Friday, January 3, 2014

አዲዮስ ማኅበረ ቅዱሳን፤ አዲዮስ!!



ስጳኛውያን ደህና ሰንብት፤ ደህና ሁን! ብለው ሲሰናበቱ «አዲዮስ!» ማለት ልምዳቸው ነው። እኛም ይህንን ቃል ተውሰው ሲናገሩ እንደቆዩት አበው ዛሬም ለማኅበረ ቅዱሳን «አዲዮስ» ብለነዋል።
መነሻ ምክንያታችን ሁለት ነው።
1/ ማኅበሩ ራሱ እያደገ ከመጣበት የኢኮኖሚ አቅምና የመዋቅር ስፋት አንጻር በቤተ ክርስቲያኒቱ ስር ተጠልሎ ያለስጋት መዝለቅ እንደማይችል በመረዳቱ  ወደ «ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ድርጅት» ወይም ሼር ካምፓኒ የመዛወር ፍላጎት እንዳለው ውሰጥ አወቅ ምንጮች በመጠቆማቸው የተነሳ ይህ እውን ከሆነ ለዓላማው ስኬት የምንሰጠው ድጋፍ «ማኅበረ ቅዱሳን አዲዮስ» በማለት ነው። Good bye MK!!
2/ በ23/ 4/2006 ዓ/ም  በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ከፓትርያርኩ ጋር ተገናኝተው በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ላይ ሊተገበር በተፈለገው የማኅበረ ቅዱሳን ድርጅታዊ ጥናት ላይ የቀረበው የአስተዳዳሪዎችና የማኅበረ ካህናቱ ተወካዮች የተቃውሞ ሃሳብ ማኅበረ ቅዱሳን ከቤተ ክርስቲያን ታዛ ተገፍትሮ የመውጣቱን የጅማሬ ያመላከተ በመሆኑ «አዲዮስ ማኅበረ ቅዱሳን» ብለነዋል።
3/  በማኅበረ ካህናቱ መካከል ካለን መረጃ አንጻር ከዚህ በፊት «የማኅበረ ቅዱሳን መግነንና ብቀላ መሳ ለመሳ ናቸው፤ እንደጠዋት ጤዛም ቀትር ላይ ይጠፋሉ!» በሚል ርዕስ ባወጣነው ጽሁፍ ላይ እንደዚህ የሚል ቃል ጠቅሰን ነበር።
« ምናልባትም የማኅበረ ቅዱሳን በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ውስጥ የማቡካት የመጋገር ጅማሮ የማኅበሩን ዕድሜ ቀጣይነት ወሳኝ ምዕራፍ ከፋች ሊሆን እንደሚችል ይገመታል። በሂደት የምናየውም ይሆናል» (የጥቅሱ መጨረሻ)
ይህንን ጽሁፋችንን ወደተግባር ስለመቀየሩ የሚያመላክቱ ክስተቶች በቤተ ክህነቱ ደጃፍ በተግባር እያስተዋልን ነው። ወደፊት ማኅበሩ ራሱን እንዴት ሊከላከል ይችላል? በመናጆ ጳጳሳቱ በኩል እስከየት ይራመዳል? የሚሉ ጥያቄዎቻችን እንዳሉ ሆነው አሁን ያለው የማኅበረ ካህናቱ ድምጽ የማኅበሩን ረጅም ጉዞ በትክክል ባለበት አቁሞታል ብቻ ሳይሆን ለወደፊቱም ከዚህ በላይ እንዳይሄድ አስሮታል ማለት ይቻላል።
 አሁን በተያዘው የአስተዳዳሪዎችና የማኅበረ ካህናቱ አጠቃላይ በማኅበረ ቅዱሳን ላይ ያለው ተቃውሞ ቀጣይነት የማኅበሩን እድሜ ቀጣይነት ወሳኝ ምዕራፍ ከፋች መሆኑን አሳይቶናል። ለዚህ የሚጠቀስ በማኅበሩ ላይ በስብከተ ወንጌል አዳራሽ የቀረበው ተቃውሞ በጣም ከፍተኛ ሆኖ መገኘቱ፤ ፓትርያርኩም የካህናቱን ጥያቄ ተፈጻሚ ለማድረግ ቃል መግባታቸው አረጋጋጭ መሆኑ ነው።
