Wednesday, June 11, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን በፓትርያርኩ ላይ የመጨረሻ የስም ማጥፋት መርዙን መርጨት ጀመረ!!

ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ ስንል እንደቆየነው ከማኅበረ ቅዱሳን ስውር መሰሪ ተግባር ውስጥ አንዱ ጉዳይ የሊቃነ ጳጳሳቱን የሕይወት ታሪክ ባለው የገንዘብና የስለላ አቅም አስቀድሞ በመሰብሰብ ለችግር ቀን ሊጠቀምበት ከመሳቢያው ውስጥ ቆልፎ የማስቀመጥ ጥበቡ ነው። ሊቃነ ጳጳሳቱ ማኅበሩ ለሚፈልገው አገልግሎት የጎበጠ ጀርባ ለማቅረብ ፈቃደኝነት ሲጎድላቸው ወይም ሲያገለግሉት ቆይተው የጎበጠ ጀርባቸውን ቀና በማድረግ የነጻነት አየር ለመተንፈስ ሲፈልጉ ያንን ከመሳቢያው ውስጥ ቆልፎ ያስቀመጠውንና ስም ለማጥፋት ይጠቅመኛል ብሎ ያሰበበትን የቆሸሸ ሥራ እንደአዲስ ግኝት ብቅ በማድረግ በሕዝብ ዘንድ እንዲጠሉ የክፋት መርዙን በልዩ ልዩ አቅጣጫ መርጨት ይጨምራል።
እነሆ « የለውጥ አባት፤ ሙስናን ለመዋጋት ቃል የገቡ ፓትርያርክ» በማለት በማሞካሸት ጉሮሮው እስኪነቃ ውዳሴ ከንቱ ማብዛቱ ሳያንስ  በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ለማስረግ ሞክሮ ያልተሳካለትን «የሕግና የለውጥ አተገባበር መመሪያ» በማለት ያንቆለጳጰሰውን የቅጥፈት ስርዋጹን ሰነድ፤ ፓትርያርኩ «በመላ ሀገሪቱ ሊተገበር የሚገባው» በማለት አድናቆት እንደቸሩት ሲደሰኩር እንዳልነበር ሁሉ ፓትርያርኩ የማኅበሩን አካሄድ አይተው ፊታቸውን ሲያዞሩበት  በመረቀበት አፉ እርግማኑን ለማውረድ የተፋው ምራቅ ገና አልደረቀም ነበር።
የማኅበሩ የክፋት ጥግ ርኅራኄ የለሽ መሆኑን የሚያሳየን ሲያገለግሉት የቆዩት ሰለቸን ማለት ከጀመሩ ወይም ፊት ሰጥተው ሲያሳስቁት የነበሩት አባቶች ቅጭም ያለ ገጽታ ወደማሳየት ከተሸጋገሩ ስማቸውን በማጥፋት የነበራቸውን ስም ከአፈር በመደባለቅ እንዳይነሱ አድርጎ የመምታት ልኬታው ከባድ ነው።
ሰሞኑን በፓትርያርክ ማትያስ ላይ በግል ጋዜጦች፤ በአፍቃሬ እንዲሁም ስውር ብሎጎቹና በመንግስት ተቃዋሚ ድረ ገጾች ሳይቀር እየተቀባበሉ «ፓትርያርኩ የደርግ አገልጋይ ናቸው» ወደሚል የጋራ የስም ማጥፋት ዘመቻ ወርደዋል። «አንድ ሰሞን ማመስገን፤ አንድ ሰሞን መራገም» የማኅበረ ቅዱሳን «ሲመች በእጅህ፤  በማንኪያ ሲፈጅህ» መፈክር መገለጫ መሆኑ ነው።
አይሆንም እንጂ ቢሆንለት ፓትርያርኩ ነገ አዲስ ሀሳብ ይዘው ብቅ ቢሉና »ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያናችን የዓይን ብሌን ነው» የሚል መግለጫ ቢሰጡ  «12 ክንፍ ያላቸው ቅዱስ ፓትርያርኩ የክፍለ ዘመኑን አዲስ መግለጫ ሰጡ» በማለት እንደ ደብረ ብርሃኑ መብረቅ በብርሃን ወረደልን የፈጠራ ዜና ይለውጠውና ለፓትርያርኩ ገድል ይጽፍላቸው ነበር።
ይሁን እንጂ ይህ እንዳይሆን ለማኅበረ ቅዱሳን ህልም በመሰለ የእውነታ ውጥረት በፓትርያርኩ ስለተያዘ እርግማኑንና ስም ማጥፋቱን ስራዬ ብሎ ገፍቶበታል። ነገሩ ሲታይ «የማያድግ ጥጃ እንትን ይበዛበታል» እንዲሉ የስም ማጥፋት ዘመቻው የእስትንፋሱ የመጨረሻ ምዕራፍ እንደሆነ አመላካች ይመስለናል።
