Wednesday, October 29, 2014

«የነብር ጅራት አይዙም፤ ከያዙም አይለቁም!»

በጥያቄ እንጀምር! ማኅበረ ቅዱሳን ይፍረስ፤ ይበተን አልተባለም። ወደሕግና ሥርዓት ይገባ ነው እየተባለ ያለው። ማኅበሩ ይሁን ማፈሪያ ሊቃነ ጳጳሳቱ በዚህ አባባል የሚናደዱት ለምንድነው? «ደረጃ፤ ቦታና መጠን ተበጅቶለት መቀጠል ይገባዋል» የሚለውን የማኅበረ ካህናቱን ድምጽ ለመስማት ያለመፈለግ ምክንያት ከምን የመነጨ ነው? እኮ አሳማኝ ምክንያት አቅርቡ!!
 አለበለዚያ «እኛ ሊቃነ ጳጳሳት ስለሆንና ጉባዔው በድምጽ ብልጫ ስለሚመራ የአድማ እጃችንን ቀስረን ማኅበረ ቅዱሳን የሚደሰትበትን እንወስናለን» የሚለው ፈሊጥ የተበላ ዕቁብ ነውና ዘንድሮ አይሠራም።  በትክክል ዘንድሮ አልሠራም፤ አይሠራምም።

 ሊቃነ ጳጳሳቱ በየአህጉረ ስብከታቸው የካህናት ማሰልጠኛ ኮሌጆችን በመክፈት፤ የሴሚናሪ ትምህርት ቤቶችን በማስፋፋት የመንፈሣዊና ሳይንሳዊ እውቀት ባለቤት እንዲሆን ለቤተ ክርስቲያን እድገት እንዲሁም ፤ ለህብረተሰቡ ደግሞ በአካባቢ ልማት ተሣትፎ፤ በመንገድ ሥራ፤ በጤና ጣቢያና በንጹህ ውሃ አቅርቦት ተግባር ላይ በመትጋት ያንን ድሃ ምእመን ሕዝባቸውን መርዳት፤ መደገፍና በሥራ ማሳየት ሲገባቸው ተሸፋፍነው በመቀመጥ ሠራተኛ ሲቀጥሩ፤ ሲያባርሩ፤ ደመወዝ ሲቀንሱና ከቦታ ቦታ ሲያዘዋውሩ እድሜአቸውን ይፈጃሉ። ንቡረ እድ አባ ገ/ማርያም የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅ በነበሩበት ጊዜ ሊቀ ጳጳስ አባ ቀውስጦስ ከራሳቸው ብሔርና ጎጥ ብቻ የመጣውን እየለዩ ለመቅጠር ሲታገሉ በተነሳ አለመስማማት የሙስና አፍ የዘጉትን ሥራ አስኪያጅ አይታዘዘኝም በሚል ውንጀላ ከስሰው እንዲቀየሩ ማስደረጋቸው አይዘነጋም። አሁን ደግሞ አባ ቀውስጦስ «ሞቴን ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ያድርገው» እያሉ ለያዥ ለገራዥ እያስቸገሩ እንዳሉ ይሰማል። ለምእመናን ልጆቹ በእኩል ዓይን አባት ይሆን ዘንድ ቃል የገባ ሊቀ ጳጳስ በዘረኝነትና በጎጠኝነት ሲታወር ሥጋውያኑማ እንዴት ይሆኑ?
የጎጃሙ ለጎጃም፤ የወሎው ለወሎ፤የጎንደሩ ለጎንደር፤ የሸዋው ለሸዋ የዘረኝነትን ገመድ የሚጎትት ሊቀ ጳጳስ ቤተ ክርስቲያንን እያወካት እንደሚገኝ ፀሀይ የሞቀው፤ አገር ያወቀው ጉዳይ ነው። እነማን? እንዴትና የት? ለሚለው በማስረጃ የተደገፈ ዝርዝር ማቅረብ ይቻላል።
ከብዙ መልካምና ጥሩ ነገሮቻቸው መካከል ሙት ወቃሽ አያድርገንና ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ የፈጸሟቸው ስህተቶች ለጵጵስና ማዕረግ ቀርቶ ለአንዲት አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪነት የማይበቁ ሰዎችን የመሾማቸው ጉዳይ ትልቁ ስህተታቸው ነበር። እሳቸውም በሕይወት ሳሉ ሊሾሙ የማይገባቸውን ሰዎች በመሾማቸው ይጸጸቱ እንደነበር እናውቃለን። ዛሬም የዚያ ስህተት ውጤት የሆኑ ሊቃነ ጳጳሳት ስንት ሥራና አገልግሎት ባለባት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለአንድ ማኅበር ጥብቅና ቆመው «ሞታችንን ከማኅበረ ቅዱሳን ጓሮ ያድርገው» ሲሉ ይታያሉ። ከተመቻቸውና ከሞቃቸው ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ሞታችንን ያድርገው ያሉት ይሁንላቸው። ነገር ግን ማኅበረ ቅዱሳን ራሱ ወደሕግና ሥርዓት ካልገባ መሞቱ አይቀርም። ያን ጊዜ ምን ሊውጣቸው ይሆን?

ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ የማኅበረ ካህናቱ ሙሉ ድጋፍ እንዳላቸው ይታወቃል። ማኅበሩን ሥርዓተ አልበኛ የሚያሰኙ ተግባራቱ የማኅበሩን የመጨረሻ እድል ይወስናሉ። የጳጳሳቱ ጩኸት መነሻውና መድረሻው ከጎጥ፤ ከጥቅምና ከፍርሃት የመነጨ እንጂ ለቤተ ክርስቲያን ከማሰብ አይደለም። ምክንያቱም ማኅበረ ቅዱሳን ሳይኖር ቤተክርስቲያን ነበረችና። ማኅበረ ቅዱሳንም ባይኖር ትኖራለች።  ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በሊቀ ጳጳሳቱ አድማ እንዳይፈቱ አደራችን ጥብቅ ነው። ከሕግና ከኃይል በላይ የሚሆን ማንም የለምና በበሉበት ለሚጮኹት ቦታ ሳይሰጡ ሥርዓትና ደንብ የማስገባት እርምጃዎትን ይቀጥሉ ዘንድ አበክረን እናሳስባለን። ዘንድሮን ነካክተው ከተዉት ይሄ የተደራጀ አውሬ እስከመጪው ዓመት ይበላዎታል። አቡነ ጳውሎስንም የበላው እንደዚሁ ነው። ዕድሜአቸውን በዐሥር ዓመት አሳጠርነው እያሉ የሚፎክሩት እስከየት የመጓዝ እልክ እንዳላቸው ማሳያ ነውና ይጠንቀቁ። ክፉ ሥራቸውን የሚጸየፍ እግዚአብሔር ይረዳዎታል።

«የነብር ጅራት አይዙም፤ ከያዙም አይለቁም!»






Friday, October 24, 2014

የቅዱስ ፓትርያርኩ የሲኖዶስ ጉባዔ መክፈቻ ንግግር (እዚህ ይጫኑ)