በአዳራሹ ውስጥ የተገኙትና በማኅበረ ቅዱሳን የስም ማጥፋት ዘመቻ የተከፈተባቸው፣ እንዲሁም በተገኙበት ቦታ በስውር እንዲገደሉ የተወሰነባቸው ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ እንዲህ ሲሉ ደስታቸውን መግለጽ እስኪሳናቸው ድረስ ለማኅበረ ካህናቱ መናገራቸው ታውቋል።
« ማኅበሩ አሉ ብፁዕነታቸው፤ ማኅበሩ እስከሞት ድረስ እንደሚፈልገኝ አውቃለሁ፤ እንድንስማማ ለማባበል ቢሞክር አለመቀበሌ ቢያበሳጨው ስም ማጥፋትና ልዩ ልዩ ዘመቻ እንደዘመተብኝም ለሁላችሁ የተሰወረ አይደለም። ስላልቻለ እንጂ እንደእቅዱ እስከዛሬ እኔ የለሁም። የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አሟሟት ራሱ ምስጢር ነው። የብፁዕ አቡነ መርሐ ክርስቶስ አሟሟት ራሱ ስውር ነው። ማንም እግዚአብሔር ካዘጋጀለት የሞት እድሜ ባያልፍም አሟሟት ሁሉ አንድ አይደለም። ስለዚህ ይህ ስውር አሟሟት ከተዘጋጀላቸው ሰዎች አንዱ እኔ ነኝ። ድሮ ብቻዬን የሆንኩ ያህል ይሰማኝ ነበር። ለካስ አጠቃላይ ማኅበረ ካህናቱ በዚህ መሰሪ ማኅበር ላይ ያለው እውቀትና ምሬት እኔ ከምጠብቀው በላይ ነበር። ሳልሞት እንኳን ይሄንን ለማየት በቃሁ እንጂ ከእንግዲህ ለምን ነገ አልሞትም፤ የቤተ ክርስቲያን ትንሣዔ መድረሱን ዛሬ አየሁ! ሲሉ ከፍ ያለ ጭብጨባና እልልታ በአዳራሹ አስተጋባ። አስተዳዳሪዎቹም በመረጃና በማስረጃ ስለማኅበሩ ያለውን አመለካከት የገለጹ ሲሆን ለአብነትም «ማኅበረ ቅዱሳን በሚሊዮኖች ብር እንደሚያንቀሳቅስ እናውቃለን፤ ለቤተ ክርስቲያን ፐርሰንት አይከፍልም፤ ለመንግስት ታክስ፤ ቀረጥ አይከፍልም። ይነግዳል፤ ያስነግዳል። በየዐውደ ምህረቶቻችን ይሸጣል፤ ይለውጣል። የቤተ ክርስቲያኒቱን አባላት የራሱ ምልምል አድርጎ ያደራጃል፤ ይሰልላል። ወንጌል ሰባክያንን ይነቅፋል፤ ይወነጅላል፤ ያስፈራራል። ታዲያ እንዲህ ዓይነቱን በሕጋዊነት ሽፋን የማፊያ ስራ የሚሰራ ማኅበር የምንሸከመው እስከመቼ ነው? ሲሉ ይጠይቃሉ። እኛ ይፍረስ ወይም ይጥፋ አንልም። የቤተ ክርስቲያኒቱ አባል ነኝ ካለ ሀብትና ንብረቱን በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም ያስመዝግብ፤ ገቢውን ያሳውቅ። እንደአንድ ማኅበር በሚፈቀድለት ልክ ይኑር። አልፈልግም ካለ ግን ራሱን ችሎ ቢሻው የእርዳታ ድርጅት፤ ቢሻው ኢንቨስተር ሆኖ በመንግስት አስፈቅዶ በሕግ ስር ይኑር። ዐመጻ ከፈለገ ደግሞ መንግስት እንዲያስታግስልን አቤታችንን እንቀጥላለን በማለት ተራ በተራ ለፓትርያርኩ አስረድተዋል።
ጉዞውን ጀመርን እንጂ አልጨረስንም፤ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮና  የተወካዮች ምክር ቤት ድረስ እንዲህ እንደዛሬው ተሰብስብን ጩኸታችንን እናሰማለን። ማኅበረ ቅዱሳንን እንዲያስታግስልን ሰላማዊ ሰልፍ እንወጣለን» በማለት ምሬታቸውን መግለጻቸውን ለመረዳት ተችሏል።  በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ላይ ስለተጀመረው የስራ ዋስትና የሚያሳጣው የማኅበሩና የጳጳሱን ጥናት በተመለከተም  አስተዳዳሪዎቹና ማኅበረ ካህናቱ በአንድ ድምጽ እንደተናገሩት « ቤተ ክርስቲያናችንን የሚጠቅም፤ የማኅበረ ካህናቱን ችግር የሚፈታ፤ ሙስናን፤ አድልዎን፤ መልካም ያልሆነ አስተዳደርንና በአጠቃላይ ያሉብንን ችግሮች መቅረፍ የሚችል ጥናትና እቅድ በምሁራን ልጆችዋ፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ በሕግ አዋቂዎቿና ቅዱስ ሲኖዶስ በሚሰጠው መመሪያ የሚወጣ ማንኛውንም የማሻሻያውን ትግበራ የምንደግፍና ለአፈጻጸሙም የበኩላችንን ድርሻ  ለመወጣት ቃል የምንገባ መሆኑን እየገለጽን ማኅበር በተባለ ድርጅትና በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ በኩል የመጣውን የማንቀበል መሆኑን አበክረን እናስገነዝባለን በማለት ለፓትርያርኩ በግልጽ ተነግሯል። በአዳራሹ ውስጥ የነበረው ተሰብሳቢ በድጋፍ ስሜቱን  ገልጿል።
ፓትርያርኩም በተፈጸመው ነገር ማዘናቸውን፤ ወደፊትም የቤተ ክርስቲያኒቱን አጠቃላይ ችግር በሚፈታ መልኩ ጥናት ሊደረግ እንደሚገባው፤ ካህናቱ ያልተቀበሉትንና ያልደገፉትን በካህናቱ ላይ በግድ መጫን እንደማይቻል፤ ሁላችንም ለቤተ ክርስቲያናችን ሰላምና እድገት የሚጠቅመውን ማዘጋጀት እንደሚገባን አምናለሁ በማለት ለተሰብሳቢዎቹ የተስፋ ቃል በመስጠት የካህናቱን ድምጽ በጥሞና ሰምተው ምላሻቸውን በጉባዔው ላይ አቅርበዋል። ማኅበረ ካህናቱ የአቡነ እስጢፋን ከቦታቸው መነሳት በትኩረት ያነሱት ጉዳይ ሲሆን እሳቸውን በተመለከተ በሲኖዶስ የሚታየውን ነገር በዚያ ጉባዔ ላይ ይህ ይሆናል ብሎ መናገር ለጊዜው እንደማይቻልና ችግሮችን ከግለሰቦች ጋር ማስተሳሰሩ  ወደፊት አያራምድም በማለት ፓትርያርኩ በወዳጃቸውና ለሹመታቸው በተዋደቁላቸው ሊቀ ጳጳስ ላይ ማተኮር እንደማይገባ ለመምከር ሞክረዋል። እሳቸው እንዲህ ይበሉ እንጂ ማኅበሩን በካህናቱ ጫንቃ ላይ ይዘል ዘንድ የፈቀዱት ሊቀ ጳጳሱ መሆናቸው መስተባበል የሌለበት ጉዳይ  እንደሆነ ለመግለጽ እንወዳለን።
ብዙ ሃሳቦች ተሰንዝረውና የማኅበረ ካህናቱም ጥያቄ ተቀባይነት አግኝቶ የውይይቱ ፍጻሜ ሲሆን የማኅበረ ቅዱሳን ጥናት ግን «አዲዮስ» ተብሏል።
ማሳሰቢያ፦ ለአስተዳዳሪዎችና ማኅበረ ካህናት !
አበው  «የነብር ጅራት አይዙም፤ ከያዙም አይለቁም» እንዲሉ ይህንን በነብር የተመሰለ ጥፍራም ማኅበር የበለጠ እንዳይቧጥጠን ጥፍሩን ከተቻለ መከርከም ወይም ተይዞ ሰው በማይጎዳበት ሁኔታ እንዲኖር ማድረግ እንጂ አንድ እርምጃ በመጓዝ ውጤት ተገኝቷል ብሎ መቀመጥ የበለጠ እንዲደራጅ እድል መስጠት ስለሆነ ማኅበሩ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ጥጉን እንዲይዝ በሚደረገው ርብርብ ውስጥ እንቅስቃሴያችሁ ቀጣይነት ያለው ይሁን ምክራችን ነው። « ማኅበረ ቅዱሳን» በቅዱሳን ስም የተሰየመ ነጋዴ ቡድን፤ አዲዮስ!!!