ፓትርያርክ ማትያስ«የደርግ ተላላኪ ነበሩ፤ አሁን ደግሞ የኢህአዴግ ተላላኪ ሆነው ተገልብጠዋል» በማለት ማጣጣሉ የሚያሳየን ነገር  የማኅበረ ቅዱሳን ተላላኪ ለመሆን በጭራሽ ፈቃደኝነት ቀርቶ ሃሳብ እንደሌላቸው ስላየ እንጂ ማኅበሩን እያሞጋገሱና ከወንበራቸውም ትንሽ ከፍለው ቢሰጡት ኖሮ ይህንን ወደመሰለ የብስጭት ማሳያ ነቀፋ ባልወረደም ነበር። እውነትን ለሕዝብ ለመግለጽ ፈልጎ ቢሆንማ ኖሮ አባ ገብርኤልን የመሰሉ የማኅበሩ ደጋፊ ጳጳስ በአንድ ወቅት አቶ ኢያሱ የመባላቸውን ዜና፤ አቡነ ጳውሎስን አውግዘው ወደአሜሪካ መፈርጠጣቸውን፤ እዚያም ሄደው የኢህአዴግ የተቃውሞ ሰልፍ አስተባባሪ ሆነው በአደባባይ መጮሃቸውንና 360 ዲግሪ ተሽከርክረው ወደጠሉት ሀገር መመለሳቸውን ዜና አድርጎ ለምን አይሰራም ነበር? ይህንንማ እንዳያደርግ አባ ገብርኤል የማኅበሩ ቀኝ እጅ ሆነው ስለሚያገለግሉ  ብቻ ነው።  ነገ ተነስተው «በዚህ ማኅበር ታምሰን የምንሞተው፤ እስከመቼ ነው?» የሚል ጥያቄ አቡኑ ቢያነሱ የታወቀና ያልታወቀ ኃጢአታቸውን እንደሸረሪት ድር ይዘከዝክላቸው ነበር።
በዘንድሮውም የሲኖዶስ ጉባዔ ላይ እንዳገኘው መረጃ ከሆነ የማኅበሩ ደጋፊ መሆናቸው በደንብ የሚታሙት ጳጳሳት ሳይቀሩ የድጋፍ ቀንዳቸውን አቁመው ሊከራከሩለት አለመድፈራቸው አንድም የማኅበሩ የእድሜ ዘመን ማጠሩን ከመገመት አንጻር አለያም በማኅበሩ ጥፋት የተነሳ ከኑግ እንደተገኘች ሰሊጥ እንዳይወቀጡ ከመስጋት የተነሳ ይመስለናል። ጥቅም ዓይናቸውን ካሳወራቸው መካከል ጥቂቶች ለመንጫጫት ከመሞከራቸው በስተቀር ከዚህ በፊት ሲያደርግ እንደነበረው ማኅበሩ አጀንዳ አስረቅቆ፤ ሲያስጸድቅ የነበረውን ጉልበት ዘንድሮ ሳያገኝ መክኖ ቀርቷል። አቡነ ጳውሎስን ተባብረው በአድማ ሲያዳክሙና ለራስ ምታት ሲዳርጓቸው የነበረው የሴራ አቅም በፓትርያርክ ማትያስ ተቀልብሶ በተገላቢጦች የማኅበሩና የደጋፊዎቹ ራስ ምታት ሆኖ የጫወታው ሜዳ ተጠናቋል።
ከዚህ በፊት ስንል እንደቆየነው አሁንም ደግመን የምንለው «የማኅበረ ቅዱሳን አባል መሆን መብት ሲሆን ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ወደማኅበር አባልነት ወይም ደጋፊነት ከወረደ ያለበትን መንፈሳዊ ሥልጣን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስረክቦ በተራ አባልነቱ እንዲቀጥል የማስድረጉ ነገር መዘንጋት የለበትም» እንላለን። ሊቀ ጳጳስ በቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ መንፈሳዊ ሥልጣን ላይ ተቀምጦ ከመንጋው ውስጥ በተለየ መልኩ የሚወደው ወይም የሚንከባከበው ወይም በጥብቅና የሚከራከርለት የተወሰነ የቤት ልጅ እና የእንጀራ ልጅ የሚባል ሊኖረው አይችልም። በሀዋሳ ታይቶ የነበረው ሁከት መነሻው በአባ ገብርኤል በኩል ማኅበረ ቅዱሳንን የቤት ልጅ አድርጎ የማየትና ማኅበሩን የሚቃወሙትን ደግሞ የእንጀራ ልጅ አድርጎ በማቅረብ መንጋውን በእኩል ለማገልገል ያለመቻል የጳጳሳት አባል የመሆን ልክፍት የተነሳ ነው። ይህ ችግር በቦረና፤ በሐረር፤  በመንፈሳዊ ኮሌጆችና በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ውስጥ ሳይቀር በተግባር ታይቷል። ማኅበሩ «ከኛ ጋር ያልቆመ ጠላታችን ነው» በሚል ፈሊጥ በአባልነት የያዛቸውን ጳጳሳት እንደዱላ በክርስቶስ መንጋ ላይ እየወረወረ ይጠቀምባቸዋል።
ስለዚህ ፓትርያርክ ማትያስ በስም አጥፊው ማኅበርና ለማኅበሩ በተለየ አድረው መንጋውን በእኩል ዓይን ማየት በተሳናቸው ላይ ፍትሃዊና የተጨበጠ እርምጃ ለመውሰድ ማቅማማት እንደሌለባቸው ለማስገንዘብ እንወዳለን።
የስም ማጥፋት ዘመቻው የማኅበሩን ማንነት ገላጭ ሲሆን በንስሐ ተመልሶ ቤተ ክርስቲያን በሰጠችው ልክ ከመንቀሳቀስ ይልቅ ክፋቱን ለመተው ያለመፈለጉ ማሳያ መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም።