ሐራ ተዋሕዶ የተባለው የማኅበረ ቅዱሳን ቀኝ ክንፍ መካነ ጦማር ቅዱስ ፓትርያርኩ በሲኖዶሱ መክፈቻ ላይ ባቀረቡት ንግግር ተወገዙ፤ ውሳኔም ተላለፈባቸው ሲል ከብራዘር ሁድ ጳጳሳቱ ጋር ያለውን የምስጢር ትስስር በሚያሳብቅ መልኩ ዘገባውን አቅርቧል። ማኅበሩ የሲኖዶስ አባል ሆኖ በጉባዔው ላይ በመገኘት የጉባዔው ተካፋይ መሆን አይጠበቅበትም። በሱ ምትክ የጉባዔውን እስትንፋስ እየለኩ ምስጢር የሚያካፍሉ አባላት የሆኑ ጳጳሳት እንዳሉት ይታወቃል። ማኅበሩን ያናደደውና ደረጃውን ያልጠበቀ የፓትርያርኩ የመክፈቻ ንግግር ያሰኘው ነገር ቅዱስ ፓትርያርኩ ከመቼውም ጊዜ በላይ ስለማኅበሩ ቀጥተኛ አቋም ይዘው በመክፈቻ ንግግራቸው ላይ አበክረው ስላሳሰቡ ከደረሰበት ጭንቀት የተነሳ መሆኑ ይገባናል። የፓትርያርኩን ንግግር ደረጃ የሚያወጣና ማስጠንቀቂያ የሚሰጥ እሱ ማነው? አባ ሉቃስ? አባ ማቴዎስ?
በዚህ ዓመት ስለማኅበረ ቅዱሳን አቅምና ጡንቻ የመጨረሻ ገደብ ካልተደረገበት የነብርን ጅራት ይዞ እንደመልቀቅ ይቆጠራል። ጳጳሳቱም ቢሆን ክብራቸውን ካልጠበቁና ለማኅበሩ በአድማ ተሰልፈው ከቆሙ በተመዘገበ ግለ ታሪካቸው ቦታ ቦታቸውን እንዲይዙ ሊደረግ ይገባል። በአጭር ቃል ባለትዳሮቹና የልጅ አባቶቹ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ ማዕረግ ወርደው ከምዕመናን አንድነት ሊቀላቀሉ የሚገባው ዓመትም ይህ ዓመት ነው። ሳይገባቸው ከፍታ ላይ የተቀመጡ ሰዎች ባለበት አስተዳደር ምን ጊዜም ሁከት፤ ክፍፍልና እርስ በእርስ መለያየት መኖሩ እርግጥ ነው።
ይህ ዓመት ቤተ ክርስቲያንን የሚያምሱ፤ በአድማ የሚወስኑ ሰዎች ሰልፍ የሚሰበርበት እንዲሆን እንመኛለን።

Wednesday, October 22, 2014

ማኅበረ ቅዱሳንን ክርስቲያናዊ ብራዘር ሁድ የሚያሰኙ ማስረጃዎችና መመሳሰሎች!

ሙስሊም ብራዘር ሁድ ወይም የሙስሊም ወንድማማቾች ማኅበር የተባለው ድርጅት በ1928 ዓ/ም በግብጽ ተመሠረተ። ከሰማንያ ዐመታት በኋላ በጄኔራል አልሲሲ መንግሥት በአሸባሪነት ተፈርጆ ድምጥማጡ እስኪጠፋ ድረስ በ70 ሀገሮች ውስጥ ቅርንጫፎቹን ከፍቶ በዘመናዊና ሃይማኖታዊ ትምህርት ቤቶች፤ በገበያ ማዕከላት፤ በንግድ ሱቆች፤ በማከፋፈያ ድርጅቶች፤ በሚዲያ ተቋማት ወዘተ የሀብት ማግበስበሻ መንገዶች እየተሳተፈ ክንዱን በማፈርጠም ለእንቅስቃሴው የሚጠቅመውን የገንዘብ ምንጭ ሲፈጥር ቆይቷል። ይህ የግብጹ ሙስሊም ብራዘር ሁድ በዐረብ ሀገራት ውስጥ ተመሳሳይ የሙስሊም ወንድማማች ማኅበራትን በማደራጀትና በማሰልጠን መንግሥታቱን ሲያስጨንቅ የቆየ ሲሆን አሁንም እያስጨነቀ ይገኛል።