Thursday, January 2, 2014

ከፈረሱ ጋሪው የቀደመበት በማኅበረ ቅዱሳን የቀረበው የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት አዲሱ ጥናት!



ማኅበረ ቅዱሳን ባልታጠበ እጁ የመቅደሱን አገልግሎት ለመናኘትና የአስተዳደሩን ወንበር ለመጨበጥ ላይ ታች ማለት የጀመረው ገና አቡነ ጳውሎስን ገፍቶ እስከሞት ድረስ ከመታገሉ አስቀድሞ ነው። ተላላኪ ጳጳሳቱን ካሰማራ በኋላ በአዋጅ ባለባቸው ህመም ሳቢያ እንደሞቱ የሚነገርላቸው እና በውስጥ አዋቂዎች ደግሞ ከህመሙ ባሻገር የሰው እጅም አለበት የሚለውን  የስውር አካሄድን ይትበሃል የተመለከተ የአቡነ ጳውሎስ ኅልፈት  ከመድረሱ በፊት ማኅበሩ ራሱን ከሰንበት ት/ቤቶች መምሪያ ነጻ በማውጣት በቀጥታ ተጠሪነቱ ለሲኖዶሱና ለሥራ አስኪያጁ እንዲሆን ነጋሪት አስመታ። ከዚህ አዋጅ በኋላ ማኅበረ ቅዱሳን የማይደፈር፤ የማይነካ የቤተ ክህነቱ አንበሳ ሆነ።  በግንቦቱ የ2004 ዓ/ም  ሲኖዶስ ላይ ይህንን አስወስኖ ድል በድል በሆነበት ዋዜማ ሟቹን ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እንዲህ ብለን ነግረናቸው ነበር።
«አመኑንም አላመኑም ፓትርያርክ ጳውሎስ፤አንድ ነገር አስረግጠን እንነግርዎታለን። በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው» ብለን ነበር። [1]
እንዳልነውም ይህንን ከተናገርን ከሁለት ወራት በኋላ አቡነ ጳውሎስ ወደማያልፈው ዓለም ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ሄዱ። ነብይ ስለሆንን ወይም ከሰው የተለየ ራእይ ስለመጣልን አልነበረም። በወቅቱ የነበረው የማኅበሩና በገዛ እጃቸው ጰጵሰው የጥላቻ ፈረስ ያሰገራቸው ጳጳሳት አካሄድ ጤናማ ስላልነበር አንድ ነገር ሊመጣ እንዳለ ይጠቁመን ነበርና ነው። ያልነውም ሆነ። ማኅበሩም ተደላድሎ ቤተ ክህነቱን ያዘ። ከእንግዲህ ምን ቀረው ማለት ነው? ቤተ መንግሥቱ? በዚህ ዙሪያ በሌላ ርእስ እንመለስበታለን።

 አሁን አንድ ነገር እዚህ ላይ አስረግጠን በመናገር ወደርእሰ ጉዳያችን እናምራ።
ጳጳሳቱ አንድም በራስ የመተማመን ጉድለት ባመጣው ፍርሃት ለማኅበሩ አጎብድደዋል፤ በሌላም አንድ ምክንያት ግለ ነውራቸውን አደባባይ እንዳያወጣ የበደል ምርኮኝነታቸውን አስበው ራሳቸውን ለማኅበረ ቅዱሳን አሳልፈው ሰጥተዋል። ይሁን እንጂ፤
«አመናችሁም፤ አላመናችሁም እናንተም የአባ ጳውሎስን የጥላቻ ጽዋ ከማኅበረ ቅዱሳን ዋንጫ በተራችሁና በሰዓቱ ትጎነጫላችሁ። ወደማይቀረውም ሞት ተራ በተራ በጊዜአችሁም፤ አለጊዜአችሁም ትሸኛላችሁ፤ በሕይወት እያለን ይህንን የማኅበረ ቅዱሳንን ሚዛን ስትቀበሉ እናያለን፤ ያኔ ደግሞ እንደዚህ ብለናችሁ ነበር እንላለን» ይህም ደግሞ በቅርቡ ይጀምራል»