Sunday, June 8, 2014

«የዓላማ ሰው ከመሆን የሚከለክል ማንነትና መፍትሄው»

[«ከዓላማ መር መጽሐፍ» ለንባብ እንዲመች ተደርጎ የተወሰደ]

ማንኛውም ሰው ሕይወት በአንድ ነገር ግፊት ይመራል። ብዙ መዝገበ ቃላት «አንቀሳቀሰ» ለሚለው ግሥ፦ መራ፤ ተቆጣጠረ ወይም አቅጣጫን ወሰነ» የሚል ፍቺ ይሰጡታል። መኪናም ነዳህ፤ ሚስማር በመዶሻ መታህ ወይም ኳስ አንከባለልህ፤ በዚያን ወቅት ያንን ነገር እየመራህ፤ እየተቆጣጠርክና አቅጣጫውን እየወሰንክ ነው። ታዲያ ልክ እንዲሁ ሕይወትህን የሚመራው ኃይል ምንድነው?
   በአሁኑ ጊዜ በአንድ በሆነ ችግር በሆነ ጫና፤ ወይም ማለቅ ያለበትን ሥራ ለመጨረስ በጥድፊያ በመራመድና በመንቀሳቀስ ላይ ትገኝ ይሆናል። በክፉ ትዝታ፤ በአስበርጋጊ ፍርሃት ወይም በቅጡ ባልገባህ አንድ ኅሊናዊ እምነት ትመራ ይሆናል። ሕይወትህን ሊያንቀሳቅሱና ሊመሩ የሚችሉ ብዙ ሁኔታዎች፤ የሕይወት ፋይዳዎችና ስሜቶች አሉ። ቀጥሎ የተዘረዘሩት አምስቱ /5/ በጣም የተለመዱና የታወቁ ናቸው።

1/ ብዙ ሰዎች በበደለኛነት ስሜት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ዘመናቸውን ሁሉ ጸጸትና ቁጭት ከወለደው ሃፍረታቸው ለመሸሸግ ሲሸሹ ይኖራሉ። ቁጭትና ጸጸት የሚመራቸው ሰዎች የትዝታ ተጠቂዎች ናቸው። ያለፈው ሕይወታቸው መጪውን ህይወታቸውን እንዲቆጣጠረው ይፈቅዱለታል። ብዙውን ጊዜ ሳያውቁት የሕይወት ስኬታቸውን እያበላሹ እራሳቸውን ይቀጣሉ። ቃየል ኃጢአትን በሠራ ጊዜ በደሉ ከእግዚአብሔር ህልውና ለየው፤ እግዚአብሔርም እንዲህ አለው፦ «በምድር ላይ ኮብላይና ተንከራታች ትሆናለህ» ዘፍ 4፤12። ይህ ቃል በዘመናችን ያለ ዓላማ በሕይወት ጎዳና የሚንከራተቱ ብዙ ሰዎችን ይገልጣል።
  ምንም እንኳን የዛሬ ኑሯችን የትናንት ውጤት ቢሆንም፤ የትናንት ኑሯችን ግን የዛሬ እስረኞች ሊያደርገን አይገባም። ምክንያቱም እግዚአብሔር ዓላማ ባለፈው ሕይወትህ የሚወሰን አይደለም። እግዚአብሔር ሙሴ የተባለውን ሰው ገዳይ የነበረ ወደ ሕዝብ መሪነት፤ ጌዴዎን የተባለው ፈሪ ደግሞ ወደ ደፋር ጀግና ለውጧቸዋል። በአንተ ቀሪ ሕይወትም እንዲሁ አስደናቂ ነገሮችን ሊያደርግ ይችላል። እግዚአብሔር ለሰዎች አዲስ የሕይወት ጅማሬ በመስጠት የተካነ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል። «መተላለፉ የተከደነለት፤ ኃጢአቱም የተሸነፈችለት እንዴት ብሩክ ነው» መዝ 32፤1