የሙስሊም ብራዘር ሁድ ለተባለው ሃይማኖታዊ-ፖለቲካዊ ድርጅት ዋነኛ ተቀባይነት ማግኘት ዋናው ምክንያት የሆነው በእስላሙ ሕብረተሰብ ውስጥ ቶሎ ሰርጾ እንዲገባ የሚያካሂደው ሃይማኖታዊ አስተምህሮቱና  ለዚህ እምነት መክፈል የሚገባውን ዋጋ ሁሉ በመክፈል ከአላህ ዘንድ የሚከፈለውን ምንዳ ለመቀበል ቶሎ መሽቀዳደም ተገቢ መሆኑን አበክሮ በመስበኩ የተነሳ ነው።

1/ የሙስሊም ብራዘር ሁድ መዋቅራዊ እንቅስቃሴ 

 ሙስሊም ብራዘር ሁድ መዋቅሩ በሀገሪቱ የመንግሥት ሲቪላዊ መዋቅር ደረጃ የተዘረጋ ነው። ይህም ከማዕከላዊ ቢሮው ተነስቶ አባል በሆኑ በእያንዳንዱ ቤተሰብ ውስጥ በሰንሰለት የተያያዘ ነው። ቤተሰባዊውን የአባልነት ማኅበር «ኡስራ» ይሉታል። አንድ «ኡስራ» አምስት አባላት ሲኖሩት ከአምስት በላይ ከሆነ በሁለተኛ የኡስራ ስያሜ ደረጃ ይዋቀራል። በቤተሰቡ ያሉትን ኡስራዎች የሚመራ ደግሞ የቤተሰቡ አባል የሆነ በእስልምና ሃይማኖቱ የበሰለና የብራዘር ሁድ አስተምህሮት በደንብ የገባውን ሰው የቤተሰቡ ጉባዔ ይመርጠውና «ናቂብ» ተብሎ ይሰየማል። ይህ «ናቂብ» የተባለው ሰው የቤተሰቡ አባላት በእስልምናው ደንብ ዘወትር ስለመንቀሳቀሱ ይቆጣጠረዋል፤ ያስተምረዋል፤ ይነግረዋል። ያልተመለሰውን በማኅበረሰቡ ደረጃ ለተቀመጠውና ከፍ ላለው ሃይማኖታዊ መሪ ያቀርበዋል። ይህ ሁሉ ሲሆን ስለእስልምናው የሚደረግ እርምጃ በመሆኑ በደስታ ከሚቀበል በስተቀር ማንም በተቃውሞ አያንገራግርም፤ ሊያንገራግርም አይችልም። ምክንያቱም ጸረ እስልምና እንደሆኑ ራሳቸውን አስገዝተዋልና። በዚህ ዓይነት አደረጃጀት የሙስሊም ወንድማማቾች ማኅበር ከላይ ወደታችና ከታች ወደላይ የተሳሰረ መዋቅር አለው።

2/   የገንዘብ ምንጮቹን ማሳደግ

ገንዘብ የዚህ ዓለም እንቅስቃሴ የደም ሥር ነው። አባላት ለመመልመል፤ እንቅስቃሴውን ለማስፋፋት፤ የሽብር ተግባሩን ለመፈጸም፤ ለመደለል፤ ለመሰለል፤ ሃይማኖታዊ ዶክትሪኑን ለማስተማር  እጅግ ጠቃሚ ነገር መሆኑን ጠንቅቆ የተረዳው ብራዘር ሁድ የገንዘብ አቅሙን ለሀገር ውስጥና ድንበር ዘለል ተግባሩ ያውለው ዘንድ ተግቶ ይሰራል።

የእስላም ወንድማማቾች ማኅበር ሁለት ዓይነት የገንዘብ ምንጮች አሉት። አንዱ በውጪ ሀገራት ካሉ አባላቱ በመዋጮ የሚሰበሰብ እንዲሁም ብዙ ሃብት ካላቸው የድርጅቱ ደጋፊ ሚሊየነሮች  የሚደረግለት የገንዘብ ፈሰስና በእስላማዊ መንግሥታት ስር ከተሸሸጉ ባለስልጣናት የሚዋጣለት ገንዘብ ነው።  ሁለተኛው ደግሞ በተራድዖ ስም ከውጭ የሚያሰባስበውን ገንዘብ ወደልማት ካዝና በመቀየር በአካባቢ ልማት፤ በትምህርት ቤቶችና መድራሳ ማቋቋም፤ ሥራ አጥ ህብረተሰብን በማደራጀት፤ የራስ አገዝ እንቅስቃሴን በመመሥረት የሚሳተፍ ሲሆን ለዚህም ሀገር በቀል የእርዳታ ስልት በመቀየስ መዋጮውን ቅርጹን ለውጦ ያግበሰብሳል። ይህም፤

