Showing posts with label ታሪክ. Show all posts
Showing posts with label ታሪክ. Show all posts

Sunday, February 16, 2014

ዕርቅና ሰላም፤ የሕይወት ቅመም


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እንደውለታ ቢስ ለሚቆጥሩ ወገኛ ሁሉ መልስ የሚሆን ጽሁፍ እነሆ!
በፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ 
 
   አንድ ጥናት ሳነብ፥ ምናልባት እናንተም አንብባችሁት ይሆናል፥ የተፈጥሮ ሀብት ባላት ሀገር ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች ከተራቡ፥  የማሰብ ችሎታቸው ዝቅተኛ ቢሆን ነው ሲል አገኘሁት። "ጥልቀት የሌለው ረጋ-ሠራሽ ጥናት ነው" ብዬ ጣልኩት። ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ሀብት ባለጠጋ መሆኗን እርግጥ ባለሞያዎች የመሰከሩት ነው። ማዳበሪያ የማያስፈልገው መሬት ታርሶ አያልቅም። የወንዞቿ ውሀ ለጎረቤት አገሮች ሳይቀር ይተርፋል። ይኸንን እውነታ በቀጥታ ከተመራማሪዎቹ  አፍ ለመስማት የፈለገ ፕሮፌሰር ስዩም ገላየን ማዳመጥ ይችላል።  
   እንዲህ ከሆነ፥ ትኩረቱ በኢትዮጵያውያን የማሰብ ችሎታ ላይ ሊሆን ነው። እውነት የኢትዮጵያ ሕዝብ ተመጽዋች ሆኖ የቀረው የማሰብ ችሎታው ዝቅተኛ ሆኖ ነው? አይመስለኝም።  ሰውየው ጥናቱን ማስተካከል አለበት። አለዚያ፥ ከዚያ ቀጥሎ፥ "አንድ ሰው እሱቁ ውስጥ ከመስተዋቱ በስተኋላ ድፎ ዳቦ እያየ ከተራበ የአስተሳሰብ ችሎታው ዝቅተኛ ቢሆን ነው" ሊለን ነው። ምንም ከፍተኛ የማሰብ ችሎታ ቢኖረው፥ ዳቦውን እንደማያገኘው ለማንም ግልጽ ነው። 
  እርግጥ ነው፥ በአስተሳሰብ ደከም የሚል ሰው ሊጎዳ ይችላል። ሌላው ቢቀር፥ የብልሁ ጓደኛውን ያህል አይደላውም።  ግን በከፍተኛ ደረጃ የማሰብ ችሎታ ያለው ሰውም ሊቸገር ይችላል።  ስንቶች ናቸው ኢትዮጵያ ውስጥ በችግር የሚኖሩ፥ መውጫ ቢያገኙ ግን ለሌላው ሳይቀር የሚተርፉ? በአፍሪካ፥ በአውሮፓ፥ በአሜሪካ ዩኒቨርስቲዎች ውስጥ በማስተማርና በምርምር ላይ ያሉ ኢትዮጵያውያን ቊጥር ቀላል አይደለም። በንግዱ ዓለምም ቢሆን፥ "የሺ ብር ጌቶችን" ጓዳ ይቊጠራቸው። 
የለም፥ የተፈጥሮ ሀብት ባለጠጋ የሆነች ኢትዮጵያ ብልሁ ሕዝቧ ለምን እንደሚራብ የተከበረ ጥናት መደረግ አለበት። ዋና ዋናዎቹን ምክንያቶች ፕሮፌሰር ስዩም ገላየ ደርድሯቸዋል። አንዱ፥ የመሬት ይዞታ መበላሸት ነው ይለናል። "የመሬት ላራሹ" ጩኸት ውጤቱ "መሬት ለነጋሹ" ሆኗል፤ ለገበሬው የታሰበውን መሬት ወያኔ ወሰደው። የዱሮ ንጉሣዊ ገዢዎቿ ቤተ ሰቦች ስለነበሩ በቊጥራቸው ማነስ ምክንያት እነሱን በማር ግብር ለማጥገብና በሰላም ለመኖር ቀላል ነበረ። የዛሬዎቹ ገዢዎች ብሔረ ሰቦች ስለሆኑ እነሱን ሁሉ በሚሊዮን ዶላር ማጥገብ መራቆትን አስከትሏል። ሌላው፥ አገሪቱ በክልል መከፋፈል ነው። ማንም ሰው በገዛ ሀገሩ ከመሰለው ክፍለ ሀገር ሄዶ በሰፊው ማረስ አይችልም። ዛሬ ኢትዮጵያ ለአንድ ኢትዮጵያዊ ሙሉ በሙሉ አገሩ አይደለችም። ኢትዮጵያ ለልጆቿ እናትነቷ በሙሉ ሰውነቷ እንዳይሆን ተከልክላለች። 
 የታሪክ ተመራማሮዎችም ያዩት ምክንያት ይኖራቸዋል። ክርስቲያኖችና እስላሞች፥ ኦሮሞዎችና ሌሎች መሆናችንን ዐውቀን በብልህነት አለማስተናገዳችን ጒዳት እንዳመጣብን ይናገራሉ። ሁላችንም የአንድ ሃይማኖት ተከታዮች፥ አንድ ቋንቋ ተናጋሪዎች ብንሆን ኖሮ ከምሰሶ ጋር በእግር ብረት እንደተቈራኘ ሰው እጃችንን ብቻ ወደ እግዚአብሔር እያደረስን አንድ ዘመን ላይ ቆመን አንቀርም ነበር ይላሉ።  
  በሃይማኖት አንድ ባለመሆናችን ያስከተለውን ጕዳት ለማሳየት የአክሱምን ሥልጣኔ ያከሰመውን የጉዲትን አመፅና የአምሐራን ("የአማራን" ማለቴ አይደለም)ሥልጣኔ እሳት የለቀቀበትን የግራኝን ወረራ ይተርካሉ።