2/ ብዙ ሰዎች በቂምና በቁጣ ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ደረሰብን የሚሉትን ጉዳት ከማስወገድ ይልቅ አቅፈውት ይኖራሉ። የጉዳታቸውን ስቃይ በይቅርታ ከማስወገድ ይልቅ በመደጋገም ያብሰለስሉታል። አንዳንዶቹ ደግሞ ዝም በማለት ንዴታቸውን ውስጣቸውን  «አምቀው» ይይዙታል። የቀሩት ደግሞ የታመቀ ቁጣቸውን «በማፈንዳት» በሌሎች ላይ ያምባርቃሉ። እነዚህ ሁሉ አጸፋዎች ጤናማ ያልሆኑ የማይጠቅሙ ናቸው።
  የአንተ ቂም መያዝ፤ ቂም በያዝክበት ሰው ላይ ከሚያደርሰው ጉዳት ይበልጥ የሚጎዳው አንተን ነው። የጎዳህ ወይም ያስቀየመህ ሰው ድርጊቱን ረስቶ የራሱን ኑሮ እየመራ ይሆናል፤ አንተ ግን ያለፈውን ቂም አምቀህ በመያዝ በብስጭት ትብሰለሰላለህ።
 ልብ በል! ከዚህ በፊት የጎዱህ ሰዎች አልጥል ባልከው የገዛ ቂምህ ካልሆነ በቀር እየጎዱህ ሊኖሩ አይችሉም። ያለፈው ነገርህ አልፏል። ማንም ሊቀይረው አይችልም። በመራርነትህ ራስህን ብቻ ነው የምትጎዳው። በቃ ለራስህ ስትል ካለፈው ተማርና ተወው። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፤ «ሞኙን ሰው ብስጭት ይገድለዋል፤ ቂሉንም ቅናት ያጠፋዋል» ኢዮብ 5፤2

3/ ብዙ ሰዎች በፍርሃት ይመራሉ።

   እንዲህ ላሉ ሰዎች የሥጋታቸው ምክንያት ሊሆኑ የሚችሉት ነገሮች በሕይወታቸው ያሳለፉት አስፈሪ ጉዳት በእውነት ላይ ያልተመሠረተ ምኞትና ጉጉት፤ ቁጥጥር ባለበት ቤተሰብ ውስጥ ማደግ፤ ወይም በተፈጥሮ የመጣ ፍርሃት ያለባቸው ይሆኑ ይሆናል። ምክንያቱም ምንም ሆነ ምን በፍርሃት የሚኖሩ ሰዎች ድፍረት ከማጣታቸው የተነሳ ሁኔታዎችን ስለማይጋፈጡ ብዙ እድሎች ያመልጧቸዋል። ፍርሃትን በድፍረት ከማሸነፍ ይልቅ ችግር ካለበት ሁኔታ መሸሽንና ባሉበት ሁኔታ ውስጥ መቆየትን ይመርጣሉ።
ፍርሃት እግዚአብሔር ያቀደልህን እንዳትሆን የሚያደርግህና እራስህን ያስገባህበት እስር ቤት ነው። በፍቅርና በእምነት መሣሪያነት ልትጋፈጠው ይገባል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ «በፍቅር ፍርሃት የለም፤ ፍጹም ፍቅር ግን ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል፤ ፍርሃት ከቅጣት ጋር የተያያዘ ነውና፤ የሚፈራም ሰው ፍቅሩ ፍጹም አይደለም።

4/ ብዙ ሰዎች ለመበልጸግ ባላቸው ምኞት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉት ሰዎች የሕይወታቸው ዋና ግብ ሀብት ማግኘት ነው። እንዲህ ያለው ሁልጊዜ ሀብት የመፈለግ ግፊት የሚመነጨው ብዙ ሀብት ሲኖረኝ ይበልጥ ደስተኛ፤ ይበልጥ ታዋቂና ዋስትና ያለኝ እሆናለሁ ከሚል የተሳሳተ አመለካከት ነው። እነዚህ ሦስቱም አስተሳሰቦች ስህተት ናቸው። ሀብት ሊያስገኝ የሚችለው ጊዜያዊ ደስታን ነው። ምክንያቱም ቁሳዊ ነገሮች ስለማይለወጡ ያሰለቹናል። በመሆኑም አዳዲስ ትልልቅና የተሻሉ ነገሮችን እንደገና እንፈልጋለን።
   ብዙ ሀብት ካለኝ ይበልጥ የተከበርኩና ተፈላጊ ሰው እሆናለሁ የሚልና የማይጨበጥ እምነትም አለ። እኛ እራሳችንን የተመንበት ዋጋ ከትክክለኛ ዋጋችን ጋር ተመሳሳይ አይደሉም። ዋጋህ አንተ አሉኝ ከምትላቸው ውድ ነገሮች አይወሰንም። በሕይወት እጅግ ዋጋ ያላቸው ቁሳዊ ነገሮች እንዳልሆኑ እግዚአብሔርም ይነግረናል።
  ስለ ገንዘብ በጣም የተለመደው የማይጨበጥ እምነት ብዙ ገንዘብ ካለኝ በሁሉ ነገር ዋስትናዬ በጣም የተጠበቀ ይሆናል የሚለው ነው። አይሆንም! በተለያዩና ከአቅም በላይ በሆኑ ምክንያቶች ሀብት ወይም ገንዘብ በቅጽበት ይጠፋል። እውነተኛ ድነት ወይም ዋስትና የምታገኘው ፈጽሞ ማንም ሊወስድብህ ከማይቻለው ማለት ከእግዚአብሔር ጋር ካለህ ግንኙነት ነው።