ሀ/ ከአባልነት መዋጮ
ለ/ ከንግድ ድርጅቶቹና ከሚዲያ ተቋማቱ የሚገኝ ገቢ ነው።


ይህንን ገንዘብ በተለያየ የገንዘብ ማስቀመጫ ስልቶችና በብዙ የሂሳብ አካውንቶች ቋት ውስጥ በተለያየ ስም በማስቀመጥ ለሚፈልገው ዓላማ በፈለገበት ሰዓት ማንም ሳያውቅበት ያውለው ነበር። በተለይም የእስልምና ባንኮች ተመራጭ መንገዶቹ ነበሩ።

3/ በመንግስታዊ ተቋማት ውስጥ ሰርጎ መግባት

ብራዘር ሁድ አባላቱን ሲመለምል ነጻና ገለልተኛ የሆኑትን ብቻ አይደለም። ከሚኒስትሮች እስከፍርድ ቤቶች፤ ከመከላከያ እስከ ፖሊስ መምሪያዎች፤ ከድርጅት ሥራ አስኪያጆች እስከ አስተዳደር ኃላፊዎች ድረስ በአባልነት መልምሎ፤ አሰልጥኖና ሃይማኖታዊ ትጥቅ አስታጥቆ የሚንቀሳቀስ ድርጅት ነበር። እነዚህ የመንግሥታዊ አካላት ክፍሎች ድርጅታቸው ለሚነሳበት ተቃውሞና ኅልውናውን ፈታኝ ለሆኑ ችግሮች የግብዓት ምንጭ ሆነው ያገለግላሉ። አስፈላጊ በሆነ የመረጃ፤ የፋይናንስና የአፈና ሥራው በትጋት ይሰራሉ።
ይህ ድርጅት እንደሃይማኖታዊ ተቋም አራማጅነት ተነስቶ ወደፖለቲካዊ ሥልጣን መቆናጠጥ እርምጃው ለማደግ መሠረት አድርጎ የሚነሳው የእስልምና ሃይማኖትን ነው። ይህም ብራዘር ሁድን መቃወም እስልምናን እንደመቃወም እንዲቆጠር በሕብረተሰቡ ዘንድ የኅልውናውን ስዕል በማስቀመጥ እንዳይነካ ወይም እንዳይጠፋ ረድቶታል። የእስልምናውን አስተምህሮ መነሻ በማድረጉ የማይነቃነቅ ፖለቲካዊ ግብ ለማስረጽ ያገዘው ሲሆን የዚህም መገለጫው በአልሲሲ መንግሥት ላይ በአንድ ጊዜ እስከ 33 ሚሊዮን ተቃዋሚ ሰልፈኞችን በመላ ሀገሪቱ ማንቀሳቀስ የሚችል ድርጅት አድርጎታል።
 ይሁን እንጂ የጀነራል አልሲሲ መንግሥት እርምጃ ስልታዊ በመሆኑ በአንድ ቀን ብቻ ከሁለት ሺህ በላይ ከፍተኛና ዝቅተኛ አመራሩንና የሃይማኖታዊ ተፍሲር መምህራኖቹን ለቃቅሞ ወደማጎሪያ ካምፕ በመክተቱ ድርጅቱ በ85 ዓመት እድሜው አይቶት የማያውቀውን ውድቀት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲያስተናግድ አድርጎታል። በአልሲሲ መንግሥት የተተገበረው «ወፎቹ እንዲበተኑ ቅርንጫፉን መቁረጥ» የሚለው አባባል ብቻ ሳይሆን ግንዱን መንቀል በመሆኑ የብራዘር ሁድ ዋና መሪ መሐመድ ሙርሲን ጨምሮ ከፍተኛውን የሹራ ካውንስል ሳይቀር ከስር ገርስሶታል። በሺዎች የሚቆጠሩ አባላቱም የሞትና የእስራት ፍርድ ተከናንበዋል። አልሲሲ በቲቪ ቀርበው "ብራዘር ሁድን ከስረ መሠረቱ ነቅለን ካላጠፋን ሰላም የለንም" በማለት ድራሹን አጥተውታል። ዛሬም ድረስ የተቃውሞ ሰልፎች ያሉ ቢሆንም በሃይማኖት ካባ ስር በተሸፈነው ድርጅት በኩል የአእምሮ አጠባ ተደርጎ የተታለለው ሕብረተሰብ እንጂ ብራዘር ሁድ እንደተቋም በግብጽ ታሪክ ግብዓተ መሬቱ ተፈጽሟል። ያ ማለት ግን ብራዘር ሁድን የሚደግፍ፤ የሚጠባበቅና እንዲያንሰራራ የሚፈልግ የለም ማለት አይደለም።