እነዚህ ሁለት ሥልጣኔዎች ኢትዮጵያን በዚያ ዘመን ከገነኑ አገሮች እኩል አስሰልፈዋት ነበረ፤ ጠፉ፤ ባለንበት ቆመን ቀረን። 
ዛሬ ስለሁለቱ ሥልጣኔዎች የምናውቀው ከመጥፋታቸው በፊት ከተጻፈው ታሪካቸውና ከጥፋት ካመለጠው  ርዝራዣቸው ነው። ሀገሪቱ ከግራኝ ምች ልታንሰራራ አልቻለችም። የግራኝ ምች የምለው እስላሞች በዓሥራ ስድስተኛው ምእት ዓመት በክርስቲያኖች ላይ ያደረሱትን ጒዳት ነው;ታሪኩን ክርስቲያኖቹ በሐዘን፥እስላሞቹ በደስታ መዝግበውታል፤ ዛሬም በዚያው ስሜት ያስታውሱታል። የደረሰው የሰውና የንብረት ጥፋት ሁሉ የሚያሳዝን ቢሆንም፥ሁልጊዜ የሚታወሱኝ ቅጂ ያልተገኘላቸው ስማቸው ብቻ የቀረልን ብርቅ ድርሰቶች ናቸው።
እስላሞቹ ክርስቲያኖቹን ለማጥፋት ከጂሃድ በቀር ሌላ ምንም ምክንያትአልነበራቸውም። መንግሥቱን ተወደደም ተጠላ ያቋቋሙት ክርስቲያኖቹ  ነበሩ። ከሀገሪቱ ክፍል ሱማሌዎችና ይፋቴዎች እንደሚኖሩባቸው አንዳንድ ክፍሎች ሲሰልሙ፥ በኢትዮጵያ ስር ሆነው ራሳቸውን በራሳቸው እንዲያስተዳድሩ ሙሉ ሥልጣን ተሰጥቷቸው ነበረ። በዛሬው ዓይናችን እንኳ ስናየው፥ የንጉሣዊው መንግሥት ከዚህ የተሻለ ሌላ ምን አማራጭ አገዛዝ ነበረው? የጂሃዱ መንሥኤ ኦርቶዶክሱን ሕዝብ በሞላ አስልሞ በሸሪዓ ሕግ መግዛት  ነበር። 
እስላሞቹ፥ "መንግሥቱን ወስደን፥ ክርስቲያኖቹ ራሳቸውን እንዲያስተዳድሩ እናደርጋለን" ቢሉ እንኳን ያባት ነበር። ኦሮምኛ ተናጋሪዎችና ሌሎች መሆናችን ያስከተለውን ጕዳት ለማሳየት ደግሞ የኦሮምኛ ተናጋሪ ጎሳዎችን ወደማህል ኢትዮጵያ የመፍለስ ታሪክ ይተርካሉ። ለአባ ባሕርይና የዘመኑን ነገሥታት ታሪክ ለጻፉ፥ በተለይም ለተክለ ሥላሴ ጢኖና ለተክለ ኢየሱስ ዋቅጂራ ምስጋና ይድረሳቸውና የኦሮሞ ጎሳዎች ወደማህል ኢትዮጵያ ፍልሰት ያስከተለው የሥልጣኔ ውድመት ከብዙው በጥቂቱ ተመዝግቧል። ኦሮምኛ የሚናገሩ ጎሳዎች የእስላሞቹ አመፅ በተገታ ማግስት ፈልሰው፥ ከእስላሞቹ የተረፈውን የሥልጣኔ ምልክት ጠራረጉት። ጋዳ በሚሉት ሁሉን ለጦርነት በሚያሰልፍ የማፊያ ሥርዓት በውትድርና ተደራጅተው፥ በግብርና፥ በንግድ፥ በድብትርና ("በዕውቀትና በምርምር"ማለቴ ነው) የሚተዳደረውን ሰላማዊ ሕዝብ አረዱት፤ ንብረቱን አወደሙት። በእርሻው፥ በሰብሉ ላይ ከብታቸውን አስሠማሩበት። በባህላቸው መሠረት፥ ክርስቲያን ያልገደለ በቅማል ይሰቃያል እንጂ ራሱን አይላጭም ነበር። ሸዋን፥ ጎንደርን፥ ጎጃምን፥ አምሐራን (የዛሬውን ወሎ) ደመሰሷቸው።  
እስላሞቹ የክርስቲያኖቹን ሥልጣኔ አጥፍተው በራሳቸው ሥነ ጽሑፋዊ ሥልጣኔ ሊተኩት አስበው ነበረ። ኦሮምኛ ተናጋሪዎቹ ግን እረኞች ስለነበሩ ሥልጣኔን በሥነ ጽሑፋዊ ሥልጣኔ የመተካት ግዴታ አልነበረባቸውም። ግን በባህል ረገድ ከወረሩት ሕዝብ አብዛኛውን እንደነሱ ኦሮምኛ ተናጋሪ፥ የቀረውን ገበር (አሽከር) አደረጉት። እስላሞቹና ኦሮምኛ ተናጋሪዎቹ ሰውና ቅርስ ባወደሙበት ቦታ ሁሉ ሐውልት ቢቆም ሀገሪቱ "ሀገረ ሐውልት" ትሆን ነበረ።  
  ከግድያቸው ሰለባቸው ይብስ ነበረ። ባለቅኔው፥ "ጃዊ ቀደደ ሆድ ሆድሆዶሙ ወሰለቦሙ እስከ ሕምብርት" (ጃዊ ሆድ ሆዳቸውን ቀደደው፤ እምብርታቸው ድረስ ሰለባቸው) ያለው በጎንደር ዘመነ መንግሥት የደረሰውን መቅሠፍት አይቶ ነው። የሆነውን በታሪክ ዓይን አይቶ በማለፍ ፈንታ፥ ዛሬ አቻው እንዲሆን ታስቦ ያልሆነ፥ ያልተደረገ የአረመኔነት ታሪክ ለራስ ጎበና ዳጨ ወታደር መፍጠር፥ ግፋ ቢል ሞኞችን በሞኝነታቸው እንዲኖሩ ከማድረግ የበለጠ አገልግሎት አይኖረውም። ውሸት ታሪክ አይሆንም።  
  ማንም መጥቶ ኢትዮጵያ ውስጥ ቢሰፍር የኢትዮጵያ ነገሥታት አይከለክሉም ነበር። ሰው የሌለበት ሰፊ ቦታ ስለሞላ ማንም ከዚያ ቢሰፍር ማን ነህ የሚለው አልነበረም። ችግሩ፥ ኦሮምኛ  ተናጋሪ ጎሳዎች ከአንድ ቦታ ፈልሰው ከባዶ ቦታ በመስፈር ፈንታ፥ ሌሎች ያቀኑትን ቦታና ያተረፉትን ቅርስና ውርስ እንንጠቅ ማለታቸው ነበር። በዚያ ላይ፥ ማህል ኢትዮጵያን ከያዙ በኋላ፥ ለኢትዮጵያ መንግሥት አንገብርም ማለትን አመጡ። በዚህ ጊዜ የንጉሣዊው መንግሥት ምርጫ ምን መሆን ነበረበት?  