ከአቡነ ጳውሎስ ሞት በኋላ ሲኖዶስ ማለት ማኅበረ ቅዱሳን ነው። ቀንደኛ የማኅበሩ መዘውሮች ደግሞ አፍንጫና ጆሮ በመቁረጥ በራሱ የተአምር መጽሐፍ ላይ የተመሰከረለት የዘርዓ ያዕቆብ ደቀመዛሙርት ናቸው። በእርግጥ የማኅበሩን እርጥባን እየተቀበሉ በመናጆነት የሚያገለግሉ የሉም ማለት አይደለም። እነዚህ የዘርዓ ያዕቆብ ጉዶች በረቀቀ ስልት ቤተ ክህነቱን በእጃቸው አድርገዋል። ዋነኛ መፈክራቸው ቤተ ክህነትን « በገንዘባችን፤ በጉልበታችን፤ በእውቀታችን እናገለግላለን» ነው። ገንዘባቸውን  እንደሆነ ቤተ ክህነት በጭራሽ አታውቀውም። ጉልበታቸውንም  ቢሆን እንደአበራ ሞላ በአካባቢ ጽዳት ተሰማርተው ወይም  ጥቃቅንና አነስተኛ አቋቁመው ስራ አጥ ካህናቱን ወደስራ ሲያስገቡ አላየንም። እውቀታቸውን ግን እነሆ ለአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ባቀረቡት ጥናት ሽፋን የቁጥጥር መረባቸውን ሲዘረጉ አይተናል። ይህም የረጅም ጊዜ ህልማቸውን እውን ያደረጉበት እውቀት በመሆኑ ቤተ ክህነት የጀመረችው የቁልቁለት መንገድ ነው ብሎ መናገር ይቻላል። መጨረሻውም እንደማያምር ጀማሪውን አይቶ መተንበይ አይከብድም። ይህንን እንድንል የሚያደርጉን ምክንያቶች አሉ። በጥቂቱ እንያቸው።
1/ የፕሮጀክት ጥናቱ አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግሮችን የዳሰሰ መሆን ነበረበት። የችግሮቹን መግፍኢ ምክንያቶች፤ ያስከተሉት ውጤትና የመፍትሄ መንገዶችን ያመላከተ ሊሆን ይገባዋል።  የጥናቱ ዝርዝር ሁሉንም አሳታፊ በሆነ ውይይት ዳብሮ ለመፍትሄና አፈጻጸም በሚያመች መልኩ ተዘጋጅቶ አተገባበሩ ግን ለናሙና በተመረጠ አንዱ ሀ/ስብከት መሆን በተገባው ነበር እንላለን። እየሆነ ያለው ግን ማኅበሩ በሚነዳቸው ጳጳስ ፈቃጅነትና ማኅበሩ በሚዘውረው ቋሚ ሲኖዶስ ይሁንታ ከማኅበሩ ቤተ ክህነቷን የመቆጣጠር ምኞት ተፈብርኮ አዲስ አበባ ላይ የመዋቅር ብረዛ ችካል መትከል ተጀመረ።
2/ በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግሮች ላይ ሊደረግ የሚገባው ሁለ ገብ ጥናት የቤተ ክርስቲያኒቱን አባላት፤ ሊቃውንት፤ ምሁራን፤ የሕግ አዋቂዎች፤  ጋዜጠኞች፤ ስልጣን ያላቸው ከፍተኛ ሹማምንት፤ የዩኒቨርሲቲ ምሁራን ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱ መሪዎች የተካተቱበትና የቤተ ክርስቲያኒቱ እድገትና ልማት የሚመለከታቸው ሁሉ ተቀናጅተው ይህን የማስተባባር ኃላፊነት ቢቻል በአንድ ሊቀ ጳጳስ የሚመራ ራሱን የቻለ ክፍል ተዋቅሮ መካሄድ በተገባው ነበር። ጋኖች አለቁና ማኅበረ ቅዱሳን አርቃቂ ሆኖ ጳጳሳቱ ከየትም ይምጣ እንጂ እንቀበላለን ብለው አረፉ። በማፈሪያዎች ዘመን የሚያሳፍር ነገር የለምና ብዙም አያስገርምም።