5/ ብዙ ሰዎች በሌሎች ዘንድ ተቀባይነት በመፈለግ ማንነት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ወላጆቻቸው ወይ ልጆቻቸው  ወይ ደግሞ አስተማሪዎቻቸው አለዚያም ሌሎች ወዳጆቻቸው ከእነርሱ የሚጠብቁትን ነገር ለማሟላት የሚያደርጉት ጥረት ሕይወታቸውን እንዲቆጣጠር ይፈቅዳሉ። አንዳንድ ሰዎች ከጎለመሱ በኋላም እንኳን ለማስደሰት አስቸጋሪ በሆኑ ወላጆቻቸው ተቀባይነትን ለማግኘት ይፈልጋሉ። ሌሎች ደግሞ ሰዎች ስለ እነርሱ የሚያስቡት ነገር እያስጨነቃቸው በእኩዮቻቸው ተጽእኖ ይመራሉ። የሚያሳዝነው  ግን ብዙዎችን ለማስደሰት የሚሞክሩ ሰዎች በሂደቱ ራሳቸውን ያጣሉ።
ለስኬት የሚያበቁ ቁልፍ ነገሮችን በሙሉ ባላውቅም ለውድቀት የሚያበቃው ዋነኛ፤ ነገር ግን ሁሉን ለማስደሰት መሞከር ነው። በሌሎች አስተሳሰብ መመራት እግዚአብሔር ለሕይወትህ ያለውን ዓላማ እንድትስት የሚያደርግህ መንገድ ነው። አላስፈላጊ ጭንቀት፤ እርካታ ያጣ ሕይወት ጥቅም ላይ ያላዋልከው ችሎታና ሌሎች ብዙ ነገሮች ሕይወትህን ሊያሸከረክሩት ይችላሉ። ሁሉም ግን የትም የማያደርሱ ናቸው።

ማጠቃለያ፤

ከላይ የተዘረዘሩትን አስወግደህ በዚህ ምድር ላይ የምትኖርበትን ዓላማ ያወቅህ ከሆንህ፤
1/ ኑሮህን እያጨናነቅህ አትመራውም።
2/ ትኩረት ማድረግ የሚገባህን ለይተህ ታውቃለህ።
3/ ለዓላማህ ትጋት ትቆማለህ።
4/ ለዘላለም ሕይወት ዋጋ ትሰጣለህ።
5/ የዚህ ዓለም መሪህ፤ አሳብህ ወይም የሌሎች ጫና ሳይሆን እግዚአብሔር ብቻ እንዲሆን ትፈቅዳለህ።


ስለሆነም በዚህ ምድር ላይ የምትኖረው ለምን እንደሆነ አስቀድመህ እወቅ! የምትኖረው እንደሰው በልተህና ጠጥተህ ቀንና ሌሊትን በማንነትህ ላይ እያፈራረቅህ ለመኖር አይደለም። ይህንንማ ሌሎች እንስሳትም ያደርጉታል። አንተ ግን በእግዚአብሔር ዓላማ የተፈጠርክ፤ ለእግዚአብሔር ዓላማ የተሰራህ ነህና በዚህ ዓላማ ላይ ቆመህ መገኘት አለብህ!

በዚህ ምድር ላይ የተፈጠረከው ለየትኛው ዓላማ እንደሆነ ታውቃለህ? እርምጃህን እየወሰንክ ያለኸውስ እንዴት ነው?

Wednesday, June 4, 2014

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ችግር፤ የአንድ ጤናማ ሰው የጤንነት መስተጓጎልን ይመስላል!


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከሚገጥሟት ፈተናዎች ሁሉ ከውስጧ እንደሚነሳው ፈተና የሚከፋ የለም። ቤተ ክርስቲያኒቱ የኢኮኖሚ አቅሟ እያደገና ውጫዊው ተግዳሮቶቿ እየገዘፉ በመጡ ቁጥር የውስጥ ፈተናዎቿ መቀነስ ሲገባቸው በተቃራኒው እንደአዲስ ቤተ ክርስቲያን ከመቼውም ጊዜ በላይ መከራዋ ገዝፎ መልህቅ መጣያ ወደብ እንዳጣች መርከብ በእስራ ምእቱ የአስተዳደር እክል የባህር ማእበል እየተናጠች ትገኛለች። ይህንን ውስጣዊ ፈተና በቅድሚያ አትኩሮ የሚመለከት ዓይን የሌለው ማንም ቢሆን ውጫዊ ተግዳሮቶቿን ለመመከት የሚያስችል አቅም በምንም ተአምር ሊኖረው አይችልም። ስለሆነም ውስጣዊ ፈተናዎቿን ለይቶ በማስቀመጥ ለመፍትሄውም መንገድ ማስቀመጥ ተገቢ ይሆናል። በዚሁ መሠረት ተለይተው መቀመጥ የሚገባቸውን አንኳር ችግሮች እንደታየን መጠን ለማስቀመጥ ወደድን።