  
ያምናው በሽታ፤ 

  በዚህ እኛ ባለንበት ዘመን፥ እስላሞች ቤተክርስቲያን ሲያቃጥሉ፥ አንዳንድ ኦሮምኛ ተናጋሪዎች ሰላማዊውን ሰው በሕይወት ገደል ሲሰዱ፥ በ ዩቲዩብ  (youtube) ሳይ፥ ሰውየው፥ "ኧረ እናንተ ሰዎች ሰው አይድንም ታሞ፤ ያምናው በሽታየ አገረሸ ደግሞ፡" ያለው ትዝ አለኝ። በሽታውን ማስገርሸት አንዱን ጠቅሞ ሌላውን አይጐዳም። ሁሉም ተጐጂ ነው የሚሆነው። ሁል ጊዜ ሳይሞቱ መግደል አይቻልም። 
ሌላውን የሚገድሉት እየሞቱ ነው። በዚያ ላይ በማህል ቤት የሚሆነውን ማንም አያውቀውም። ለምሳሌ፥ የኦሮሞን አመፅ ይመሩ የነበሩ የወለጋ ፕሮቴስታንቶች እንደነበሩ ይታወሳል። አሁን አመፁን ከነሱ ተቀብለው በኦሮሞ ስም የሚያካሂዱት፥ "ከኦሮሞው ሕዝብ አርባ በመቶው እስላም ነው" የሚሉ የኦሮሞ እስላሞች ናቸው። ቊጥራቸውን ቢያጋንኑትም፥ እስላሞቹ ከፕሮቴስታንቶቹ መብለጣቸው አያጠራጥርም።  እንግዲህ፥ የፕሮቴስታንት ክርስቲያኖች በኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች መንግሥት  ላይ  ያካሄዱት ትግል በፍትሐ ነገሥት ቀርቶ በሸሪዓ ሕግ በሚያምኑ ወገኖች ለመተዳደር ሊሆን ነው።  የግብጽ ክርስቲያኖች የመለካውያን ክርስቲያኖችን የበላይነት በመጥላት አገሪቷን ዐረቦች እንዲወስዷት ረድተው፥ ዋጋ ከሌለው ጸጸት ላይ እንደወደቁ የምናየው ነው። 


 የመጀመሪያው እርምጃ፤ 

ከላይ እንደገለጥኩት፥ እስላሞችና ኦሮምኛ ተናጋሪ ጎሳዎች ኢትዮጵያን እንዴት እንዳቈረቈዟት ታሪኩ እንዳይፋቅ ሆኖ ተጽፏል፤ የሚፈለገው ግን ዕርቅና ሰላም እንዲወርድ ነው።ዕርቅና ሰላም የሚወርድ ከሆነ፥ታሪኩ ባይፋቅም ተከቶ ከድንቊርናና ከረኀብ የምንላቀቅበትንና ከፍተኛ የማሰብ ችሎታ እንዳለን የምናስመሰክርበትን ብልሀት ልንፈልግ እንችላለን።ለዚህም መሆን ያለበት የመጀመሪያው እርምጃ አባቶቻችንን እንወክላለን የሚሉ እስላሞችና ኦሮሞዎች የአባቶቻቸውን ጥፋት ከመቀጠል አባቶቻችው በኢትዮጵያ ላይ ላደረሱት መጠን አልባ ጥፋት የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ መጠየቅ ይሆናል። 
የጥፋቱን ታሪክ ጸሐፊዎቹ ለወገኖቻቸው እያዳሉ ጽፈውታል እንዳይሉ፥የጻፉት ራሳቸው እስላሞቹ እነሽሀብ እዲን ዐረብ ፈቂህ፥ የአማራውና የኦሮሞ ተወላጆች እነ አባ ባሕርይ፥ እነ ተክለ ሥላሴ ጢኖ፥ እነ ተክለ ማርያም ዋቅጂራ ናቸው። ታሪካችንን ደብተራዎች አይጽፉትም የሚሉ ካሉ፥ የጸሐፊዎቹን ማንነት ባለማወቅ ሊሆን ይችላል። የሌሎችም ታሪክ ጸሐፊዎች ስማቸውና ሥራቸው "የአባ ባሕርይ ድርሰቶች፤ ኦሮሞችን ከሚመለከቱ ሌሎች ሰነዶች ጋራ"  በተባለው መጽሐፌ ውስጥ ተዘርዝሯል።  ይህን መጽሐፍ ብዙ ሰው ስለሚፈልገው፥ ማንም ሰው  እያወረደና እያተመ  እንዲያነበው በማሰብ፥ www.ethiopiawin.net or www.ethiopiawin.org  ብለን ካቋቋምነው ድረ ገጽ ላይ ተለጥፏል። ኢትዮጵያን ለማገልገል ላቋቋምነው ድርጅት እርዳታ የሚሆን በፈቃድ ከሚሰጥ ገንዘብ በቀር የመጽሐፉን ዋጋ አንጠይቅም።  

ሁለተኛው እርምጃ፤ 

ሁለተኛው እርምጃ ኦሮምኛ ተናጋሪዎችን የሚመለከት ነው፤ አፄ ምኒልክና ራስ ጎበና ዳጨ ስፍር ቊጥር በሌለው ጎሳ የተበታተኑትንና እርስ በርሳቸው የሚባሉትን ኦሮምኛ ተናጋሪዎች አንድ ያደረጉበትን ቀን በየዓመቱ ማክበር አለባቸው። ግን ሁሉንም አንድ ያደረጉት በአንድ ቀን ድል ስላይደለ፥  የትኛውን ቀን እንደሚያከብሩ በጨፌያቸው ሊወስኑት ይችላሉ። ሆኖም በአፄ ምኒልክ ሐውልት ስር አበባ ማስቀመጥ የበዓሉ ክፍል መሆን አለበት። ራስ ጎበና ሐውልት ስለሌላቸው፥ ሳይውል ሳያድር ከተከበረ አደባባይ ላይ የጎላ ሐውልት እንዲተከልላቸው ባለውለታዎቹ መገፋፋት ይኖርባቸዋል።        