3/ ቤተ ክርስቲያኒቱ በሥጋዊ ወመንፈሳዊ አገልግሎቷ የሚጠበቅባትን ያህል እየተራመደች እንዳይደለ እርግጥ ነው። በአብዛኛው ውጫዊ ምክንያቶች እንደሆነ ተደርጎ ቢወሰድም፤ ለድክመቷ በዋናነት መነሳት ያለበት ከውስጧ ባለው ጉድለት መሆኑን ማወቅ ተገቢ ነው። ሲኖዶስና የሲኖዶስ የሕግ አመራር የዘመኑን የቤተ ክርስቲያን ሁኔታ የተመለከተ ስለመሆኑ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያኒቱ አጠቃላይ የመዋቅር ዝርጋታው፤ አተገባበሩ፤ መመሪያውና ደንቦቿ ሁሉ ችግሮቿን የቃኙ፤ መፍትሄ ማምጣት የሚችሉና የሚያራምዱ አይደሉም። ቃለ ዓዋዲ የተባለው ደንብ በምንም መልኩ የዛሬይቱን ቤተ ክርስቲያን የማስተዳደር አቅም የሌለው ስለመሆኑ በማስረጃ አስደግፎ መናገር ይቻላል። ስለሆነም አጠቃላይ ጥናት ያስፈልጋል ሲባል ይህንን የተመለከተ መሆን ስላለበት ጭምር ነው። አንዱን ጥሎ አንዱን በማንጠልጠል የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን ችግር ለብቻው ለመፍታት በፍጹም አይቻልም። የጳጳሳቱ ስሜትና የማኅበረ ቅዱሳን መንቀዥቀዥ ችግሩን ከማወሳሰብ በስተቀር የችግሩን ሰንኮፍ በፍጹም አይነቅልም።
4/ እስካሁን ያልተነገረለትና ሊነገርም ያልተወደደው የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር መንፈሳዊ ብልጽግናዋን የተመለከተው ክፍል ነው። በእርግጥ የአፄ ዘርዓያዕቆብ ትራፊዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥንታዊነትና ሐዋርያዊ አስተምህሮዋን የበረዘ የብርሃን ወረደልን ደብረ ብርሃናዊ ዜማ በጭራሽ እንዲነካ አይፈልጉም። የአባ እስጢፋኖስና ደቀ መዛሙርቱ የአፍንጫና ጆሮ መቆረጥን ተገቢነት ዛሬም እንደታመነበት እንዲቀጥል ይፈልጋሉ። ቤተ ክርስቲያኒቱ መከራን የተቀበለችበትን የክርስቶስን ወንጌል ወደጎን ገፍተው አለያም ወንጌሉን ጨብጠናል ለማለት ብቻ መሳ መሳ የሚራመዱት ተረት፤ እንቆቅልሽና አልፎ ተርፎም ክህደት ያለባቸው አስተምህሮዎች በጥናቱ ውስጥ በመካተት እርምት ሊወሰድባቸው የሚገባቸውን በቃለ እግዚአብሔር ሚዛንነት የመለየት ስራ ፈጽሞ ሊታለፍ የማይገባው ነው። ዘመናዊው አስተዳደር ያለመንፈሳዊ ልማት በጭራሽ አይታሰብም።
 የሰይጣን መነኮሰ ክህደትና እርምት ሲነገር ለምን ይሄ ተነክቶ በማለት ጸጉራቸው እንደጃርት እሾክ ከሚቆመው መካከል ማኅበረ ቅዱሳን አንዱ ነው። ይህ የተረት አባት የሆነ ማኅበር ነው እንግዲህ ሕግ አርቃቂ የሆነልን። ስለዚህ በወርቅ የቃለ ወንጌል ወራጅና ቋሚ ዐምድ የተተከለችው ቤተ ክርስቲያን በዘመናት ውስጥ ማንም ሳይፈቅድላቸው ገብተው የሸረሪት ድራቸውን ያደሩባት የዘመን እራፊዎች ጸድተው መገኘቷ አገልግሎቷን ምሉዕ፤ ክብሯንም በሚጠሏት ላይ ሳይቀር ከፍ ከፍ እንድትል ያደርጋታል። ደርግም፤ ኢህአዴግም ገፉን እያሉ ማልቀስ መነሻው የቀደመ መንፈሳዊ ክብሯ ስለቀነሰ ካልሆነ ሲያቦኩንና ሲጋግሩን አናይም ነበር።
ስለሆነም ከላይ ባየናቸው አራት ዋና ዋና መግፍኢ ምክንያቶች የተነሳ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ላይ የቀረበው የማኅበረ ቅዱሳን ጥናት ተብዬ ከፈረሱ ጋሪው የቀደመበት ነው ማለት ይቻላል። በየግል ጋዜጣው የላኩትን ጽሁፍ መልሶ እንደአዲስ ግኝት በዜና መልክ ማቅረብ ወሬ ማብዛት የሚወድ የወፈፌ ስራ እንጂ የቤተ ክርስቲያን ችግር እንደሰጎን እንቁላል አትኩሮ የተመለከተ የመልካም ዘር ተስፈኛ አስተሳሰብ አይደለም። ስለዚህ ይንን ጋሪው ከፈረሱ የቀደመበትን ጥናት በየትም ይምጣ ቀልደኞችን ጥሎ ጋሪው ፈረሱን የሚጎትትበት አግባብ ቶሎ መፍትሄ ይሰጠው።
