Tuesday, November 5, 2013

የኑሮ መድኅን - ምዕራፍ ሁለት የፀሐይ ዕድሜ

የዲ/ን አሸናፊ መኰንን ገጽ --    ረቡዕ ታኅሳስ ፳፬/ ፳፻፭ ዓ/ም
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፤
 አንድ ሰው በጫካ በተከበበና ጭር ባለ መንገድ ብቻውን ሲሄድ ፍርሃት ይይዘውና «ጌታ ሆይ» ብሎ ይጮኻል፡፡ «ጌታ ሆይ እንደምታየኝ ጫካ ውስጥ ነኝ፡፡ መንገዱም ጭር ያለ ነው፡፡ ብቻዬን ነኝና ፈራሁ፣ እባክህ ድረስልኝ» ሲል ይጮኻል፡፡ ትንሽ እንደ ቆየ ብቻውን በሚሄድበት መንገድ የሁለት ሰው ጥላ ያያል፡፡ ያን ጊዜም ደንግጦ እንደ ገና ወደ እግዚአብሔር «ጌታ ሆይ ፍርሃቴ ጨመረ ብቻዬን እየሄድኩ የሚታየኝ የሁለት ሰው ጥላ ነው፡፡ ነገሩ ምንድነው?» ሲል ጮኸ፡፡ እግዚአብሔርም፡- «አይዞህ ልጄ ብቻህን አይደለህም፣ የምታየው ሁለተኛ ጥላ የእኔ ነው፡፡ እኔ አብሬህ ነኝና አትፍራ» አለው፡፡ በዚያን ጊዜ ሰውዬው ደስ ብሎት ያለ አሳብ ጉዞውን ቀጠለ፡፡ ተጉዞ ተጉዞ ረግረጋማና ዳገታማ ስፍራ ላይ ሲደርስ ዞር ብሎ ቢያይ ጥላው ከአጠገቡ የለም፡፡ ይህን ጊዜ ፍርሃት ያዘውና «ጌታ ሆይ» ይል ጀመረ፡፡ «ጌታ ሆይ ቅድም በተደላደለው መንገድ ስሄድ አንተ ከጎን ጎኔ ትሄድ ነበር፡፡ አሁን ግን እንዲህ ባለ ለጉዞ በማይመች የአንተ እርዳታ እጅጉን በሚያስፈልገኝ ረግረጋማና ዳገታማ ቦታ ላይ ስደርስ ግን ጥለኸኝ ሄድክ፡፡ ጌታ ሆይ ምን አጥፍቼ ነው ይህ የተደረገብኝ?» ሲል ጮኸ፡፡ እግዚአብሔርም «በዝግታ አይዞህ ልጄ የቅድሙ መንገድ የተመቻቸ ስለነበር አብሬህ እንዳለሁ እንዲሰማህ ብቻ ጎን ጎንህ እሄድ ነበር፡፡ የአሁኑ መንገድ ግን ለጉዞ የማይመች አስቸጋሪ መንገድ ስለሆነ ጥላዬ የጠፋብህ አዝዬህ ነውና አይዞህ፡፡ የምታየው የእኔን ጥላ ነውና በርታ» አለው፡፡
እግዚአብሔር አብሮን የሚሆነው እኛ ግድ ስላልነው ሳይሆን ፍቅር ስለሆነ ነው፡፡ በአስቸጋሪ ስፍራም አይለየንም፡፡ ሲደክመንም ጥሎን አይሄድም፣ ይልቁንም ይሸከመናል እንጂ፡፡ የአሕዛብ ጣዖታት ሰዎች የሚሸከሟቸው ናቸው፡፡ የሚያምኗቸውን ግን የሚሸከሙ አይደሉም፡፡ የእኛ ጌታ  እግዚአብሔር ግን የሚሸከመን አምላክ ነው፡ ፡ 
የአገራችን መምህራን የሰውን ዕድሜ በፀሐይ ይመስሉታል፡፡ ፀሐይ በማለዳ ስትወጣ ድካምና ፍርሃት ተወግዶ ሁሉም ሰው አዲስ በሚላት ቀን ተግባሩን ሊጀምርባት ይነሣል፡፡ የጠዋት ፀሐይ ተናፋቂና ተወዳጅ ናት፡፡ ሌሊቱን ሲፋንኑ ያደሩ አራዊትና ሌቦች ወደ ጎሬአቸው ሲገቡ የብርሃን ልጆች ግን ይወጡባታል፡፡ ይህችን የማለዳ ፀሐይ ዱካ ያለው ዱካውን ይዞ የሌለውም በድንጋይ ላይ ተቀምጦ ይሞቃታል፡፡ በቤት ውስጥ የሚሸፋፈኑ አራስ ሕፃናትም በእናታቸው ጉልበት ላይ ሆነው ራቁታቸውን ይሞቋታል፡፡ 