ሶስተኛው እርምጃ 

ሶስተኛው እርምጃ አስተሳሰብን ከሰብአ ትካት አስተሳሰብ ወደ ሰብአ ዘመን አስተሳስብ ማራመድ ነው። '"ሰብአ ትካት" በእንግሊዝኛ  primitive people የሚባሉት ናቸው። አስተሳሰባቸው ከመንደራቸው ርቆ አይሄድም፤ የዚያኛው መንደር ሰው ጠላታቸው ነው፤ የዚያኛው ብሔረ ሰብ አባል ባለጋራቸው ነው። "ሰብአ ዘመን" modern man ነው። መንደሩ ጠቅላላዋ ሀገር ነች። በሰብአ ዘመን አስተሳሰብ የዚያ መንደር ወይም የዚህ መንደር ነባር መሆንና የዚያ ቋንቋ ወይም የዚህ ቋንቋ ተናጋሪ መሆን ዋጋ ሊሰጠው የማይገባ አጋጣሚ ነው። የሰብአ ዘመን አስተሳሰብ ከዚያም መጥቆ ሄዶ ዓለም አቀፍ ላይ ይድርሳል። በሰብአ ትካት አስተሳሰብ ያሉ ብሔርተኞችን በአንድ ጊዜ ወደዓለም አቀፍ አስተሳሰብ ይሸጋገራሉ ብለን አንገምትም፤ ለጊዜው ፍላጎታችንም አይደለም። ግን በሰላምና በብልጽግና ለመኖር ከብሔርተኛነትና ከሰብአ ትካት አስተሳሰብ ወጥቶ ዲሞክራት መሆን አማራጭ የሌለው እርምጃ ነው። በአካል የሰብአ ዘመን አባል ሆኖ በአስተሳሰብ ሰብአ ትካት መሆን፥ "የሚራቡት የማሰብ ችሎታቸው ዝቅተኛ ቢሆን ነው"  ለሚለው ጥናት ማስረጃ መሆን ነው። እንደማየው፥ ብሔርተኞች ከዲሞክራሲ ጋር ያላቸው ግንኙነት በፍቅርና በጥላቻ የተሳሰረ ነው። የዲሞክራሲ ዋና መለዮ ሰብአዊ መብቶችን ማስከበር ነው። በአሁኑ ሰዓት ከገዢዎቹና ከደጋፊዎቻቸው በቀር ይኸንን የማይቀበል ያለ አይመስለኝም። እዚህ ላይ ብሔርተኞችና ዲሞክራሲ ፍቅረኞች ናቸው። ግን  ሰብአዊ መብቶች የሚባሉት የግለሰብ ብቻ ናቸው ወይስ ማኅበሮችና ብሔረ ሰቦችም ሰብአዊ መብቶች አሏቸው? የላቸውም ከተባለ፥ ብሔርተኞች ዲሞክራሲን አይቀበሉም።  

መብት በመሠረቱ የግለሰብ ነው። ሆኖም ብሔረሰቦች በደፈናው መብት የላቸውም አይባልም። አቅም ካላቸው ቋንቋቸውንና ሌላ ሌላ ባህላቸውን ማዳበር መብታቸው ነው። ይኸንን በሥራ ላይ ለማዋል ሲሰበሰቡ ጸጥታቸውን መንግሥት ያስከብርላቸዋል። የአንድ ሀገር ሕዝብ ሆኖ ብሔረሰባዊ  ፓርቲ መመሥረት ግን ከሌላው ብሔረ ሰብ ጋር የጋራ ጥቅም የለንም ማለት ይሆናል። የፓርቲ መሠረቱ የግለሰብን ሕይወት በኢኮኖሚ እድገት ማሻሻል ነው። ለዚህ ዓላማ ፓርቲው ጉራጌ፥ አደሬ፥ ጉጂ፥ ወዘተ መሆን የለበትም።  ሆኖም፥ የብሔረሰብ አባላት በይፋ አድመው ድምጻቸውን ይጠቅመናል ለሚሉት ፓርቲ ሊሰጡ ይችላሉ። በዲሞክራሲ አስተዳደር ብሔርተኞች ብሔራቸውን የሚጠቅሙት በዚህ መንገድ ብቻ ነው።            
 
 

Wednesday, December 4, 2013

አይ አበሻ! አበሻና ሆድ!