ዋና ዋና ችግሮቿ፤

1/ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የሚችል በእውቀት፤ በልምድና በችሎታ የዳበረ ላዕላይ መዋቅር አለመኖሩ፤

2/ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ፤ ደንብና መመሪያ ጤናማ ሥራ የሚያሠራ ካለመሆኑም በላይ እንደአስፈላጊነቱ አለመሻሻሉ፤


3/ በልምድ፤ በባህልና በትውፊት እንጂ በወንጌል እውነት የታነጸና ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው ተከታይ ትውልድ መቅረጽ አለመቻሉ፤


በዋናነት የሚቀመጡ ናቸው ብለን እንገምታለን። ይህ ማለት አጠቃላይ ችግሮች እነዚህ ብቻ ናቸው ማለት ሳይሆን ዘርፈ ብዙ ችግሮቿ መነሻ የሚያደርጉት እነዚህ ሦስት ዐበይት የአንድ ሰው የሕይወት እስትንፋስን የማግኘት ያህል ህልውና ያላቸው ነጥቦች ናቸው የሚል እምነት አለን።
አንድ ሰው ሕልውና አለው የሚያሰኘው ነፍስና ሥጋው ሲዋሃድ ነው። ሥጋውም ሕይወት አለው የሚባለው አእምሮው፤ አጥንትና ጅማት ከውስጥ ሕዋሱ ጋር ተገቢ ሥራውን ማከናወን ሲችል መሆኑ ይታወቃል። ከዚህ ተነስተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ ሕይወት እንዳለው ሰው ለመቁጠር የሚያስችለን የቁመና መለኪያችን ዋና ዋና ችግሮች ከላይ በሦስት ልየታ ያስቀመጥናቸው ነጥቦች ናቸው። እንዴት? የሚለውን ቀጥለን እንመልከት።

1/ «ቤተ ክርስቲያኒቱ ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የሚችል በመንፈስ፤ በእውቀት፤ በልምድና በችሎታ የዳበረ ላዕላይ መዋቅር አለመኖሩ» የሚለው የጉድለት ነጥብ የአንድን ሰው የአእምሮ አስተሳሰብ ይወክላል። ሰውን ከሌላው እንስሳ የሚለየው ይህ አእምሮና ከአእምሮው የተያያዘው የጀርባው አጥንት በሚያስተላልፉት ኅብለ ሰረሰራዊ መዋቅር የተነሳ ነው። አእምሮ ካልሰራ ሰው ሊያሰኝ የሚችለውን የማንነት መገለጫዎችን ለመሥራት አይችልም። ስለዚህ በዚህ ደረጃ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአእምሮ ማዕርግ የተቀመጠው «ቅዱስ ሲኖዶስ» የሚባለው ክፍል ነው። ይህ ላዕላይ መዋቅር ህልውና እንዳለውና ምሉዕ ሰው ሊሰራ እንደሚገባው እንደባለ አእምሮ መስራት ካልቻለ ሌላው የሰውነት ክፍል በተገቢው መንገድ ሊሰራ አይችልም። ይህ የአንድ ጤናማ ሰው ዋና ማዕከል የሆነው አእምሮ በዚህ ሰዓት በተገቢው መንገድ እየሰራ አይደለም። ስለዚህ አካል የሆነችው ቤተክርስቲያን እክል ገጥሟታል ማለት ነው። እክሎቹ በምን በምን ይገለጻሉ? የሚለውን ጥያቄ በሌላ ጽሁፍ እንመለስበታለን። በጥቅሉ ግን እዚህ ላይ ማስገንዘብ የምንፈልገው ነገር አንድ ጤናማ ሰው እንዳለው አእምሮ መስራት ያለመቻል ችግሮች ነጸብራቅ የሚመሰለው «ቅዱስ ሲኖዶስ» ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ አለመቻሉና የመንፈሳዊነት ብቃት፤ የእውቀት፤ የልምድና የችሎታ ጉድለት ስለሚታይበት የቤተ ክርስቲያኒቱ አእምሮ ችግር ላይ መሆኑን እንረዳለን ማለት ነው። አእምሮ ካልሰራ፤ ሰው ጤናማ ሊሆን አይችልም። ይህ አእምሮና የኅብለ ሰረሰር መዋቅሩ የሚታከመው እንዴት ነው? ጤናማ ካልሆነ ቤተ ክርስቲያን ታማለች ማለት ነው።