ሰው ሁሉ ተጠራርቶ የሞቃት ያች የጠዋት ፀሐይ ቀትር ላይ ሁሉም ሰው ይሸሻታል፣ ይጠላታል፣ ይመረርባታል፣ በትንሽ ጥላ እንኳን ሊደበቃት ይሞክራል፡፡ ተጠራርቶ እንዳልሞቃት ምን ዓይነት ቍጣ ነው? ይላታል፡፡ ፀሐዩ እስኪበርድም ከቤት አትውጡ ይባላል፡፡ የጠዋቱ አድናቆትና ምስጋና ቀርቶ ምሬት ይተካል፡፡
ቀትር ላይ ሁሉም ሰው የተመረረባት ፀሐይ ሠርክ ላይ ልትጠልቅ ስትል ሁሉም ሰው ይሳሳታል፡፡ ጨርሳ ሳትጠልቅ ይሯሯጥባታል፣ ወደ የቤቱ ይሰበሰብባታል፣ ጥበበኞችም በባሕር ዳርቻ ላይ ከውኃው ጋር የምትሰጠውን ውበት ለማስቀረት ፎቶ ግራፋቸውን አስተካክለው ይጠብቋታል፡፡  ጠዋት ላይ ጨለማን ወደ ፊት እየገፋች የወጣችው ፀሐይ ሠርክ ላይ ጨለማውን ወደ ኋላዋ አድርጋ ትጠልቃለች፡፡ እግዚአብሔር ፀሐይን በውበት አውጥቶ በውበት ያስገባታል፡፡ 
አንዷ ፀሐይ ጠዋት ላይ ሁሉም ሰው የሚሻማት፣ ቀትር ላይ የሚሸሻት ሠርክ ላይ የሚሳሳላት ናት፡፡ ለአንዲቱ ፀሐይ ያለንን ተለዋዋጭ ስሜት ግን አስተውለነው አናውቅም፡፡ የሰው ዕድሜም በፀሐይ ይመሰላል፡፡ ፀሐይ በቀን ውስጥ ሦስት ዓይነት ስሜት ትፈጥራለች፡፡ ሕይወትም እንዲሁ ናት፡፡
ፀሐይ በምሥራቅ ስትወጣ ሁሉም ሰው በናፍቆት እንደሚቀበላት፣ ተጠራርቶ እንደሚሞቃት ሕይወትም ገና በጅምሯ ጣፋጭና የማትጠገብ ናት፡፡ ሕጻን ሲወለድ ሁሉም ሰው ተጠራርቶ ይቀበለዋል፣ ሴቶች በእልልታ ወንዶች በጥይት ተኩስ ደስታቸውን ይገልጣሉ፡፡ ያ ልጅም ሮጦ አይደክምም፣ ዘሎ አይጠግብም፡፡ «ሁሉም ነገር በጠዋቱ ቀዝቃዛ ነው» እንደሚባለው የሕይወት ትግሉም ለእርሱ ቀላል ነው፡፡
አዋቂዎች ስለ ብርቱ ችግር ሲያወሩ ሕጻኑ ግን ስላማረው ምግብና መጫወቻ ያወራል፡፡ የእንግሊዝዋ ንግሥት ልጅ ሰው ተራበ የሚል ወሬ ብትሰማ አይስክሬም አይበሉም ወይ? ቢጠፋ ቢጠፋ አይስክሬም ይጠፋል ወይ? አለች እንደሚባለው ሕፃኑም ልክ እንደዚህች ልዕልት ነው፡፡ አዋቂዎች ሲያለቅሱ ልጆች ግር ይላቸዋል፡፡ ሕይወት ታስለቅሳለች ብለው ማመን በፍጹም አይሆንላቸውም፡፡ 