 
አይ አበሻ! አበሻና ሆድ፤
Posted on
by መስፍን ወልደ-ማርያም (Mesfin Wolde-Mariam)
ጥቅምት 2006


አበሻ ድግስ ይወዳል፤ ድግስ የሚወደው መብላትና ማብላት ስለሚወድ ነው፤ ለመብላት የአበሻ ምክንያቱ ብዙ ነው፤ ልጅ ተወለደ ብሎ መብላት ነው፤ ልጅ ክርስትና ተነሣ ብሎ መብላት ነው፤ ልጅ አገባ ብሎ መብላት ነው፤ ልጅ ሞተ ብሎ መብላት ነው፤ አበሻ ሰው ቀብሮ ሲመለስ በንፍሮ ይጀምርና ቀስ በቀስ ወደሌላው ይተላለፋል።
ሃይማኖትም ቢሆን ለመብላት ካልሆነ የነፍሱ ጉዳይማ በጣም ሩቅ ነው፤ ሕያዋን ለነገሥታት፣ ሙታን ለካህናት ይገብራሉ፤ በሚለው መመሪያ መሠረት
ግብር መቀበል ያለ ነው፤ ክርስቶስ ተወለደ መብላት ነው፤ ክርስቶስ ተጠመቀ መብላት ነው፤ ክርስቶስ ሞተና ተቀበረ መብላት ነው፤ ክርስቶስ ተነሣ መብላት ነው፤ ማርያም አረገች መብላት ነው።
ማኅበርም የሚጠጣው (የሚበላው ለማለት ነው፤) ለመብላት ነው፤ አምላክ በተለያዩ ስሞቹ፣ ቅድስት ማርያም በተለያዩ ስሞችዋ፣ መላእክት፣ ቅዱሳን፣ ሰማዕታት ሁሉ ለመብላትና ለማብላት ያገለግላሉ፤ ወደመንግሥተ ሰማያት ለመግባት አማላጅ ሊሆኑ የሚችሉ ሁሉ ማኅበር ለመብላት ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ፤ የሌሎች አገሮች ክርስቲያኖች በመብል አይመለሱም፤ ገበያቸው በጠገራ ብር ነው፤ ስለዚህም አብሮ መብላት ብሎ ነገር የለም።
አበሻ የሚበላው የመጣውን ሲቀበል ብቻ አይደለም፤ የሚሄደውን ሲሰናበትም  መብላት ይወዳል፤ ሞትም ቢሆን ለመብላት ምክንያት ነው፤ ቀብር ብሎ እዝን እያቀረቡ መብላት ነው፤ ሠልስት ብሎ መብላት ነው፤ ለሰባት መብላት ነው፤ ለዓርባው መብላት ነው፤ የሙት-ዓመት ደግሶ መብላት ነው፤ በቀብር ላይም  ቢሆን ለቅሶውም ‹‹ሆዴ! ሆዴ!›› ነው።
ለአበሻ ጾምም ቢሆን ለመብላት ነው፤ የጾም ትልቁ ምሥጢሩ ምግብ እንዲናፍቅ ለማድረግ ነው፤ የፍስኩ የተትረፈረፈ ምግብና ጥጋብ ባይኖር ማን ይጾማል? የለየላቸው ጠጪዎች በሁዳዴ መለኪያውንና ብርጭቆውን አርግፍ አድርገው የሚተውት ሲፈሰክ በናፍቆት ዊስኪውንና ቢራውን ለመጋት ነውኮ! ይህ ባይሆን አንድ ጊዜ ሞጣ ያየሁትየበግ ሌባ ለምን ይጦም ነበር? ታሪኩ እንዲህ ነው፤ በሞጣ አውሮጵላን ማረፊያ አንድ የበግ ቆዳ የያዘ ሰውዬ በፖሊሶች ይጠበቃል፤ እንደሰማሁት በግ ሰርቆ ጫካ ይወስድና ቆዳውን ገፎ ለመሸጥ ወደገበያ ሲሄድ ተይዞ ነው፤ የሁዳዴ ጾም ስለነበረ ሥጋውን ለማይጾሙ አውሬዎች ጫካ ውስጥ ጥሎ ነው! አሁን ይህ ሰውዬ የሚጾመው ሲፈሰክ ደህና አድርጎ በናፍቆት ለመብላት ካልሆነ ለሌላ ለምንድን ነው ሊባል ነው?
ሥራም ቢሆን ለመብል ነው፤ ከመኝታው ሲነሣ ጀምሮ እስኪተኛ ቢበላ ደስታውን አይችለውም፤ለገና፣ ለፋሲካ፣ ለእንቁጣጣሽና ለመስቀል ለገናና ለፋሲካ፣ ለእንቁጣጣሽና ለመስቀልም ከሌሊት ጀምሮ ከአንዱ ቤት አንዱ ቤት እየተዘዋወሩ በመብላት ቀኑ ያልፍ የለም እንዴ! በእውነት አበሻ መብላት የሚወደውን ያህል ማብላትም ይወዳል፤ ስሞት! ስቀበር! አፈር ስገባ! … ወዘተ. እየተባባለ የጠገበውን ሰው በቁንጣን እንዲሰቃይ ማድረግ የአበሻ ልዩ የፍቅር መግለጫ ነው! መጎራረስም አለ፤ ፍቅርና ጉርሻ ሲያስጨንቅ ነው እየተባለ ፍቅርና ሆድን ያያይዛል፤ አነጋገሩ አበሻ ለመብላት ያለውን እንጂ ፍቅርን አይገልጽም፤ ማሰጨነቅንና ፍቅርን ምን አገናኛቸው! አበሻ ሌላም ተረት አለው፤ የወለዱትን ካልሳሙለትና የሠሩትን ካልበሉለት ደስ አይለውም ይባላል፤ የልጅ ፍቅር ከምግብ ፍቅር ጋር ተስተካክሎ የቀረበ ይመስላል፤ ደሞም ብቻውን የበላ ብቻውን ይሞታል፤ ይላል፤ ጉድ ነው! ሲሞትም ተከተሉኝ የሚል ይመስላል!! ለነገሩማ ፍቅርምኮ አበሻ ዘንድ ምግብ ነው፤ ሆዴ! አንጀቴ! ጎንደሬዎች ሲያሳምሩት ደግሞ ራቴዋ! ይሉታል።
ዛሬ ዛሬ አበሻ ከማብላት ይልቅ ማጠጣት ይወዳል፤ እስቲ ሰዎች ሰብሰብ ብለው በሚጠጡበት ቦታ ብቅ በሉ፤ ያቺን የፈረደባትን ጉበት ለማቃጠል በአቦ፣ በሥላሴ የማይል የለም፤ ቸገረኝ ብሎ ገንዘብ የሚጠይቅ አይምጣ እንጂ ለማብላትና ለማጠጣት፣ ለአንድ ጥሪኝ ፈሳሽ አበሻ ቸር ነው፤ በላኤ ሰብስ በማርያም ስም አንድ ጥሪኝ ውሀ ሰጥቶ አይደለም እንዴ የበላው ሰው ሁሉ የተሰረዘለት? አበሻ በሆድ አይጨክንም።
ለአበሻ ምግብ ክቡር ነው፤ ስለዚህም ምንም ነገር ሲበላ ተቀምጦ ነው፤ ፈረንጅ ቂሉ በየመንገዱ እንደመጋዣ ያመነዥካል፤ በየመንገዱ ማመንዠክ ምግቡን ማዋረድ ነው፤ ከዚያም በላይ ቆመው ሲበሉ ወደጉልበት ይወርዳል ይላል፤ ለአበሻ ጨጉዋራና ጉልበት በቀጥታ የተገናኙ ናቸው፤ ሳይንሱ የሚለው ሌላ ቢሆንም አበሻ አበሻ ምን ቸገረው?
ለመሆኑ ከሆድ ጋር ያልተያያዘ ነገር አበሻ ምን አለው?  ነገርን በሆድህ ያዘው ምን ማለት ነው? ነገርን ማብላላት የማሰብ ምትክ መሆኑ ነው፤ ልጆች ሆነን አይጥ አበላሁት እንል ነበር፤ አሸነፍሁት ለማለት ነው፤ ዛሬም ቢሆን ቁማርተኞች በላሁ-ተበላሁ ይባላሉ፤ አይጥ ከማብላት ገንዘብ ወደማብላት ተለወጠ እንጂ ከሆድ አልወጣም፤
አበሻ በሆዱ የማይዘው ምን ነገር አለ? ፍቅርም፣ ጥላቻም በሆድ ነው፤ ቂምም በሆድ ነው፤ ምኞትም ፍላጎትም በሆድ ነው፤ ተስፋም በሆድ ነው፤ መጥኔ ይስጠው የአበሻ ሆድ! ሁሉን ከተናገሩት ሆድ ባዶ ይቀራል፤ አይ የአበሻ ሆድ! የነገር ስልቻ ከመሆኑ በላይ ነገር አልቆበት ‹‹ነገር እንዳይርበው(!)›› ጥንቃቄ ማድረግ አለበት! የአበሻ ሆድ እህል ቢያጣና ከእህል ባዶ ቢሆንም ከነገር ባዶ መሆን የለበትም፤ እህል ቢጠፋም ነገር አይጥፋ!
የአበሻና የሆድ ነገር በዚህ አያበቃም፤ አበሻ ሲያመው ቡዳ በልቶት ነው፤ ቆንጆውን ሁሉ ቡዳ ይበላዋል፤ ልብ በሉ ለአበሻ በዓይንም ይበላል ማለት ነው! አንዳንዴም ሲያመው መድኃኒቱ ምግብ ነው፤ ለሆድ ቁርጠት ብላበት፤ አበሻ ሲሞትም ለቅሶው ሁሉ ስለሆድ ነው፤ ‹‹የኔ ሆድ፣ ሆዴ እንዴት ይቻለው! ፋሲካን የት ልፈስክ?››
እስከናካቴው ‹‹ሆድ›› የሚባል ቃል ከአበሻ ቋንቋ ፈጽሞ ቢሰረዝ ቋንቋው ብቻ ሳይሆን አበሻም ጉድ ይፈላበታል፤ አእምሮ፣ ኅሊና የሚባሉትን ቃላት አበሻ አያውቃቸውም፤ ተግባራቸውንም ሁሉ ለሆድ ሰጥቶታል።