------------------------------------------------------

Saturday, December 28, 2013

የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የደብር ሃላፊዎችና ሠራተኞች አዲሱን መዋቅር ተቃወሙ


(ደጀብርሃን) ሁሉን ዐቀፍ ጥናት ያልተደረገበትና በአናቱ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ላይ የለውጥ ሽፋን ሽብልቅ ሆኖ የገባው ማኅበረ ቅዱሳን ካህናቱንና የቤተ ክርስቲያኑን ላዕላይ አመራር ለሁለት እየሰነጠቀ ይገኛል። አባ ሉቃስን፤ አባ እስጢፋኖስንና ሌሎች የማኅበረ ቅዱሳን አገልጋይ ጳጳሳትን የያዘው ማኅበሩ ከጀርባ ሆኖ በቢሮው አርቅቆ ያመጣውንና በቤተ ክህነት መዋቅር ውስጥ የማንነት አሻራውን ለመትከል ታች ላይ እያለ የሚገኝ ሲሆን ቅዱስ ፓትርያርኩ ጉዳዩ እንዲጠናና ሁሉንም አሳታፊ እንዲሆን የነበራቸውን አቋም በማስለወጥ በጓሮ ያቀረበውን «የያብባል ገና» ፕሮጄክት በመደገፍ ላይ እንደሆኑ ውስጥ አዋቂ ምንጮቻችን መረጃውን አድርሰውናል። ሰሞኑን በፓትርያርኩ ቢሮ የከተመው ማኅበሩና አቀንቃኝ ጳጳሳቱ ለውጡን የሚቃወሙት ወገኖች በጣት እንደማይቆጠሩና ለዚያው ሌቦችና ዘራፊዎች ናቸው በማለት በማጠየም ላይ ተጠምዶ ሰንብቷል። ፓትርያርኩ ከዚህ በፊት የነበራቸው ሃሳብ ሁሉን አሳታፊ፤ አጠቃላይ የለውጥ እቅድ እንዲሆንና የቤተ ክርስቲያኒቱ አመራር የሚያወጣውና የሁሉንም ካህናት ሃሳብ ያካተተ ሊሆን እንደሚገባው የነበራቸውን አቋም ትተው ማኅበሩ እየተሯሯጠለት የሚገኘውን እቅድ እንዲደግፉ ሲወተውት ሰንብቶ ፓትርያርኩን የቀደመ ሃሳባቸውን አስጥሎ የራሱን እቅድ እንዳስጨበጠ መረጃችን አክሎ ገልጿል። ጉዳዩ እስከየት ይሄዳል? የሚለውን ወደፊት የምናየው ሆኖ አሁን ባለው ሁኔታ አለቆችን ለብቻ የነጠለ በሚመስል ስልት እየታከከ፤ የካህናቱን የስራ ዋስትና በመንጠቅ የራሱን አዲስ መዋቅር እየተከለ የሚገኘውን እንቅስቃሴ ማኅበረ ካህናቱ በዝምታ የሚያልፈው ከሆነ አሉታዊ ውጤቱ ለቤተ ክርስቲያኒቱም፤ ለሀገርም የሚተርፍ ይሆናል።
ይህንን በመቃወም የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት አስተዳዳሪዎችና ሠራተኞች እያቀረቡ ያለውን አቤቱታ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ዛሬ እንዲህ ዘግቦታል።