4/ማኅበረ ቅዱሳን እንደክርስቲያን ብራዘር ሁድ ስንል ምን ማለታችን ነው?

1/ ተቋማዊ አደረጃጀቱ ከመንግሥትም፤ ከቤተ ክህነትም ቁጥጥር ነጻ መሆኑ
2/ የራሱን አባላት የሚመለምልና የሚያደራጅ መሆኑ
3/ የራሱ የሆነ የገቢ ምንጭ ያለውና የንግድ ተቋማትን የሚያንቀሳቅስ መሆኑ
4/ ከአባላቱ ልዩ ልዩ መዋጮዎችና የስጦታ ገቢዎችን በመሰብሰብ በልማት ውስጥ እየተንቀሳቀሰ እንዳለ የማሳየት ብልሃት ያለው መሆኑ
5/ በመንግሥት ተቋማትና መሥሪያ ቤቶች፤ ፍርድ ቤቶች፤ ፖሊስ መምሪያዎች፤ በኮሌጆችና ዩኒቨርሲቲዎች ስውር መዋቅር ያለው መሆኑ
6/ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላዕላይ መዋቅርና እስከ አጥቢያ ድረስ በተዘረጋው አስተዳደር የራሱ አደረጃጀት የዘረጋ መሆኑ
7/ በቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ውስጥ የራሱን ጳጳሳት በመመልመል ማስሾም የቻለ መሆኑ
9/ ከሀገር ውጭ ዓለም አቀፍ ቢሮዎችን ከፍቶ የሚንቀሳቀስና አባላት ያሉት መሆኑ
10/ ከዓለም አቀፍ የገቢ ፈጠራው ውስጥ በልማት ሰበብ የሚያጋብስ መሆኑ
11/ የመረጃ፡ የስለላና የትንተና መዋቅር ያለው መሆኑ
12/ የቤተ ክርስቲያኒቱን አደረጃጀቶች ለራሱ ዓላማ የመጠቀም አቅም ያለው መሆኑ
( ሰንበት ት/ቤቶችን፤ የጥምቀት ተመላሽና የጽዋ ማኅበራትን)
14/ የግለሰቦችን ስም በማጥፋት ወይም ራሳቸውን በማጥፋት፡በማባረር፡በመደብደብ ወይም ግለታሪካቸውን ለራሱ ዓላማ ጠምዝዞ በማዋል እርምጃ መውሰድና ማስወሰድ የቻለ መሆኑ
15/ ስሙን ለማግነን፤ ክብሩን ለማስጠበቅ የሚያስችል በራሱ የሚመራ እንዲሁም በፖለቲካ የተቃውሞው ጎራ የተሰለፉ ደጋፊዎችና በስውር መረብ የሚንቀሳቀስ የሚዲያ ተቋም ያለው መሆኑ፤
ማኅበረ ቅዱሳንን ክርስቲያናዊ ብራዘር ሁድ እንድንለው ያስችለናል።