Friday, October 25, 2013

ኢትዮጵያውያን እንኳን በሀገራቸው በባዕድ ሀገር የነጻነትና የሃይማኖት መምህራን ነበሩ!!


በ1808 እ/ኤአ ኢትዮጵያውያን የንግድ ሰዎች ወደአሜሪካ ያቀናሉ። በቆይታቸውም ከነጮቹ ቤተ ክርስቲያን  የሰማይና የምድር ገዢ ለሆነው አምላካቸው ጸሎት ለማድረስ ይገባሉ። ይሁን እንጂ የዘር፤ የቆዳ ቀለምና የነገድ ልዩነት በሌለው አምልኮተ እግዚአብሔር ኢትዮጵያውያንን በነጮቹ ቤተ ክርስቲያን ያጋጠማቸው ነገር የተለየ ነው። ለጥቁሮቹ ተለይቶ ከተሰጠው ክልል ውጪ በጸሎት ቤት ውስጥ ከነጮቹ ጋር በእኩልነት መጸለይ ይከለከላሉ። ኢትዮጵያውያኑም የነጭና የጥቁር ተብሎ የተለየ አምላክ ሳይኖር በጸሎት ቤት ጥቁሮቹን የማግለል አሠራር ባለመቀበላቸው ጸሎት ቤቱን ለቀው ይወጣሉ። በዚህን ጊዜ በዚያ የነበሩ አሜሪካውያን ጥቁሮችም የመገለሉን እርምጃ ከተቃወሙት ኢትዮጵያውያን ጋር ተከትለው ይወጣሉ። በኢትዮጵያውያኑ መሪነት ጥቁሮቹ አሜሪካውያን በኒውዮርክ ከተማ አዲስ ቤተ ክርስቲያን በመመስረት ጸሎታቸውን በነጻነት ለመቀጠል ቻሉ።  ጥቁር አሜሪካውያን እስከዛሬ ድረስ በዚሁ ቤተ ክርስቲያን እያከናወኑ የሚገኝ ሲሆን በየጊዜው በሚያዘጋጁት መንፈሳዊ ጉዞ የእምነት ነጻነትን ስላስተማረቻቸው ቤተ ክርስቲያንና ባርነት በመዋጋት ነጻ ሀገር ሆና የመዝለቋን ታሪክ በማስታወስ እናት ምድራችን የሚሏትን ኢትዮጵያን ይጎበኛሉ። በተቃራኒው ደግሞ እናት ምድር ኢትዮጵያን ትተው ኢትዮጵያውያን ደግሞ ይሰደዳሉ። አሳዛኝ ነገር ነው። ከዚህ በፊት ይህንን በተመለከተ ያወጣነውን ዘገባ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ።
የአቢሲኒያን ባፕቲስት ቤተ ክርስቲያን መሪ የሆኑት ዶ/ር ቄስ ካልቪን በትስ በየዓመቱ በሚታሰበው የጥቁር አሜሪካውያን ታሪክና ማንነት ጥናታዊ ጉባዔ ላይ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ከነባለቤታቸው በተገኙበት ትልቅ ንግግር አድርገዋል። ፎክስ ኒውስ ደግሞ ስለኢትዮጵያ ታላቅ ሀገርነት፤ ታሪክና እምነት ሰፊ ሽፋን ሰጥቷል።  በዚህ በአፍሪካውያን ታሪክና ባህል ዓመታዊ የጥናት ጉባዔ ላይ የፕሮግራም መሪ የነበረችው በታዋቂው የቢል ኮስቢ/Bill Cosby/ ተከታታይ የቤተሰብ ፊልም ላይ መሪ ተዋናይት የነበረችው ፊሊሺያ ራሻድ ነበረች። ኢትዮጵያውያን ነጻነትን በሀገራቸው ብቻ ሳይሆን በባዕድ ሀገር ጭምር ሄደው ማስተማር የቻሉ ሕዝቦች ነበሩ። እንደዚህ እንደዛሬው በባርነት መልክ በዐረብ ሀገራቱና በየምዕራቡ ዓለም በስደት ጉልበታቸውን እንደሸቀጥ ከነነጻነታቸው ጭምር  ከመሸጣቸው በፊት ማለት ነው። ለማንኛውም ኢትዮጵያና የጳውሎስ መልዕክት ትርጉም የተወደሰበት ዝግጅት ይህንን ይመስላል።

«አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና» ገላ 3፤28

 

Sunday, October 20, 2013

እውነቱ ስንናገር ጳጳሳቱ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ዘብ አልቆሙም!!