ያቺ ተናፋቂ የጠዋት ፀሐይ ቀትር ላይ እንደምታስመርር ሕይወትም ልጅነቱን ለፈጸመውና ለራሱ ማሰብ ለጀመረው ወጣት እንግዳና አስፈሪ ናት፡፡ ለራሱ ምንም ባያደርግ እንኳ ለራሱ ማሰብ ብቻውን ወጣቱን ያደክመዋል፡፡ ወጣቱ ጭምብሉን ሲያወልቅ፣ ዓለምን ብቻውን ሲያያት፣ ሁሉም ነገር ሲለዋወጥበት ግር ይለዋል፡፡ ሲወለድ ወንድ ተወለደ ተብሎ የተደሰቱ ሰዎች አሁን እነዚህን ጎረምሶች ይንቀልልን ሲሉ ይደነግጣል፡፡ ሲስሙት የኖሩት አሁን ችላ ይሉታል፡፡ መንገድ ሲጠፋበት ከመምራት ያዋክቡታል፡፡ መንግሥትም ወጣቱ ኃይል ነው ብሎ ስለሚሰጋ ሠራዊት ያደራጅበታል፡፡ ሲወድቅ ጎበዝ ይባል የነበረው ሕፃን አሁን ትንሽ ሲሳሳት ፖሊስ ይጠራበታል፡፡ እደግ ተብሎ የተመረቀው ሲያድግ ይረገማል፡፡ በዚህና በሌሎች የሕይወት ትግል እንዴት እኖራለሁ? የሚለው ጥያቄ ያስጨንቀዋል፡፡  
ቀትሩ ፀሐይ በአናት ላይ የምትወጣበት ሰዓት ስለሆነ ከባድ ሰዓት ነው፡፡ ሕይወትም በወጣቱ ላይ ብርቱ የምትሆንበት ቀትር አላት፡፡ እስከ ዕድሜ ልክ የሚዘልቁ ሱሶችና ስህተቶች የሚጀመሩት በዚህ በወጣትነት ዘመን ነው፡፡ በወጣትነት የተፈጸሙ ስህተቶችና የማይገቡ ምርጫዎች እስከ ዕድሜ ልክ የማይስተካከሉበት ጊዜ ብዙ ነውና ወጣቱ ማስተዋል ይገባዋል፡፡ ሕይወትን ከትዕግሥት በቍጣ፣ ከትሕትና በትዕቢት ለመምራት መሞከር ለቀጣዩ መንገድ መሰናክል ማስቀመጥ ነው፡፡ የአሁን መሳካት የሁልጊዜ መሳካት፣ የአሁን አለመሳካት የሁልጊዜ አለመሳካት አለመሆኑን ወጣቱ ሊያስተውል ይገባዋል፡፡ ዕድል እግዚአብሔር፣ መከራም የጥራት መገኛ መሆኑን ወጣቱ ሊያስተውል ሲገባው መልካም ዕድልም የሚሰጥ ሳይሆን የሚመረጥ መሆኑን መገንዘብ አለበት፡፡ 
የሌለውን እንዳለው አድርጎ የሚያስብ ጉረኝነት የቀትሩ አጉል አመል ነው፡፡ ቀትርን ሁሉም እንደሚሸሸው ወጣቱም ሕይወትን ለመደበቅ ይሞክራል፡፡ ሕይወትን ግን ስንጋፈጣት እንጂ ስንሸሻት አትሸነፍም፡፡ ቀትሩን በትንሽ ጥላ ለመጋረድ እንደሚሞክር የሕይወት ጥያቄ ሲበዛም በሱስ፣ በቁማርና በኃጢአት ውስጥ ለመደበቅ ቀትር ላይ የደረሰው ሰው ይጥራል፡፡ በእርግጥ የወጣትነት ክፉ ባሕርያት ከባልንጀራም እንደሚወረሱ አንዘነጋም፡፡ ወጣቱ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ መጀመሪያ የተቀበሉትን ቤተሰቤ ብሎ እንደ ኖረ ከቤቱ ሲወጣም በሰፊው ዓለም መጀመሪያ የተቀበሉትን ቤተሰብ ያደርጋል፡፡ ሕይወት ቀትር የሆነችበት ሰው በቶሎ ተስፋ በመቍረጥ ሞቱን ይመኛል፡፡ ወላጆቹ የእርሱንና የራሳቸውን ደግሞም የቤተሰቡን ሕይወት ተሸክመው ሳለ መኖር የእርሱን ያህል አልከበዳቸውም፡፡ እርሱ ግን በአሳብ ጭነት ለምን እንደሚንገዳገድ አያስተውልም፡፡ 