ዲግሪ ያላቸው በየአስተዳደሩ እንዲገቡ መደረጉ አግባብ አይደለምበኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የአዲስ አበባ ሃገረ ስብከት፣ ካለፈው ህዳር ወር ጀምሮ እያካሄደ ያለውን አዲስ የመተዳደሪያ ደንብ የማፅደቅ ሂደት እና መዋቅራዊ ለውጥ አጥብቀው እንደሚቃወሙ የሃገረ ስብከቱ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎችና ሠራተኞች ለቅዱስ ፓትሪያርኩና ለጠቅላይ ሚኒስትር /ቤት አስታወቁ፡፡ ቅሬታ አቅራቢዎቹ ለፅ/ቤቶቹ ባስገቡት ደብዳቤ፤ የሃገረ ስብከቱ አዲስ መተዳደሪያ ደንብ ሁሉም የቤተክርስቲያኒቱ ሊቃውንት ሳይሳተፉበት በጥቂት አመራሮች ብቻ የተቀረፀና በውይይት ያልዳበረ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ መተዳደሪያ ደንቡ ከነባሩ ህገ ቤተ ክርስቲያንና ከቃለ-አዋዲ ደንብ ጋር የሚጋጭና የሚጣረስ ነው ያሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ደንቡ፤ ነባሩን የቤተክርስቲያኒቱን ሠራተኛ በማፈናቀል በምትኩ ስለቤተ ክርስቲያን ትምህርት ምንም እውቀት የሌላቸውን ግለሠቦች በስመ ድግሪና ዲፕሎማ በመሠግሠግ የቤተክርስቲያኗን ሙሉ አስተዳደራዊ መዋቅር ለመቆጣጠር ያለመ ነውሲሉ ተቃውመዋል፡፡

አዲሱን መዋቅር ያዘጋጁት አካላት ማንነታቸው በግልፅ እንደማይታወቅ በደብዳቤያቸው የጠቀሡት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ የቤተክርስቲያኗ የመጨረሻ ስልጣን ያለውን ቅዱስ ፓትርያርክ ስልጣንን በመገደብ፣ ቤተክርስቲያኗ የእነዚህ አካላት ሠለባ እንዳትሆን ስጋት አለን ብለዋል፡፡ የቤተክርስቲያኒቱን ቃለ አዋዲ ያልጠበቀ ነው ያሉትን አዲሱን መተዳደሪያ ደንብ እንደማይቀበሉትም አስተዳዳሪዎቹ ገልፀዋል፡፡ ለቅሬታው መነሻ የሆነው ደንብ፣ ህግ በማርቀቅና በማዘጋጀት ከፍተኛ ልምድና እውቀት ባላቸው ገለልተኛ ምሁራንና የቤተክርስቲያኗ ሊቀ ሊቃውንት እንዲሰናዳ የጠየቁት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ህጉን አርቅቋል የተባለውን ማንነቱ ማህበር ፓትሪያርኩ እንዲያጣሩ ተጠይቀዋል፡፡አዲሱ ደንብ የካህናት ቅነሣ መርሃ ግብርም እንዳካተተ በግልፅ ተረድተናልያሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ድርጊቱ መንግስት ስራ አጥን ለመቀነስ የሚያደርገውን ጥረት የሚፃረር ነውሲሉ ያጣላሉት ሲሆን ብዙ ሊቃውንትን ከስራ በማፈናቀል ለችግር እና ለእንግልት የሚዳረግ በመሆኑ ህጉ መፅደቅ እንደሌለበት አሳስበዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ ማብራሪያ የጠየቅናቸው የፓትርያርኩ ልዩ /ቤት ሃላፊ አቶ ታምሩ አበራ የቅሬታ አቅራቢዎቹ ደብዳቤ ወደ /ቤት ሳይገባ በቀጥታ ለፓትርያሪኩ የደረሰ በመሆኑ በጉዳዩ ላይ ምላሽም ሆነ አስተያየት ለመስጠት እንደሚቸግራቸው ተናግረዋል፡፡ ቅሬታ አለን የሚሉ ወገኖች በተናጥል ከሚቀርቡ፣ ለቤተክርስቲያኗ ይጠቅማል የሚሉትን ኮሚቴ መርጠው ሃሣባቸውን በማደራጀት ቢያቀርቡ እንደሚሻል የጠቆሙት ሃላፊው፤ የእነሡ ሃሣብ ተቀባይነት ባያገኝም እንኳ በውይይት ለመተማመን ዝግጁ መሆን እንዳለባቸው ገልፀዋል፡፡