የካህናቱና ጡረተኞች የተሰገሰጉበት የሰበካ ጉባዔ ምእመናን ተወካዮች በዓመት አንድ ጊዜ ተሰብስበው በሚመሰጋገኑበትና የድግስ ጋጋታ በሚያስተናግዱበት የሰበካ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባዔ ላይ ስለመቻቻል የቀረበውን አጀንዳ አስታከው ጳጳሳቱ ስሜታቸውን መግለጻቸውን ሰምተን ጥቂት ተደነቅን። እንዴት ወንድ ወጣቸው? ብለንም ጥቂት አድናቆትን ቸርናቸው። ለካስ ከቀሚሳቸው ስር ሱሪ ታጥቀዋል?  ይሁን እንጂ  ሱሪ ነገረ ስር አይሆንምና ነገሩ አጋጣሚን የመጠቀም እንጂ የወንድነት አይደለም።
  በዚያች የመቻቻል መድረክ ለመተንፈስ ከመፈለጋቸው በስተቀር በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱን ችግር ለመፍታት አንዳችም ህልምና ርእይ እንደሌላቸው የተገነዘብንበት ሁኔታ ነበር። ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደተቋም የት ነበረች? አሁንስ የት ነው ያለችው? ወደፊት እንዴትና የት ትራመዳለች? ለሚለው አንኳርና ቁልፍ የመንፈሳዊ ጉዞ መልህቅ መጣያ የሚሆን የሃሳብ ወደብ አንዳችም ሳናይ በማለፉ ግንፍል ንግግራቸውን ታዘብነው። አንድም አባል ቢሆን ሲጎዳ ማየት ልብን እንደሚሰብርና መንፈሳዊ ልማት ማካሄድ የሚቻልበትን አንድም ጋት ይዞታን ማጣቱ ቢያንገበግብም  የቤተ ክርስቲያኒቱ አጠቃላይ ችግር በመሬት ተወሰደብኝና አንድ አባል ታሰረብኝ በሚል አቤቱታ የሚገለጽ አልነበረም። ይሁን እንጂ ጳጳሳቱ ሲጮሁ የሰማነው ንግግር በቁራሽ መሬትና በአንድ ምእመን መጎዳት ላይ ማተኮሩ የችግሩን ስፋት ለመመልከት አለመቻላቸውን ያመላከተ ሆኖ አልፏል።

በጳጳሳቱ ሊታይ ያልቻለውና መታየት የነበረበት የቤተ ክርስቲያኒቱ የውስጥና የውጪ ችግር፤
  1/ ቤተ ክርስቲያን ሲቃጠል፤ ሲዘረፍ፤ ምእመናንና ምእመናት ሲሰደዱ፤ በአሸባሪና በአክራሪዎች ሲገደሉ መቆየታቸው ዓመታት ተቆጥረዋል። ነገር ግን አንድም ጊዜ የጳጳሳቱን የድፍረት ሱሪ በንግግር አላየንም። ለምን? አንድም የፍርሃት ቆፈን ወሮአቸዋል። አለያም የመንፈሳዊነት እንጥፍጣፊ አልቆባቸዋል። የመቻቻል ፖለቲካ ዲስኩር ሲፈነዳ አብሮ ማንዳዳት ያስተዛዝባል እንጂ አባቶች ለቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር ዘብ ቆሙላት አያሰኝም።

2/ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንግሥታዊ ሃይማኖት ሆና ለዘመናት በመቆየቷ ብቻ ጊዜ አመጣሾች እንደጠላት ቢመለከቷትም ዘመንና ወቅት እንደዚያ ሆና እንድታልፍ ያደረጋትን ከመቀበል ውጪ «መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው» የሚል ሕግ ለመቅረጽ ስለማትችል ይህንን ሁሉ አስልተው እንደባላንጣ ለሚቆጥሯት ወገኖች ለመንግሥት አካላትም ሆነ ለሌሎች የሃይማኖት ተቋሟት መናገር፤ ማስረዳትና ማሳመን የሚችል አቋም በቤተ ክህነቱ ፕሮግራም ውስጥ ባለመኖሩ ቤተ ክርስቲያኒቱ የነፍጠኞችና የትምክህተኞች መናኸሪያ ተደርጋ በሌሎች ዘንድ በተሳለው ስዕል የተነሳ አጋጣሚውን ጠብቀው ብድር የመመለስ ጨለምተኛ አካሄድ ሲታይ ያንን በመጠቆም ብቻ ችግሩን መግፈፍ አይቻልም። ስለዚህም ጳጳሳቱ መናገር የሚገባቸውን  ሰዓት ቀድሞ አሳልፈውት ዛሬ ለችግሩ ማልቀስ የቤተ ክርስቲያን ዘብ አያሰኝም።
  3/ ዋናው ችግር ከውስጥ መንፈሳዊ ማንነትን መታጠቅ ያስፈልጋል። ታሪክና ዘመን የሰጣቸውን ሥልጣንና እድሜ ሊሰሩበት እንደሚገባ የሚረዳ ውስጠት ሊኖራቸው የግድ ይላል። ውጪያዊ ተጽእኖን ለመጋፈጥና ለማሸነፍ መንፈሳዊ ትጥቅ የሌለው ሹም በጦር አውድማው ላይ የመጠቃትና የተሸናፊነት ድምጽ ማስተጋባቱ አይቀርም። ተመሪዎቹንም ለጥቃት ያጋልጣል። አሁንም ያየነው ያንን ጩኸት ነው።  ጳጳሳቱ ይህንን የመንፈሳዊ ማንነትን ትጥቅ በተዋቡባቸው አልባሳት ለመካካስ ይፈልጋሉ። ክብሩ ግን በመንፈሳዊ ስብእና እንጂ በመልክና በቁመና ስለማይገኝ ድፍረት፤ መንፈሳዊ ቅንዓትና ጥብዓት የራቃቸውም ለዚህ ነው።