2/  «የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ፤ ደንብና መመሪያ ጤናማ ሥራ የሚያሠራ ካለመሆኑም በላይ እንደአስፈላጊነቱ አለመሻሻሉ» የሚለው ነጥብ ምሳሌነቱን ወስደን ለአንድ እንደ ባለአእምሮ ጤናማ ሰው ግዘፈ አካል ብንወስድና ብንተረጉመው የሰውየውን ሥጋ የውስጥ አካሎቹን ያሳየናል። ሕግ፤ ደንብ፤ መመሪያና ሌሎች የማስፈጸሚያ ስልቶች ማለት «ልብ፤ ኩላሊት፤ ጉበት ወዘተ» ውስጣዊ የዝውውር ሕዋሳትን ይወክላል። ጤናማ አእምሮ የሌለው ሰው ካለበት ችግር በተጨማሪ ከእነዚህ ውስጣዊ አካላቱ ውስጥ በአንዱ ላይ ሌላ እክል ካለበት የሕመሙን መጠን የከፋ ያደርገዋል። ስለዚህ ሲኖዶሱ እንደባለ አእምሮ ፤ አእምሮውን ማሠራት አለመቻሉ እንዳለ ሆኖ በላይ የሰው ልጅ የሕልውና ክፍሎቹ እንደሆኑት የውስጥ አካላቱ ተጨማሪ እክል ዓይነት የሕግ፤ የደንብ፤ የመመሪያ ወይም የማስፈጸሚያ ስልቶች ዓይነትና መጠን ተገቢ የሥራ እንቅስቃሴ ማድረግ የሚያስችል ካልሆነ በሽታው አደገኛ ሁኔታ ውስጥ መሆኑን ለመረዳት አይከብድም። ከአእምሮው ላይ በተጨማሪ ከውስጥ ክፍሎቹ ባንዱ ላይ ችግር የገጠመውን አንድ ሰው እስኪ በዓይነ ልቡናዎ ይሳሉና ይመልከቱ! እጅግ አሳዛኝና አስጊ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኝ ለመረዳት የሚከብድዎ አይመስለንም። ቤተ ክርስቲያን አእምሮውን በታመመ አመራር ስር መሆኗ ሳያንስ ስራዋን በተገቢውን መንገድ የሚያስኬድላት የውስጥ አካላቷን መጠበቂያ ማዕቀፍ አለመኖሩ የችግሯን ውስብስብነት የሚያሳይ ይሆናል።

3/ በልምድ፤ በባህልና በትውፊት እንጂ በወንጌል እውነት የታነጸና ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው ተከታይ ትውልድ መቅረጽ አለመቻሉ፤ የሚለውን ደግሞ የአንድ ምሉዕ ሰው ወሳኝ የክፍል እንቅስቃሴ ምሳሌያዊ መገለጫ አድርገን ብንወስደው  ደም፤ አጥንት፤ ጅማትና ቆዳን ይወክልልናል። ሰውየው ግዘፍ እንዲነሳ የሚያደርጉት፤ እንቅስቃሴውን የሚወስኑትና የዑደት ዝውውሩን የሚያገናኙት እነዚህ ዋና የሰውነት ክፍሎቹ ናቸው። ቤተ ክርስቲያን ስንል የክርስቶስ ጉባዔ ምዕመናን ማለታችን እንደመሆኑ መጠን ለቤተ ክርስቲያን ኅልውና ደም፤ አጥንት፤ ጅማትና ቆዳ ሆኖ ያስተሳሰረው ይህ የመዘወሪያ አካል ንጹህ፤ ያልተበከለ፤ ያልተጣመመና ጤናማ የህንጻ ክፍል ካልሆነ ጉባዔ ቤተ ክርስቲያን ጤናማ ልትሆን በጭራሽ አትችልም። በነዚህ መሠረቶች ላይ የቆመው አካላዊ ህልውና የዝውውር ዑደቱ ከፈጣሪው በተቸረውና እፍ በተባለበት የሕይወት እስትንፋሱ በኩል አምላኩን በተገቢው ሊያመሰግን አለመቻሉ ጉባዔው የሚታወክ፤ የሚታመስ፤ በወሬ በሽታ የተጠመደ ይሆናል። በእድሜው መኖር በመቻሉና ነፍስያው አለመለየቷ ብቻውን አንድን ሰው ሕያው ሰው አያሰኘውም። በመንፈሱ የሞተ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ የለውም።
«በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና» ሮሜ 8፤14
በዚህም የተነሳ ጉባዔ አክሌሲያ እንደሆነ የሚታሰበው ትውልድ በልምድ፤ በባህል፤ በትውፊት ገመድ ተጠፍንጎ ከወንጌል እውነት ሳይታረቅና ፈሪሃ እግዚአብሔርን በልቡናው ሰሌዳ ላይ ሳይጽፍ ነገር ግን አንገቱ ላይ የመስቀልና ምስል አንጠልጥሎ የሚሳደብ፤ የሚዋሽ፤ የሚሰክር፤ የሚያጨስ፤የሚያመነዝር፤ የሚሰርቅ፤ እምነት የማይጣልበት የባህል እምነት ተከታይ ሆኖ የሚታየው የእውነትን ወንጌል በመጋት አሳድጎ የቃሉን አጥንት መጋጥ ወደሚያስችል ሰውነት ማድረስ ስላልተቻለ ነው። በእምነት ሳይሆን በሃይማኖት የኖረውም በልምድ እንጂ እውነት ስለገባው አይደለም።  «እውነት ባለበት በዚያ አርነት አለ» የተባለው አንገት ላይ መስቀል አንጠልጥሎ ነገር ግን ነጻ እንዳልወጣ ሰው የሥጋ ሥራ የሚሰራ ሰው ማለት አይደለም። ስለዚህ ትውልዱ በወንጌል ነጻ የመሆን የእውነት ቃል ተኮትኩቶና በቀደምት አባቶቹ አስተምህሮ ታንጾ ባለመኖሩ አርነት ያልወጣ ሰው የሚያደርገውን የሥጋ ሥራ እየፈጸመ  በስም ክርስቲያን እየተሰኘ የባህልና የልምድ ተከታይ ሆኖ እንዲኖር ተፈርዶበታል።  ከልምድና ከባህል መንፈስ ነጻ መውጣት አለበት።
2ኛ ቆሮንቶስ 3፥17  «ጌታ ግን መንፈስ ነው፤ የጌታም መንፈስ ባለበት በዚያ አርነት አለ»