እስካሁንም ማንም ምላሽ ሊሰጥበት ያልቻለው ዋናው ነጥብ ማኅበረ ቅዱሳን ከመንግሥት እይታ ውጪ መሆን ባይችልም ከመንግሥት ቁጥጥር ውጪ የሆነ ክርስቲያናዊ ማኅበር መሆኑ ሲሆን እንደክርስቲያናዊ ተቋምነቱ  ደግሞ ቤተ ክርስቲያኒቱ በማኅበሩ ላይ ቁጥጥርና ክትትል የማድረግ ችሎታ አንዳችም አቅም የሌላት በመሆኑ ያሳዝናል:: በመንግሥትም፤ በቤተ ክህነቱም ማንም ጠያቂ የሌለው ሆኖ መቆየቱን ለማመን ያለመፈልግ ዝንባሌ መኖሩም ያስገርማል::  ማኅበሩ እንደምክንያት ሁልጊዜ የሚያቀርበው ሲኖዶስ በሰጠኝ ደንብ እመራለሁ ቢልም እውነታው ግን ብራዘር ሁድ በሆኑ ጳጳሳት አባላቱ በኩል የሚመቸውን ደንብ አስጸድቆ ያለጠያቂ በነጻነት ከሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የገቢ አቅሙን እያሳደገ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን አባላት ለራሱ አባላት እየመለመለ፤በቤተ ክርስቲያኒቱ ቁመናና መልክ የራሱን አደረጃጀት፤ መዋቅርና እንቅስቃሴ እያከናወነ ያለ ማኅበር መሆኑ የማይካድ እውነታ ነው። ለምሳሌ የማኅበሩ ብራዘር ሁድ አባላት ጳጳሳቱ አባ ማቴዎስ፡አባ ቀውስጦስ፡ አባ ቄርሎስ፡ አባ ያሬድ፡አባ አብርሃም፡አባ ሳሙኤል፡ በአባ ማቴዎስ አደራዳሪነት የትግሬን መንግስት በጋራ መዋጋት በሚል ፈሊጥ ከማኅበሩ እግር ላይ ወድቀው የታረቁት አባ ፋኑኤል ተጠቃሾች ናቸው:: አባ ገብርኤል ግን ከአቶ ኢያሱነታቸው ጀምሮ የተጠጋቸው የውግዘት በሽታ  መቼም አይለቃቸውም::

5/ ለመሆኑ አሁን ያለው ማኅበረ ቅዱሳን አደረጃጀት፤   

የሰንበት ት/ቤት ስብስብ ነው? እርዳታ ድርጅት ነው? የልማት ተቋም ነው? የበጎ አድራጎት ማኅበር ነው? ራሱን ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ውጪ አስደርጓል። በዋና ሥራ አስኪያጅ ሥር የሚተዳደር ነገር ግን የቤተ ክህነቱ መምሪያ ያልሆነ መምሪያ ነው?
በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ሥፍራው ከየት ነው? በምንስ እንመድበው? ማኅበሩ በምን ሂሳብ እንደተቋቋመና በምን አደረጃጀት ኅልውና እንዳገኘ አይታወቅም::

እስከሚገባን ድረስ እንቅስቃሴውንና ያለውን አደረጃጀት ተመልክተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳናዊ ብራዘር ሁድ ብንለው ተግባሩ ያረጋግጣል።
በሌላ መልኩ መንግሥት በኢትዮጵያ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ እንዲህ ዓይነት ማኅበር ከእስልምና ምክር ቤቱ ውጪ እንዲቋቋም ይፈቅዳል ወይ ብለን እንጠይቃለን? መልስ የሚያሻው ጥያቄ ነው።