እውነቱን እንነጋገር ከተባለ ዘረኝነትን፤ አድመኝነትን፤ ሙስናን፤ አድልዎን፤ ብቀላን፤ ዘረፋን፤ ግለኝነትን፤ ስብእናን የሚያጎድፍ አስነዋሪ ተግባራትን በማድረግም ይሁን የሚያደርጉትን ባለመገሰጽ፤ ይልቁንም ስር እንዲሰድና እንዲስፋፋ ምክንያት በመሆን ግምባር ቀደሞቹ ራሳቸው ጳጳሳቱ ናቸው። ጳጳሳቱ ራሳቸውን ያውቃሉ፤ ካህናቱም በትክክል ያውቋቸዋል።  ሌላው ቀርቶ ምእመናንም ጭምር። ምንም እንኳን እንዲህ ማለቱ ቢያሳፍርም እውነቱን አለመናገር በራሱ ወደፊት ሊቀጥል በሚችለው የቤተ ክርስቲያኒቱ መገፋት ላይ መፍትሄ እንዳይኖር ማድረግ ነውና ከመናገር ውጪ ሌላ መንገድ የለንም። ሰው ድካሙን አውቆ፤ በንስሀ ተመልሶ፤ ብርታት በሚሰጠው በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ለመሥራት እስካልተጋ ድረስ በልብስ ውስጣዊ ማንነትን ቢሸፍኑት ተግባር ማንነትን፤ የኃጢአት ዋጋ እዳን ሲያስከትል በግልጽ መታየቱ አይቀርም። የጥቃቱ መብዛት የኃጢአትን ደመወዝ እየተቀበሉ የመገኘት ምልክት ነው እንጂ እግዚአብሔር በፈተና ውስጥ ቤተ ክርስቲያንን ስለተዋት አይደለም።
   ከዚህ በፊት ስለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ባወጣነው ጽሁፍ ስንጠቁም  «የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትና ቅጠል የሌለው ዛፍ አንድ ናቸው» ለማለት እንደሞከርነው ጉዳዩን በሂደት ስንመለከት ዛፍነቱ ከቅጠል አልባነት በከፋ መልኩ እየበሰበሰ በመሄድ ላይ እንዳለ በመረጃና በማስረጃ የተደገፈ ጭብጥ ማቅረብ የሚቻልበት ሲሆን  በአጠቃላይ ጳጳሳቱ ከውጪያዊ ተግዳሮቶች በከፋ መልኩ ቤተ ክርስቲያኒቱን እየገፉ ወደ ገደል በመንዳት ላይ እንደሚገኙ የሚያስረዳን እውነታ ነው። አዲስ አበባ ላይ የሚፈጸመው የቤተ ክርስቲያን የዐመጻ ተግባር ጊምቢ ላይ ዋጋ አያስከፍላትም ያለው ማነው?

ከዚህ አንጻር የቤተ ክርስቲያኒቱ ዋና ችግር የበሰበሰው የቤተ ክርስቲያኒቱ የመነኮሳት አባቶች አመራር ከፍተኛውን ድርሻ ይወስዳል ማለት ይቻላል። በዚህ መልኩ ከቀጠለ በወለጋ ወይም በጋሞጎፋ መሬት ተወሰደ አለያም ገበሬ ተገረፈ ከሚለው ጩኸት ይልቅ ከውስጥ በሚመጣው የዐመጽ ተግባር  የተነሳ የሚከሰተው ጥፋት የከፋ ይሆናል።
  ከሰሞነኛው የሰበካ ጉባዔው ስብሰባ ላይ የማቅ ቀኝ ክንድ አቡነ ቄርሎስ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ድምጽ እንደሆኑ የተደሰኮረ ቢሆንም አቡነ ቄርሎስን የምናውቃቸው በዘመነ ሥራ አስኪያጅነታቸው ቤተ ክህነቱን ላስታ ላሊበላ ማድረጋቸውን እንጂ ዘረኝነትን ስለመዋጋታቸው አይደለም። ሌሎቹን በስምና በቦታ መጥራት ይቻላል። ይሁን እንጂ ጊዜና ቦታ የማይበቃን ስለሆነና ተግባራቱን በውል የሚያውቁ ስለሚያውቁት ሾላ በድፍን ማለቱን መርጠነዋል። ሌሎቹ ቢሆኑ እንዲሁ ናቸው!!

በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የአቡነ እስጢፋኖስን የሙስና ስፋትና ጥልቀት፤ የሰው ሽያጭና ከስራ ማፈናቀል ተግባር በማስረጃ አስደግፈን በሌላ ዓምድ እንመለስበታለን።
  ስናጠቃልል ጳጳሳቱ ለቤተ ክርስቲያኒቱ መሽመድመድ ዋና ተጠያቂዎች ናቸው። የተቀበሉትን አደራ እስከሞት ድረስ የመወጣት አለያም ካልቻሉ ደግሞ ወደበረሃቸው የመግባት ግዴታ እንዳለባቸው ስለማያውቁ አሁን ደርሶ በመቻቻል ፖለቲካዊ መድረክ ላይ ወኔ የታጠቁ መስሎ መታየት አንድም እንደዚህ አልኩኝ ለማለት አለያም የማኅበረ ቅዱሳንን መነካት በተዘዋዋሪ መንገድ በችግሮች ሽፋን ለማካካስ ከመፈለግ የመነጨ ከመሆን አይዘልም። ጥያቄአችንም የሚነሳው ከዚህ ነው። ይህ «መቻቻል» የሚለው መድረክ ሳይመጣ በፊት የት ነበራችሁ? ነው ጥያቄያችን። በእነ አቡነ ገብርኤል ዓይነቶቹ የምትመራ ቤተ ክርስቲያን መቼም ከችግር አትጸዳም።

እውነታውን ስንናገር ጳጳሳቱ ለቤተ ክርስቲያን ዘብ አልቆሙም ነው የምንለው!!!

Saturday, October 5, 2013

የተሻለ የሥራ ጊዜ እንዲሆንልን ጸልዩልን!

 
በሃሳባችሁ፤ በምክራችሁ፤ በእውቀታችሁ፤ በገንቢ አስተያየታችሁ አብራችሁን ለዘለቃችሁ ሁሉ ምስጋናችን ይድረሳችሁ!
በዘለፋ፤ በፉከራ፤በስድብና በኢ-ክርስቲያናዊ ጽሁፎቻችሁ ለቆያችሁም አስተዋይ ልቡና ይስጣችሁ! ከጥላቻ የራቀ ማንነት እንዲሰጣችሁ እንመኛለን።
አግዚአብሔር ኢትዮጵያችንን ይባርክ
                                    ደጀብርሃን