ያች ተናፋቂ የጠዋት ፀሐይ ቀትር ላይ እንዳስመረረች ልትጠልቅ ስትል ደግሞ ታሳሳለች፡፡ ለዚህ ነው ወጣቱ ሞትን ሲመኝ የታመሙትና ሽማግሌዎች ግን ዕድሜን ይለምናሉ፡፡ በሕይወት ሠርክ ላይ ኑሮን ኖርኩበት ወይስ ኖረብኝ ብለን ሂሳብ እንተሳሰባለን፡፡ ይህ የፈቃዳችን ጉዳይ ሳይሆን ግድ ነው፡፡ ማድረግ በማንችልበት ጊዜ ከማዘን እግዚአብሔር ይጠብቀን፤ ቢሆንም ለንስሓ እስካለን ጊዜ አያልፍምና ንስሓ መግባት ይገባናል፡፡ ንስሓ ከምግባራት ሁሉ ትበልጣለች፡፡ ፀሐይ ስትወጣ ጨለማን ወደ ፊቷ እየገፋች ሲሆን ስትጠልቅ ግን ጨለማን በስተኋላዋ አድርጋ ነው፡፡ ይህን ዓለም ለቀን ስንሄድም ከክርስቶስ ጋር ከሆንን ጨለማው ከኋላችን ነው፡፡ የዚህ ዓለም መከራና ድካም አይከተለንም፡፡ ሕፃኑ ሲወለድ ዙሪያውን የከበቡ ሰዎች እልል ይላሉ፡፡ እርሱ ግን በተፈጥሮው ወደዚህች አድካሚ ዓለም መምጣቱን እያወቀ ያለቅሳል፡፡ ይህን ዓለም ተሰናብቶ ሲሄድም ዘመድ አዝማዶቹ ያለቅሳሉ፡፡ እርሱ ግን ወደ ዕረፍቱ ይሄዳልና ዝም ይላል፡፡ የቆሙት ሰዎች ግን አያስተውሉም፡፡ 
እግዚአብሔር ፀሐይን በውበት አውጥቶ በውበት ያጠልቃታል፡፡ ዕድሜም በሕፃንነትና በሽምግልና ውበት ይልቁንም በጨዋነት እንድትፈጸም የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው፡፡ ዘመንህ በውበት እንዲፈጸም በሕፃንነትህ ሽማግሌ አክባሪ፣ በወጣትነትህ ታታሪ ሠራተኛ፣ በሽምግልናህ አስታራቂ ከሁሉ በላይ ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታህና መድኃኒትህ የሆነልህ ሰው ሁን፡፡ ምንም ኑሮ ቢከብድብህ ሞትን አትለምን፡፡ ወጣቱ ወደ አንድ አባት ዘንድ ሄዶ «አባቴ መሞት እፈልጋሁ» አላቸው፡፡ እርሳቸውም ዘና ብለው «ሞትን ባትፈልገውም ወዳንተ ይመጣል፤ ካልፈለግሃቸው ግን ወዳንተ የማይመጡ ብዙ መልካም ነገሮች አሉና ለምን እነርሱን አትፈልግም?» ብለውታል፡፡ 
ከኮሚኒስት ርእዮተ ዓለም ወዲህ የብዙ የዓለማችን ወጣቶች ሕይወት ተዘርቶ ያልተሰበሰበ ፍሬ ሆኗል፡፡ ተስፋ የቆረጠ፣ ሞራሉ የወደቀ፣ በቦምብ ኳስ የሚጫወት ትውልድን ያተረፍነው ዓለም እግዚአብሔር የለም ብላ ካወጀች ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ እግዚአብሔር ከሌለ መልካም ሥራ ዋጋ፣ ክፉ ሥራም ቅጣት ሊኖረው እንዴት ይችላል? ስለዚህ ዓለምን ባለቤት የሌላት ቤት ስናደርጋት የዛሬውን የትውልድ መዝረክረክ አተረፍን፡፡ ኮሚኒዝም ከአደባባይ ቢወድቅም ገና የአደባባይ ንስሓ ስላልገባንበት ከሰው ልብ አልወደቀም፡፡ በአዋጅ ክደን በተናጥል ነው ንስሓ የገባነው፡፡ ወጣቱ ትውልድ ወደ እግዚአብሔር ቤት ሲመጣ ብናይም ውስጡ ግን በዚህ ክፉ ሥርዓት ተገዝቷል፡፡ አሁን ያሉት ትልልቅ ሰዎችና የወደፊት ሽማግሌዎችም እግዚአብሔር የለሾች መሆናቸው አይቀርምና ልናስብበት ይገባል፡፡
