ የቢራ አምራች አክስዮን ማኅበራት ከፍተኛ አክስዮን በሚገዙ በቤተክርስቲያን ብር ለኃጢአት ተግባር  ገንዘብ ከሚመድቡ እድሜ ያላስተማራቸው ግለሰቦች ቤተክርስቲያኗን እየበጠበጡዋት ይገኛሉ፡፡ ቤተክርስቲያኑንም የሚመራው አካል አንድ ዘላቂ እርምጃ ካልወሰደ በተደጋጋሚ እንደሚዝቱትና በተግባርም እንደሚሞክሩት ገለልተኛ ቤተክርስቲያን በሚል ሕዝበ ክርስቲያኑን መክፈላቸውና ቋመጡለትንና ለዘመናት ያልተሳካላቸውን  የፖለቲካ ሥራ በድብቅ ለማካሄድ በሚፈጥሩት ችግር ቤተክርስቲያኗ የሰላም ስፍራነቷን ማጣት የለባትም፡፡ እነሱም ካለፈው የስህተት ዘመናቸው በመነሳት ይህ ወቅት የንስሀ ሊሆንላቸው ይገባ ነበር፡፡ ዛሬም ቤተክርስቲያን ውስጥ ባሉት አንዳንድ ደላሎች አማካኝነት ወልዴ የምሸጠው 5 ፉካ አለና ሰዎች በሕይወት እያሉ ይጫረቱ በማለት የግለሰቦችን ገንዘብ እየሰበሰበ ይገኛል፡፡ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የጥቅምቱ ሲኖዶሰ በወሰነው መሠረት የነጋዴ ሰንበቴ ማኅበራት ጉዳይ እልባት ይሰጠው፡፡ መንግሥትም እነዚህን ድብቅ የፖለቲካ ኃይሎች ሕጋዊ እርምጃ በመውሰድ ምነው በእንቁላሉ የሚሉበትን ጊዜ ሊያቀርብ ይገባል፡፡