ማጠቃለያ፤

አንድ ሰው ጤናማ የሚባለው አእምሮው፤ ኅብለ ሰረሰሩ፤ የውስጥ አካላቶቹ፤ ደም፤ ስጋ፤ አጥንትና ጅማቱ ተዋሕደው በጤንነት ሲገኙ ነው። ምሉዕ ሰው ሆኖ ሕይወት ያለው መንፈሳዊ ጤንነቱ የሚጠበቀው ደግሞ የነፍስያው ራስ የሆነው ፈጣሪውን ሲያውቅና በተገቢው መንገድ ሲያመልክ ብቻ ነው። ከእነዚህ ባንዱ ጉድለት ቢገኝ አደጋ ውስጥ መሆኑ እርግጥ ነው። ከዚህ ተነስተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችንን የሕይወት ኅልውና ስንመለከት ጤናማ ሁኔታ ውስጥ እንዳይደለች ከላይ ያነሳናቸው ነጥቦች ያስረዱናል። የተከታዮቿ ቁጥር ወደታች የማሽቆልቆሉ ምክንያት የበሽታውን ደረጃ ያሳየናል። የአስተዳደር ሰላም አለመኖር፤ የነበራት ክብርና ተደማጭነት ማነሱም የገጠማት የህመም ደረጃ አደገኛ መሆኑን ያስረዳናል። የመከፈፋሏ መነሻ፤ የመከባበር ድቀት፤ የነውር ገመና ማደግ፤ ዋልጌነት፤ የብክነትና የዝርፊያው የትየሌለነት የበሽታዋ ደረጃ ምን ያህል እንደገዘፈ ለማወቅ ምርምር አይጠይቀንም። ቤተ ክርስቲያኒቱ ያልጠፋችውም ከእግዚአብሔር ታጋሽነትና ለንስሐ የሚሆን እድሜ ከመስጠት አምላካዊ ባሕርይው የተነሳ ይመስለናል። እንደሚገባን ሆነን መልካም ፍሬ ካላፈራን ግን መቆረጣችን አይቀርም።
የፈለገውን ያህል ተኩራርተን የቀደመችቱ መንገድ እያልን ብንደሰኩር ከእግዚአብሔር አስቀድሞ የተቀበልነውንና የሰማውን ዛሬ ይዘን በተግባር ካልተገኘን ከያዝነው የቁልቁለት መንገድ አያድነንም።  በአንድ ወቅት በትንሹ እስያ ለነበረችውና በተመሳሳይ የቁልቁሊት መንገድ ላይ ለነበረችው ለሰርዴስ ቤተ ክርስቲያን በዮሐንስ በኩል መልእክት ደርሷት ነበር።  ነገር ግን መስማት ስላልቻለች እየወረደች ካለበት የቁልቁሊት መንገድ ወጥታ፤ ስህተቶቿን አርማ፤ በእውነት የጌታዋ መንገድ ላይ ለመጓዝ የሚያስችላትን የንስሐ እድሜ ባለመጠቀሟ ከ500 ዓመት በኋላ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመጥፋት በቅታለች። በፍርስራሾቿ ላይም የእስልምና አዛን የሚያስተጋባባት የታሪክ ቤተ ክርስቲያን ሆናለች። ከመሆኗ በፊት የተነገራት ቃል ይህ ነበር።
«እንግዲህ እንዴት እንደ ተቀበልህና እንደ ሰማህ አስብ፥ ጠብቀውም ንስሐም ግባ። እንግዲያስ ባትነቃ እንደ ሌባ እመጣብሃለሁ በማናቸውም ሰዓት እንድመጣብህ ከቶ አታውቅም» ዮሐ 3፤3
( በቀጣይ ጽሁፋችን  ዝርዝር ነገሮችን ለማየት እንሞክራለን)