በአንድ ቀን ውስጥ ሁለት ወጣቶችን ሳማክር በተለያየ ሰዓት ቢመጡም የጠየቁኝ ጥያቄ አንድ ዓይነት ነበር፡- «ይህን ወጣትነቴን ምን ላድርገው? ይህን ዕድሜዬን ምን ላድርገው?» ስሰማቸው ልቤ ቢያዝንላቸውም ነጻ የሚያወጣቸው ክርስቶስ ግን እንደ ተሰቀለ ሆኖ ይታየኝ ስለነበር ደስ አለኝ፡፡ አሁን እነዚህ ወጣቶች ወጣት ለዘፈን፣ ወጣት ለዝሙት የሚለውን መመሪያ ጥለው ወጣት ለክርስቶስ መሆኑ ገብቷቸው ተጽናንተዋል፡፡ ለዛሬ ወጣቶች እግዚአብሔር ለእነርሱ ያለውን ዓላማ ልንነግራቸው ይገባል፡፡ ትዕግሥት የለሾችና በቶሎ ተስፋ የሚቆርጡ ናቸውና፡፡ ፍቅር የተሞላን ሆነን ልንቀርባቸው ይገባል፡፡ በዕድሜ የቀደምን ሰዎች ለእነዚህ ግራና ቀኛቸውን ለማያውቁ ወጣቶች ዕዳ አለብን፡፡ ቤተ ክርስቲያን መማፀኛ ልትሆናቸው ትምህርት ቤቶችም የግብረ ገብ መማሪያቸው ሊሆኑአቸው ያስፈልጋል፡፡ ሕይወት የማይኖር የመሰለህ አንተ ወጣት ወደ ጎዳና ውጣና አረጋውያንን ተመልከት፡፡ ለዚህ የደረሱት በአንተ መንገድ አልፈው ነው፡፡ ሽበታቸው በአንድ ትልቅ ጦር ሜዳ ላይ አሸንፈው የተቀዳጁት ዘውድ መሆኑን ይመሰክራል፡፡ ሽበታቸው ራሱ ደካማነትህን ይነቅፈዋል፡፡ ከሁሉ በላይ መጽሐፍ ቅዱስህን ገልጠህ በእምነትና በጸሎት አንብበው፡፡ እርሱ የመንገድህ ካርታ  /መሪህ/ ነው፡፡  
የፀሐይ ዕድሜ አጭር ነው፡፡ አንድ ቀን እንኳ አይሞላም፡፡ ከመሐልም ጭጋግና ደመና ይጋርዳታል፡፡ ነገር ግን ሃያ አራት ሰዓት እንኳ በማይሞላው የፀሐይ ዕድሜ ብዙ ስሜቶች ይፈራረቃሉ፡፡ ቢሆንም አጭር ነው፡፡ ሰውም በምድራዊ ኑሮው ብዙ ነገሮችን ቢያይም የዚህ ዓለም ቆይታው ግን በጣም ትንሽ ነውና መጨነቅ የለበትም፡፡ ሰባና ሰማንያ ዓመት ማለት ትንሽ ቆይታ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ ሺህ ዓመት እንደ አንድ ቀን ነው ይላል 2ጴጥ.3፡8፡፡ ሺህ ዓመት እንደ አንድ ቀን ከሆነ አምስት መቶ ዓመት እንደ 12 ሰዓት ነው፡፡ ሁለት መቶ ሃምሳ ዓመት ደግሞ እንደ 6 ሰዓት ነው፡፡ 125 ዓመት ደግሞ እንደ ሦስት ሰዓት ነው፡፡ 62 ዓመት ደግሞ እንደ አንድ ሰዓት ተኩል ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ሰማንያ ዓመት ብንኖር እንኳ በዚህ ዓለም ላይ የምናሳልፈው ዕድሜ በእግዚአብሔር አቆጣጠር ሁለት ሰዓት እንኳ የማይሞላ ነው፡፡ ይህ አንድ አውሮፕላን በአንድ አገር ላይ ነዳጅ ለመቅዳት አርፎ ለመነሣት የሚፈጅበት ሰዓት ነው፡፡ በጣም አጭር ነው፡፡ ሰው በዚህ ዓለም ላይ የሚያሳልፈው ዕድሜ ከዘላለም አንጻር ቢሰላ አንድ ቀን እንኳ አይሞላም፡፡ ከዘላለም አንጻር ቆይታችን ንሥር ሥጋ አይቶ እስኪያነሣ ያለውን ጊዜ የሚያህል ቅጽበታዊ ነው፡፡ ስለዚህ በጣም መጨነቅና ማዘን አይገባንም፡፡
የጽሞና ጊዜ
እግዚአብሔር አይተውህም፣ አይጥልህም፡፡ እንደማይተውህ ቃል ገብቶልሃል ዕብ.13፡5፤ኢያ.1፡5፡፡ እግዚአብሔር ቃል የገባልህ ተገዶ ሳይሆን በፈቃዱ ነውና ለመፈጸም አይፈተንም፡፡ ስለዚህ አሁን ለራስህ ንገረው፡- ጌታዬ አይጥለኝም፣ ፍጹም አይተወኝም፡፡ ደግመህ ለራስህ ንገረው፡፡ አሁን የገጠመህ ሰዎች ከዚህ በፊት የገጠማቸው ነው፡፡ አሁን የደረሰብህ ብዙ ትውልዶች ያለፉበት ነው፡፡ አዲስ ነገር የለም፡፡ አዲስ ነገር የገጠመህ መስሎህ አትደነቅ፡፡ ጉልበት የሚጨርስ መደነቅ ነው፡፡ በእግዚአብሔርና በሥራው ብቻ ተደነቅ፡፡ ደግሞም፡-
- የሚሸከም አምላክ እንዳለህ፣
- ከቀትሩ በኋላ ሠርክ እንደሚመጣ፣
- ሕይወትህ በውበት ወጥታ በውበት እንድትጠልቅ፣
- ከምንም በላይ የሚያስፈልግህ እግዚአብሔር መሆኑን፣ 
- ዘመንህ አጭር ቢሆንም ዘላለማዊ ውሳኔ የምትወስንበት መሆኑን አስብ፡፡
ጸሎት
ጌታዬ እግዚአብሔር ሆይ የዘመኔ ጌታ መሆንህን አምናለሁ፡፡ የሸረሪት ድር ተደግፌ ብዙ ጊዜ ተበጥሶብኛል፡፡ በራሴና በእውቀቴ መመካትም አልጠቀመኝም፡፡ ከሞት የማያድነውን እውቀት ጠልቼዋለሁ፡፡ ዛሬም ልትሠራኝ እንደቆምክ አይሃለሁ፡፡ አንተን መፍራት ስለተሳነኝ ኑሮና ሰዎች ያስፈሩኛል፡፡ ያረፍኩበትን ጊዜ አላውቀውም፡፡ አንዱ ጭንቀት ለአንደኛው መሬት ላይ ሳላርፍ ይሰጠኛል፡፡ ሰላም ይህና እንዲያ ሲሆን እንደማይገኝ ገብቶኛልና እንዲሁ አሳርፈኝ፡፡ መታገሥ እያቃተኝ ገበታ ስገለብጥ፣ የተሻገርኩበትን ድልድይ ስሰብር ኖሬአለሁና አሁንስ አሰልጥነኝ፡፡ ተስፋ መቍረጤን ሳልጨርሰው ቅደመኝ፡፡ በሚያስጠልለው ስምህ በኢየሱስ ክርስቶስ አሜን፡፡ 
የኑሮ መድኅን - ለሰባተኛ ጊዜ የታተመ
በዲ/ን አሸናፊ መኰንን
የመጀመሪያ እትም መጋቢት 2000 ዓ/ም
አድራሻ፡ 0911 39 3521/0911 67 8251
 መ.ሳ.ቁ.  62552